text
stringlengths
4
267
ምክንያቱም መጀመሪያ እውቅና የሰጣቸው ሰዎች የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ወስኗል፤ ይኸውም ልጁ ከብዙ ወንድሞች መካከል በኩር እንዲሆን ነው።
ከዚህም በተጨማሪ አስቀድሞ የወሰናቸውን እነዚህን ጠራቸው፤ የጠራቸውን እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው። በመጨረሻም ያጸደቃቸውን እነዚህን አከበራቸው።
እንግዲህ ስለ እነዚህ ነገሮች ምን እንበል? አምላክ ከእኛ ጋር ከሆነ ማን ሊቃወመን ይችላል?
ለገዛ ልጁ እንኳ ያልሳሳው፣ ከዚህ ይልቅ ለእኛ ለሁላችን አሳልፎ የሰጠው አምላክ፣ ከእሱ ጋር አብሮ ሌሎች ነገሮችን ሁሉ እንዴት በደግነት አይሰጠንም?
አምላክ የመረጣቸውን ማን ሊከሳቸው ይችላል? ምክንያቱም የሚያጸድቃቸው አምላክ ራሱ ነው።
እነሱን የሚኮንን ማን ነው? ምክንያቱም የሞተው ብሎም ከሞት የተነሳውና በአምላክ ቀኝ የተቀመጠው እንዲሁም ስለ እኛ የሚማልደው ክርስቶስ ኢየሱስ ነው።
ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ወይስ ጭንቀት ወይስ ስደት ወይስ ረሃብ ወይስ ራቁትነት ወይስ አደጋ ወይስ ሰይፍ?
ይህም “ስለ አንተ ቀኑን ሙሉ ሞትን እንጋፈጣለን፤ እንደ እርድ በጎችም ተቆጠርን” ተብሎ እንደተጻፈው ነው።
ከዚህ ይልቅ በወደደን በእሱ አማካኝነት እነዚህን ነገሮች ሁሉ ሙሉ በሙሉ በድል አድራጊነት እንወጣለን።
ምክንያቱም ሞትም ቢሆን፣ ሕይወትም ቢሆን፣ መላእክትም ቢሆኑ፣ መንግሥታትም ቢሆኑ፣ አሁን ያሉት ነገሮችም ቢሆኑ፣ ወደፊት የሚመጡት ነገሮችም ቢሆኑ፣ ማንኛውም ኃይል ቢሆን፣
ከፍታም ቢሆን፣ ዝቅታም ቢሆን፣ ሌላ ማንኛውም ፍጥረት ቢሆን በጌታችን በክርስቶስ ኢየሱስ አማካኝነት ከተገለጸው የአምላክ ፍቅር ሊለየን እንደማይችል ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ነኝ።
እኔ የክርስቶስን አርዓያ እንደምከተል እናንተም የእኔን አርዓያ ተከተሉ።
በሁሉም ነገር ስለምታስቡኝና ለእናንተ ያስተላለፍኳቸውን ወጎች አጥብቃችሁ ስለያዛችሁ አመሰግናችኋለሁ።
ይሁንና የወንድ ሁሉ ራስ ክርስቶስ፣ የሴትም ራስ ወንድ፣ የክርስቶስ ራስ ደግሞ አምላክ እንደሆነ እንድታውቁ እወዳለሁ።
ራሱን ሸፍኖ የሚጸልይ ወይም ትንቢት የሚናገር ወንድ ሁሉ የእሱን ራስ ያዋርዳል፤
ራሷን ሳትሸፍን የምትጸልይ ወይም ትንቢት የምትናገር ሴት ሁሉ ደግሞ የእሷን ራስ ታዋርዳለች፤ እንዲህ የምታደርግ ሴት ራሷን እንደተላጨች ሴት ትቆጠራለች።
አንዲት ሴት ራሷን የማትሸፍን ከሆነ ፀጉሯን ትቆረጥ፤ ፀጉሯን መቆረጧ ወይም መላጨቷ የሚያሳፍራት ከሆነ ግን ትሸፈን።
ወንድ የአምላክ አምሳልና ክብር ስለሆነ ራሱን መሸፈን የለበትም፤ ሴት ግን የወንድ ክብር ናት።
ሴት ከወንድ ተገኘች እንጂ ወንድ ከሴት አልተገኘምና።
ከዚህም በተጨማሪ ሴት ለወንድ ተፈጠረች እንጂ ወንድ ለሴት አልተፈጠረም።
ከዚህ የተነሳም ሆነ ለመላእክት ሲባል ሴት በሥልጣን ሥር መሆኗን የሚያሳይ ምልክት በራሷ ላይ ታድርግ።
ይሁንና በጌታ ተከታዮች ዘንድ ሴት ያለወንድ አትኖርም፤ ወንድም ያለሴት አይኖርም።
ሴት ከወንድ እንደተገኘች ሁሉ ወንድም የተገኘው በሴት አማካኝነት ነውና፤ ሆኖም ሁሉም ነገሮች የተገኙት ከአምላክ ነው።
እስቲ እናንተ ራሳችሁ ፍረዱ፦ ሴት ሳትሸፈን ወደ አምላክ ብትጸልይ ተገቢ ይሆናል?
ወንድ ፀጉሩን ቢያስረዝም ውርደት እንደሚሆንበት ተፈጥሮ ራሱ እንኳ አያስተምራችሁም?
ሴት ግን ፀጉሯን ብታስረዝም ለእሷ ክብር አይደለም? ፀጉሯ የተሰጣት በመሸፈኛ ምትክ ነውና።
ይሁን እንጂ ማንም ሰው ሌላ ልማድ መከተል አለብን በሚል ለመከራከር ቢፈልግ እኛም ሆን የአምላክ ጉባኤ ከዚህ የተለየ ልማድ የለንም።
ሆኖም ስብሰባችሁ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ ስለሚያመዝን እነዚህን መመሪያዎች ስሰጣችሁ ላመሰግናችሁ አልፈልግም።
በመጀመሪያ ደረጃ፣ በጉባኤ በምትሰበሰቡበት ጊዜ በመካከላችሁ ክፍፍል እንዳለ እሰማለሁ፤ ደግሞም ይህ በተወሰነ መጠን እውነትነት እንዳለው አምናለሁ።
በዚህ ሁኔታ በእናንተ መካከል ኑፋቄዎች ብቅ ማለታቸው አይቀርም፤ ይህም መሆኑ ከእናንተ መካከል ተቀባይነት የሚያገኙት ሰዎች ተለይተው እንዲታወቁ ያስችላል።
አንድ ላይ በምትሰበሰቡበት ጊዜ የሚኖረው ሁኔታ የጌታ ራትን በአግባቡ ለማክበር የሚያስችል አይደለም።
የጌታ ራትን በምትበሉበት ጊዜ አንዳንዶች አስቀድመው የራሳቸውን ራት ስለሚበሉ አንዱ ይራባል ሌላው ደግሞ ይሰክራል።
የምትበሉበትና የምትጠጡበት ቤት የላችሁም? ወይስ የአምላክን ጉባኤ በመናቅ ምንም የሌላቸውን ታሳፍራላችሁ? እንግዲህ ምን ልበላችሁ? ላመስግናችሁ? በዚህ ነገርስ አላመሰግናችሁም።
እኔ ከጌታ የተቀበልኩትን ለእናንተ አስተላልፌአለሁና፤ ጌታ ኢየሱስ አልፎ በተሰጠበት ሌሊት ቂጣ አንስቶ
ካመሰገነ በኋላ ቆርሶ “ይህ ስለ እናንተ የሚሰጠውን ሥጋዬን ያመለክታል። ይህን ሁልጊዜ ለመታሰቢያዬ አድርጉት” አለ።
በተጨማሪም ራት ከበሉ በኋላ ጽዋውን አንስቶ ልክ እንደዚሁ አደረገ፤ እንዲህም አለ፦ “ይህ ጽዋ በደሜ አማካኝነት የሚመሠረተውን አዲሱን ቃል ኪዳን ያመለክታል። ከዚህ ጽዋ በጠጣችሁ ቁጥር ይህን ሁልጊዜ ለመታሰቢያዬ አድርጉት።”
ይህን ቂጣ በበላችሁና ከዚህ ጽዋ በጠጣችሁ ቁጥር ጌታ እስከሚመጣ ድረስ ሞቱን ታውጃላችሁ።
እንግዲህ የማይገባው ሆኖ ሳለ ከቂጣው የሚበላ ወይም ከጌታ ጽዋ የሚጠጣ ከጌታ አካልና ደም ጋር በተያያዘ ተጠያቂ ይሆናል።
አንድ ሰው የሚገባው እንደሆነ ለማወቅ በቅድሚያ ራሱን ይመርምር፤ ቂጣውን መብላትና ጽዋውን መጠጣት የሚችለው ይህን ካደረገ ብቻ ነው።
ምክንያቱም አካሉ ምን ትርጉም እንዳለው ሳይገነዘብ የሚበላና የሚጠጣ በራሱ ላይ ፍርድ የሚያመጣበትን ነገር መብላትና መጠጣት ይሆንበታል።
ከእናንተ መካከል ብዙዎቹ የተዳከሙትና ታማሚ የሆኑት እንዲሁም ጥቂት የማይባሉት በሞት ያንቀላፉት በዚህ ምክንያት ነው።
ሆኖም ራሳችንን መርምረን ብናውቅ ኖሮ ባልተፈረደብን ነበር።
ይሁን እንጂ በሚፈረድብን ጊዜ፣ ከዓለም ጋር አብረን እንዳንኮነን ሲል ይሖዋ ይገሥጸናል።
ስለዚህ ወንድሞቼ፣ ይህን ራት ለመብላት በምትሰበሰቡበት ጊዜ እርስ በርሳችሁ ተጠባበቁ።
የምትሰበሰቡት ለፍርድ እንዳይሆን የራበው ሰው ካለ እዚያው ቤቱ ይብላ። የቀሩትን ጉዳዮች ግን ስመጣ አስተካክላለሁ።
በአምላክ ፈቃድ የክርስቶስ ኢየሱስ ሐዋርያ እንዲሆን ከተጠራው ከጳውሎስና ከወንድማችን ከሶስቴንስ፣
በቆሮንቶስ ለሚገኘው የአምላክ ጉባኤ ይኸውም ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር ባላችሁ አንድነት ለተቀደሳችሁ፣ እንዲሁም የእነሱም ሆነ የእኛ ጌታ የሆነውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም በየስፍራው ሆነው ከሚጠሩ ሁሉ ጋር ቅዱሳን ለመሆን ለተጠራችሁ፦
ከአባታችን ከአምላክና ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን።
በክርስቶስ ኢየሱስ ለእናንተ በሰጠው ጸጋ የተነሳ አምላኬን ሁልጊዜ ስለ እናንተ አመሰግናለሁ፤
ምክንያቱም በሁሉም ነገር ይኸውም በመናገር ችሎታ ሁሉና በእውቀት ሁሉ በክርስቶስ በልጽጋችኋል፤
ደግሞም ስለ ክርስቶስ የተሰጠው ምሥክርነት በእናንተ መካከል በሚገባ ሥር ሰዷል፤
ስለዚህ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን መገለጥ በጉጉት ስትጠባበቁ ማንኛውም ስጦታ ፈጽሞ አይጎድልባችሁም።
በተጨማሪም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቀን ከማንኛውም ክስ ነፃ መሆን እንድትችሉ እስከ መጨረሻው ያጸናችኋል።
ከልጁ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ የጠራችሁ አምላክ ታማኝ ነው።
እንግዲህ ወንድሞች፣ ሁላችሁም ንግግራችሁ አንድ እንዲሆንና በመካከላችሁ መከፋፈል እንዳይኖር፣ ከዚህ ይልቅ በአስተሳሰብም ሆነ በዓላማ ፍጹም አንድነት እንዲኖራችሁ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አጥብቄ አሳስባችኋለሁ።
ወንድሞቼ ሆይ፣ የቀሎኤ ቤተሰብ አባላት የሆኑ አንዳንዶች በመካከላችሁ አለመግባባት እንዳለ ነግረውኛል።
ይኸውም እያንዳንዳችሁ “እኔ የጳውሎስ ነኝ፣” “እኔ ግን የአጵሎስ ነኝ፣” “እኔ ደግሞ የኬፋ ነኝ፣” “እኔ የክርስቶስ ነኝ” ትላላችሁ።
ታዲያ የክርስቶስ ጉባኤ ተከፋፍሏል ማለት ነው? ጳውሎስ ለእናንተ ሲል በእንጨት ላይ ተሰቅሏል እንዴ? ወይስ የተጠመቃችሁት በጳውሎስ ስም ነው?
ከቀርስጶስና ከጋይዮስ በስተቀር ከእናንተ አንዳችሁንም ባለማጥመቄ አምላክን አመሰግናለሁ፤
በመሆኑም ከእናንተ መካከል በእኔ ስም እንደተጠመቀ ሊናገር የሚችል ማንም የለም።
እርግጥ የእስጢፋናስን ቤተሰብም አጥምቄአለሁ። ከእነዚህ ሌላ ግን ያጠመቅኩት ሰው መኖሩን አላስታውስም።
ክርስቶስ የላከኝ እንዳጠምቅ ሳይሆን ምሥራቹን እንዳውጅ ነው፤ ደግሞም የክርስቶስ የመከራ እንጨት ከንቱ እንዳይሆን ምሥራቹን የማውጀው በንግግር ጥበብ አይደለም።
ስለ መከራው እንጨት የሚነገረው መልእክት ወደ ጥፋት እያመሩ ላሉት ሞኝነት፣ ወደ መዳን በሚወስደው ጎዳና ላይ ላለነው ለእኛ ግን የአምላክ ኃይል መገለጫ ነው።
“የጥበበኞችን ጥበብ አጠፋለሁ፤ የሊቃውንትንም ማስተዋል ወዲያ እጥላለሁ” ተብሎ ተጽፏልና።
የዚህ ሥርዓት ጥበበኞች የት አሉ? ጸሐፍትስ የት አሉ? ተሟጋቾችስ የት አሉ? አምላክ የዓለምን ጥበብ ሞኝነት አላደረገም?
ዓለም በራሱ ጥበብ አምላክን ሊያውቀው ስላልቻለ አምላክ በጥበቡ፣ እንደ ሞኝነት በሚቆጠረውና እየተሰበከ ባለው መልእክት አማካኝነት የሚያምኑትን ሰዎች ለማዳን መርጧል።
አይሁዳውያን ተአምራዊ ምልክቶች ማየት ይፈልጋሉ፤ ግሪካውያን ደግሞ ጥበብን ይሻሉ፤
እኛ ግን በእንጨት ላይ የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን፤ ይህም ለአይሁዳውያን መሰናክል ለአሕዛብ ደግሞ ሞኝነት ነው።
ይሁን እንጂ ክርስቶስ ለተጠሩት፣ ለአይሁዳውያንም ሆነ ለግሪካውያን የአምላክ ኃይልና የአምላክ ጥበብ ነው።
ምክንያቱም የአምላክ ሞኝነት እንደሆነ ተደርጎ የሚታሰበው ነገር ከሰዎች ጥበብ ይበልጣል፤ የአምላክ ድክመት እንደሆነ ተደርጎ የሚታሰበው ነገር ደግሞ ከሰዎች ብርታት ይበልጣል።
ወንድሞች፣ ከራሳችሁ ሁኔታ መረዳት እንደምትችሉት በሰብዓዊ አመለካከት ጥበበኞች የሆኑ ብዙዎች፣ ኃያላን የሆኑ ብዙዎች እንዲሁም ከትልቅ ቤተሰብ የተወለዱ ብዙዎች አልተጠሩም፤
ከዚህ ይልቅ አምላክ ጥበበኞችን ያሳፍር ዘንድ የዓለምን ሞኝ ነገር መረጠ፤ ብርቱውንም ነገር ያሳፍር ዘንድ የዓለምን ደካማ ነገር መረጠ፤
አምላክ በሰዎች ዘንድ ትልቅ ግምት የሚሰጠውን ነገር ከንቱ ያደርግ ዘንድ በዚህ ዓለም ዝቅ ተደርጎ የሚታየውንና የተናቀውን ነገር ይኸውም ከንቱ መስሎ የሚታየውን ነገር መረጠ፤
ይህን ያደረገው ማንም ሰው በአምላክ ፊት እንዳይኩራራ ነው።
ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድነት ሊኖራችሁ የቻለው በእሱ ምክንያት ነው፤ ክርስቶስ ደግሞ ለእኛ ከአምላክ የመጣ ጥበብ፣ ጽድቅና ቅድስና ሆኖልናል፤ እንዲሁም በቤዛው ነፃ አውጥቶናል፤
ይህም “የሚኩራራ በይሖዋ ይኩራራ” ተብሎ እንደተጻፈው ነው።
በደብዳቤያችሁ ላይ ያነሳችኋቸውን ጥያቄዎች በተመለከተ፣ አንድ ወንድ አንዲትን ሴት ባይነካ ይሻላል፤
ይሁንና የፆታ ብልግና ስለተስፋፋ እያንዳንዱ ወንድ የራሱ ሚስት ትኑረው፤ እያንዳንዷም ሴት የራሷ ባል ይኑራት።
ባል ለሚስቱ የሚገባትን ያድርግላት፤ ሚስትም ብትሆን ለባሏ እንደዚሁ ታድርግለት።
ሚስት በራሷ አካል ላይ ሥልጣን የላትም፤ ሥልጣን ያለው ባሏ ነው፤ በተመሳሳይም ባል በራሱ አካል ላይ ሥልጣን የለውም፤ ሥልጣን ያላት ሚስቱ ናት።
አንዳችሁ ለሌላው የሚገባውን አትከልክሉ፤ እንዲህ ማድረግ የምትችሉት በጋራ ስምምነት የተወሰነ ጊዜ ለጸሎት ለማዋል ካሰባችሁ ብቻ ነው፤ ደግሞም ራሳችሁን መግዛት አቅቷችሁ ሰይጣን እንዳይፈታተናችሁ እንደገና አብራችሁ ሁኑ።
ይሁን እንጂ ይህን ያልኩት እንዲህ ማድረግ እንደሚቻል ለመግለጽ ነው እንጂ ለማዘዝ አይደለም።
ይሁንና ሰው ሁሉ እንደ እኔ ቢሆን ደስ ባለኝ ነበር። ነገር ግን እያንዳንዱ ሰው ከአምላክ ያገኘው የራሱ ስጦታ አለው፤ አንዱ አንድ ዓይነት ስጦታ ሲኖረው ሌላው ደግሞ ሌላ ዓይነት ስጦታ አለው።
ሆኖም ላላገቡና መበለት ለሆኑ እንደ እኔ ሆነው ቢኖሩ የተሻለ ነው እላለሁ።
ራሳቸውን መግዛት ካቃታቸው ግን ያግቡ፤ በፍትወት ከመቃጠል ማግባት ይሻላልና።
ላገቡት ሰዎች ይህን መመሪያ እሰጣለሁ፤ ይህ መመሪያ የጌታ እንጂ የእኔ አይደለም፤ ሚስት ከባሏ አትለያይ።
ብትለያይ ግን ሳታገባ ትኑር ወይም ከባሏ ጋር ትታረቅ፤ ባልም ሚስቱን መተው የለበትም።
ለሌሎች ደግሞ እንዲህ እላለሁ፤ ይህን የምለው እኔ እንጂ ጌታ አይደለም፦ አንድ ወንድም አማኝ ያልሆነች ሚስት ካለችውና አብራው ለመኖር ከተስማማች አይተዋት፤
እንዲሁም አንዲት ሴት አማኝ ያልሆነ ባል ካላትና ባሏ አብሯት ለመኖር ከተስማማ አትተወው።
አማኝ ያልሆነ ባል ከሚስቱ ጋር ባለው ዝምድና የተነሳ ተቀድሷልና፤ አማኝ ያልሆነች ሚስትም ከወንድም ጋር ባላት ዝምድና የተነሳ ተቀድሳለች፤ እንዲህ ባይሆን ኖሮ ልጆቻችሁ ርኩሳን በሆኑ ነበር፤ አሁን ግን ቅዱሳን ናቸው።
ይሁንና አማኝ ያልሆነው ወገን ለመለየት ከመረጠ ይለይ፤ እንዲህ ያለ ሁኔታ በሚፈጠርበት ጊዜ አንድ ወንድም ወይም አንዲት እህት ምንም ዓይነት ግዴታ የለባቸውም፤ አምላክ የጠራችሁ ለሰላም ነውና።
አንቺ ሚስት፣ ባልሽን ታድኚው እንደሆነ ምን ታውቂያለሽ? ወይስ አንተ ባል፣ ሚስትህን ታድን እንደሆነ ምን ታውቃለህ?
ያም ሆነ ይህ እያንዳንዱ ሰው ይሖዋ በሰጠው ድርሻና አምላክ ሲጠራው በነበረበት ሁኔታ ይመላለስ። ለጉባኤዎችም ሁሉ ይህን መመሪያ እሰጣለሁ።
አንድ ሰው የተጠራው ተገርዞ እያለ ነው? እንዳልተገረዘ ሰው አይሁን። አንድ ሰው የተጠራው ሳይገረዝ ነው? ከሆነ አይገረዝ።
መገረዝ ምንም ማለት አይደለም፤ አለመገረዝም ቢሆን ምንም ማለት አይደለም፤ ዋናው ነገር የአምላክን ትእዛዛት መጠበቅ ነው።
እያንዳንዱ ሰው በተጠራበት ጊዜ የነበረበት ሁኔታ ምንም ይሁን ምን በዚያው ይቀጥል።
የተጠራኸው ባሪያ እያለህ ነው? ይሄ አያስጨንቅህ፤ ሆኖም ነፃ መውጣት የምትችል ከሆነ አጋጣሚውን ተጠቀምበት።
ባሪያ እያለ የተጠራ ማንኛውም የጌታ ደቀ መዝሙር ነፃ የወጣ የጌታ ሰው ነውና፤ በተመሳሳይም ነፃ እያለ የተጠራ ሰው የክርስቶስ ባሪያ ነው።
በዋጋ ተገዝታችኋል፤ የሰው ባሪያ መሆናችሁ ይብቃ።
ወንድሞች፣ እያንዳንዱ ሰው በተጠራበት ጊዜ የነበረበት ሁኔታ ምንም ይሁን ምን በአምላክ ፊት በዚያው ሁኔታ ይቀጥል።