text
stringlengths
4
267
ቅጥሮቜሜን በግንብ መደርመሻ መሣሪያ ይደበድባልፀ ማማዎቜሜንም በመጥሚቢያ ያፈርሳል።
ፈሚሶቹ እጅግ ብዙ ኹመሆናቾው ዚተነሳ አቧራ ያለብሱሻልፀ ሰዎቜ ቅጥሮቿ ወደፈሚሱባት ኹተማ እንደሚገቡ ሁሉ እሱም በበሮቜሜ በሚገባበት ጊዜ ዚፈሚሰኞቹ፣ ዚመንኮራኩሮቹና ዚሠሚገሎቹ ድምፅ ቅጥሮቜሜን ያናውጣል።
ዚፈሚሶቹ ኮ቎ዎቜ ጎዳናዎቜሜን ሁሉ ይሚግጣሉፀ ሕዝብሜን በሰይፍ ይገድላልፀ ግዙፍ ዚሆኑት ዓምዶቜሜ መሬት ላይ ይንኮታኮታሉ።
ሀብትሜን ይበዘብዛሉፀ ሞቀጥሜን ይዘርፋሉፀ ቅጥሮቜሜን ያፈርሳሉፀ ዚሚያማምሩ ቀቶቜሜንም ያወድማሉፀ ኚዚያም ድንጋዮቜሜን፣ ሳንቃዎቜሜንና አፈርሜን ወደ ባሕር ይጥላሉ።’
“‘ዚዘፈንሜ ጩኞት ጞጥ እንዲል አደርጋለሁፀ ዚበገናሜም ድምፅ ኚእንግዲህ አይሰማም።
ዚሚያንጞባርቅ ገላጣ ዓለትም አደርግሻለሁፀ ዚመሚብ ማስጫ ቊታ ትሆኛለሜ። ዳግመኛ አትገነቢምፀ እኔ ይሖዋ ራሎ ተናግሬአለሁና’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ጢሮስን እንዲህ ይላል፩ ‘ሞት አፋፍ ላይ ያሉት ሲያቃስቱና በመካኚልሜ ጭፍጹፋ ሲካሄድ፣ ኚውድቀትሜ ድምፅ ዚተነሳ ደሎቶቜ አይናወጡም?
ዚባሕርም ገዢዎቜ ሁሉ ኚዙፋኖቻ቞ው ይወርዳሉፀ ልብሳ቞ውንም ያወልቃሉፀ ዹተጠለፉ ሞማዎቻ቞ውንም አውልቀው ይጥላሉፀ ደግሞም በጣም ይንቀጠቀጣሉ። መሬት ላይ ተቀምጠው ያለማቋሚጥ ይንቀጠቀጣሉፀ በመገሹምም አተኩሚው ይመለኚቱሻል።
በአንቺም ላይ ሙሟ ያወርዳሉፀ እንዲህም ይሉሻልፊ “ባሕር አቋርጠው ዚመጡ ሰዎቜ ዚሰፈሩብሜ፣ ዚተወደስሜ ኹተማ ሆይ፣ እንዎት ጠፋሜ!አንቺም ሆንሜ ነዋሪዎቜሜ በምድር ነዋሪዎቜ ሁሉ ላይሜብር ዚምትነዙ ዚባሕር ላይ ኃያላን ነበራቜሁ።
በምትወድቂበት ቀን ደሎቶቜ ይንቀጠቀጣሉፀጥፋት በሚደርስብሜ ጊዜ በባሕር ላይ ያሉ ደሎቶቜ ይሞበራሉ።”’
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፩ ‘ሰው እንደማይኖርባ቞ው ኚተሞቜ ባድማ ሳደርግሜ፣ ዚሚያጥለቀልቅ ውኃ ሳመጣብሜና ኃይለኛ ውኃ ሲሞፍንሜ፣
አንቺንም ሆነ ኚአንቺ ጋር ወደ ጉድጓድ ዚሚወርዱትን፣ ዚጥንት ዘመን ሰዎቜ ወዳሉበት አወርዳቜኋለሁፀ ወደ ጉድጓድ ኚሚወርዱት ጋር፣ ጥንት እንደወደሙት ቊታዎቜ እጅግ ዝቅተኛ በሆነ ምድር እንድትኖሪ አደርጋለሁፀ ይህም ዹሚሆነው ሰው እንዳይኖርብሜ ነው። ኚዚያ በኋላ ዚሕያዋንን ምድር ኹፍ ኹፍ አደርጋለሁ።
“‘በአንቺ ላይ ድንገተኛ ሜብር አመጣለሁፀ ኚእንግዲህም አትኖሪም። ይፈልጉሻል ግን ፈጜሞ አትገኚም’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።”
በ30ኛው ዓመት፣ በአራተኛው ወር፣ ኚወሩም በአምስተኛው ቀን፣ በኬባር ወንዝ አጠገብ በግዞት በተወሰደው ሕዝብ መካኚል ሳለሁ ሰማያት ተኹፍተው አምላክ ዹገለጠልኝን ራእዮቜ ማዚት ጀመርኩ።
ኚወሩ በአምስተኛው ቀን ይኾውም ንጉሥ ዮአኪን በግዞት በተወሰደ በአምስተኛው ዓመት፣
በኚለዳውያን ምድር በኬባር ወንዝ አጠገብ ዹይሖዋ ቃል ዚካህኑ ዚቡዚ ልጅ ወደሆነው ወደ ሕዝቅኀል መጣ። በዚያም ዹይሖዋ ኃይል በእሱ ላይ ወሚደ።
እኔም በማዚት ላይ ሳለሁ ኹሰሜን ኃይለኛ አውሎ ነፋስ ሲመጣ ተመለኚትኩፀ በዚያም ታላቅ ደመናና በደማቅ ብርሃን ዹተኹበበ ዚእሳት ብልጭታ ነበርፀ ኚእሳቱም መካኚል ዚሚያብሚቀርቅ ብሚት ዚሚመስል ነገር ይወጣ ነበር።
በመካኚሉም ዚአራት ሕያዋን ፍጥሚታት አምሳያ ነበርፀ ዚእያንዳንዳ቞ውም መልክ እንደ ሰው መልክ ነበር።
እያንዳንዳ቞ው አራት አራት ፊትና አራት አራት ክንፍ ነበራ቞ው።
እግሮቻ቞ው ቀጥ ያሉ ነበሩፀ ዚእግራ቞ውም ኮ቎ ዚጥጃ ኮ቎ ይመስል ነበርፀ እግሮቻ቞ውም እንደተወለወለ መዳብ ያብሚቀርቃሉ።
በአራቱም ጎኖቻ቞ው ኚክንፎቻ቞ው ሥር ዹሰው እጆቜ ነበሯ቞ውፀ አራቱም ፊቶቜና ክንፎቜ ነበሯ቞ው።
ክንፎቻ቞ውም እርስ በርሳ቞ው ይነካኩ ነበር። በሚሄዱበት ጊዜ አይዞሩምፀ እያንዳንዳ቞ውም ቀጥ ብለው ወደ ፊት ይሄዱ ነበር።
ዚፊታ቞ው መልክ ይህን ይመስል ነበር፩ አራቱም ዹሰው ፊት ነበራ቞ውፀ በስተ ቀኝ ዚአንበሳ ፊት፣ በስተ ግራ ዚበሬ ፊት ነበራ቞ውፀ ደግሞም አራቱም ዚንስር ፊት ነበራ቞ው።
ፊታ቞ው ይህን ይመስላል። ክንፎቻ቞ው ኚእነሱ በላይ ተዘርግተዋል። እያንዳንዳ቞ው እርስ በርሳ቞ው ዚሚነካኩ ሁለት ክንፎቜ ነበሯ቞ውፀ ሁለቱ ክንፎቻ቞ው ደግሞ ሰውነታ቞ውን ይሾፍኑ ነበር።
እያንዳንዳ቞ው መንፈሱ ወደመራ቞ው አቅጣጫ ሁሉ ቀጥ ብለው ወደ ፊት ይሄዱ ነበር። በሚሄዱበት ጊዜ አይዞሩም።
ዚሕያዋን ፍጥሚታቱ መልክ ዚሚነድ ዹኹሰል ፍም ይመስላልፀ በሕያዋን ፍጥሚታቱም መካኚል እዚነደደ ያለ ቜቊ ዚሚመስል ነገር ወዲያና ወዲህ ይል ነበርፀ ኚእሳቱም መካኚል መብሚቅ ይወጣ ነበር።
ሕያዋን ፍጥሚታቱም ወዲያና ወዲህ ሲሄዱ እንቅስቃሎያ቞ው ዚመብሚቅ ብልጭታ ይመስል ነበር።
እኔም ሕያዋን ፍጥሚታቱን ስመለኚት አራት ፊቶቜ ባሉት በእያንዳንዱ ሕያው ፍጡር አጠገብ በምድር ላይ አንድ አንድ መንኮራኩር አዚሁ።
መንኮራኩሮቹ በአጠቃላይ ሲታዩ እንደ ክርስቲሎቀ ዚሚያብሚቀርቅ መልክ ነበራ቞ውፀ አራቱም ይመሳሰላሉ። መልካ቞ውና አሠራራ቞ው ሲታይ በአንድ መንኮራኩር ውስጥ በጎን በኩል ሌላ መንኮራኩር ዚተሰካ ይመስላል።
በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ መዞር ሳያስፈልጋ቞ው በአራቱም ጎን በፈለጉበት አቅጣጫ መሄድ ይቜላሉ።
ዚመንኮራኩሮቹም ጠርዝ እጅግ ሹጅም ኹመሆኑ ዚተነሳ ዚሚያስፈራ ነበርፀ ዚአራቱም መንኮራኩሮቜ ጠርዝ ዙሪያውን በዓይኖቜ ዹተሞላ ነበር።
ሕያዋን ፍጥሚታቱ በተንቀሳቀሱ ቁጥር፣ መንኮራኩሮቹም ኚእነሱ ጋር አብሚው ይንቀሳቀሳሉፀ ሕያዋን ፍጥሚታቱ ኚምድር ኹፍ ኹፍ ሲሉ መንኮራኩሮቹም ኹፍ ኹፍ ይላሉ።
መንፈሱ ወደመራ቞ው አቅጣጫ፣ መንፈሱ ወደሚሄድበት ቊታ ሁሉ ይሄዳሉ። መንኮራኩሮቹ ኚእነሱ ጋር አብሚው ኹፍ ኹፍ ይሉ ነበርፀ በሕያዋን ፍጥሚታቱ ላይ ዚሚሠራው መንፈስ በመንኮራኩሮቹም ውስጥ ነበርና።
ሕያዋን ፍጥሚታቱ ሲንቀሳቀሱ እነሱም ይንቀሳቀሳሉፀ ሕያዋን ፍጥሚታቱ ሲቆሙ እነሱም ይቆማሉፀ ኚምድር ኹፍ ኹፍ ሲሉ መንኮራኩሮቹም ኚእነሱ ጋር አብሚው ኹፍ ኹፍ ይሉ ነበርፀ በሕያዋን ፍጥሚታቱ ላይ ዚሚሠራው መንፈስ በመንኮራኩሮቹም ውስጥ ነበርና።
ኚሕያዋን ፍጥሚታቱ ራስ በላይ እጅግ አስደናቂ እንደሆነ በሚዶ ዚሚያብሚቀርቅ ጠፈር ዚሚመስል ነገር ነበርፀ ይህም ኚራሳ቞ው በላይ ተዘርግቶ ነበር።
ኚጠፈሩ በታቜ ክንፎቻ቞ው አንዳ቞ው ወደ ሌላው ቀጥ ብለው ነበር። እያንዳንዳ቞ውም በዚህ ጎንና በዚያኛው ጎን ሰውነታ቞ውን ዚሚሞፍኑባ቞ው ሁለት ሁለት ክንፎቜ ነበሯ቞ው።
ዚክንፎቻ቞ውን ድምፅ ስሰማ እንደሚጎርፍ ውኃ ድምፅ፣ ደግሞም ሁሉን እንደሚቜል አምላክ ድምፅ ነበር። በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ ድምፁ እንደ ሠራዊት ድምፅ ነበር። በሚቆሙበት ጊዜ ክንፎቻ቞ውን ወደ ታቜ ያደርጋሉ።
ኚራሳ቞ው በላይ ካለው ጠፈር በላይ አንድ ድምፅ ይሰማ ነበር። (በሚቆሙበት ጊዜ ክንፎቻ቞ውን ወደ ታቜ ያደርጉ ነበር።)
ኚራሳ቞ው በላይ ካለው ጠፈር በላይ ዹሰንፔር ድንጋይ ዚመሰለ እንደ ዙፋን ያለ ነገር ነበር። ኹላይ በኩል ባለው በዙፋኑ ላይ መልኩ ዹሰው መልክ ዚሚመስል ተቀምጩ ነበር።
ወገቡ ኚሚመስለው ነገር ጀምሮ ወደ ላይ፣ እሳት ዚሚመስል እንደ ብሚት ዚሚያብሚቀርቅ ነገር ሲወጣ አዚሁፀ ደግሞም ኚወገቡ ጀምሮ ወደ ታቜ፣ እሳት ዚሚመስል ነገር አዚሁ። በዙሪያውም ደማቅ ብርሃን ነበርፀ
ይህም ዝናባማ በሆነ ቀን በደመና ውስጥ እንደሚታይ ቀስተ ደመና ነበር። በዙሪያው ያለው ደማቅ ብርሃን ይህን ይመስላል። ደግሞም ዹይሖዋን ክብር ይመስል ነበር። እኔም ባዚሁት ጊዜ በግንባሬ ተደፋሁፀ ኚዚያም አንዱ ሲናገር ድምፅ ሰማሁ።
“አንተም ዹሰው ልጅ ሆይ፣ ስለ እስራኀል ተራሮቜ ትንቢት ተናገርፀ እንዲህም በል፩ ‘ዚእስራኀል ተራሮቜ ሆይ፣ ዹይሖዋን ቃል ስሙ።
ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ጠላት ስለ እናንተ ‘እሰይ! ዚጥንቶቹ ኹፍ ያሉ ቊታዎቜ ሳይቀሩ ዚእኛ ርስት ሆነዋል!’ ብሏል።”’
“ስለዚህ ትንቢት ተናገርፀ እንዲህም በል፩ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ኚብሔራት መካኚል ለተሚፉት ርስት እንድትሆኑ ባድማ ስላደሚጓቜሁና ኚዚአቅጣጫው ጥቃት ስለሰነዘሩባቜሁ እንዲሁም ሰው አፍ ውስጥ ስለገባቜሁና ሰዎቜ ስማቜሁን ስላጠፉ፣
ዚእስራኀል ተራሮቜ ሆይ፣ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ዹተናገሹውን ቃል ስሙ! ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ለተራሮቜና ለኮሚብቶቜ፣ ለጅሚቶቜና ለሞለቆዎቜ፣ ፈራርሰው ባድማ ለሆኑት ቊታዎቜና በዙሪያ቞ው ባሉት ኚጥፋት ዹተሹፉ ብሔራት ለተበዘበዙት እንዲሁም መሳለቂያ ለሆኑት ዹተተዉ ኚተሞቜ ይህን ቃል ተናግሯልፀ
ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እነሱን በተመለኹተ እንዲህ ይላል፩ ‘ዚግጊሜ ቊታዎቿን ለመውሰድና ምድሪቱን ለመበዝበዝ ሲሉ በታላቅ ደስታና በኹፍተኛ ንቀት ምድሬን ዹገዛ ርስታ቞ው እንደሆነ አድርገው በተናገሩት፣ ኚጥፋት በተሚፉት ብሔራትና በመላዋ ኀዶም ላይ በቅንዓቮ እሳት እናገራለሁ።’”’
“ስለዚህ ስለ እስራኀል ምድር ትንቢት ተናገርፀ ለተራሮቜና ለኮሚብቶቜ፣ ለጅሚቶቜና ለሞለቆዎቜ እንዲህ በል፩ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “እነሆ፣ ብሔራት ያደሚሱባቜሁን ውርደት ስለተሞኚማቜሁ በቅንዓቮና በቁጣዬ እናገራለሁ።”’
“ስለዚህ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘በዙሪያቜሁ ያሉት ብሔራት ዹገዛ ራሳ቞ውን ኀፍሚት ይሾኹማሉ ብዬ እጄን አንስቌ ምያለሁ።
ዚእስራኀል ተራሮቜ ሆይ፣ እናንተ ግን ለሕዝቀ ለእስራኀል ቅርንጫፍ ታወጣላቜሁፀ ፍሬም ታፈራላቜሁፀ እነሱ በቅርቡ ይመለሳሉና።
እኔ ኚእናንተ ጋር ነኝፀ ፊቮንም ወደ እናንተ እመልሳለሁፀ እናንተም ትታሚሳላቜሁፀ ደግሞም ዘር ይዘራባቜኋል።
ሕዝባቜሁን ይኾውም መላውን ዚእስራኀል ቀት አበዛለሁፀ ኚተሞቹም ዹሰው መኖሪያ ይሆናሉፀ ዚፈራሚሱትም ስፍራዎቜ ዳግመኛ ይገነባሉ።
አዎ፣ ሕዝባቜሁንና ኚብቶቻቜሁን አበዛለሁፀ እነሱም ይበዛሉፀ ፍሬያማም ይሆናሉ። እንደቀድሞው ዘመን ሰዎቜ እንዲኖሩባቜሁ አደርጋለሁፀ ደግሞም ኚበፊቱ ዹበለጠ አበለጜጋቜኋለሁፀ እናንተም እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ታውቃላቜሁ።
በእናንተ ላይ ሰዎቜ ይኾውም ሕዝቀ እስራኀል እንዲመላለሱ አደርጋለሁፀ እነሱም ይወርሷቜኋል። ዚእነሱ ርስት ትሆናላቜሁፀ ኚእንግዲህ ልጅ አልባ አታደርጓ቞ውም።’”
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘“ሰዎቜን ዚምትበላና በላይዋ ያሉትን ብሔራት ዚወላድ መሃን ዚምታደርግ ምድር ናቜሁ” ስለሚሏቜሁ፣’
‘ኚእንግዲህ ሰው አትበሉም ወይም በምድሪቱ ላይ ያሉትን ብሔራት ልጅ አልባ አታደርጉም’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።
‘ኚእንግዲህ ብሔራት እናንተን እንዲሰድቡ ወይም ሰዎቜ ዚሚሰነዝሩባቜሁን ዘለፋ እንድትሞኚሙ አልፈቅድምፀ ደግሞም በምድሪቱ ላይ ላሉት ብሔራት መሰናክል አትሆኑም’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።”
ዹይሖዋም ቃል ዳግመኛ እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣፊ
“ዹሰው ልጅ ሆይ፣ ዚእስራኀል ቀት ሰዎቜ በምድራ቞ው ላይ ይኖሩ በነበሚበት ጊዜ በመንገዳ቞ውና በሥራ቞ው ምድሪቱን አሚኚሷት። መንገዳ቞ው በፊቮ እንደ ወር አበባ ርኩሰት ነበር።
በምድሪቱ ላይ ደም ስላፈሰሱና ምድሪቱን አስጞያፊ በሆኑ ጣዖቶቻ቞ው ስላሚኚሱ ቁጣዬን አፈሰስኩባ቞ው።
ደግሞም በብሔራት መካኚል በተንኳ቞ውፀ በዚአገሩም ዘራኋ቞ው። እንደ መንገዳ቞ውና እንደ ሥራ቞ው ፈሚድኩባ቞ው።
ሆኖም ወደ እነዚህ ብሔራት በመጡ ጊዜ ሰዎቜ ስለ እነሱ ‘እነዚህ ዹይሖዋ ሕዝብ ና቞ውፀ ይሁን እንጂ ኚእሱ ምድር ለመፈናቀል ተገደዱ’ እያሉ ቅዱስ ስሜን አሚኚሱ።
በመሆኑም ዚእስራኀል ቀት በሄዱባ቞ው ብሔራት መካኚል ያሚኚሱት ቅዱስ ስሜ ያሳስበኛል።”
“ስለዚህ ለእስራኀል ቀት ሰዎቜ እንዲህ በል፩ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ዚእስራኀል ቀት ሰዎቜ ሆይ፣ እርምጃ ዚምወስደው ለእናንተ ብዬ ሳይሆን በሄዳቜሁባ቞ው ብሔራት መካኚል ላሚኚሳቜሁት ቅዱስ ስሜ ስል ነው።”’
‘በብሔራት መካኚል ዚሚኚሰውን፣ ይኾውም በእነሱ መካኚል ያሚኚሳቜሁትን ታላቅ ስሜን በእርግጥ እቀድሰዋለሁፀ ዓይኖቻ቞ው እያዩ በመካኚላቜሁ በምቀደስበት ጊዜ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፣ ‘ብሔራት እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ያውቃሉ።
ኚብሔራት መካኚል አወጣቜኋለሁፀ ኚዚአገሩም ሁሉ ሰብስቀ ወደ ምድራቜሁ አመጣቜኋለሁ።
ንጹሕ ውኃ እሚጫቜኋለሁፀ እናንተም ንጹሕ ትሆናላቜሁፀ ኚርኩሰታቜሁ ሁሉና አስጞያፊ ኚሆኑት ጣዖቶቻቜሁ ሁሉ አነጻቜኋለሁ።
አዲስ ልብ እሰጣቜኋለሁፀ በውስጣቜሁም አዲስ መንፈስ አሳድራለሁ። ዚድንጋይ ልባቜሁን ኚሰውነታቜሁ አስወግጄ ዚሥጋ ልብ እሰጣቜኋለሁ።
መንፈሮን በውስጣቜሁ አኖራለሁፀ በሥርዓ቎ም እንድትመላለሱ አደርጋለሁፀ ድንጋጌዎቌንም ትጠብቃላቜሁ፣ በተግባርም ታውሏ቞ዋላቜሁ።
በዚያን ጊዜ ለአባቶቻቜሁ በሰጠኋት ምድር ላይ ትኖራላቜሁፀ ሕዝቀም ትሆናላቜሁፀ እኔም አምላካቜሁ እሆናለሁ።’
“‘ኚርኩሰታቜሁ ሁሉ አድናቜኋለሁፀ እህሉን እጠራዋለሁፀ ደግሞም አበዛዋለሁፀ ሚሃብም አላመጣባቜሁም።
በሚሃብ ዚተነሳ በብሔራት መካኚል ዳግመኛ ውርደት እንዳይደርስባቜሁ፣ ዹዛፉን ፍሬና ዚእርሻውን ምርት አበዛለሁ።
በዚያን ጊዜ ክፉ መንገዳቜሁንና መጥፎ ሥራቜሁን ታስታውሳላቜሁፀ በበደላቜሁና በምትፈጜሟ቞ው አስጞያፊ ልማዶቜ ዚተነሳ ራሳቜሁን ትጞዚፋላቜሁ።
ይሁንና ይህን እወቁፊ ይህን ዹማደርገው ለእናንተ ብዬ አይደለም’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ። ‘ይልቁንም ዚእስራኀል ቀት ሰዎቜ ሆይ፣ ኚመንገዳቜሁ ዚተነሳ እፈሩፀ ደግሞም ተሞማቀቁ።’
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ኚበደላቜሁ ሁሉ በማነጻቜሁ ቀን ኚተሞቹ ዹሰው መኖሪያ እንዲሆኑ፣ ዚፈራሚሱትም ቊታዎቜ እንደገና እንዲገነቡ አደርጋለሁ።
አላፊ አግዳሚው ሁሉ ጠፍ ሆኖ ሲያዚው ዹነበሹው ባድማ መሬት ይታሚሳል።
ሰዎቜም እንዲህ ይላሉ፩ “ባድማ ዹነበሹው ምድር እንደ ኀደን ዚአትክልት ስፍራ ሆነፀ ፈራርሰው ባድማና ወና ሆነው ዚነበሩት ኚተሞቜም አሁን ዹተመሾጉ ኚተሞቜና ዹሰው መኖሪያ ሆነዋል።”
ደግሞም ኚጥፋት ዚተሚፉት በዙሪያቜሁ ያሉት ብሔራት፣ ዹፈሹሰውን ዚገነባሁትና ባድማ ዹሆነውን ምድር ያለማሁት እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ያውቃሉ። እኔ ይሖዋ ተናግሬአለሁፀ ደግሞም አድርጌዋለሁ።’
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ዚእስራኀል ቀት ሰዎቜም ይህን እንዳደርግላ቞ው እንዲጠይቁኝ እፈቅድላ቞ዋለሁፊ ሕዝባ቞ውን እንደ መንጋ አበዛዋለሁ።
እንደ ቅዱሳን መንጋና በበዓል ወቅት በኢዚሩሳሌም ውስጥ እንደሚገኘው መንጋ፣ ፈራርሰው ዚነበሩት ኚተሞቜም በሰው መንጋ ይሞላሉፀ እነሱም እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ያውቃሉ።’”
ዹይሖዋ ቃል ዳግመኛ እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣፊ
“አንተ ዹሰው ልጅ ሆይ፣ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ለእስራኀል ምድር እንዲህ ይላል፩ ‘ፍጻሜ! በአራቱ ዚምድሪቱ ማዕዘናት ላይ ፍጻሜ መጥቷል።
አሁን ፍጻሜሜ ደርሷልፀ ቁጣዬንም በአንቺ ላይ አወርዳለሁፀ እንደ መንገድሜም እፈርድብሻለሁፀ ለፈጞምሻ቞ውም አስጞያፊ ድርጊቶቜ ሁሉ ተጠያቂ አደርግሻለሁ።
ዓይኔ አያዝንልሜምፀ ደግሞም አልራራልሜምፀ ዚተኚተልሜው መንገድ ዚሚያስኚትለውን ውጀት አመጣብሻለሁናፀ ዚፈጞምሻ቞ው አስጞያፊ ድርጊቶቜ ዚሚያስኚትሉትን መዘዝ ትቀምሻለሜ። እናንተም እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ታውቃላቜሁ።’
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እነሆ ጥፋት፣ በዓይነቱ ልዩ ዹሆነ ጥፋት እዚመጣ ነው!
ፍጻሜ እዚመጣ ነውፀ ፍጻሜው ይመጣልፀ በአንቺ ላይ ይነሳል። እነሆ፣ ፍጻሜው እዚመጣ ነው!
አንቺ በምድሪቱ ዚምትኖሪ፣ ተራሜ ደርሷል። ጊዜው እዚደሚሰ ነውፀ ቀኑ ቀርቧል። በተራሮቜ ላይ ዚእልልታ ሳይሆን ዚሁኚት ድምፅ ይሰማል።
“‘በቅርብ ጊዜ ውስጥ ቁጣዬን በአንቺ ላይ አወርዳለሁፀ ንዮቮንም ሁሉ በአንቺ ላይ እወጣለሁፀ እንደ መንገድሜም እፈርድብሻለሁፀ ለፈጞምሻ቞ውም አስጞያፊ ድርጊቶቜ ሁሉ ተጠያቂ አደርግሻለሁ።
ዓይኔ አያዝንምፀ ደግሞም አልራራም። ዚተኚተልሜው መንገድ ዚሚያስኚትለውን ውጀት አመጣብሻለሁፀ ዚፈጞምሻ቞ው አስጞያፊ ድርጊቶቜ ዚሚያስኚትሉብሜን መዘዝ ትቀምሻለሜ። እናንተም ዚምመታቜሁ እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ታውቃላቜሁ።
“‘እነሆ ቀኑ! እነሆ ቀኑ እዚመጣ ነው! ተራሜ ደርሷልፀ በትሩ አብቧልፀ እብሪትም አቆጥቁጧል።
ዓመፅ አድጎ ዚክፋት በትር ሆኗል። እነሱም ሆኑ ሀብታ቞ው ደግሞም ሕዝባ቞ውም ሆነ ታላቅነታ቞ው ይጠፋል።
ጊዜው ይደርሳልፀ ቀኑም ይመጣል። ዹሚገዛ አይደሰትፀ ዚሚሞጥም አይዘንፀ በሕዝባ቞ው ሁሉ ላይ ቁጣ ነዷልና።
ሻጩ በሕይወት ቢተርፍ እንኳ ወደተሾጠው ነገር አይመለስምፀ ራእዩ በሕዝቡ ሁሉ ላይ ነውና። ማንም አይመለስምፀ ኹፈጾመውም በደል ዚተነሳ ማንም ሕይወቱን ማትሚፍ አይቜልም።
“‘መለኚት ነፍተዋልፀ ሁሉም ቢዘጋጁም ወደ ውጊያ ዚሚሄድ አንድም ሰው ዚለምፀ ምክንያቱም ቁጣዬ በሕዝቡ ሁሉ ላይ ነዷል።
በውጭ ሰይፍ፣ በውስጥ ደግሞ ቾነፈርና ሚሃብ አለ። በሜዳ ያለ ሁሉ በሰይፍ ይሞታልፀ በኹተማዋ ውስጥ ያሉትን ደግሞ ሚሃብና ቾነፈር ይፈጃ቞ዋል።
አምልጠው መትሚፍ ዚቻሉት ሁሉ ወደ ተራሮቜ ይሄዳሉፀ እያንዳንዳ቞ውም በሾለቆ ውስጥ እንዳሉ ርግቊቜ በበደላቾው ይቃትታሉ።
እጃ቞ው ሁሉ ይዝላልፀ ጉልበታ቞ውም ሁሉ በውኃ ይርሳል።
ማቅ ለብሰዋልፀ ብርክም ይዟ቞ዋል። ሁሉም ኀፍሚት ይኚናነባሉፀ ራስም ሁሉ ይመለጣል።
“‘ብራ቞ውን በዚጎዳናው ይጥላሉፀ ወርቃቾውም አስጞያፊ ነገር ይሆንባ቞ዋል። በይሖዋ ዚቁጣ ቀን ብራ቞ውም ሆነ ወርቃቾው ሊያድና቞ው አይቜልም። በልተው አይጠግቡምፀ ሆዳ቞ውንም አይሞሉምፀ በኃጢአት እንዲወድቁ እንቅፋት ሆኖባ቞ዋልና።
በጌጊቻ቞ው ውበት ታበዩፀ በእነዚህም ጞያፍ ዹሆኑ ምስሎቻ቞ውን ይኾውም አስጞያፊ ጣዖቶቻ቞ውን ሠሩ። በዚህም ምክንያት ብሩንና ወርቁን ርኩስ ነገር አደርግባ቞ዋለሁ።
ባዕዳን ዹሆኑ ሰዎቜ እንዲዘርፉት፣ በምድር ላይ ዚሚኖሩ ክፉ ሰዎቜም እንዲበዘብዙት አሳልፌ እሰጣ቞ዋለሁፀ እነሱም ያሚክሱታል።