text
stringlengths
4
267
ኢየሱስም ከጀልባዋ ሲወርድ እጅግ ብዙ ሕዝብ ተመለከተ፤ እረኛ እንደሌላቸው በጎች ስለነበሩም በጣም አዘነላቸው። ብዙ ነገርም ያስተምራቸው ጀመር።
ሰዓቱ እየገፋ በመሄዱ ደቀ መዛሙርቱ ወደ እሱ ቀርበው እንዲህ አሉት፦ “ይህ ቦታ ራቅ ያለ ነው፤ ሰዓቱ ደግሞ ገፍቷል።
በአካባቢው ወዳሉት ገጠሮችና መንደሮች ሄደው ለራሳቸው ምግብ እንዲገዙ አሰናብታቸው።”
እሱም መልሶ “እናንተ የሚበሉት ነገር ስጧቸው” አላቸው። እነሱም “ሄደን በ200 ዲናር ዳቦ ገዝተን እንዲበሉ እንስጣቸው?” አሉት።
እሱም “ስንት ዳቦ አላችሁ? እስቲ ሄዳችሁ እዩ!” አላቸው። ሄደው ካዩ በኋላ “አምስት ዳቦና ሁለት ዓሣ” አሉት።
ከዚያም ሕዝቡ ሁሉ በቡድን በቡድን ሆኖ በለመለመው መስክ ላይ እንዲቀመጥ አዘዘ።
በመሆኑም ሕዝቡ መቶ መቶና ሃምሳ ሃምሳ እየሆነ በቡድን ተቀመጠ።
እሱም አምስቱን ዳቦና ሁለቱን ዓሣ ይዞ ወደ ሰማይ ቀና በማለት ባረከ። ከዚያም ዳቦውን ቆርሶ ለሕዝቡ እንዲያቀርቡ ለደቀ መዛሙርቱ ሰጣቸው፤ ሁለቱን ዓሣም ለሁሉም አከፋፈለ።
ሁሉም በልተው ጠገቡ፤
ከዚያም ቁርስራሹን ሰበሰቡ፤ ቁርስራሹም ዓሣውን ሳይጨምር 12 ቅርጫት ሙሉ ሆነ።
ዳቦውን የበሉትም 5,000 ወንዶች ነበሩ።
ወዲያውም፣ እሱ ሕዝቡን እያሰናበተ ሳለ ደቀ መዛሙርቱ ጀልባ ተሳፍረው በቤተሳይዳ አቅጣጫ ወዳለው የባሕር ዳርቻ ቀድመውት እንዲሻገሩ አደረገ።
ከተሰናበታቸው በኋላ ግን ለመጸለይ ወደ አንድ ተራራ ወጣ።
በመሸም ጊዜ ጀልባዋ በባሕሩ መካከል ነበረች፤ እሱ ግን ብቻውን የብስ ላይ ነበር።
ነፋሱ ከፊት ለፊታቸው ይነፍስ ስለነበር ለመቅዘፍ ሲታገሉ ባያቸው ጊዜ በአራተኛው ክፍለ ሌሊት ገደማ በባሕሩ ላይ እየተራመደ ወደ እነሱ መጣ፤ ይሁንና አልፏቸው ሊሄድ ነበር።
እነሱም በባሕሩ ላይ ሲራመድ ባዩት ጊዜ “ምትሃት ነው!” ብለው ስላሰቡ በኃይል ጮኹ።
ሁሉም እሱን ባዩት ጊዜ ተረበሹ። ሆኖም ወዲያውኑ አነጋገራቸው፤ ደግሞም “አይዟችሁ! እኔ ነኝ፤ አትፍሩ” አላቸው።
ከዚያም ጀልባዋ ላይ ወጥቶ አብሯቸው ሆነ፤ ነፋሱም ቆመ። በዚህ ጊዜ በከፍተኛ የአድናቆት ስሜት ተዋጡ፤
ይህም የሆነው የዳቦውን ተአምር ትርጉም ባለማስተዋላቸው ነው፤ ልባቸው አሁንም መረዳት ተስኖት ነበር።
ወደ የብስ በተሻገሩ ጊዜ ጌንሴሬጥ ደረሱ፤ በአቅራቢያውም ጀልባዋን አቆሙ።
ሆኖም ከጀልባዋ እንደወረዱ ሰዎች አወቁት።
ወደ አካባቢው ሁሉ በመሮጥ ሕመምተኞችን በቃሬዛ እየተሸከሙ እሱ ይገኝበታል ወደተባለው ቦታ ያመጡ ጀመር።
በገባበት መንደር ወይም ከተማ ወይም ገጠር ሁሉ ሕመምተኞቹን በገበያ ስፍራ ያስቀምጡ ነበር፤ የልብሱንም ዘርፍ እንኳ ለመንካት ይማጸኑት ነበር። የነኩትም ሁሉ ተፈወሱ።
በዚያን ወቅት፣ እንደገና ብዙ ሰዎች ተሰበሰቡ፤ የሚበሉትም አልነበራቸውም። ስለዚህ ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱን ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦
“እነዚህ ሰዎች ሦስት ቀን ሙሉ ከእኔ ጋር ስለቆዩና የሚበሉት ስለሌላቸው አዝንላቸዋለሁ።
እንዲሁ ጦማቸውን ወደ ቤታቸው ብሰዳቸው መንገድ ላይ ዝለው ይወድቃሉ፤ ደግሞም አንዳንዶቹ የመጡት ከሩቅ ነው።”
ደቀ መዛሙርቱ ግን “በዚህ ገለልተኛ ስፍራ እነዚህን ሰዎች የሚያጠግብ በቂ ዳቦ ከየት ማግኘት ይቻላል?” ሲሉ መለሱለት።
በዚህ ጊዜ “ስንት ዳቦ አላችሁ?” ሲል ጠየቃቸው። እነሱም “ሰባት” አሉት።
እሱም ሕዝቡ መሬት ላይ እንዲቀመጥ አዘዘ። ከዚያም ሰባቱን ዳቦ ይዞ አምላክን አመሰገነ፤ ቆርሶም እንዲያድሉ ለደቀ መዛሙርቱ ሰጣቸው፤ እነሱም ለሕዝቡ አደሉ።
ጥቂት ትናንሽ ዓሣዎችም ነበሯቸው፤ እነዚህንም ከባረከ በኋላ እንዲያድሉ ነገራቸው።
ሕዝቡም በልቶ ጠገበ፤ ከዚያም የተረፈውን ቁርስራሽ ሰበሰቡ፤ ቁርስራሹም ሰባት ትላልቅ ቅርጫት ሙሉ ሆነ።
በዚያም 4,000 ገደማ ወንዶች ነበሩ። በመጨረሻም አሰናበታቸው።
ወዲያውኑ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በጀልባ ተሳፍሮ ዳልማኑታ ወደተባለ ክልል መጣ።
እዚያም ፈሪሳውያን መጥተው እሱን ለመፈተን ከሰማይ ምልክት እንዲያሳያቸው በመጠየቅ ይከራከሩት ጀመር።
እሱም እጅግ አዝኖ በረጅሙ ከተነፈሰ በኋላ “ይህ ትውልድ ምልክት የሚፈልገው ለምንድን ነው? እውነት እላችኋለሁ፣ ለዚህ ትውልድ ምንም ምልክት አይሰጠውም” አለ።
ከዚያም ትቷቸው ሄደ፤ እንደገና ጀልባ ተሳፍሮም ወደ ባሕሩ ማዶ ተሻገረ።
ይሁንና ዳቦ መያዝ ረስተው ስለነበር በጀልባው ውስጥ ከአንድ ዳቦ በስተቀር ምንም አልነበራቸውም።
ኢየሱስም “ተጠንቀቁ፣ ከፈሪሳውያን እርሾና ከሄሮድስ እርሾ ተጠበቁ” ሲል በግልጽ አስጠነቀቃቸው።
እነሱም ዳቦ ባለመያዛቸው እርስ በርሳቸው ይከራከሩ ጀመር።
ኢየሱስም ይህን አውቆ እንዲህ አላቸው፦ “ዳቦ ባለመያዛችሁ ለምን ትከራከራላችሁ? አሁንም አልገባችሁም? ደግሞስ አላስተዋላችሁም? ልባችሁ መረዳት እንደተሳነው ነው?
‘ዓይን እያላችሁ አታዩም? ጆሮ እያላችሁ አትሰሙም?’ ደግሞስ አታስታውሱም?
አምስቱን ዳቦ ለ5,000ዎቹ ወንዶች በቆረስኩ ጊዜ ስንት ቅርጫት ሙሉ ትርፍራፊ ሰበሰባችሁ?” እነሱም “አሥራ ሁለት” አሉት።
“ሰባቱን ዳቦ ለ4,000ዎቹ ወንዶች በቆረስኩ ጊዜ ስንት ትላልቅ ቅርጫት ሙሉ ትርፍራፊ አነሳችሁ?” እነሱም “ሰባት” አሉት።
እሱም “ታዲያ አሁንም አልገባችሁም?” አላቸው።
ከዚያም ወደ ቤተሳይዳ መጡ። በዚያም ሰዎች አንድ ዓይነ ስውር ወደ ኢየሱስ አምጥተው እንዲዳስሰው ተማጸኑት።
እሱም ዓይነ ስውሩን፣ እጁን ይዞ ከመንደሩ ውጭ ወሰደው። በዓይኖቹ ላይ እንትፍ ካለ በኋላ እጆቹን ጫነበትና “የሚታይህ ነገር አለ?” ሲል ጠየቀው።
ሰውየውም ቀና ብሎ በማየት “ሰዎች ይታዩኛል፤ ሆኖም የሚራመዱ ዛፎች ይመስላሉ” አለ።
ኢየሱስ እንደገና እጆቹን ሰውየው ዓይኖች ላይ ጫነ፤ በዚህ ጊዜ ሰውየው አጥርቶ አየ። ዓይኖቹም በሩ፤ ሁሉንም ነገር በደንብ ለይቶ ማየት ቻለ።
በመጨረሻም “ወደ መንደሩ አትግባ” ብሎ ወደ ቤቱ ሰደደው።
ኢየሱስና ደቀ መዛሙርቱ ወደ ቂሳርያ ፊልጵስዩስ መንደሮች አመሩ፤ በመንገድም ላይ ሳሉ ደቀ መዛሙርቱን “ሰዎች እኔን ማን ይሉኛል?” ሲል ጠየቃቸው።
እነሱም “አንዳንዶች መጥምቁ ዮሐንስ፣ ሌሎች ኤልያስ፣ ሌሎች ደግሞ ከነቢያት አንዱ ነው ይሉሃል” አሉት።
ከዚያም እነሱን “እናንተስ ስለ እኔ ማንነት ምን ትላላችሁ?” ሲል ጠየቃቸው። ጴጥሮስም “አንተ ክርስቶስ ነህ” ብሎ መለሰለት።
በዚህ ጊዜ ስለ እሱ ለማንም እንዳይናገሩ አጥብቆ አዘዛቸው።
በተጨማሪም የሰው ልጅ ብዙ መከራ መቀበሉ እንዲሁም በሽማግሌዎች፣ በካህናት አለቆችና በጸሐፍት ተቀባይነት ማጣቱ ብሎም መገደሉና ከሦስት ቀን በኋላ መነሳቱ እንደማይቀር ያስተምራቸው ጀመር።
ደግሞም ይህን በግልጽ ነገራቸው። ጴጥሮስ ግን ኢየሱስን ለብቻው በመውሰድ ይገሥጸው ጀመር።
በዚህ ጊዜ ዞር ብሎ ደቀ መዛሙርቱን ተመለከተና ጴጥሮስን “ወደ ኋላዬ ሂድ፣ ሰይጣን! የሰውን እንጂ የአምላክን ሐሳብ አታስብም” ሲል ገሠጸው።
ከዚህ በኋላ ሕዝቡን ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወደ እሱ ጠርቶ እንዲህ አላቸው፦ “ሊከተለኝ የሚፈልግ ማንም ቢኖር ራሱን ይካድ፤ የራሱን የመከራ እንጨት ይሸከም፤ ያለማቋረጥም ይከተለኝ።
ሕይወቱን ማዳን የሚፈልግ ሁሉ ያጣታልና፤ ለእኔና ለምሥራቹ ሲል ሕይወቱን የሚያጣ ሁሉ ግን ያድናታል።
ደግሞስ አንድ ሰው ዓለምን ሁሉ የራሱ ቢያደርግና ሕይወቱን ቢያጣ ምን ይጠቅመዋል?
ሰው ለሕይወቱ ምትክ የሚሆን ምን ነገር ሊሰጥ ይችላል?
በዚህ አመንዝራና ኃጢአተኛ ትውልድ መካከል በእኔና በቃሌ የሚያፍር ሁሉ የሰው ልጅም ከቅዱሳን መላእክቱ ጋር በአባቱ ክብር ሲመጣ ያፍርበታል።”
ከዚያም ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አላቸው፦ “ሰዎችን የሚያሰናክሉ ነገሮች መከሰታቸው የማይቀር ነው። ሆኖም ለመሰናክሉ ምክንያት ለሚሆነው ለዚያ ሰው ወዮለት!
ከእነዚህ ከታናናሾቹ አንዱን ከሚያሰናክል የወፍጮ ድንጋይ በአንገቱ ታስሮ ወደ ባሕር ቢጣል ይሻለዋል።
ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። ወንድምህ ቢበድልህ ገሥጸው፤ ከተጸጸተም ይቅር በለው።
በቀን ሰባት ጊዜ ቢበድልህ እንኳ ‘ተጸጽቻለሁ’ እያለ ሰባት ጊዜ ወደ አንተ ከመጣ ይቅር ልትለው ይገባል።”
በዚህ ጊዜ ሐዋርያቱ ጌታን “እምነት ጨምርልን” አሉት።
ጌታም እንዲህ አለ፦ “የሰናፍጭ ዘር የሚያህል እምነት ካላችሁ ይህን የሾላ ዛፍ ‘ከዚህ ተነቅለህ ባሕሩ ውስጥ ተተከል!’ ብትሉት ይታዘዛችኋል።
“ከእናንተ መካከል አራሽ ወይም እረኛ የሆነ ባሪያ ያለው ሰው ቢኖር፣ ባሪያው ከእርሻ ሲመለስ ‘ቶሎ ናና ወደ ማዕድ ቅረብ’ ይለዋል?
ከዚህ ይልቅ ‘ራቴን አዘጋጅልኝ፤ በልቼና ጠጥቼ እስክጨርስም ድረስ አሸርጠህ አገልግለኝ፤ ከዚያ በኋላ መብላትና መጠጣት ትችላለህ’ አይለውም?
ባሪያው የተሰጠውን ሥራ በማከናወኑ ጌታው የሚያመሰግነው ይመስላችኋል?
በተመሳሳይ እናንተም የተሰጣችሁን ሥራ ሁሉ ባከናወናችሁ ጊዜ ‘ምንም የማንጠቅም ባሪያዎች ነን። ያደረግነው ልናደርገው የሚገባንን ነገር ነው’ በሉ።”
ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም እየሄደ ሳለ በሰማርያና በገሊላ መካከል አለፈ።
ወደ አንድ መንደር እየገባም ሳለ የሥጋ ደዌ የያዛቸው አሥር ሰዎች አዩት፤ እነሱም በርቀት ቆሙ።
ድምፃቸውንም ከፍ በማድረግ “ኢየሱስ፣ መምህር፣ ምሕረት አድርግልን!” አሉ።
እሱም ባያቸው ጊዜ “ሄዳችሁ ራሳችሁን ለካህናት አሳዩ” አላቸው። ከዚያም እየሄዱ ሳሉ ነጹ።
ከእነሱ አንዱ እንደተፈወሰ ባየ ጊዜ አምላክን በታላቅ ድምፅ እያመሰገነ ተመለሰ።
ኢየሱስ እግር ላይ ተደፍቶም አመሰገነው። ሰውየውም ሳምራዊ ነበር።
ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለ፦ “የነጹት አሥሩም አይደሉም እንዴ? ታዲያ ዘጠኙ የት አሉ?
ከዚህ ከባዕድ አገር ሰው በስተቀር አምላክን ለማመስገን የተመለሰ ሌላ አንድም ሰው የለም?”
ከዚያም ሰውየውን “ተነስና ሂድ፤ እምነትህ አድኖሃል” አለው።
ፈሪሳውያን የአምላክ መንግሥት መቼ እንደሚመጣ ሲጠይቁት እንዲህ ሲል መለሰላቸው፦ “የአምላክ መንግሥት በግልጽ በሚታይ ሁኔታ አይመጣም፤
ሰዎችም ‘እነሆ እዚህ ነው!’ ወይም ‘እዚያ ነው!’ አይሉም። እነሆ፣ የአምላክ መንግሥት በመካከላችሁ ነውና።”
ከዚያም ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አላቸው፦ “ከሰው ልጅ ቀኖች አንዱን ለማየት የምትመኙበት ጊዜ ይመጣል፤ ግን አታዩትም።
ሰዎችም ‘እዚያ ነው!’ ወይም ‘እዚህ ነው!’ ይሏችኋል። ነገር ግን አትሂዱ ወይም አትከተሏቸው።
ምክንያቱም መብረቅ ከአንዱ የሰማይ ክፍል እስከ ሌላኛው የሰማይ ክፍል እንደሚያበራ ሁሉ የሰው ልጅ በሚገለጥበትም ቀን እንዲሁ ይሆናል።
በመጀመሪያ ግን ብዙ መከራ መቀበሉና በዚህ ትውልድ ተቀባይነት ማጣቱ የግድ ነው።
በተጨማሪም በኖኅ ዘመን እንደተከሰተው ሁሉ በሰው ልጅ ዘመንም እንዲሁ ይሆናል፦
ኖኅ ወደ መርከቡ እስከገባበትና የጥፋት ውኃ መጥቶ ሁሉንም እስካጠፋበት ቀን ድረስ ሰዎች ይበሉና ይጠጡ እንዲሁም ወንዶች ያገቡ፣ ሴቶችም ይዳሩ ነበር።
በተመሳሳይም በሎጥ ዘመን እንደተከሰተው ሁሉ እንዲሁ ይሆናል፦ ሰዎች ይበሉ፣ ይጠጡ፣ ይገዙ፣ ይሸጡ፣ ይተክሉና ቤቶችን ይገነቡ ነበር።
ሆኖም ሎጥ ከሰዶም በወጣበት ቀን ከሰማይ እሳትና ድኝ ዘንቦ ሁሉንም አጠፋቸው።
የሰው ልጅ በሚገለጥበትም ቀን እንዲሁ ይሆናል።
“በዚያን ቀን በጣሪያ ላይ ያለ ሰው በቤቱ ውስጥ ያለውን ዕቃ ለመውሰድ አይውረድ፤ እርሻም ላይ ያለ ሰው በኋላው ያለውን ነገር ለመውሰድ አይመለስ።
የሎጥን ሚስት አስታውሱ።
ሕይወቱን ጠብቆ ለማቆየት የሚፈልግ ሁሉ ያጣታል፤ ሕይወቱን የሚያጣት ሁሉ ግን በሕይወት ጠብቆ ያቆያታል።
እላችኋለሁ፣ በዚያች ሌሊት ሁለት ሰዎች በአንድ አልጋ ላይ ይሆናሉ፤ አንዱ ይወሰዳል፤ ሌላኛው ግን ይተዋል።
ሁለት ሴቶች በአንድ ወፍጮ ይፈጫሉ፤ አንዷ ትወሰዳለች፤ ሌላኛዋ ግን ትተዋለች።”
እነሱም መልሰው “ጌታ ሆይ፣ የት?” አሉት። እሱም “በድን ባለበት ንስሮች ይሰበሰባሉ” አላቸው።
ከዚያም ኢየሱስ ወደ ኢያሪኮ ገብቶ በዚያ እያለፈ ነበር።
በዚያም ዘኬዎስ የተባለ አንድ ሀብታም ሰው የነበረ ሲሆን ይህ ሰው የቀረጥ ሰብሳቢዎች አለቃ ነበር።
እሱም ኢየሱስ የሚባለው ማን እንደሆነ ለማየት ይፈልግ ነበር፤ ሆኖም አጭር በመሆኑ ከሕዝቡ ብዛት የተነሳ ማየት አልቻለም።