text stringlengths 4 267 |
|---|
ተመልሶ ሲመጣ ተኝተው አገኛቸውና ጴጥሮስን እንዲህ አለው፦ “ስምዖን፣ ተኝተሃል? አንድ ሰዓት እንኳ ነቅተህ መጠበቅ አልቻልክም? |
ወደ ፈተና እንዳትገቡ ነቅታችሁ ጠብቁ፤ ሳታሰልሱም ጸልዩ። እርግጥ፣ መንፈስ ዝግጁ ነው፤ ሥጋ ግን ደካማ ነው።” |
እንደገናም ሄዶ ስለዚያው ነገር ጸለየ። |
ዳግመኛም ተመልሶ ሲመጣ እንቅልፍ ተጫጭኗቸው ስለነበር ተኝተው አገኛቸው፤ በመሆኑም የሚሉት ነገር ጠፋቸው። |
ለሦስተኛ ጊዜም ተመልሶ እንዲህ አላቸው፦ “ይህ የእንቅልፍና የእረፍት ሰዓት ነው? በቃ! ሰዓቱ ደርሷል! እነሆ፣ የሰው ልጅ ለኃጢአተኞች አልፎ ሊሰጥ ነው። |
ተነሱ፣ እንሂድ። እነሆ፣ አሳልፎ የሚሰጠኝ ቀርቧል።” |
ወዲያውም ገና እየተናገረ ሳለ ከአሥራ ሁለቱ አንዱ የሆነው ይሁዳ መጣ፤ ከካህናት አለቆች፣ ከጸሐፍትና ከሽማግሌዎች የተላኩ ሰይፍና ቆመጥ የያዙ ብዙ ሰዎችም አብረውት ነበሩ። |
አሳልፎ የሚሰጠውም “እኔ የምስመው ሰው እሱ ነው፤ ያዙትና እንዳያመልጥ ተጠንቅቃችሁ ውሰዱት” በማለት አስቀድሞ ምልክት ሰጥቷቸው ነበር። |
ይሁዳም በቀጥታ መጥቶ ወደ እሱ በመቅረብ “ረቢ!” ብሎ ሳመው። |
ሰዎቹም ያዙት፤ ደግሞም አሰሩት። |
ይሁን እንጂ አጠገቡ ቆመው ከነበሩት አንዱ ሰይፉን በመምዘዝ የሊቀ ካህናቱን ባሪያ መትቶ ጆሮውን ቆረጠው። |
ኢየሱስ ግን መልሶ እንዲህ አላቸው፦ “ወንበዴ የምትይዙ ይመስል ሰይፍና ቆመጥ ይዛችሁ የመጣችሁት እኔን ለመያዝ ነው? |
በየዕለቱ በቤተ መቅደስ እያስተማርኩ ከእናንተ ጋር ነበርኩ፤ ሆኖም ያን ጊዜ አልያዛችሁኝም። ይሁንና ይህ የሆነው ቅዱሳን መጻሕፍት እንዲፈጸሙ ነው።” |
በዚህ ጊዜ ሁሉም ጥለውት ሸሹ። |
ሆኖም እርቃኑን ለመሸፈን በፍታ ብቻ የለበሰ አንድ ወጣት በቅርብ ርቀት ይከተለው ጀመር፤ ሊይዙትም ሞከሩ፤ |
እሱ ግን በፍታውን ትቶ ራቁቱን አመለጠ። |
ኢየሱስንም ወደ ሊቀ ካህናቱ ወሰዱት፤ የካህናት አለቆች፣ ሽማግሌዎችና ጸሐፍትም በሙሉ ተሰበሰቡ። |
ይሁንና ጴጥሮስ እስከ ሊቀ ካህናቱ ግቢ ድረስ በርቀት ተከተለው፤ ከዚያም ከቤቱ አገልጋዮች ጋር ተቀምጦ እሳት ይሞቅ ጀመር። |
በዚህ ጊዜ የካህናት አለቆችና መላው የሳንሄድሪን ሸንጎ ኢየሱስን ለመግደል በእሱ ላይ የምሥክሮች ቃል እየፈለጉ ነበር፤ ነገር ግን ምንም አላገኙም። |
እርግጥ ብዙዎች በእሱ ላይ የሐሰት ምሥክርነት ይሰጡ ነበር፤ ሆኖም ቃላቸው ሊስማማ አልቻለም። |
አንዳንዶችም ተነስተው እንዲህ ሲሉ በሐሰት ይመሠክሩበት ነበር፦ |
“‘ይህን በእጅ የተሠራ ቤተ መቅደስ አፍርሼ በሦስት ቀን ውስጥ በእጅ ያልተሠራ ሌላ እገነባለሁ’ ሲል ሰምተነዋል።” |
በዚህ ጉዳይም ቢሆን የምሥክርነት ቃላቸው ሊስማማ አልቻለም። |
ከዚያም ሊቀ ካህናቱ በመካከላቸው ቆሞ ኢየሱስን “ምንም መልስ አትሰጥም? እነዚህ ሰዎች በአንተ ላይ ስለሰጡት ምሥክርነት ምን ትላለህ?” ሲል ጠየቀው። |
እሱ ግን ዝም አለ፤ ምንም መልስ አልሰጠም። ሊቀ ካህናቱም እንደገና “አንተ ብሩክ የሆነው አምላክ ልጅ ክርስቶስ ነህ?” እያለ ይጠይቀው ጀመር። |
ኢየሱስም “አዎ ነኝ፤ እናንተም የሰው ልጅ በኃያሉ ቀኝ ተቀምጦ በሰማይ ደመና ሲመጣ ታያላችሁ” አለ። |
በዚህ ጊዜ ሊቀ ካህናቱ ልብሱን ቀዶ እንዲህ አለ፦ “ከዚህ በላይ ምን ምሥክሮች ያስፈልጉናል? |
አምላክን ሲሳደብ ሰምታችኋል። ታዲያ ውሳኔያችሁ ምንድን ነው?” ሁሉም ሞት ይገባዋል ብለው ፈረዱበት። |
አንዳንዶች ይተፉበት ጀመር፤ ፊቱንም ሸፍነው በቡጢ እየመቱት “ነቢይ ከሆንክ እስቲ ማን እንደመታህ ንገረን!” ይሉት ነበር። የሸንጎው አገልጋዮችም በጥፊ እየመቱ ወሰዱት። |
ጴጥሮስ ግቢው ውስጥ በታች በኩል ሳለ ከሊቀ ካህናቱ ሴት አገልጋዮች አንዷ መጣች። |
እሳት ሲሞቅ አይታ ትኩር ብላ ተመለከተችውና “አንተም ከዚህ ከናዝሬቱ ኢየሱስ ጋር ነበርክ” አለችው። |
እሱ ግን “ሰውየውን አላውቀውም፤ ምን እንደምታወሪም አላውቅም” ሲል ካደ፤ ከዚያም ወደ መግቢያው ሄደ። |
አገልጋይዋም እዚያ አየችውና በአጠገቡ ለቆሙት “ይህ ከእነሱ አንዱ ነው” ብላ እንደገና ትናገር ጀመር። |
አሁንም ካደ። ከጥቂት ጊዜ በኋላ ደግሞ በዚያ ቆመው የነበሩት ጴጥሮስን እንደገና “የገሊላ ሰው ስለሆንክ፣ በእርግጥ አንተም ከእነሱ አንዱ ነህ” ይሉት ጀመር። |
እሱ ግን “ይህን የምትሉትን ሰው አላውቀውም!” ሲል ይምልና ራሱን ይረግም ጀመር። |
ወዲያውኑ ዶሮ ለሁለተኛ ጊዜ ጮኸ፤ ጴጥሮስም “ዶሮ ሁለት ጊዜ ሳይጮኽ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ” ሲል ኢየሱስ የተናገረው ቃል ትዝ አለው። ከዚያም እጅግ አዝኖ ያለቅስ ጀመር። |
ወዲያውኑ በማለዳ የካህናት አለቆች፣ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ማለትም መላው የሳንሄድሪን ሸንጎ አባላት ተሰብስበው ተማከሩ፤ ኢየሱስንም አስረው በመውሰድ ለጲላጦስ አስረከቡት። |
ጲላጦስም “አንተ የአይሁዳውያን ንጉሥ ነህ?” ሲል ጠየቀው። እሱም መልሶ “አንተው ራስህ ተናገርከው” አለው። |
የካህናት አለቆቹ ግን በእሱ ላይ በርካታ ክስ መደርደራቸውን ቀጠሉ። |
በዚህ ጊዜ ጲላጦስ “ምንም መልስ አትሰጥም? በስንት ነገር እየከሰሱህ እንዳሉ ተመልከት” ሲል እንደገና ጠየቀው። |
ሆኖም ኢየሱስ ምንም ተጨማሪ መልስ አልሰጠም፤ በመሆኑም ጲላጦስ ተገረመ። |
ጲላጦስ ሁልጊዜ በዚህ በዓል ወቅት፣ ሕዝቡ ይፈታልን ብለው የጠየቁትን አንድ እስረኛ የመፍታት ልማድ ነበረው። |
በወቅቱ፣ በመንግሥት ላይ ዓመፅ በማነሳሳት ሰው ገድለው ከታሰሩ ዓመፀኞች መካከል በርባን የሚባል ሰው ይገኝ ነበር። |
ሕዝቡም መጥተው ጲላጦስ እንደ ልማዱ ያደርግላቸው ዘንድ ይጠይቁት ጀመር። |
እሱም መልሶ “የአይሁዳውያንን ንጉሥ እንድፈታላችሁ ትፈልጋላችሁ?” አላቸው። |
ጲላጦስ ይህን ያለው የካህናት አለቆች አሳልፈው የሰጡት በቅናት ተነሳስተው እንደሆነ ያውቅ ስለነበር ነው። |
ይሁንና የካህናት አለቆቹ በኢየሱስ ምትክ በርባንን ይፈታላቸው ዘንድ እንዲጠይቁ ሕዝቡን አነሳሱ። |
ጲላጦስም እንደገና መልሶ “እንግዲያው የአይሁዳውያን ንጉሥ የምትሉትን ምን ባደርገው ይሻላል?” አላቸው። |
እነሱም “ይሰቀል!” ብለው እንደገና ጮኹ። |
ሆኖም ጲላጦስ “ለምን? ምን ያጠፋው ነገር አለ?” አላቸው። እነሱ ግን “ይሰቀል!” እያሉ የባሰ ጮኹ። |
በዚህ ጊዜ ጲላጦስ ሕዝቡን ለማስደሰት ስለፈለገ በርባንን ፈታላቸው፤ ኢየሱስንም ካስገረፈው በኋላ በእንጨት ላይ እንዲሰቀል አሳልፎ ሰጠው። |
ወታደሮቹ ወደ ግቢው ይኸውም ወደ አገረ ገዢው መኖሪያ ቤት ወሰዱት፤ ሠራዊቱንም ሁሉ አንድ ላይ ሰበሰቡ። |
ሐምራዊ ልብስም አለበሱት፤ የእሾህ አክሊል ጎንጉነውም በራሱ ላይ ደፉበት፤ |
ደግሞም ድምፃቸውን ከፍ አድርገው “የአይሁዳውያን ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን!” ይሉት ጀመር። |
ከዚህም ሌላ ራሱን በመቃ ይመቱትና ይተፉበት ነበር፤ ተንበርክከውም እጅ ነሱት። |
ሲያፌዙበት ከቆዩ በኋላም ሐምራዊውን ልብስ ገፈው የራሱን መደረቢያዎች አለበሱት። ከዚያም በእንጨት ላይ ሊቸነክሩት ይዘውት ሄዱ። |
ስምዖን የተባለ አንድ የቀሬና ሰው ከገጠር መጥቶ በዚያ ሲያልፍ አግኝተው ኢየሱስ የሚሰቀልበትን የመከራ እንጨት እንዲሸከም አስገደዱት፤ ይህ ሰው የእስክንድርና የሩፎስ አባት ነበር። |
በኋላም ኢየሱስን ጎልጎታ ወደተባለ ቦታ አመጡት፤ ትርጉሙም “የራስ ቅል ቦታ” ማለት ነው። |
እዚያም ከርቤ የተቀላቀለበት የወይን ጠጅ ሰጡት፤ እሱ ግን አልተቀበለም። |
ከዚያም እንጨት ላይ ቸነከሩት፤ ማን ምን እንደሚወስድ ለመወሰንም ዕጣ ተጣጥለው መደረቢያዎቹን ተከፋፈሉ። |
እንጨት ላይ ሲቸነክሩትም ጊዜው ሦስት ሰዓት ነበር። |
የተከሰሰበትን ጉዳይ የሚገልጽ “የአይሁዳውያን ንጉሥ” የሚል ጽሑፍ ተጽፎ ነበር። |
ከእሱም ጋር ሁለት ዘራፊዎችን፣ አንዱን በቀኙ ሌላውን ደግሞ በግራው በእንጨት ላይ ሰቀሉ። |
በዚያ የሚያልፉም ይሰድቡትና ራሳቸውን እየነቀነቁ እንዲህ ይሉት ነበር፦ “ቤተ መቅደሱን አፍርሼ በሦስት ቀን እሠራዋለሁ ባይ! |
እስቲ ከተሰቀልክበት እንጨት ላይ ወርደህ ራስህን አድን።” |
የካህናት አለቆችም እንደዚሁ ከጸሐፍት ጋር ሆነው እርስ በርሳቸው እንዲህ እያሉ ያፌዙበት ነበር፦ “ሌሎችን አዳነ፤ ራሱን ግን ማዳን አልቻለም! |
አይተን እናምን ዘንድ የእስራኤል ንጉሥ ክርስቶስ እስቲ አሁን ከተሰቀለበት እንጨት ይውረድ።” ከእሱ ጋር በእንጨት ላይ የተሰቀሉትም እንኳ ሳይቀሩ ይነቅፉት ነበር። |
ስድስት ሰዓት በሆነ ጊዜም አገሩ በሙሉ እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ በጨለማ ተሸፈነ። |
በዘጠነኛውም ሰዓት ኢየሱስ በታላቅ ድምፅ “ኤሊ፣ ኤሊ፣ ላማ ሳባቅታኒ?” ብሎ ጮኸ፤ ትርጉሙም “አምላኬ፣ አምላኬ ለምን ተውከኝ?” ማለት ነው። |
በአቅራቢያው ቆመው ከነበሩት አንዳንዶቹ ይህን ሲሰሙ “አያችሁ! ኤልያስን እየተጣራ ነው” ይሉ ጀመር። |
ከዚያም አንድ ሰው ሮጦ በመሄድ የኮመጠጠ የወይን ጠጅ ውስጥ ሰፍነግ ከነከረ በኋላ በመቃ ላይ አድርጎ እንዲጠጣ ሰጠውና “ተዉት! እስቲ ኤልያስ መጥቶ ያወርደው እንደሆነ እንይ” አለ። |
ሆኖም ኢየሱስ በታላቅ ድምፅ ጮኾ ሞተ። |
የቤተ መቅደሱ መጋረጃም ከላይ እስከ ታች ለሁለት ተቀደደ። |
ከፊት ለፊቱ ቆሞ የነበረው መኮንንም በዚህ ሁኔታ መሞቱን ሲያይ “ይህ ሰው በእርግጥ የአምላክ ልጅ ነበር” አለ። |
በተጨማሪም ከሩቅ ሆነው የሚያዩ ሴቶች የነበሩ ሲሆን ከእነሱም መካከል መግደላዊቷ ማርያም እንዲሁም የትንሹ ያዕቆብና የዮሳ እናት ማርያምና ሰሎሜ ነበሩ፤ |
እነዚህም በገሊላ ሳለ ይከተሉትና ያገለግሉት የነበሩ ናቸው፤ ከእሱ ጋር ወደ ኢየሩሳሌም የመጡ ሌሎች በርካታ ሴቶችም ነበሩ። |
ቀኑ በመገባደዱና የዝግጅት ቀን ማለትም የሰንበት ዋዜማ በመሆኑ |
የተከበረ የሸንጎ አባል የሆነውና የአምላክን መንግሥት ይጠባበቅ የነበረው የአርማትያሱ ዮሴፍ መጣ። ደፍሮም ወደ ጲላጦስ ገባና የኢየሱስ አስከሬን እንዲሰጠው ጠየቀ። |
ጲላጦስ ግን ኢየሱስ ሞቶ እንደሆነ ለማወቅ የመቶ አለቃውን ጠርቶ በእርግጥ ሞቶ እንደሆነ ጠየቀው። |
መሞቱን ከመቶ አለቃው ካረጋገጠ በኋላም አስከሬኑን እንዲወስድ ለዮሴፍ ፈቀደለት። |
እሱም በፍታ ገዝቶ አስከሬኑን ካወረደ በኋላ በበፍታው ገነዘው፤ ከዚያም ከዓለት ተፈልፍሎ በተሠራ መቃብር ውስጥ አኖረው፤ ድንጋይ አንከባሎም የመቃብሩን ደጃፍ ዘጋው። |
በዚህ ጊዜ መግደላዊቷ ማርያምና የዮሳ እናት ማርያም አስከሬኑ የተቀመጠበትን ቦታ ይመለከቱ ነበር። |
ዳግመኛም በባሕሩ አጠገብ ሆኖ ያስተምር ጀመር፤ እጅግ ብዙ ሕዝብም ወደ እሱ መጥቶ ተሰበሰበ። በመሆኑም ጀልባ ላይ ወጥቶ ከተቀመጠ በኋላ ከባሕሩ ዳርቻ ፈቀቅ አለ፤ ሕዝቡ ሁሉ ግን በባሕሩ ዳርቻ ነበር። |
ከዚያም ብዙ ነገር በምሳሌ ያስተምራቸው ጀመር፤ እንዲህም አላቸው፦ |
“ስሙ። እነሆ፣ ዘሪው ሊዘራ ወጣ። |
በሚዘራበት ጊዜ አንዳንዶቹ ዘሮች መንገድ ዳር ወደቁ፤ ወፎችም መጥተው ለቀሟቸው። |
ሌሎቹ ደግሞ ብዙ አፈር በሌለው ድንጋያማ መሬት ላይ ወደቁ፤ አፈሩም ጥልቀት ስላልነበረው ወዲያውኑ በቀሉ። |
ፀሐይ በወጣ ጊዜ ግን ተቃጠሉ፤ ሥር ስላልነበራቸውም ደረቁ። |
ሌሎቹ ዘሮች ደግሞ በእሾህ መካከል ወደቁ፤ እሾሁም አድጎ አነቃቸው፤ ፍሬም አልሰጡም። |
ሌሎቹ ግን ጥሩ አፈር ላይ ወድቀው ከበቀሉና ካደጉ በኋላ ፍሬ ማፍራት ጀመሩ፤ ደግሞም 30፣ 60 እና 100 እጥፍ አፈሩ።” |
ከዚያም “የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ” አለ። |
ብቻውን በሆነ ጊዜ አሥራ ሁለቱና በዙሪያው የነበሩት ሌሎች ሰዎች ስለ ምሳሌዎቹ ይጠይቁት ጀመር። |
እሱም እንዲህ አላቸው፦ “ለእናንተ የአምላክን መንግሥት ቅዱስ ሚስጥር የመረዳት ችሎታ ተሰጥቷችኋል፤ በውጭ ላሉት ግን የሚሰሙት ነገር ሁሉ እንዲሁ ምሳሌ ብቻ ሆኖ ይቀርባቸዋል፤ |
በመሆኑም ማየቱን ያያሉ ግን ልብ አይሉም፤ መስማቱን ይሰማሉ ግን ትርጉሙን አይረዱም፤ ደግሞም ሙሉ በሙሉ ስለማይመለሱ ይቅርታ አያገኙም።” |
በተጨማሪም እንዲህ አላቸው፦ “ይህን ምሳሌ ካልተረዳችሁ ታዲያ ሌሎቹን ምሳሌዎች ሁሉ እንዴት ትረዳላችሁ? |
“ዘሪው ቃሉን ይዘራል። |
ቃሉ ሲዘራ መንገድ ዳር እንደወደቁት ዘሮች የሆኑት እነዚህ ናቸው፤ ቃሉን እንደሰሙ ግን ሰይጣን መጥቶ በውስጣቸው የተዘራውን ቃል ይወስደዋል። |
በተመሳሳይም በድንጋያማ መሬት እንደተዘሩት ዘሮች የሆኑት እነዚህ ናቸው፤ ቃሉን እንደሰሙ በደስታ ይቀበሉታል። |
ሆኖም ቃሉ በውስጣቸው ሥር ስለማይሰድ የሚቆዩት ለጥቂት ጊዜ ነው፤ ከዚያም በቃሉ የተነሳ መከራ ወይም ስደት ሲደርስባቸው ወዲያውኑ ይሰናከላሉ። |
በእሾህ መካከል እንደተዘሩት ዘሮች የሆኑ ሌሎች ደግሞ አሉ። እነዚህ ቃሉን የሰሙ ናቸው፤ |
Subsets and Splits
No community queries yet
The top public SQL queries from the community will appear here once available.