text
stringlengths
4
267
ያመኑትም ሁሉ አብረው ነበሩ፤ ያላቸውም ነገር ሁሉ የጋራ ነበር፤
በተጨማሪም ያላቸውን ሀብትና ንብረት በመሸጥ ገንዘቡን ለሁሉም አከፋፈሉ። ለእያንዳንዱም ሰው የሚያስፈልገውን ያህል ሰጡ።
በየዕለቱም በአንድ ልብ ሆነው በቤተ መቅደሱ አዘውትረው ይገኙ ነበር፤ ምግባቸውንም በተለያዩ ቤቶች ይበሉ የነበረ ሲሆን የሚመገቡትም በታላቅ ደስታና በንጹሕ ልብ ነበር፤
አምላክንም ያወድሱ የነበረ ከመሆኑም በላይ በሰው ሁሉ ፊት ሞገስ አግኝተው ነበር። ይሖዋም የሚድኑ ሰዎችን በየዕለቱ በእነሱ ላይ ይጨምር ነበር።
በቂሳርያ “የጣሊያን ክፍለ ጦር” ተብሎ በሚጠራ ሠራዊት ውስጥ ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ የጦር መኮንን ነበር።
እሱም ከመላው ቤተሰቡ ጋር ለአምላክ ያደረና ፈሪሃ አምላክ የነበረው ሰው ሲሆን ለሰዎች ምጽዋት የሚሰጥና ዘወትር ወደ አምላክ የሚማልድ ሰው ነበር።
ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ገደማ አንድ የአምላክ መልአክ ወደ እሱ ሲመጣ በራእይ በግልጽ አየ፤ መልአኩም “ቆርኔሌዎስ!” አለው።
ቆርኔሌዎስም በድንጋጤ ትኩር ብሎ እያየው “ጌታ ሆይ፣ ምንድን ነው?” በማለት ጠየቀው። እሱም እንዲህ አለው፦ “ጸሎትህና ምጽዋትህ በአምላክ ፊት መታሰቢያ እንዲሆን አርጓል።
ስለዚህ አሁን ወደ ኢዮጴ ሰዎች ልከህ ጴጥሮስ ተብሎ የሚጠራውን ስምዖንን አስጠራው።
ይህ ሰው፣ ቤቱ በባሕሩ አጠገብ በሚገኘው በቆዳ ፋቂው በስምዖን ቤት በእንግድነት አርፏል።”
ያነጋገረው መልአክ ተለይቶት እንደሄደ ከአገልጋዮቹ ሁለቱን እንዲሁም እሱን በቅርብ ከሚያገለግሉት ወታደሮች መካከል ለአምላክ ያደረ አንድ ወታደር ጠራ፤
የሆነውንም ነገር ሁሉ ከነገራቸው በኋላ ወደ ኢዮጴ ላካቸው።
በማግስቱም የተላኩት ሰዎች ተጉዘው ወደ ከተማዋ ሲቃረቡ ጴጥሮስ ከቀኑ ስድስት ሰዓት ገደማ ሊጸልይ ወደ ሰገነት ወጣ።
ይሁን እንጂ በጣም ከመራቡ የተነሳ መብላት ፈለገ። ምግብ እየተዘጋጀ ሳለም ሰመመን ውስጥ ገባ፤
ሰማይም ተከፍቶ ትልቅ ጨርቅ የሚመስል ነገር በአራቱም ጫፍ ተይዞ ወደ ምድር ሲወርድ አየ፤
በላዩም የተለያዩ በምድር ላይ የሚኖሩ አራት እግር ያላቸው እንስሳትና በምድር ላይ የሚሳቡ ፍጥረታት እንዲሁም የሰማይ ወፎች ነበሩ።
ከዚያም አንድ ድምፅ “ጴጥሮስ፣ ተነሳና አርደህ ብላ!” አለው።
ጴጥሮስ ግን “ጌታ ሆይ፣ በጭራሽ፤ ምክንያቱም እኔ ንጹሕ ያልሆነና የረከሰ ነገር በልቼ አላውቅም” አለ።
ያም ድምፅ እንደገና ለሁለተኛ ጊዜ “አምላክ ንጹሕ ያደረገውን ነገር ርኩስ ነው ማለትህን ተው” አለው።
ይህም ለሦስተኛ ጊዜ ተደገመ፤ ወዲያውኑም ጨርቅ የሚመስለው ነገር ወደ ሰማይ ተወሰደ።
ጴጥሮስ ‘የራእዩ ትርጉም ምን ይሆን’ በማለት በጣም ግራ ተጋብቶ እያለ ቆርኔሌዎስ የላካቸው ሰዎች የስምዖንን ቤት አጠያይቀው መጡና የውጭው በር ላይ ቆሙ።
ከዚያም ተጣርተው ጴጥሮስ ተብሎ የሚጠራው ስምዖን በዚያ በእንግድነት አርፎ እንደሆነ ጠየቁ።
ጴጥሮስ ያየውን ራእይ በሐሳቡ እያወጣና እያወረደ ሳለ መንፈስ እንዲህ አለው፦ “እነሆ፣ ሦስት ሰዎች ይፈልጉሃል።
ስለዚህ ተነስተህ ወደ ታች ውረድ፤ የላክኋቸው እኔ ስለሆንኩ ምንም ሳትጠራጠር አብረሃቸው ሂድ።”
ጴጥሮስም ሰዎቹ ወዳሉበት ወርዶ “የምትፈልጉት ሰው እኔ ነኝ። ወደዚህ የመጣችሁት ለምንድን ነው?” አላቸው።
እነሱም እንዲህ አሉ፦ “በአይሁዳውያን ሁሉ የተመሠከረለት ቆርኔሌዎስ የተባለ ጻድቅና አምላክን የሚፈራ አንድ የጦር መኮንን፣ ወደ አንተ መልእክተኞች ልኮ ወደ ቤቱ እንዲያስመጣህና የምትለውን ነገር እንዲሰማ አንድ ቅዱስ መልአክ መለኮታዊ መመሪያ ሰጥቶታል።”
እሱም ወደ ቤት አስገብቶ አስተናገዳቸው። በማግስቱም ተነስቶ ከእነሱ ጋር ሄደ፤ በኢዮጴ ያሉ አንዳንድ ወንድሞችም አብረውት ሄዱ።
በሚቀጥለው ቀንም ወደ ቂሳርያ ገባ። ቆርኔሌዎስም ዘመዶቹንና የቅርብ ወዳጆቹን ሰብስቦ እየጠበቃቸው ነበር።
ጴጥሮስም በገባ ጊዜ ቆርኔሌዎስ ተቀበለውና እግሩ ላይ ወድቆ ሰገደለት።
ጴጥሮስ ግን “ተነስ፣ እኔም እንደ አንተው ሰው ነኝ” ብሎ አስነሳው።
ከእሱ ጋር እየተነጋገረ ወደ ውስጥ ሲገባም ብዙ ሰዎች ተሰብስበው አገኘ።
እሱም እንዲህ አላቸው፦ “አንድ አይሁዳዊ ከሌላ ዘር ጋር ይወዳጅ ወይም ይቀራረብ ዘንድ ሕጉ እንደማይፈቅድ በሚገባ ታውቃላችሁ፤ ሆኖም አምላክ ማንንም ሰው ንጹሕ ያልሆነ ወይም ርኩስ ማለት እንደማይገባኝ ገልጦልኛል።
በመሆኑም በተጠራሁ ጊዜ ምንም ሳላንገራግር መጣሁ። ስለዚህ ለምን እንዳስጠራችሁኝ ማወቅ እፈልጋለሁ።”
ቆርኔሌዎስም እንዲህ አለ፦ “ከአራት ቀን በፊት በዚሁ ሰዓት ይኸውም ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በቤቴ ሆኜ እየጸለይኩ ሳለ የሚያንጸባርቅ ልብስ የለበሰ ሰው ድንገት ፊቴ ቆሞ
እንዲህ አለኝ፦ ‘ቆርኔሌዎስ፣ ጸሎትህ ተሰምቶልሃል፤ ምጽዋትህም በአምላክ ፊት ታስቦልሃል።
ስለዚህ ወደ ኢዮጴ ሰዎች ልከህ ጴጥሮስ ተብሎ የሚጠራውን ስምዖንን አስጠራው። ይህ ሰው፣ ቤቱ በባሕሩ አጠገብ በሚገኘው በቆዳ ፋቂው በስምዖን ቤት በእንግድነት አርፏል።’
እኔም ወዲያውኑ ሰዎች ላክሁብህ፤ አንተም በመምጣትህ መልካም አድርገሃል። ስለዚህ አሁን እኛ ይሖዋ እንድትናገር ያዘዘህን ነገር ሁሉ ለመስማት ይኸው ሁላችንም በአምላክ ፊት ተገኝተናል።”
በዚህ ጊዜ ጴጥሮስ እንዲህ ሲል መናገር ጀመረ፦ “እነሆ፣ አምላክ እንደማያዳላ በእርግጥ አስተዋልኩ፤
ከዚህ ይልቅ ከየትኛውም ብሔር ቢሆን እሱን የሚፈራና ትክክል የሆነውን ነገር የሚያደርግ ሰው በእሱ ዘንድ ተቀባይነት አለው።
አምላክ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለእስራኤል ልጆች የሰላም ምሥራች ለማወጅ ቃሉን ላከላቸው፤ ይህም ምሥራች ኢየሱስ የሁሉ ጌታ እንደሆነ የሚገልጽ ነው።
ዮሐንስ ስለ ጥምቀት ከሰበከ በኋላ ከገሊላ አንስቶ በመላው ይሁዳ ይወራ ስለነበረው ጉዳይ ታውቃላችሁ፤
የተወራውም ስለ ናዝሬቱ ኢየሱስ ነው። አምላክ በመንፈስ ቅዱስ ቀባው፤ ደግሞም ኃይል ሰጠው፤ ኢየሱስም አምላክ ከእሱ ጋር ስለነበር መልካም ነገር እያደረገና በዲያብሎስ ቁጥጥር ሥር የወደቁትን እየፈወሰ በዚያ አገር ሁሉ ተዘዋወረ።
እሱ በአይሁዳውያን አገርም ሆነ በኢየሩሳሌም ላደረጋቸው ነገሮች ሁሉ እኛ ምሥክሮች ነን፤ እነሱ ግን በእንጨት ላይ ሰቅለው ገደሉት።
አምላክ እሱን በሦስተኛው ቀን አስነሳው፤ ከዚያም ለሰዎች እንዲገለጥ አደረገው፤
የተገለጠው ግን ለሁሉም ሰው ሳይሆን አምላክ አስቀድሞ ለመረጣቸው ምሥክሮች ይኸውም ከሞት ከተነሳ በኋላ አብረነው ለበላንና ለጠጣን ለእኛ ነው።
በተጨማሪም አምላክ እሱን በሕያዋንና በሙታን ላይ ፈራጅ አድርጎ እንደሾመው ለሰዎች እንድንሰብክና በተሟላ ሁኔታ እንድንመሠክር አዘዘን።
በእሱ የሚያምን ሁሉ በስሙ የኃጢአት ይቅርታ እንደሚያገኝ ነቢያት ሁሉ ስለ እሱ ይመሠክራሉ።”
ጴጥሮስ ስለዚህ ጉዳይ ገና እየተናገረ ሳለ ቃሉን እየሰሙ በነበሩት ሁሉ ላይ መንፈስ ቅዱስ ወረደ።
ከጴጥሮስ ጋር የመጡት የተገረዙ አማኞች የመንፈስ ቅዱስ ነፃ ስጦታ ከአሕዛብ ወገን በሆኑ ሰዎችም ላይ በመፍሰሱ ተገረሙ።
ምክንያቱም በባዕድ ቋንቋዎች ሲናገሩና አምላክን ሲያወድሱ ይሰሟቸው ነበር። በዚህ ጊዜ ጴጥሮስ እንዲህ አለ፦
“እንደ እኛው መንፈስ ቅዱስ የተቀበሉትን እነዚህን ሰዎች በውኃ እንዳይጠመቁ ሊከለክላቸው የሚችል አለ?”
ይህን ካለ በኋላ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲጠመቁ አዘዛቸው። ከዚያም የተወሰነ ቀን አብሯቸው እንዲቆይ ለመኑት።
ከዚያም ጳውሎስ ወደ ደርቤና ወደ ልስጥራ ሄደ። በዚያም አማኝ የሆነች አይሁዳዊት እናትና ግሪካዊ አባት ያለው ጢሞቴዎስ የሚባል አንድ ደቀ መዝሙር ነበር፤
እሱም በልስጥራና በኢቆንዮን ባሉ ወንድሞች፣ በመልካም ምግባሩ የተመሠከረለት ነበር።
ጳውሎስ፣ ጢሞቴዎስ አብሮት እንዲሄድ እንደሚፈልግ ገለጸ፤ አባቱ ግሪካዊ መሆኑን ሁሉም ሰው ያውቅ ስለነበረም በእነዚያ አካባቢዎች ስላሉት አይሁዳውያን ሲል ወስዶ ገረዘው።
በየከተሞቹ ሲያልፉም በዚያ ለሚያገኟቸው ሁሉ በኢየሩሳሌም ያሉት ሐዋርያትና ሽማግሌዎች ያስተላለፏቸውን ውሳኔዎች እንዲጠብቁ ጉዳዩን ያሳውቋቸው ነበር።
ጉባኤዎቹም በእምነት እየጠነከሩና ከዕለት ወደ ዕለት በቁጥር እየጨመሩ ሄዱ።
ከዚህም ሌላ መንፈስ ቅዱስ ቃሉን በእስያ አውራጃ እንዳይናገሩ ስለከለከላቸው በፍርግያና በገላትያ አድርገው አለፉ።
ደግሞም ወደ ሚስያ በወረዱ ጊዜ ወደ ቢቲኒያ ሊገቡ ሞከሩ፤ ሆኖም የኢየሱስ መንፈስ አልፈቀደላቸውም።
ስለዚህ በሚስያ በኩል አልፈው ወደ ጥሮአስ ወረዱ።
ጳውሎስም ሌሊት በራእይ አንድ የመቄዶንያ ሰው በዚያ ቆሞ “ወደ መቄዶንያ ተሻገርና እርዳን” ብሎ ሲለምነው አየ።
ጳውሎስ ይህን ራእይ እንዳየም ‘አምላክ ምሥራቹን እንድንሰብክላቸው ጠርቶናል’ የሚል መደምደሚያ ላይ ስለደረስን ወደ መቄዶንያ ለመሄድ ሞከርን።
ስለዚህ ከጥሮአስ መርከብ ተሳፍረን በቀጥታ ወደ ሳሞትራቄ ሄድን፤ በማግስቱ ደግሞ ወደ ኔያጶሊስ ተጓዝን፤
ከዚያም ተነስተን የሮማውያን ቅኝ ግዛትና የመቄዶንያ አውራጃ ቁልፍ ከተማ ወደሆነችው ወደ ፊልጵስዩስ መጣን። በዚህች ከተማም ለተወሰኑ ቀናት ቆየን።
በሰንበት ቀን የጸሎት ስፍራ ይገኝበታል ብለን ወዳሰብነው ከከተማው በር ውጭ ወዳለ አንድ ወንዝ ዳር ሄድን፤ በዚያም ተቀምጠን ተሰብስበው ለነበሩት ሴቶች መናገር ጀመርን።
ከትያጥሮን ከተማ የመጣች፣ ሐምራዊ ጨርቅ የምትሸጥና አምላክን የምታመልክ ሊዲያ የተባለች አንዲት ሴት እያዳመጠች ነበር፤ ይሖዋም ጳውሎስ የሚናገረውን በማስተዋል እንድትሰማ ልቧን በደንብ ከፈተላት።
እሷና በቤቷ የሚኖሩ ሰዎች ከተጠመቁ በኋላ “ለይሖዋ ታማኝ እንደሆንኩ አድርጋችሁ ከቆጠራችሁኝ ወደ ቤቴ ገብታችሁ እረፉ” ብላ ተማጸነችን። እንድንገባም አስገደደችን።
አንድ ቀን ወደ ጸሎት ስፍራ እየሄድን ሳለ መንፈስ ይኸውም የጥንቆላ ጋኔን ያደረባት አንዲት አገልጋይ አገኘችን። እሷም በጥንቆላ ሥራዋ ለጌቶቿ ብዙ ትርፍ ታስገኝላቸው ነበር።
ይህች ሴት ጳውሎስንና እኛን እየተከተለች “እነዚህ ሰዎች የመዳንን መንገድ የሚያውጁላችሁ የልዑሉ አምላክ ባሪያዎች ናቸው” በማለት ትጮኽ ነበር።
ለብዙ ቀናት እየደጋገመች ይህንኑ ትናገር ነበር። በመጨረሻም ጳውሎስ በዚህ ነገር በመሰላቸቱ ዞር ብሎ ያን መንፈስ “ከእሷ እንድትወጣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዝሃለሁ” አለው። መንፈሱም በዚያው ቅጽበት ወጣ።
ጌቶቿ የገቢ ምንጫቸው መቋረጡን ባዩ ጊዜ ጳውሎስንና ሲላስን ይዘው እየጎተቱ ገዢዎቹ ወደሚገኙበት ወደ ገበያ ስፍራው ወሰዷቸው።
ከዚያም የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች ፊት አቅርበዋቸው እንዲህ አሉ፦ “እነዚህ ሰዎች ከተማችንን ክፉኛ እያወኩ ነው። እነሱ አይሁዳውያን ናቸው፤
ደግሞም እኛ ሮማውያን ልንቀበለውም ሆነ ልንፈጽመው የማይገባንን ልማድ እያስፋፉ ነው።”
ሕዝቡም በአንድነት በእነሱ ላይ ተነሳ፤ የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎችም ልብሳቸውን ከገፈፏቸው በኋላ በበትር እንዲደበደቡ አዘዙ።
በጣም ከደበደቧቸው በኋላ እስር ቤት አስገቧቸው፤ የእስር ቤቱንም ጠባቂ በደንብ እንዲጠብቃቸው አዘዙት።
እሱም እንዲህ ያለ ትእዛዝ ስለተሰጠው ወደ እስር ቤቱ ውስጠኛ ክፍል አስገብቶ እግራቸውን በእግር ግንድ አሰረው።
ይሁንና እኩለ ሌሊት ገደማ ጳውሎስና ሲላስ እየጸለዩና አምላክን በመዝሙር እያወደሱ ነበር፤ ሌሎቹ እስረኞችም ያዳምጧቸው ነበር።
ድንገት ከባድ የምድር ነውጥ በመከሰቱ የእስር ቤቱ መሠረት ተናጋ። በተጨማሪም በሮቹ ወዲያውኑ የተከፈቱ ሲሆን ሁሉም የታሰሩበት ማሰሪያ ተፈታ።
የእስር ቤቱ ጠባቂም ከእንቅልፉ ነቅቶ የእስር ቤቱ በሮች መከፈታቸውን ሲያይ እስረኞቹ ያመለጡ መስሎት ራሱን ለመግደል ሰይፉን መዘዘ።
ጳውሎስ ግን ድምፁን ከፍ አድርጎ “በራስህ ላይ ክፉ ነገር አታድርግ! ሁላችንም እዚህ አለን” ሲል ተናገረ።
በዚህ ጊዜ የእስር ቤቱ ጠባቂ መብራት እንዲያመጡለት ጠይቆ ወደ ውስጥ ዘሎ ገባ፤ እየተንቀጠቀጠም በጳውሎስና በሲላስ ፊት ተደፋ።
ወደ ውጭ ካወጣቸውም በኋላ “ጌቶቼ፣ ለመዳን ምን ማድረግ ይኖርብኛል?” አለ።
እነሱም “በጌታ ኢየሱስ እመን፤ አንተም ሆንክ ቤተሰብህ ትድናላችሁ” አሉት።
ከዚያም ለእሱና በቤቱ ላሉት ሰዎች ሁሉ የይሖዋን ቃል ነገሯቸው።
ጠባቂውም ሌሊት በዚያው ሰዓት ይዟቸው ሄዶ ቁስላቸውን አጠበላቸው። ከዚያም እሱና መላው ቤተሰቡ ወዲያውኑ ተጠመቁ።
ወደ ቤቱም ወስዶ ማዕድ አቀረበላቸው፤ በአምላክ በማመኑም ከመላው ቤተሰቡ ጋር እጅግ ተደሰተ።
ሲነጋም የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች “እነዚያን ሰዎች ልቀቃቸው” ብለው እንዲነግሩት መኮንኖቹን ላኩበት።
የእስር ቤቱ ጠባቂ የላኩትን መልእክት እንዲህ ሲል ለጳውሎስ ነገረው፦ “የከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች ሁለታችሁ እንድትፈቱ ሰዎች ልከዋል። ስለዚህ አሁን ወጥታችሁ በሰላም ሂዱ።”
ጳውሎስ ግን እንዲህ አላቸው፦ “እኛ የሮም ዜጎች ሆነን ሳለ ያለፍርድ በሕዝብ ፊት ገርፈው እስር ቤት ወረወሩን። ታዲያ አሁን በድብቅ አስወጥተው ሊጥሉን ይፈልጋሉ? እንዲህማ አይሆንም! እነሱ ራሳቸው መጥተው ይዘውን ይውጡ።”
መኮንኖቹም ይህን ነገር ለከተማዋ ሕግ አስከባሪዎች ነገሯቸው። እነሱም ሰዎቹ የሮም ዜጎች መሆናቸውን ሲሰሙ ፍርሃት አደረባቸው።
በመሆኑም መጥተው ለመኗቸው፤ ከእስር ቤቱም ይዘዋቸው ከወጡ በኋላ ከተማዋን ለቀው እንዲሄዱ ጠየቋቸው።
እነሱ ግን ከእስር ቤቱ ወጥተው ወደ ሊዲያ ቤት አመሩ፤ እዚያም ወንድሞችን አግኝተው ካበረታቷቸው በኋላ ከተማዋን ለቀው ሄዱ።
ሐናንያ የሚባል አንድ ሰው ከሚስቱ ከሰጲራ ጋር መሬት ሸጠ።
ይሁንና ከገንዘቡ የተወሰነውን ደብቆ አስቀረ፤ ሚስቱም ይህን ታውቅ ነበር፤ የቀረውንም አምጥቶ ለሐዋርያት አስረከበ።
ጴጥሮስ ግን እንዲህ አለ፦ “ሐናንያ፣ ሰይጣን መንፈስ ቅዱስን እንድትዋሽና ከመሬቱ ሽያጭ የተወሰነውን ደብቀህ እንድታስቀር ያደፋፈረህ ለምንድን ነው?
ሳትሸጠው በፊት ያንተው አልነበረም? ከሸጥከውስ በኋላ ገንዘቡን የፈለግከውን ልታደርግበት ትችል አልነበረም? እንዲህ ያለ ድርጊት ለመፈጸም በልብህ ለምን አሰብክ? የዋሸኸው ሰውን ሳይሆን አምላክን ነው።”
ሐናንያ ይህን ቃል ሲሰማ ወደቀና ሞተ። ይህን የሰሙ ሁሉ እጅግ ፈሩ።
ወጣት ወንዶችም ተነስተው በጨርቅ ከጠቀለሉት በኋላ ተሸክመው አውጥተው ቀበሩት።
ይህ ከሆነ ከሦስት ሰዓት ገደማ በኋላ ደግሞ የተፈጸመውን ነገር ያላወቀችው ሚስቱ መጣች።
ጴጥሮስም “እስቲ ንገሪኝ፣ መሬቱን የሸጣችሁት በዚህ ዋጋ ነው?” አላት። እሷም “አዎ፣ በዚሁ ዋጋ ነው” አለች።