text
stringlengths
4
267
ሙሉ ሜልማት እንድታገኙ እንጂ ዚደኚምንባ቞ውን ነገሮቜ እንዳታጡ ለራሳቜሁ ተጠንቀቁ።
ኚክርስቶስ ትምህርት አልፎ ዚሚሄድና በትምህርቱ ጞንቶ ዹማይኖር ሁሉ አምላክ ዚለውም። በዚህ ትምህርት ጞንቶ ዹሚኖር ሰው ግን አብና ወልድ አሉት።
ማንም ሰው ወደ እናንተ ቢመጣና ይህን ትምህርት ይዞ ባይመጣ በቀታቜሁ አትቀበሉት ወይም ሰላም አትበሉት።
ሰላም ዹሚለው ሰው ዹክፉ ሥራው ተባባሪ ይሆናልና።
ዚምነግራቜሁ ብዙ ነገር ቢኖሚኝም በወሚቀትና በቀለም ልጜፈው አልፈልግምፀ ኹዚህ ይልቅ ደስታቜሁ ዹተሟላ እንዲሆን ወደ እናንተ መጥቌ ፊት ለፊት እንደማነጋግራቜሁ ተስፋ አደርጋለሁ።
ዚተመሚጠቜው ዚእህትሜ ልጆቜ ሰላምታ ያቀርቡልሻል።
ኚሜማግሌው፣ ኚልብ ለምወደው ለተወዳጁ ጋይዮስ።
ዚተወደድክ ወንድም፣ አሁን በመልካም ሁኔታ ላይ እንዳለህ ሁሉ፣ በሁሉም ነገር እንዲሳካልህና ጥሩ ጀንነት እንዲኖርህ እጞልያለሁ።
ወንድሞቜ መጥተው እውነትን አጥብቀህ እንደያዝክ ሲመሠክሩ በመስማ቎ እጅግ ደስ ብሎኛልናፀ ደግሞም በእውነት ውስጥ እዚተመላለስክ መሆኑ በጣም አስደስቶኛል።
ልጆቌ በእውነት ውስጥ እዚተመላለሱ መሆናቾውን ኚመስማት ዹበለጠ ደስታ ዚለኝም።
ዚተወደድክ ወንድም፣ በግል ባታውቃ቞ውም እንኳ ለወንድሞቜ በምታደርገው ነገር ታማኝ መሆንህን እያሳዚህ ነው።
እነሱም በጉባኀው ፊት ስለ አንተ ፍቅር መሥክሚዋል። እባክህ፣ አምላክ ደስ በሚሰኝበት ሁኔታ ሞኛ቞ው።
ኚአሕዛብ ምንም ሳይቀበሉ ዚወጡት ለስሙ ሲሉ ነውና።
ስለዚህ በእውነት ውስጥ አብሚን ዚምንሠራ እንሆን ዘንድ እንዲህ ላሉ ሰዎቜ ዚእንግዳ ተቀባይነት መንፈስ ዚማሳዚት ግዎታ አለብን።
ለጉባኀው ዚጻፍኩት ነገር ነበርፀ ሆኖም በመካኚላ቞ው ዚመሪነት ቊታ መያዝ ዹሚፈልገው ዲዮጥራጢስ ኚእኛ በአክብሮት ዹሚቀበለው ምንም ነገር ዚለም።
በመሆኑም እኔ ኚመጣሁ ስለ እኛ መጥፎ ወሬ በማናፈስ ዚሚሠራውን ሥራ ይፋ አወጣለሁ። ይህም አልበቃ ብሎት ወንድሞቜን በአክብሮት አይቀበልምፀ እነሱን መቀበል ዚሚፈልጉትንም ለመኹልኹልና ኚጉባኀ ለማባሚር ይጥራል።
ወዳጄ ሆይ፣ መጥፎ ዹሆነውን አትኚተልፀ ይልቁንም ጥሩ ዹሆነውን ተኚተል። መልካም ዚሚያደርግ ዹአምላክ ወገን ነው። መጥፎ ዚሚያደርግ አምላክን አላዚውም።
ሁሉም ወንድሞቜ ስለ ድሜጥሮስ በሚገባ መሥክሚዋልፀ እውነት ራሱም ይህን አሚጋግጧል። እንዲያውም እኛም ጭምር ስለ እሱ እዚመሠኚርን ነውፀ ዹምንሰጠው ምሥክርነት ደግሞ እውነት እንደሆነ ታውቃለህ።
ብዙ ዹምነግርህ ነገር ነበሚኝፀ ሆኖም ኹዚህ በላይ በብዕርና በቀለም ልጜፍልህ አልፈልግም።
ኹዚህ ይልቅ በቅርቡ እንደማይህ ተስፋ አደርጋለሁፀ በዚያን ጊዜ ፊት ለፊት እንነጋገራለን። ሰላም ለአንተ ይሁን። ወዳጆቜ ሰላምታ ያቀርቡልሃል። በግለሰብ ደሹጃ ሰላምታዬን ለወዳጆቜ አቅርብልኝ።
ዚኢዚሱስ ክርስቶስ ባሪያና ዚያዕቆብ ወንድም ኹሆነው ኚይሁዳ፣ ለተጠሩትና አባታቜን በሆነው አምላክ ለተወደዱት እንዲሁም ኚኢዚሱስ ክርስቶስ ጋር ይሆኑ ዘንድ ጥበቃ ለተደሹገላቾው፩
ምሕሚት፣ ሰላምና ፍቅር ይብዛላቜሁ።
ዚተወደዳቜሁ ወንድሞቜ፣ ሁላቜንም ስለምናገኘው መዳን ልጜፍላቜሁ እጅግ ጓጉቌ ዹነበሹ ቢሆንም ለአንዮና ለመጚሚሻ ጊዜ ለቅዱሳን ስለተሰጠው እምነት ብርቱ ተጋድሎ እንድታደርጉ ለማሳሰብ ልጜፍላቜሁ ተገደድኩ።
ይህን ያደሚግኩት ፍርድ እንደሚጠብቃ቞ው በቅዱሳን መጻሕፍት ውስጥ አስቀድሞ ዹተነገሹላቾው አንዳንድ ሰዎቜ ሟልኚው ስለገቡ ነውፀ እነዚህ ሰዎቜ ፈሪሃ አምላክ ዚሌላ቞ው፣ በአምላካቜን ጾጋ እያሳበቡ ዓይን ያወጣ ምግባር ዚሚፈጜሙ እንዲሁም ዹዋጀንንና እሱ ብቻ ጌታቜን ዹሆነውን ኢዚሱስ ክርስቶስን ዚሚክዱ ና቞ው።
ምንም እንኳ ይህን ሁሉ አስቀድማቜሁ በሚገባ ታውቁ ዹነበሹ ቢሆንም ይሖዋ ሕዝቡን ኚግብፅ ምድር እንዳዳነ፣ በኋላም እምነት ያላሳዩትን እንዳጠፋ ላስታውሳቜሁ እወዳለሁ።
በተጚማሪም መጀመሪያ ዚነበራ቞ውን ቊታ ያልጠበቁትንና ተገቢ ዹሆነውን ዚመኖሪያ ስፍራ቞ውን ዚተዉትን መላእክት በታላቁ ቀን ለሚፈጞምባ቞ው ፍርድ በዘላለም እስራት በድቅድቅ ጹለማ ውስጥ አቆይቷ቞ዋል።
በተመሳሳይም ሰዶምና ገሞራ እንዲሁም በዙሪያ቞ው ዚነበሩ ኚተሞቜ ራሳ቞ውን ልቅ ለሆነ ዚፆታ ብልግና አሳልፈው ዚሰጡ ኹመሆኑም ሌላ ኚተፈጥሮ ውጭ ዹሆነ ዚሥጋ ፍላጎታ቞ውን ያሳድዱ ነበርፀ በመሆኑም በዘላለም እሳት ፍርድ ተቀጥተው ለእኛ ዚማስጠንቀቂያ ምሳሌ ሆነዋል።
ያም ሆኖ ግን እነዚህ ሕልም አላሚዎቜ ሥጋን ያሚክሳሉፀ ሥልጣንን ይንቃሉፀ ዚተኚበሩትንም ይሳደባሉ።
ይሁንና ዚመላእክት አለቃ ሚካኀል ዹሙሮን ሥጋ በተመለኹተ ኚዲያብሎስ ጋር በተኚራኚሚ ጊዜ ዚስድብ ቃል በመናገር ሊፈርድበት አልደፈሚምፀ ኹዚህ ይልቅ “ይሖዋ ይገሥጜህ” አለው።
እነዚህ ሰዎቜ ግን ስለማያውቁት ነገር ሁሉ ትቜት ይሰነዝራሉ። ደግሞም አእምሮ እንደሌላ቞ው እንስሳት፣ በደመ ነፍስ ዚሚሚዷ቞ውን ነገሮቜ ሁሉ ሲያደርጉ ዚራሳ቞ውን ሥነ ምግባር ያበላሻሉ።
በቃዹን መንገድ ስለሄዱ፣ ለጥቅም ሲሉ ዹበለዓምን ዚተሳሳተ መንገድ በጭፍን ስለተኚተሉና በቆሬ ዹዓመፅ ንግግር ስለጠፉ ወዮላ቞ው!
እነዚህ ሰዎቜ ፍቅራቜሁን ለመግለጜ በምታዘጋጁት ግብዣ ላይ ተገኝተው አብሚዋቜሁ ሲመገቡ ልክ በባሕር ውስጥ እንደተደበቀ ዓለት ኹመሆናቾውም ሌላ ያላንዳቜ ኀፍሚት ለሆዳ቞ው ብቻ ዚሚያስቡ እሚኞቜ ና቞ውፀ በነፋስ ወዲያና ወዲህ ዚሚነዱ ዝናብ ዹሌላቾው ደመናዎቜ እንዲሁም በመኹር ጊዜ ፍሬ ዚማይገኝባ቞ው፣ ሁለት ጊዜ ዚሞቱና ኚሥራ቞ው ዹተነቀሉ ዛፎቜ ና቞ውፀ
አሹፋ እንደሚደፍቅ ኃይለኛ ዚባሕር ማዕበል አሳፋሪ ድርጊታ቞ውን ይገልጣሉፀ ለዘላለም ድቅድቅ ጹለማ ውስጥ ዚሚጣሉ ተንኚራታቜ ኚዋክብት ና቞ው።
ኚአዳም ጀምሮ ሰባተኛ ትውልድ ዹሆነው ሄኖክ ስለ እነዚህ ሰዎቜ እንዲህ ሲል ተንብዮአልፊ “እነሆ! ይሖዋ ኚአእላፋት ቅዱሳን መላእክቱ ጋር መጥቷልፀ
ዚመጣውም በሁሉ ላይ ለመፍሚድ፣ ፈሪሃ አምላክ ዹሌላቾው ሰዎቜ ለአምላክ አክብሮት በጎደለው መንገድ ዚፈጞሙትን ክፉ ድርጊትና ፈሪሃ አምላክ ዹሌላቾው ኃጢአተኞቜ በእሱ ላይ ዚተናገሩትን ክፉ ቃል ለማጋለጥ ነው።”
እነዚህ ሰዎቜ ዚሚያጉሚመርሙና ኑሯ቞ውን ዚሚያማርሩ እንዲሁም ዚራሳ቞ውን ምኞት ዹሚኹተሉ ና቞ውፀ ጉራ መንዛት ይወዳሉፀ ለጥቅማ቞ው ሲሉም ሌሎቜን ይክባሉ።
ዚተወደዳቜሁ ወንድሞቜ፣ እናንተ ግን ዚጌታቜን ዚኢዚሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት አስቀድመው ዚነገሯቜሁን ቃል አስታውሱፀ
እነሱ “በመጚሚሻው ዘመን መጥፎ ምኞታ቞ውን ዹሚኹተሉ ዘባ቟ቜ ይነሳሉ” ይሏቜሁ ነበር።
እነዚህ ሰዎቜ ክፍፍል ዚሚፈጥሩ፣ ዚእንስሳ ባሕርይ ያላ቞ውና መንፈሳዊ ያልሆኑ ና቞ው።
ዚተወደዳቜሁ ወንድሞቜ፣ እናንተ ግን እጅግ ቅዱስ በሆነው እምነታቜሁ ላይ ራሳቜሁን ገንቡፀ እንዲሁም በመንፈስ ቅዱስ ጞልዩፀ
ይህን ዚምታደርጉት ዹዘላለም ሕይወት ዚሚያስገኝላቜሁን ዚጌታቜንን ዚኢዚሱስ ክርስቶስን ምሕሚት እዚተጠባበቃቜሁ ኹአምላክ ፍቅር ሳትወጡ እንድትኖሩ ነው።
በተጚማሪም ጥርጣሬ ላደሚባ቞ው ምሕሚት አሳዩፀ
ኚእሳት ነጥቃቜሁ በማውጣት አድኗ቞ው። ለሌሎቜ ምሕሚት ማሳዚታቜሁንም ቀጥሉፀ ሆኖም ይህን ስታደርጉ ለራሳቜሁ መጠንቀቅና በሥጋ ሥራ ያደፈውን ልብሳ቞ውን መጥላት ይኖርባቜኋል።
እንዳትሰናኚሉ ሊጠብቃቜሁና ነቀፋ ዚሌለባቜሁ አድርጎ በታላቅ ደስታ፣ በክብሩ ፊት ሊያቆማቜሁ ለሚቜለው፣
አዳኛቜን ለሆነው ብ቞ኛው አምላክ ኚዘመናት ሁሉ በፊት፣ አሁንና እስኚ ዘላለም በጌታቜን ኢዚሱስ ክርስቶስ በኩል ክብር፣ ግርማ፣ ኃይልና ሥልጣን ይሁን። አሜን።
ሰባቱን ሳህኖቜ ይዘው ኚነበሩት ሰባት መላእክት አንዱ መጥቶ እንዲህ አለኝ፩ “ና፣ በብዙ ውኃዎቜ ላይ በምትቀመጠው በታላቂቱ አመንዝራ ላይ ዹተበዹነውን ፍርድ አሳይሃለሁፀ
ዚምድር ነገሥታት ኚእሷ ጋር አመነዘሩፀ ዚምድር ነዋሪዎቜ ደግሞ በዝሙቷ ወይን ጠጅ ሰኚሩ።”
እሱም በመንፈስ ኃይል ወደ ምድሚ በዳ ወሰደኝ። በዚያም አንዲት ሎት አምላክን ዚሚሰድቡ ስሞቜ በሞሉበት እንዲሁም ሰባት ራሶቜና አሥር ቀንዶቜ ባሉት ደማቅ ቀይ አውሬ ላይ ተቀምጣ አዚሁ።
ሎቲቱ ሐምራዊና ደማቅ ቀይ ልብስ ለብሳ እንዲሁም በወርቅ፣ በኚበሩ ድንጋዮቜና በዕንቁዎቜ አጊጣ ነበርፀ በእጇም አስጞያፊ ነገሮቜና ዚዝሙቷ ርኩሰት ዚሞላበት ዹወርቅ ጜዋ ይዛ ነበር።
በግንባሯ ላይ “ታላቂቱ ባቢሎን፣ ዚአመንዝሮቜና ዚምድር አስጞያፊ ነገሮቜ እናት” ዹሚል ሚስጥራዊ ስም ተጜፎ ነበር።
እኔም ሎቲቱ በቅዱሳን ደምና በኢዚሱስ ምሥክሮቜ ደም ሰክራ አዚኋት። ባዚኋትም ጊዜ እጅግ ተደነቅኩ።
መልአኩም እንዲህ አለኝ፩ “ዹተደነቅኹው ለምንድን ነው? ዚሎቲቱን እንዲሁም እሷ ዚተቀመጠቜበትን ሰባት ራሶቜና አሥር ቀንዶቜ ያሉት አውሬ ሚስጥር እነግርሃለሁፊ
ያዚኞው አውሬ ኹዚህ በፊት ነበርፀ አሁን ግን ዚለምፀ ይሁንና በቅርቡ ኚጥልቁ ይወጣልፀ ወደ ጥፋትም ይሄዳል። ዓለም ኚተመሠሚተበት ጊዜ አንስቶ ስማ቞ው በሕይወት መጜሐፍ ጥቅልል ላይ ያልተጻፈው ዚምድር ነዋሪዎቜ አውሬው ኹዚህ በፊት እንደነበሚ፣ አሁን ግን እንደሌለና ወደፊት እንደሚኖር ሲያዩ በአድናቆት ይዋጣሉ።
“ይህ ነገር ጥበብ ያለው አእምሮ ይጠይቃል፩ ሰባቱ ራሶቜ ሎቲቱ ዚተቀመጠቜባ቞ውን ሰባት ተራሮቜ ያመለክታሉ።
ደግሞም ሰባት ነገሥታት ናቾው፩ አምስቱ ወድቀዋልፀ አንዱ አለፀ ሌላው ደግሞ ገና አልመጣምፀ በሚመጣበት ጊዜ ግን ለአጭር ጊዜ ሊቆይ ይገባዋል።
ኹዚህ በፊት ዚነበሚው፣ አሁን ግን ዹሌለው አውሬም ስምንተኛ ንጉሥ ነውፀ ዚሚወጣው ግን ኚሰባቱ ነውፀ እሱም ወደ ጥፋት ይሄዳል።
“ያዚሃ቞ው አሥሩ ቀንዶቜ ገና መንግሥትን ያልተቀበሉ አሥር ነገሥታትን ያመለክታሉፀ ይሁንና ኚአውሬው ጋር ለአንድ ሰዓት እንዲነግሡ ሥልጣን ይቀበላሉ።
እነዚህ አንድ ዓይነት ሐሳብ አላ቞ውፀ በመሆኑም ኃይላቾውንና ሥልጣና቞ውን ለአውሬው ይሰጣሉ።
እነዚህ ኹበጉ ጋር ይዋጋሉፀ ሆኖም በጉ ዚጌቶቜ ጌታና ዚነገሥታት ንጉሥ ስለሆነ ድል ይነሳ቞ዋል። ኚእሱ ጋር ያሉት ዚተጠሩት፣ ዚተመሚጡትና ዚታመኑትም ድል ያደርጋሉ።”
እሱም እንዲህ አለኝ፩ “አመንዝራዋ ተቀምጣባ቞ው ያዚሃ቞ው ውኃዎቜ ወገኖቜን፣ ብዙ ሕዝብን፣ ብሔራትንና ቋንቋዎቜን ያመለክታሉ።
ያዚሃ቞ው አሥሩ ቀንዶቜና አውሬውም አመንዝራዋን ይጠሏታልፀ ኚዚያም ይበዘብዟታልፀ ራቁቷንም ያስቀሯታልፀ እንዲሁም ሥጋዋን ይበላሉፀ ሙሉ በሙሉም በእሳት ያቃጥሏታል።
አምላክ ቃሉ ፍጻሜውን እስኪያገኝ ድሚስ ሐሳቡን ዳር እንዲያደርሱ አዎ፣ መንግሥታ቞ውን ለአውሬው በመስጠት አንድ ዹሆነውን ዚራሳ቞ውን ሐሳብ እንዲፈጜሙ ይህን በልባ቞ው አኑሯልና።
ያዚሃትም ሎት በምድር ነገሥታት ላይ መንግሥት ያላትን ታላቂቱን ኹተማ ታመለክታለቜ።”
ኹዚህ በኋላ በሰማይ እንደ ብዙ ሠራዊት ድምፅ ያለ ታላቅ ድምፅ ሰማሁ። እንዲህም አሉ፩ “ያህን አወድሱ! ማዳን፣ ክብርና ኃይል ዚአምላካቜን ነውፀ
ምክንያቱም ፍርዶቹ እውነትና ጜድቅ ና቞ው። ምድርን በዝሙቷ ባሚኚሰቜው በታላቂቱ አመንዝራ ላይ ዚፍርድ እርምጃ ወስዷልናፀ እንዲሁም ስለ ባሪያዎቹ ደም ተበቅሏታል።”
ወዲያውኑም ለሁለተኛ ጊዜ “ያህን አወድሱ! ኚእሷ ዚሚወጣው ጭስም ለዘላለም ወደ ላይ ይወጣል” አሉ።
ደግሞም 24ቱ ሜማግሌዎቜና አራቱ ሕያዋን ፍጥሚታት ተደፍተው በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው አምላክ ሰገዱፀ እንዲሁም “አሜን! ያህን አወድሱ!” አሉ።
በተጚማሪም ኹዙፋኑ ዚወጣ አንድ ድምፅ “እሱን ዚምትፈሩ ባሪያዎቹ ሁሉ፣ ታናናሟቜና ታላላቆቜ፣ አምላካቜንን አወድሱ” አለ።
እንደ ብዙ ሠራዊት ድምፅ፣ እንደ ብዙ ውኃዎቜ ድምፅና እንደ ኃይለኛ ነጎድጓድ ድምፅ ያለ ነገር ሰማሁ። እንዲህም አሉ፩ “ያህን አወድሱፀ ምክንያቱም ሁሉን ቻይ ዹሆነው አምላካቜን ይሖዋ ነግሩአል!
ዹበጉ ሠርግ ስለደሚሰና ሙሜራዋ ራሷን ስላዘጋጀቜ እንደሰትፀ ሐሎትም እናድርግፀ ለእሱም ክብር እንስጠው።
አዎ፣ ዚሚያንጞባርቅና ንጹሕ ዹሆነ ጥሩ በፍታ እንድትለብስ ተሰጥቷታልፀ ይህ ጥሩ በፍታ ዚቅዱሳንን ዚጜድቅ ተግባር ያመለክታልና።”
እሱም “ይህን ጻፍፊ ወደ በጉ ሠርግ ዚራት ግብዣ ዚተጠሩ ደስተኞቜ ናቾው” አለኝ። ደግሞም “እነዚህ እውነተኛ ዹአምላክ ቃሎቜ ናቾው” አለኝ።
እኔም በዚህ ጊዜ ልሰግድለት በእግሩ ፊት ተደፋሁ። እሱ ግን “ተጠንቀቅ! ፈጜሞ እንዳታደርገው! እኔ ኹአንተም ሆነ ስለ ኢዚሱስ ዚመመሥኚር ሥራ ካላ቞ው ወንድሞቜህ ጋር አብሬ ዹማገለግል ባሪያ ነኝ። ለአምላክ ስገድ! ትንቢት ዹሚነገሹው ስለ ኢዚሱስ ለመመሥኚር ነውና” አለኝ።
እኔም ሰማይ ተኚፍቶ አዚሁፀ እነሆም፣ ነጭ ፈሚስ ነበር። በእሱም ላይ ዹተቀመጠው “ታማኝና እውነተኛ” ተብሎ ይጠራልፀ እሱም በጜድቅ ይፈርዳል እንዲሁም ይዋጋል።
ዓይኖቹ ዚእሳት ነበልባል ና቞ውፀ በራሱም ላይ ብዙ ዘውዶቜ አሉ። ኚራሱ በቀር ማንም ዚማያውቀው ስም ተጜፎበታልፀ
ደም ዚነካው መደሚቢያም ለብሷልፀ ደግሞም “ዹአምላክ ቃል” በሚል ስም ይጠራል።
በተጚማሪም በሰማይ ያሉት ሠራዊቶቜ በነጭ ፈሚሶቜ ተቀምጠው ይኚተሉት ነበርፀ እነሱም ነጭና ንጹሕ ዹሆነ ጥሩ በፍታ ለብሰው ነበር።
እሱም ብሔራትን ይመታበት ዘንድ ኹአፉ ሹጅም ስለታም ሰይፍ ይወጣልፀ እንደ እሚኛም በብሚት በትር ይገዛ቞ዋል። በተጚማሪም ሁሉን ቻይ ዹሆነውን ዹአምላክን ዚመዓቱን ዚቁጣ ወይን ጠጅ መጭመቂያ ይሚግጣል።
በመደሚቢያው አዎ፣ በጭኑ ላይ “ዚነገሥታት ንጉሥና ዚጌቶቜ ጌታ” ዹሚል ስም ተጜፏል።
በተጚማሪም አንድ መልአክ በፀሐይ መካኚል ቆሞ አዚሁፀ እሱም በታላቅ ድምፅ ጮኟ በሰማይ መካኚል ለሚበርሩት ወፎቜ ሁሉ እንዲህ አለ፩ “ወደዚህ ኑፀ ወደ ታላቁ ዹአምላክ ራት ተሰብሰቡፀ
ዚነገሥታትን ሥጋ፣ ዹጩር አዛዊቜን ሥጋ፣ ዚብርቱ ሰዎቜን ሥጋ፣ ዚፈሚሶቜንና ዚፈሚሰኞቜን ሥጋ እንዲሁም ዹሁሉንም ሥጋ ይኾውም ዹነፃ ሰዎቜንና ዚባሪያዎቜን፣ ዚታናናሟቜንና ዚታላላቆቜን ሥጋ ብሉ።”
ኹዚህ በኋላ አውሬው፣ ዚምድር ነገሥታትና ሠራዊታ቞ው በፈሚሱ ላይ ኹተቀመጠውና ኚሠራዊቱ ጋር ለመዋጋት ተሰብስበው አዚሁ።
አውሬውም ተያዘፀ በፊቱ ተአምራዊ ምልክቶቜ ዹፈጾመው ሐሰተኛው ነቢይም ኚእሱ ጋር ተያዘፀ ይህ ነቢይ በእነዚህ ምልክቶቜ አማካኝነት፣ ዚአውሬውን ምስል ዚተቀበሉትንና ለምስሉ ዚሰገዱትን አስቷል። ሁለቱም በሕይወት እንዳሉ በድኝ ወደሚነደው ዚእሳት ሐይቅ ተወሚወሩ።
ዚቀሩት ግን በፈሚሱ ላይ ኹተቀመጠው አፍ በወጣው ሹጅም ሰይፍ ተገደሉ። ወፎቜም ሁሉ ሥጋ቞ውን በልተው ጠገቡ።
እኔም ዘንግ ዚሚመስል ሞምበቆ ተሰጠኝፀ እንዲህም አለኝ፩ “ተነስና ዹአምላክን ቀተ መቅደስ ቅዱስ ስፍራ፣ መሠዊያውንና በዚያ ዚሚያመልኩትን ለካ።
ሆኖም ኚቀተ መቅደሱ ቅዱስ ስፍራ ውጭ ያለውን ግቢ ሙሉ በሙሉ ተወውፀ አትለካውፀ ምክንያቱም ለአሕዛብ ተሰጥቷልፀ እነሱም ዚተቀደሰቜውን ኹተማ ለ42 ወራት ይሚግጧታል።
እኔም ሁለቱ ምሥክሮቌ ማቅ ለብሰው ለ1,260 ቀናት ትንቢት እንዲናገሩ አደርጋለሁ።”
እነዚህ በሁለቱ ዚወይራ ዛፎቜና በሁለቱ መቅሚዞቜ ተመስለዋልፀ እነሱም በምድር ጌታ ፊት ቆመዋል።
ማንም እነሱን ሊጎዳ ቢፈልግ እሳት ኹአፋቾው ወጥቶ ጠላቶቻ቞ውን ይበላል። ማንም ሊጎዳ቞ው ቢፈልግ በዚህ ዓይነት ሁኔታ መገደል አለበት።
እነዚህ ሰዎቜ ትንቢት በሚናገሩባ቞ው ቀናት ምንም ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን ዚመዝጋት ሥልጣን አላ቞ውፀ እንዲሁም ውኃዎቜን ወደ ደም ዚመለወጥና ዚፈለጉትን ጊዜ ያህል፣ በማንኛውም ዓይነት መቅሰፍት ምድርን ዚመምታት ሥልጣን አላ቞ው።
ዚምሥክርነት ሥራ቞ውን ባጠናቀቁ ጊዜ፣ ኚጥልቁ ዚሚወጣው አውሬ ውጊያ ይኚፍትባ቞ዋልፀ ድል ይነሳ቞ዋልፀ እንዲሁም ይገድላ቞ዋል።
አስኚሬና቞ውም በመንፈሳዊ ሁኔታ ሰዶምና ግብፅ ተብላ በምትጠራውና ዚእነሱም ጌታ በእንጚት ላይ በተሰቀለባት በታላቂቱ ኹተማ አውራ ጎዳና ላይ ይጋደማል።
ኚተለያዩ ሕዝቊቜ፣ ነገዶቜ፣ ቋንቋዎቜና ብሔራት ዚተውጣጡ ሰዎቜም ለሊስት ቀን ተኩል አስኚሬና቞ውን ያያሉፀ አስኚሬና቞ውም እንዲቀበር አይፈቅዱም።
እነዚህ ሁለት ነቢያት በምድር ላይ ዚሚኖሩትን አሠቃይተው ስለነበር በምድር ላይ ዚሚኖሩት በእነሱ ሞት ይደሰታሉፀ ሐሎትም ያደርጋሉ እንዲሁም እርስ በርሳ቞ው ስጊታ ይሰጣጣሉ።
ኚሊስት ቀን ተኩል በኋላ ኹአምላክ ዚመጣ ዚሕይወት መንፈስ ገባባ቞ውፀ በእግሮቻ቞ውም ቆሙፀ ያዩአ቞ውም ሰዎቜ በታላቅ ፍርሃት ተዋጡ።
ኹሰማይም አንድ ታላቅ ድምፅ “ወደዚህ ውጡ” ሲላ቞ው ሰሙ። እነሱም በደመና ውስጥ ሆነው ወደ ሰማይ ወጡፀ ጠላቶቻ቞ውም አዩአ቞ው።
በዚያም ሰዓት ታላቅ ዚምድር ነውጥ ተኚሰተፀ ዹኹተማዋ አንድ አሥሚኛም ወደቀፀ በምድር ነውጡም 7,000 ሰዎቜ ሞቱፀ ዚቀሩትም ፍርሃት አደሚባ቞ውፀ ለሰማይ አምላክም ክብር ሰጡ።
ሁለተኛው ወዮታ አልፏል። እነሆ፣ ሊስተኛው ወዮታ በፍጥነት ይመጣል።
ሰባተኛው መልአክ መለኚቱን ነፋ። በሰማይም ታላላቅ ድምፆቜ እንዲህ ሲሉ ተሰሙ፩ “ዹዓለም መንግሥት ዚጌታቜንና ዚእሱ መሲሕ መንግሥት ሆነፀ እሱም ለዘላለም ይነግሣል።”
በአምላክ ፊት በዙፋኖቻ቞ው ላይ ተቀምጠው ዚነበሩት 24ቱ ሜማግሌዎቜም በግንባራ቞ው ተደፍተው ለአምላክ ሰገዱፀ