text
stringlengths 26
19k
|
|---|
የፎቶው ባለመብት EPA-EEE/REX/SHUTTERSTOCK-በሁቲዎች ጥቃት የሰመጠችው የመጀመሪያዋ መርከብ ሩቢይማር-የየመን ሁቲዎች አማጺያን በቀይ ባሕር በኩል በሚያቋርጡ መርከቦች ላይ ጥቃት መፈጸም ከመጀመሩ ከወራት በኋላ የመጀመሪያዋ ግዙፍ መርከብ ሰመጠች።-በብሪታኒያ የተመዘገበችው የጭነት መርከብ ማዳበሪያ ጭና በቀይ ባሕር በኩል ለማቋረጥ ስትሞክር ነበር ከሁለት ሳምንት በፊት በኤደን ባሕረ ሰላጤ ላይ በሁቲ ታጣቂዎች ሚሳኤል ተመትታ የቆመችው።-የየመን መንግሥት ባለሥልጣናት እንዳስታወቁት ሪቢይማር የተባለችው መርከብ ጥቃት ከተፈጸመባት በኋላ ውሃ ወደ ውስጧ እየገባ ለቀናት በባሕሩ ላይ ስትዋልል ቆይታ ሰምጣለች።-በኢራን የሚደገፉት ሁቲ አማጺያን ካለፈው ኅዳር አንስቶ በቀይ ባሕር የሚያቋርጡ መርከቦችን ዒላማ ማድረግ ከጀመሩ ወዲህ ይህች መርከብ ጥቃት ከተፈጸመባቸው መካከል በመስመጥ የመጀመሪያዋ ሆናለች።-የሰመጠችው መርከብ ማዳበሪያ ጭና እየተጓዘች ሳለ ነው በሁቲዎች ሚሳኤል የተመታችው። የመርከቧ መስመጥ በቀይ ባሕር ላይ “የተፈጥሮ አካባቢ ጉዳትን” የሚደቅን ነው ሲሉ ባለሙያዎች ተናግረዋል።-ሩቢይማር የተባለችው ይህች መርከብ በኤደን ባሕረ ሰላጤ በኩል ባብ ኤል መንደብ አቅራቢያ ሳለች ነው በየመን ሁቲ አማጺያን በተተኮሱ ሁለት ሚሳኤሎች የተመታችው።-ከአስር ቀናት በፊት የብሪታኒያ መንግሥት መርከቧ ላይ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ ወደ ውስጧ ውሃ እየሰረገ መሆኑን እና 24 የመርከቧ ሠራተኞችን ማትረፍ መቻሉን ገልጾ ነበር።-ከአንድ ሳምንት በፊት ቢቢሲ ያገኘው ምሥል ላይ የተወሰነ የመርከቧ ክፍል በውሃ ተውጦ ቀሪው ክፍል በውሃ ላይ እየተንሳፈፈ ያሳይ ነበር።-የመርከቧ ባለቤቶች በወቅቱ መርከቧ ተጎትታ በአቅራቢያ ወደሚገኘው የጂቡቲ ወደብ እየተወሰደች መሆኗን፣ ነገር ግን ልትሰምጥ እንደምትችል አመልክተው ነበር።-መርከቧ በብሪታኒያ ተመዝግባ በአንድ የሊባኖስ ተቋም አማካይነት ስትንቀሳቀስ የቆየች ናት። ጥቃቱ በተፈጸመባት ጊዜም አሞኒየም ናይትሬት የተባለውን ማዳበሪያ ጭና እንደነበር ተነግሯል።-በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እውቅና ያለው የየመን መንግሥት ጠቅላይ ሚኒስትር አህመድ ቢን ሙባራክ፣ የመርከቧን መስመጥ “አጋጥሞ የማያውቅ የአካባቢ አደጋ ነው” ሲሉ ገልጸውታል።-በዓለም ዙሪያ ላሉ የውሃ አካላት ደኅንነት የሚከራከረው የአካባቢ ጥበቃ ተከራካሪው ግሪን ፒስ በበኩሉ የአሞኒየም ናይትሬት ማዳበሪያው ወደ ባሕሩ መግባት “ከውሃ በታች ባለው ሥነ ምኅዳር ላይ ከፍተኛ ተጽእኖን ይፈጥራል” ብሏል።-ሁቲዎች በጋዛ ውስጥ ላሉ ፍልስጤማውያን ያላቸውን ድጋፍ ለማሳየት ካለፈው ኅዳር ጀምሮ በቀይ ባሕር እና በኤደር ባሕረ ሰላጤ በኩል በሚያቋርጡ ከእስራኤል ጋር ግንኙነት አላቸው ባሏቸው መርከቦች ላይ ጥቃት እየፈጸሙ ነው።-ለዚህም ምላሽ አሜሪካ እና ዩናይትድ ኪንግደም የመን ውስጥ በሚገኙ የሁቲ ይዞታዎች ላይ ተከታታይ የአየር ጥቃቶችን ፈጽመዋል።-ይህ በእንዲህ እንዳለ የዩናይትድ ኪንግደም የባሕር ላይ ንግድ ተቋም ቅዳሜ ዕለት እንዳሳወቀው፣ ከየመኗ ወደብ ሞካህ በስተ ምዕራብ አንዲት መርከብ ላይ ጥቃት እንደተፈጸመ ሪፖርት ደርሶታል።-ጨምሮም “የመርከቧ ሠራተኞች መልህቋን እንድትጥል አድርው በወታደራዊ ባለሥልጣናት ከመርከቧ እንዲወጡ ተደርገዋል” ብሏል።-የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ “እራስን ለመከላከል በተወሰድ እርምጃ” ከየመን በኩል በሁቲዎች ሊተኮስ ተዘጋጅቶ የነበረ ከምድር ወደ አየር የሚወነጨፍ ሚሳኤልን መምታቱን አሳውቋል።-ወታደራዊ ማዘዣው ሊወነጨፍ የነበረው ሚሳኤል በአሜሪካ አውሮፕላን ላይ አሳሳቢ ስጋትን ደቅኖ እንደነበር አመልክቷል።-የአማጺያኑ ጥቃት የዓለም የባሕር ላይ ንግድ 12 በመቶው በሚዘዋወርበት በወሳኙ የቀይ ባሕር በኩል የሚያቋርጡ የግዙፍ የጭነት መርከብ ኩባንያዎች መስመራቸውን እንዲቀይሩ አስገድዷል።-ምንም እንኳን በአሜሪካ የሚመራው የባሕር ኃይል ጥምረት አገራት በሁቲ ዒላማዎች ላይ የአየር ጥቃት መፈጸም ከጀመሩ አንድ ወር ቢያልፋቸውም፣ አማጺያኑ አሁንም በመርከቦች ላይ ከባድ ጥቃቶችን የመፈጸም አቅም እንዳላቸው አሳይተዋል።-ሁቲዎች በቀይ ባሕር ላይ በሚተላለፉ የምዕራባውያን መርከቦች ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት የሚያቆሙት፣ እስራኤል በጋዛ ሰርጥ ውስጥ በሐማስ ላይ የምታካሂደውን ወታደራዊ ዘመቻ ስታቆም መሆኑን አሳውቀዋል።
|
የፎቶው ባለመብት EPA-ለስድስት ሳምንታት በሚደረግ የተኩስ አቁም ጋዛ ፋታ ታገኛለች ተብሎ ይጠበቃል-አምስት ወራት ያስቆጠረውን የእስራኤል ጋዛ ጦርነትን ጋብ ለማድረግ በሚያስችል ንግግር ላይ ለመሳተፍ የሐማስ ልዑካን ግብፅ ካይሮ መግባታቸውን ተከትሎ አዲስ የተኩስ አቁም ስምምነት ይደረሳል የሚል ተስፋ ተፈጥሯል።-ስማቸው ያልተጠቀሰ አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን እስራኤል “ከሞላ ጎደል” የተኩስ አቁም ስምምነቱን መቀበሏን ገልጸዋል።-አሁን ይደረጋል ተብሎ በሚጠበቀው የስድስት ሳምንታት የተኩስ አቁም ስምምነት ተጨማሪ እስራኤላውያን ታጋቾች እና ፍልስጤማውያን አስረኞች ይለቀቃሉ ተብሎ ይጠበቃል።-ሁለቱ ወገኖች ተኩስ እንዲያቆሙ የሚደረገው ግፊት የተጠናከረው ባለፈው ሐሙስ ጋዛ ውስጥ እርዳታ በጫኑ ተሽከርካሪዎች ዙሪያ ከተሰበሰቡ ሰዎች መካከል ቢያንስ 112 ሰዎች መሞታቸውን ተከትሎ ነው።-የምግብ እርዳታ ለመቀበል በተሰበሰቡ ሰዎች ላይ የእስራኤል ወታደሮች ተኩስ ከፍተዋል ሲል ሐማስ ከሷል። እስራኤል ግን ይህንን ክስ በማስተባበል ወታደሮቿ ሊወሯቸው በመጡ “በርካታ ሰግለሰቦች ላይ” መተኮሳቸውን በመጀመሪያ ደረጃ ምርመራ መረዳቷን እና አብዛኞቹ ሰዎች የሞቱት በግርግር ምክንያት በተፈጠረ መረጋገጥ ነው ብላለች።-ከኳታር ጋር በመሆን በሁለቱ ወገኖች መካከል የሚካሄደውን ንግግር የሚመሩት የግብፅ ባለሥልጣናት የሐማስ እና የአስራኤል ተወካዮች በድርድሩ ላይ ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል።-በሚቀጥሉት ከ24 አስከ 48 ሰዓታት ባለው ጊዜ ውስጥ የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ሊደረስ እንደሚችል ሐማስ መናገሩ ተዘግቧል። አንድ የቡድኑ ምንጭ ለግብፅ መገናኛ ብዙኃን ስምምነቱ የሚሰምረው እስራኤል የሐማስን ጥያቄዎች ከተቀበለች እንደሆነ ገልጿል።-አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ለስድስት ሳምንታት በሚቆየው የተኩስ አቁም ማዕቀፍ ላይ እስራኤል “ስምምነት” ማሳየቷን ማረጋገጣቸውን ተከትሎ የተኩስ አቁሙ ዕውን እንደሚሆን ተስፋ ተጥሏል።-ባለፈው መስከረም 26 ሐማስ በደቡባዊ እስራኤል ላይ ጥቃት ፈጽሞ 1200 ሰዎችን በመግደል 253 የሚሆኑትን ደግሞ አግቶ ወደ ጋዛ ከወሰደ በኋላ እስራኤል ሐማስን ለማጥፋት መጠነ ሰፊ የምድር እና የአየር ጥቃቶችን እያካሄደች ነው።-ሐማስ የሚመራው የጋዛ ጤና ሚኒስቴር እንደሚለው በእስራኤል ጥቃት አስካሁን 21000 ህጻናት እና ሴቶችን ጨምሮ ቢያንስ 30410 ሰዎች መገደላቸውን፣ 71700 መቁሰላቸውን እንዲሁም 7000 ሰዎች የደረሱበት አልታወቀም።-የተኩስ አቁም እንዲደረግ ግፊቱ የበረታው የእርዳታ ድርጅቶች በሰሜናዊ ጋዛ የረሃብ አደጋ ስጋት እንዳንዣበበ ማስጠንቀቃቸውን ተከትሎ ነው።-የኖርዌይ ስደተኞች ካውንስል ኃላፊ ያን ኤግላንድ በጋዛ ለሦስት ቀናት ያደረጉትን ጉብኝት አጠናቀው ከተመለሱ በኋላ ለቢቢሲ ዛሬ እሁድ እንደተናገሩት፣ የከፋ ነገር ሊከሰት እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።-“ነዋሪዎች እየተራብን ነው፤ ልናልቅ ነው” በማለት እርዳታ ሲለምኑ እንዳዩ እና በሰሜን ጋዛ ረሃብ መኖሩን አመልክተዋል። አስራኤል እርዳታ እንዲገባ ስላለፍቀደች በስፍራው 300 ሺህ ሰዎች በፍርስራሾች ውስጥ በችግር ላይ ይገኛሉ ብለዋል።-ባለፈው ሐሙስ ከአንድ መቶ በላይ እርዳታ የሚጠብቁ ሰዎች ከተገደሉ በኋላ፣ አሜሪካ ቅዳሜ ዕለት የመጀመሪያውን የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ከሦስት የጭነት አውሮፕላኖች ላይ በፓራሹት ወደ ጋዛ አውርዳለች።-እስራኤል በበኩሏ ዛሬ እሁድ ጠንካራ የአየር ድብደባዎችን በደቡባዊቷ የጋዛ ከተማ ኻን ዩኒስ ላይ መፈጸሟን ገልጸላች። ስለደረሰው ጉዳት ግን አስካሁን የታወቀ ነገር የለም።-ትናንት ቅዳሜ የተፈናቀሉ ፍልስጤማውያን በተጠለሉበት በደቡባዊ ጋዛ የራፋህ ካምፕ ላይ እስራኤል በፈጸመችው የአየር ጥቃት ቢያንስ 11 ሰዎች መገደላቸውን ሐማስ አስታውቋል።-የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ቴድሮስ አድሃኖም ጥቃቱን “አስደንጋጭ” ያሉት ሲሆን፣ የእስራኤል ሠራዊት ደግሞ ጥቃቱ በእስላማዊ ጂሃድ ታጣቂዎች ላይ “ያነጣጠረ ነው” ብሏል።
|
የፎቶው ባለመብት Reuters-የአሜሪካ የእርዳታ አቅርቦት ከአየር ላይ ሲወርድ-አሜሪካ ለጋዛ የመጀመሪያውን ሰብአዊ እርዳታ ከ30 ሺህ በላይ ምግቦችን በሦስት ወታደራዊ አውሮፕላኖች አማካይነት በፓራሹት ከአየር ላይ ማቅረቧን አስታወቀች።-ከዮርዳኖስ አየር ኃይል ጋር በጥምረት የተካሄደው ይህ ድጋፍ በፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ለጋዛ ይሰጣል ተብሎ ከታወጀው የመጀመሪያው ነው።-ሐሙስ ዕለት ሕዝቡ ከመኪና ላይ እርዳታ ለመቀበል ሲሞክር ቢያንስ 112 ሰዎች ከተገደሉ በኋላ ፕሬዝዳንቱ እርዳታውን ለማጠናከር ቃል ገብተው ነበር።-የአየር ድጋፉ ወደ ጋዛ የተላከው አንድ ከፍተኛ የዩናይትድ ስቴትስ ባለሥልጣን በጋዛ ለስድስት ሳምንታት የሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነት ለማድረግ ዕቅድ መኖሩን ከተናገሩ በኋላ ነው።-የባይደን አስተዳደር ባለሥልጣን ቅዳሜ ዕለት እንደተናገሩት እስራኤል አዲሱን የተኩስ አቁም ስምምነት “ይብዛም ይነስም ተቀብላለች” ብለዋል።-“ሐማስ የተጋላጭ ታጋቾችን ማለትም የታመሙትን፣ የቆሰሉትን፣ አዛውንቶችን እና ሴቶችን ለመልቀቅ ከተስማማ ከዛሬ ጀምሮ በጋዛ ለስድስት ሳምንታት የሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነትተፈጻሚ ይሆናል”ሲሉ ስማቸው ያልተጠቀሰው ባለሥልጣን ተናግረዋል።-ሸምጋዮቹ ዛሬ እሁድ በካይሮ ይሰባሰባሉ። የግብፅ ባለሥልጣናት የሐማስ እና የእስራኤል ልዑካን ለድርድር ይመጣሉ ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል።-አንድ ባለሥልጣን እንደተናገሩት በስምምነቱ ዙሪያ አንዳንድ ቴክኒካዊ ጉዳዮች አሁንም መፍትሄ እንደሚያስፈልጋቸው ተናግረዋል።-ለምሳሌ ምን ያህል የፍልስጤም እስረኞች በሐማስ በተያዙ ታጋቾች ምትክ እስራኤል ትለቃለች የሚለው አንዱ ነው።-ቅዳሜ ዕለት ሲ-130 የተባሉ የማጓጓዣ አውሮፕላኖች በጋዛ የባሕር ዳርቻ ላይ ከ30 ሺህ በላይ ምግቦችን ከአየር ወደ መሬት መጣላቸውን የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል።-“ይህ የአየር እርዳታ አቅርቦት በተሽከርካሪ የመገባውን የእርዳታ ፍሰት ማስፋትን ጨምሮ ወደ ጋዛ ተጨማሪ እርዳታ ለማስገባት የሚደረጉ ቀጣይ ጥረቶች አካል ነው” ሲል አክሏል።-የፎቶው ባለመብት Reuters-ከአንድ መቶ በላይ እርዳታ ጠባቂዎች ከተገደሉበት ጥቃት በርካቶች ቆስለው በህክምና ላይ ናቸው-ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ፣ ግብፅ እና ዮርዳኖስን ጨምሮ ሌሎች አገራት በተመሳሳይ መንገድ እርዳታ ወደ ጋዛ ያደረሱ ሲሆን፣ ይህ ግን ለአሜሪካ የመጀመሪያዋ ነው።-የአሜሪካ አስተዳደር ባለሥልጣናት የሐሙሱ “አሳዛኝ ክስተት፣ ለአስከፊው የሰብአዊ ሁኔታ ምላሽ ለመስጠት የሰብአዊ እርዳታ ወደ ጋዛ እንዲደርስ ማስፋፋት እና ማስቀጠል ያለውን ጠቀሜታ” አጉልቶ አሳይቷል ብለዋል።-የእርዳታ ድርጅቶች ከአየር ላይ ወደ መሬት የእርዳታ አቅርቦትን መጣል በችግር ላይ ላሉት የጋዛ ነዋሪዎች ከሚያስፈልገው ድጋፍ አንጻር በቂ እና አስተማማኝ አይደሉም ብለዋል።-የጋዛ ከተማ ነዋሪው ሜድሃት ታሄር ለሮይተርስ የዜና ወኪል እንደተናገረው እንዲህ ዓይነቱ ዘዴ ለሚጠበቀው እርዳታ በቂ ምላሽ አይደለም።-“ይህ ለትምህርት ቤት በቂ ይሆናል? ይህ ለ10 ሺሀ ሰዎች በቂ ነው? እርዳታን በድንበር በኩል መላክ በፓራሹት ከአየር ከማውረድ የተሻለ ነው” ብሏል።-ፕሬዝዳንት ባይደን አርብ ዕለት በሰጡት መግለጫ ዩናይትድ ስቴትስ “የጋዛ ነዋሪዎች የሚያስፈልጋቸውን እርዳታ እንዲያገኙ ብዙ የጭነት መኪናዎችን እና በርካታ መንገዶችን እንድታመቻች እስራኤልን አጥብቀን እንጠይቃለን” ብለዋል።-የዩናይትድ ስቴትስ ምክትል ፕሬዝዳንት ካማላ ሃሪስ የእስራኤል የጦር ካቢኔ አባል የሆኑትን ቤኒ ጋንትዝን ሰኞ ዕለት ዋሽንግተን ውስጥ እንደሚገናኙ አንድ የዋይት ሐውስ ባለሥልጣንን ጠቅሶ ሮይተርስ ዘግቧል።-በሐሙሱ ክስተት በጋዛ ከተማ ደቡብ ምዕራብ ጫፍ ላይ የእርዳታ መኪኖችን የከበቡ 112 ሰዎች ሲገደሉ ከ760 በላይ ቆስለዋል።-በሰላማዊ ሰዎች ላይ ተኩስ በመክፈቷ የፍልስጤማውያኑ ሕይወታቸው ማለፉን ጠቅሶ ሐማስ ቢከስም ቴል አቪብ ግን የማስጠንቀቂያ ጥይት ሲተኮስ በተፈጠረ መረጋገጥ አደጋው መድረሱን ገልጻለች።-በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብአዊ ጉዳዮች አስተባባሪ (ኦቻ) የጋዛ ንዑስ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ጊዮርጊዮስ ፔትሮፖሎስ እርሳቸው እና ወደ አል-ሺፋ ሆስፒታል የተላከው ቡድን በጥይት የተጎዱ በርካታ ሰዎችን ማግኘታቸውን ለቢቢሲ ተናግረዋል።-ሐማስ በበኩሉ ቅዳሜ ዕለት በደቡባዊ ጋዛ በራፋህ በሚገኝ የመጠለያ ጣቢያ ላይ በእስራኤል በተፈጸመ የቦምብ ጥቃት በትንሹ 11 ሰዎች መገደላቸውን ተናግሯል።-የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ቴድሮስ አድሃኖም ጥቃቱን “አስደንጋጭ” ሲሉ ጠርተውታል። የእስራኤል ጦር በበኩሉ በአካባቢው በሚገኙ እስላማዊ ጂሃድ ታጣቂዎች ላይ “ዒላማውን የጠበቀ ጥቃት” ፈጽሜያለሁ ብሏል።-የተባበሩት መንግሥታት የዓለም የምግብ ፕሮግራም በቅርብ ሳምንታት ውስጥ በጣም ትንሽ እርዳታ ባገኘችው እና 300 ሺህ የሚገመቱ ሰዎች በአነስተኛ ምግብ ወይም ውሃ በሚኖሩባት ሰሜናዊ ጋዛ ውስጥ ረሃብ ሊፈጠር እንደሚችል አስጠንቅቋል።
|
የፎቶው ባለመብት EPA-ቅዳሜ ዕለት ተከታታይ የሪፐብሊካን ፓርቲ ፕሬዝዳንታዊ ዕጩ ውድድርን ያሸነፉት ዶናልድ ትራምፕ፣ የፓርቲው ዕጩ ለመሆን ተቃርበዋል።-ከድላቸው በኋላም ተቀናቃኛቸውን ፕሬዝዳንት ጆ ባይደንን ስደተኞች ከሜክሲኮ ወደ አሜሪካ እንዲገቡ መንገድ ከፍተዋል ሲሉ ከሰዋቸዋል።-የቀድሞው ፕሬዝዳንት ትራምፕ በሚዙሪ፣ ሚቺጋን እና አይዳሆ የውክልና ድምጽ ሰጪዎችን [ካውከስ] ድጋፍ ሙሉ በሙሉ በማግኘት አሸነፈዋል።-የ77 ዓመቱ ትራምፕ በቨርጂኒያ በተካሄደው የድጋፍ ሰልፍ ላይ ለደጋፊዎቻቸው እንደተናገሩት “ለሪፐብሊካን ፓርቲ ዕጩ ሆነው ለመቅረብ እንደሮኬት እየተተኮስኩ ነው” ብለዋል።-በሚቀጥለው ሳምንት ዕጩ መሆናቸውን እንደሚያረጋግጡም ይጠበቃል።-በውድድሩ የቀሩት ብቸኛ ተቀናቃኛቸው የቀድሞዋ የደቡብ ካሮላይና ገዢ ኒኪ ሄሊ እስካሁን አንድም ድል አላስመዘገቡም።-የቢቢሲ የአሜሪካ አጋር የሆነው ሲቢኤስ እንደዘገበው ከሆነ በሚዙሪ እና በአይዳሆ የሚገኙትን ሁሉንም ውክልናዎች እና በሚቺጋን የቀሩትን ሁሉ ትራምፕ እንደሚያሸንፉ ገምቷል።-በእነዚህ ግዛቶች ውስጥ ያሉ አንዳንድ ልዑካን ትራምፕ አሳማኝ በሆነ መንገድ ካሸነፉበት የመጀመሪያ ውድድር በኋላ በዚህ ሳምንት መጀመሪያም የሚፈልጉትን ድል አግኝተዋል።-ልዑካን የሚባሉት በፓርቲያቸው ብሔራዊ ጉባኤ ላይ ክልላቸውን ወይም አካባቢያቸውን የሚወክሉ እና ፕሬዝዳንታዊ ዕጩ ማን እንደሚሆን የሚወስኑ ናቸው።-ትራምፕ እስካሁን 247 የሪፐብሊካን ተወካዮችን ድጋፍ ማግኘታቸውን ሲቢኤስ ዘግቧል። ሄሊ 24 ብቻ ነው ያሳኩት።-ቅዳሜ ዕለት በቨርጂኒያ ዋና ከተማ ሪችመንድ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ትራምፕ በአካቢው የስብሰባ ማዕከል ሲናገሩ ለመስማት ለብዙ ሰዓታት ተሰብስበው ቆይተዋል።-የፎቶው ባለመብት Getty Images-15 ግዛቶች ፕሬዝዳንታዊ ዕጯቸውን በሚመርጡበት በዕለተ ማክሰኞ “ትልቅ ድል” በማስመዝገብ ፕሬዝዳንታዊ ዕጩ ለመሆን ከጫፍ የሚያደርሳቸውን ውጤት እንደሚያስመዘግቡ ቃል ገብተዋል።-“ዛሬ የማይታመኑ ቁጥሮችን አግኝተናል” ሲሉ ለደጋፊዎቻቸው ተናግረዋል።-በቨርጂኒያ እና ቀደም ሲል ደግሞ በሰሜን ካሮላይና በተካሄደው ዝግጅት ላይ ያደረጉት ንግግር በአብዛኛው ያተኮረው በዩናይትድ ስቴትስ-ሜክሲኮ ድንበር ላይ ስላለው የፍልሰተኞች ጉዳይ ነው።-ይህም የደጋፊዎቻቸው ትልቅ ትኩረት መሆኑ ታይቷል። ቅዳሜ ዕለት ሃሳባቸውን ለቢቢሲ የሰጡ ከደርዘን በላይ የሚቆጠሩ የትራምፕ ደጋፊዎች ጉዳዩ ቀዳሚ ስጋታቸው እንደሆነ ተናግረዋል።-እአአ በ2018 ልጇን ሺንን ፌንታኒል የተባለ መድኃኒትን ከመጠን በላይ በመውሰድ ያጣችው ሻሮን ሮበርትስ “ከቁጥጥር ውጭ” የሆነ ድንበር ሌሎች ቤተሰቦችም በተመሳሳይ የሚወዷቸውን እንዲያጡ ያደርጋል የሚል ስጋት ጭሮባታል።-“እኔ ድጋፌ 100 በመቶ ለትራምፕ ነው። ምክንያቱም እሱ እነዚህን ድንበሮች ይዘጋቸዋል” ስትል ተናግራለች።-ባይደን እና ትራምፕ ባለፈው ሳምንት የድንበር አካባቢዎችን ከጎበኙ በኋላ፣ ትራምፕ በቀጥታ ችግሩን ወደ ባይደን በመውሰድ እንደገና ተጠያቂ አድርገዋቸዋል።-ፕሬዝዳንት ባይደን ሆን ብለው ስደተኞችን ከሜክሲኮ ድንበር እንዲሻገሩ እያበረታቱ ነው የሚል የሴራ ሃሳብ በመሰንዘር ትራምፕ ባይደንን ከሰዋል።-“ባይደን እና ግብረ አበሮቹ የአሜሪካን ሥርዓት በማፍረስ፣ የእውነተኛ የአሜሪካ መራጮችን ፍላጎት ውድቅ በማድረግ እና ትውልድን የሚቆጣጠሩበት አዲስ የኃይል መሠረት ማቋቋም ይፈልጋሉ። በሚቀጥለው ምርጫ ድምጽ እንዲሰጡ ለማስመዝገብ እየሞከሩ ነው” ብለዋል ትራምፕ።-ለዚህም ከባይደን የምርጫ ዘመቻ ቡድን ፈጣን ምላሽ ተሰጥቶታል። የቡድኑ ቃል አቀባይ አማር ሙሳ የሁለትዮሽ የኢሚግሬሽን ሕግን በመጥቀስ “ትራምፕ በድጋሚ ለብዙ አሥርተ ዓመታት ፍትሃዊ እና ከባድ የሆነውን የድንበር ደኅንነት ሕግን ገድሏል ከሚለው እውነታ የአሜሪካን ሕዝብ ለማዘናጋት እየሞከረ ነው። ምክንያቱም ይህ ዘመቻውን ይረዳል ብለው ስለሚያምኑ ነው” ብለዋል።-ቅዳሜ ዕለት የተለቀቀው አዲስ የኒውዮርክ ታይምስ እና የሲዬና የሕዝብ አስተያየት እንዳመለከተው 48 በመቶ አሜሪካውያን መራጮች ትራምፕን እንደሚደግፉ ገልጸው፤ ለአሁኑ ፕሬዝዳንት ድጋፋቸውን የሚሰጡት 43 በመቶ ናቸው። ከሁለቱ ወገኖች መካከል በባይደን ላይ ጠንካራ ቅሬታዎችን መኖራቸው ተለይቷል።-በሪችመንድ ሰልፍ ላይ ትራምፕ ወደ ምርጫው ጣቢያ ጠቁመው ደጋፊዎቻቸው ማክሰኞ ዕለት ግልጽ “መልዕክት እንዲያስተላልፉ" አሳስበዋል። ባገኙት ድጋፍም “አከብራችኋለው” ብለዋል።-በምርጫው ግን 45 በመቶ የሚሆኑት መራጮች ሄሊን ሲመርጡ 35 በመቶዎቹ ደግሞ የወቅቱን ፕሬዝዳንት እንደሚደግፉ አሳይተዋል።-“በአጠቃላይ ምርጫ ጆ ባይደንን በሁለት አሃዝ አሸንፌአለሁ። ትራምፕ ግን ከዚህ ውጪ ናቸው” ሲሉ ሄሊ የሕዝብ አስተያየቱ ውጤት ይፋ ተደረጎ ብዙም ሳይቆይ ተናግረዋል።-ትራምፕ በሪችመንድ ባደረጉት ንግግር ሄሊን ላይ አነጠጥረው ሪፐብሊካኖች በኅዳር ላይ እንዲያተኩሩ ጥሪ አቅርበዋል።
|
የፎቶው ባለመብት Getty Images-የጀርመን ወታደሮች-ጀርመን የጦር መኮንኖቿ ለዩክሬን የረጅም ርቀት ሚሳኤሎችን ስለመስጠት እና ጥቃት ስለሚፈጸምባቸው የሩሲያ ዒላማዎች ሲወያዩ የሚሰማበት ስብሰባ የድምጽ ቅጂ በሩሲያ መጠለፉን አመነች።-በቪዲዮ የተካሄደው የወታደራዊ መኮንኖች ስብሰባው የድምጽ ቅጂ በማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮች ላይ ይፋ የተደረገው በሩሲያ መንግሥት የሚተዳደረው የቴሌቪዥን ጣቢያ አርቲ ሥራ አስኪያጅ ነው።-ሩሲያ ከዩክሬን በኃይል የነጠቀችውን ክራይሚያን ከሩሲያ ጋር የሚያገናኘውን ኬርች የተባለው ድልድይ እንዴት በሚሳኤል ሊመታ እንደሚችል የጀመርመን መኮንኖች ሲወያዩ ይሰማል።-የተጠለፈው ድምጽ ይፋ መሆንን ተከትሎ የሩሲያ ፖለቲከኞች “ደመኛ ጠላት” ያሏቸው ጥቃት እያቀዱ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል።-የተጠለፈውን ድምጽ በተመለከተ የጀርመን መራሄ መንግሥት ኦላፍ ሾልዝ ቅዳሜ ዕለት እንደተናገሩት “ክስተቱ ብርቱ ጉዳይ በመሆኑ በጣም በጥንቃቄ፣ በጥልቀት እና በፈጠነ ሁኔታ አሁን ምርመራ እየተደረገበት ነው” ብለዋል።-ዴር ስፒግል የተባለው የጀር መን መጽሔት እንደዘገበው በወታደራዊ መኮንኖቹ መካከል የተደረገው የቪዲዮ ኮንፈረንስ ደኅንነቱ በተጠበቀ የሠራዊቱ የግንኙነት መረብ ሳይሆን ዌብኤክስ በተባለ የበይነ መረብ መድረክ ላይ የተከናወነ ነው።-ባለ 38 ደቂቃው የተጠለፈ የድምጽ ቅጂ ይፋ ያደረገችው የሩሲያ መንግሥት ቴሌቪዥን ጣቢያ ኃላፊ ማርጋሪታ ሲሞንያን፣ ጀርመን ክራይሚያ ላይ ጥቃት ለመፈጸም ዕያቀደች እንደነበር የሚያረጋግጥ ነው ብላለች።-በተጠለፈው የድምጽ ቅጂ ላይ የጦር መኮንኖቹ የዩክሬን ኃይሎች የጀርመን ሥሪት የሆኑትን ታውረስ የተባሉትን ሚሳኤሎች ስለሚጠቀሙበት ሁኔታ እና ስለሚኖረው ተጽእኖ ሲወያዩ ተደምጠዋል።-የፎቶው ባለመብት Getty Images-ታውረስ የተባለው ጀርመን ሠራሽ ሚሳኤል-የጀርመን የመከላከያ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የአየር ኃይል መኮንኖች ምሥጢራዊ ውይይት መጠለፉን ለኤኤፍፒ ዜና ወኪል በማረጋገጥ፣ ነገር ግን ድምጹ ይፋ ከመሆኑ በፊት ማስተካከያ እንደተደረገበት ለማረጋገጥ እንደማይቻል ተናግረዋል።-የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ማሪያ ዛኻሮቫ ጀርመን በጉዳዩ ላይ “በአስቸኳይ” ማብራሪያ እንድትሰጥ ጠይቀዋል።-“ጥያቄውን ላለመመለስ የሚደረጉ ሙከራዎች [በድምጽ ቅጂው ላይ] የተባለውን ነገር እንደማመን ይቆጠራል” በማለት ቃል አቀባይዋ ተናግረዋል።-የሩሲያ የደኅንነት ምክር ቤት ምክትል ኃላፊ እና የፑቲን ቀኝ እጅ የሆኑት ዲሚትሪ ሜድቬዴቭ በቴሌግራም ላይ “የዘመናት ተቀናቃኞቻችን - ጀርመኖች - ደመኛ ጠላቶቻችን ሆነዋል” ሲሉ ጠንከር ያሉ ቃላትን ሰንዝረዋል።-“ጀርመኖች በእናት አገራችን እና በሕዝባችን ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ የሚያስችሉ ዒላማዎችን በጥንቃቄ እና በዝርዝር ግዛታችንን ስለማጥቃት ሲወያዩ እና ሲመርጡ ተመልከቱ” ብለዋል ከፍተኛው ባለሥልጣን።-የሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌይ ላቭሮቭ ቅዳሜ ዕለት እንደተናገሩት ውይይቱ የጀመርመን ጦር ኃይሎችን “መሰሪ ዕቅድን” ያጋለጠ ዋነኛ ማስረጃ ነው ብለዋል።-ዩክሬን ከሩሲያ ጋር ለምታካሂደው ጦርነት 500 ኪሎ ሜትሮች ያህል በመጓዝ ጥቃት ማድረስ የሚችሉትን ታውረስ የተባሉትን ሚሳኤሎች እንድትሰጣት ትፈልጋለች።-የጀርመኑ መራሄ መንግሥት ኦላፍ ሾልዝ ግን ሚሳኤሎቹን መስጠት ግጭቱን ሊያባብሰው ይችላል በሚል ፈቃደኛ ሳይሆኑ አስካሁን ቆይተዋል።-ፈረንሳይ እና ብሪታኒያ ግን 250 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ያሉ ዒላማዎችን መምታት የሚችሉትን ስካልፕ ወይም ስቶርም የተባሉትን ሚሳኤሎችን ለዩክሬን አስታጥቀዋል።-የጀርመን ወግ አጥባቂ ተቃዋሚ ፖለቲከኛ ሮድሪክ ኪስዌተር ተጨማሪ የድምጽ ቅጂዎች ሳይጠለፉ አይቀርም ሲሉ አስጠንቅቀዋል።-“በእርግጠኝነት ሌሎች በርካታ ውይይቶች በሩሲያ ተጠልፈዋል፤ በኋላ ላይ ለሩሲያ በሚጠቅም ሁኔታ ይፋ ሊደረጉ ይችላሉ” በማለት ለአንድ የጀርመን መገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።-ጨምረውም የጦር መኮንኖቹ “ውይይት በዚህ ጊዜ በሩሲያ ሆን ተብሎ ይፋ የተደረገው አንዳች ዓይነት ፍላጎትን ለማሳካት” እንደሆነ የገመቱት ፖለቲከኛው፤ ይህም “ጀርመን ታውረስ ሚሳኤሎችን ለዩክሬን እንዳትሰጥ ለማድረግ ነው” ብለዋል።
|
የፎቶው ባለመብት BBC-ሊዮኒድ ዛኩተንኮ የተባለው መርዝ ሻጭ-በዩናይትድ ኪንግደም ቢያንስ 130 ሰዎች ራሳቸውን አጥፍተውበታል የተባለውን መርዝ የሸጠውን ዩክሬናዊ ቢቢሲ ተከታትሎ ደርሶበታል።-ሊዮኒድ ዛኩተንኮ የተባለው ይህ ግለሰብ ራስ ማጥፋትን የሚያበረታታበት እንዲሁም አገልግሎቱን የሚያስተዋውቅበት ድረ ገጽ አለው።-ግለሰቡ ለቢቢሲም ምሥጢራዊ ዘጋቢ በየሳምንቱ አምስት እሽጎችን ወደ ዩናይትድ ኪንድም (ዩኬ) እንደሚልክ ተናግሯል።-ግለሰቡ ባለፈው ዓመት በቁጥጥር ስር ከዋለው እና በ14 የግድያዎች ወንጀል ከተከሰሰው ካናዳዊ ኬኔት ሎው ጋር ተመሳሳይ ንጥረ ነገር ሲያቀርብ ቆይቷል።-ቢቢሲ ንጥረ ነገሮቹን በተመለከተ ያቀረበለትን ጥያቄ ሊዮኒድ ውድቅ አድርጎታል።-ቢቢሲ ግለሰቡ ወደሚኖርበት ዩክሬን መዲና ኪዬቭ መኖሪያ ቤቱ ድረስ አቅንቶም ገዳይ የሆነውን ኬሚካል ስለመሸጡ ቢጠይቀውም አላመነም። ቢቢሲ የዚህን ንጥረ ነገር (ኬሚካል) ስም አይጠቅስም።-ግለሰቡ ባያምንም ነገር ግን ቢቢሲ በምርመራው ይህንን ገዳይ ንጥረ ነገር ለዓመታት ሲያቀርብ እንደቆየ አረጋግጧል።-ኬሚካሉ በዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ በሕጋዊ መንገድ ሊሸጥ ይችላል፤ ነገር ግን ይህ የሚሆነው አሳማኝ ለሆኑ ግልጋሎቶች ብቻ ለሚጠቀሙ ኩባንያዎች ነው።-ንጥረ ነገሩን ለምን ተግባር እንደሚውል መሠረታዊ ምርመራ እና ፍተሻ ካላደረጉ በስተቀር አቅራቢዎች ለደንበኞች መሸጥ የለባቸውም።-ንጥረ ነገሩ በአነስተኛ መጠን ቢወሰድ እንኳን ለሞት ሊዳርግ ይችላል።-ሊዮኒድ ዛኩተንኮ የተባለው መርዝ ሻጭ-ባለፈው ዓመት ይህ ግለሰብ በለንደን ነዋሪ ለሆኑት መንታ እህትማማቾች ሊንዳ እና ሳራ መርዝ ከሸጠላቸው በኋላ ሕይወታቸው አልፏል።-የሁለቱ እህትማማቾች ቤተሰቦችም ስለዚህ ግለሰብ ሲያወሩ “በጭካኔ የተሞላ እና ክፉ ሰው ነው” ሲሉ ገልጸውታል።-ከእህትማማቾቹ አንዷ ሊንዳ ስለ መርዝ ሻጩ መረጃ ያገኘችው እውቅና ባለው ራስን የማጥፋት የውይይት መድረክ ላይ እንደሆነ እህቷ ሄለን ኪት ትናገራለች። እህቷ በጥቂት ፓውንድ የሞት ጽዋዋን እንደቀመሰች ተናግራለች።-ራሷን ስላጠፋችው የ54 ዓመት እህቷ ስትናገር “አሳቢ፣ አስተዋይ እና ጎበዝ ነበረች” ስትል ታስታውሳታለች።-እህቶቿም ሆነ ሌሎች በርካታ ራሳቸውን ያጠፉ ሰዎች ኬሚካሉን እንዳያገኙ ባለሥልጣናት የወሰዱት እርምጃ አለመኖሩን በመተቸት “ብሔራዊ ቅሌት” ነው ስትል ሄለን ውቀሳለች።-ግለሰቡ የሚሸጠው ኬሚካል እነ ሊንዳ በሚጠቀሙበት የበይነ መረብ መድረክ ላይ በግልጽ ውይይት የሚደረግበት ሲሆን፣ አባላቶቹም እንዴት እንደሚገዙ እና እንደሚጠቀሙበት ምክር ይለዋወጣሉ።-በለንደን ኩዊን ሜሪ ዩኒቨርስቲ ሳይንቲስት የሆኑት ፕሮፌሰር አምሪታ አህሉዋሊያ በበኩላቸው ኬሚካሉ በዩናይትድ ኪንግደም ከአውሮፓውያኑ 2019 ጀምሮ ከተከሰቱት 130 ራስን ማጥፋቶች ጋር የተያያዘ ሊሆን እንደሚችል ገልጸዋል።-ፕሮፌሰሯ በፖሊስ እና በላብራቶሪዎች የተላኩላቸውን ደም እና ሌሎች ናሙናዎችን በመመርመራቸው ነው እንዲህ ዓይነት ድምዳሜ ላይ የደረሱት።-ከመረመሯቸው 187 ናሙናዎች ውስጥ 71 በመቶው ገዳይ የሆነ ኬሚካል መኖሩን የሚያሳይ ሲሆን፣ ይህን ቢያንስ 133 ሰዎች በዚህ ንጥረ ነገር እንደሞቱ የሚያሳይ ነው ተብሏል።-“አንድ ነገር ሊደረግ ይገባዋል” ሲሉም ፕሮፌሰሯ ያሳስባሉ።-“ለምን ጥቅም ላይ እንደሚውል ሙሉ ምርመራ ሊደረግ ይገባል። አጠቃቀሙ ለታለመለት ዓላማ ይውል ዘንድም ቁጥጥር መደረግ አለበት” ይላሉ።-የፎቶው ባለመብት Facebook-ምግብ አብሳይ የሆነው ካናዳዊው ኬኔት ሎው ባለፈው ዓመት በቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ በ14 የግድያ ወንጀሎች እና ራስን ማጥፋትን በማገዝ ክስ ቀርቦበታል።-ግለሰቡ ኬሚካሉን በዓለም ዙሪያ ባሉ 40 አገራት ሸጧል። ከ1 ሺህ 200 በላይ ሽያጮችን አካሂዷል የተባለው ይህ ግለሰብ፣ በዩናይትድ ኪንግደም ውስጥ ራሳቸውን ባጠፉ 93 ሰዎች ሞት ውስጥም እጁ አለበት ተብሏል።-ቢቢሲ ባደረገውም ምርመራ ሊዮኒድ ዛኩተንኮ የተባለው ግለሰብ ከአውሮፓውያኑ 2020 ጀምሮ ተመሳሳይ ኬሚካል እየሸጠ መሆኑን አረጋግጧል።-በተጨማሪም በበይነ መረብ ላይ ራስን የማጥፋት መመሪያዎች ውስጥ የተካተቱ ሦስት የተለያዩ በህክምና ባለሙያ የሚታዘዙ መድኃኒቶችንም ያቀርባል።-ካናዳዊው ኬኔት ሎው ራስን ማጥፋት በሚያስተዋውቅበት የበይነ መረብ መድረክ ላይ ይህም ግለሰብ ለአጭር ጊዜ አገልግሎቱን ያስተዋውቅ ነበር።-ከዚያን ጊዜም ጀምሮ የመድረኩ ተጠቃሚዎች የእሱን አድራሻ በመልዕክቶች ይቀያየሩ ነበር።-ቢቢሲ ሊዮኒድ ዛኩተንኮንን ያገኘው በዩክሬን መዲና ኪዬቭ በሶቪዬት ኅብረት ዘመን በተሠራ ህንጻ ውስጥ በሚገኝ አነስተኛ የጋራ መኖሪያ ቤት ነው።-በርካታ እሽጎችንም ለመላክ በአካባቢው ፖስታ ቤት እየተዘጋጀ ባለበት ወቅት ነው ቢቢሲ የተጋፈጠው።-ራሳቸውን ለማጥፋት ለሚፈልጉ ሰዎች ለምን መርዛማ ኬሚካል እንደሚልክም ተጠየቀ።-እጁን የቢቢሲ ካሜራን ለመሸፈን ከመሞከሩ በፊት “ይህ ውሸት ነው” በማለት ለማስተባበል ሞክሯል።-ቢቢሲም ዛኩተንኮንን በዚያች ቀን እሽግ እንዲልክለት መጠየቁን ተከትሎ ቢያንስ አንዱ እሽግ ኬሚካል እንደያዘ ለማረጋገጥ ችሏል።-ቤተሰቦቻቸውን በዚህ ኬሚካል ላጡ ሰዎች ምን ምላሽ አለህ? ተብሎ በቢቢሲ ሲጠየቅም “ስለምን እንደምታወሩ አልገባኝም” ሲል መልሷል።-ራሳቸውን ያጠፉት ቶም እና ጆ ኒሂል-ዴቪድ ፓርፌት የተባለ ግለሰብ የ22 ዓመት ልጁ ቶም ተመሳሳይ ኬሚካል ከኬኔት ሎው ገዝቶ ከሦስት ዓመታት በፊት ሕይወቱን አጥፍቷል።-ፓርፌት በአሁኑ ወቅት ከራስ ማጥፋት ጋር የተያያዙ የውይይት መድረኮችን ለማዘጋት እና እንደ ዛኩቴንኮ ያሉ መርዝ ሻጮችን ለማስቆምም ዘመቻ እያደረገ ይገኛል።-ሌላኛው የ23 ዓመት ጆ ኒሂል የተባለ ወጣት ሞት መንስዔን የመረመረው ባለሙያ ማስጠንቀቂያ ለብሪታንያ ባለሥልጣናት መድረሱን ተከትሎ ስለ ኬሚካሉም ሆነ በበይነ መረብ ላይ ስለሚፈጸመው የመርዝ ንግድ ከአውሮፓውያኑ መስከረም 2020 ጀምሮ እንደሚያውቁ ይፋ ሆኗል።-መርማሪው ለፖሊስ፣ ለአስከሬን መርማሪ ዋና ኃላፊ እንዲሁም ለኬሚካል አቅራቢዎች ስለ አደገኛው ንጥረ ነገር ንግድ አስጠንቅቆ ነበር።-ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በመላው ዩኬ የሚገኙ የአስከሬን መርማሪዎች ስለ ኬሚካሉ እና ራስን ስለ ማጥፋት እየተደረጉ ስላሉ የበይነ መረብ የውይይት መድረኮችን በተመለከተ አምስት ጊዜ ያህል ለተለያዩ የመንግሥት ተቋማት ማስጠንቀቂያ ጽፈዋል።-ዴቪድ ፓርፌትም ባለሥልጣናቱ እሽጉን ያስቆሙት እንደሆነ ለማየት እና ሥርዓቱንም ለመፈተሽ ከዛኩተንኮ መርዛማውን ኬሚካል ገዝቷል።-እሽጉን ካዘዘ ከጥቂት ቀናት በኋላ ፖሊስ ደኅንነቱን ለመጠበቅ ጎበኝቶት ነበር። ነገር ግን ኬሚካሉ በሳምንታት ውስጥ የደረሰው ሲሆን፣ ፖሊስም እንደገና አልጎበኘውም።-“ምን ያህል ሰዎች እንደሞቱ እያወቅን አሁንም እንዲህ ዓይነት ነገር ይከናወናል ብሎ ማመን ከባድ ነው” ሲልም ተናግሯል።-ኬኔት ሎው በካናዳ ከታሰረ በኋላ በዩኬ ውስጥ ንጥረ ነገሩን በሚገዙ ሰዎች ላይ ተመሳሳይ የደኅንነት ማረጋገጫ ጉብኝቶች ተካሂደዋል።-የዩኬ የብሔራዊ ወንጀል ኤጀንሲ እንዳረጋገጠው ኬሚካሉን ከኬኔት ሎው ገዝተው ፖሊስ የደኅንነት ጥየቃ ካደረገ በኋላ የሞቱ ሰዎች መኖራቸውን አረጋግጧል።-“እንዲህ አይነት ጉዳዮች የሚስተናገዱት በፖሊስ አባላት አማካይነት ፖሊሲያቸውን እና ብሔራዊ መመሪያዎችን ተከትሎ ነው” ሲሉ ቃል አቀባዩ ተናግረዋል።-የሚወዷቸውን ሰዎች በኬሚካሉ የተነጠቁት ዴቪድ ፓርፌት እና ሄለን በእነዚህ የራስ ማጥፋት የውይይት መድረኮች ላይ ጠንከር ያለ እርምጃ እንዲወሰድ እየጠየቁ ይገኛሉ።-የዩኬ መንግሥት በበኩሉ ባለፈው ዓመት የጸደቀው አዲሱ የበይነ መረብ ደኅንነት ሕግ እንደነዚህ ዓይነት የውይይት መድረኮችን በመገደብ የራሱን አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ተናግሯል።
|
ባለፈው ሲቲ ከዩናይትድ ሲገናኙ ውሃ ሰማያዊ ለባሾቹ በልበ-ሙሉነት ነበር ግጥሚያውን የረቱት። እሑድ ኢቲሃድ የሚካሄደውን ፍልሚያስ ማን በአሸናፊነት ያጠናቅቃል?-የቢቢሲ ስፖርት ተንታኝ ክሪስ ሱተን “ማንቸስተር ዩናይትድ ለጥቂት ጊዜም ቢሆን ድል ሲቀናው ነበር፤ ነገር ግን ሲቲ ያለበት ደረጃ ላይ አይደሉም” ይላል።-የዘንድሮውን ፕሪሚዬር ሊግ ጨዋታዎች እየገመተ ያለው ሱተን፣ የማንቸስተር ደርቢን ጨምሮ ከቅዳሜ እስከ ሰኞ ያሉ ጨዋታዎች ግምቱን ጀባ ብሏል።-ቼልሲ ባለፈው ቅዳሜ በካራባዎ ዋንጫ ፍፃሜ በሊቨርፑል ተረትቷል። ይህ ጨዋታውም ቀላል ይሆንላቸዋል ብዬ አልገምትም።-ብሬንትፈርድ በበኩሉ እንደ አምናው ያለ አቋም እያሳየን አይደለም። ካለፉት ስድስት የሊጉ ጨዋታዎች በአምስቱ ተረትቷል።-እና ይህን ጨዋታ ምን ብዬ ብገምት ይሻለኛል? ለብሬንትፈርድ ይህን ጨዋታ ማሸነፍ እጅግ አስፈላጊው ነው። ምክንያት ከወራጅ ቀጣና በጥቂት ነጥብ ነው ርቀው የሚገኙት።-የቼልሲው አሠልጣኝ ማውሪሲዮ ፓቼቲኖ በክለቡ መቀጠል ከፈለጉ የያዝነውን የውድድር ዘመን ጠንካራ ሆነው ማጠናቀቅ አለባቸው።-ይህ ጨዋታ ከአቻ የተለየ ውጤት ይኖረዋል ብዬ አላስብም።-ግምት፡ 1 - 1-ኤቨርተን ከወራት በፊት የተጣለበት የ10 ነጥብ ቅጣት ተቀንሶ 6 ሆኖለታል። ይህ ደግሞ ለዚህ ጨዋታ መነቃቃት ይሆነዋል።-ኤቨርተኖች ድል ካጣጣሙ ቆይተዋል። ቅጣቱ መስተካከሉ ይህን ጨዋታ ለማሸነፍ ቆርጠው እንዲገቡ ያደርጋቸዋል ብዬ አስባለሁ።-ከብራይተን ጋር የነበራቸውን ጨዋታ ማሸነፍ ይገባቸው ነበር።-ብራዚላዊው ሉካስ ፓኩዌታ ከጉዳት መመለሱ ለዌስት ሀም መልካም ዜና ነው።-ነገር ግን እኔ ኤቨርተን በሜዳው አደገኛ ቡድን ነው ብዬ ነው የማስበው። ለዚህ ነው ዌስት ሀም ያለምንም ነጥብ ይመለሳል የምለው።-ግምት፡ 1 - 0-ብራይተን በዎልቭስ ተሸንሮ ከኤፍ ኤ ዋንጫ ውጪ መሆኑ አስደንቆኛል። ነገር ግን ዘንድሮ ወጥ አቋም አለማሳየቱ መርሳት የለብንም።-በዚያ ላይ ካሮ ሚቶማ መጎዳቱ ሌላ ደንቃራ ይሆንባቸዋል። ሁለት ጨዋታ በተከታታይ ማሸነፍ ብዙም ያልሆነላቸው ብራይተኖች ይህ ጨዋታ እንደሚከብዳቸው እገምታለሁ።-ለዚህ ነው የዚህ ጨዋታ ውጤት ወደ ፉልሀም ያደላል የምለው። ፉልሀም ባለፈው ሳምንት ወደ ኦልድ ትራፈርድ ተጉዞ የሚገባውን 3 ነጥብ ይዞ ተመልሷል።-ግምት፡ 2 - 1-ምንም እንኳ ማቴውስ ኩንሀ ቢጎዳባበትም ዎልቭስ ከጨዋታ ጨዋታ እየተሻሻለ መምጣቱን መመልከት ችያለሁ።-ኒውካስልም እንደ ዎልቭስ ለኤፍ ኤ ዋንጫ ሩብ ፍፃሜ ደርሷል።-ሁሌም ኒውካስል በሜዳው ይረታል ብዬ ብገምትም በውጤቱ እያፈርኩ ነው። በሜዳው ያደረጋቸውን ያለፉትን አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም።-አሠልጣኙ ኤዲ ሃው መንበራቸው ላይ መቆየት ከፈለገ ይህን መቀየር አለበት። ምንም እንኳ የመባረር ስጋት ባይኖርበትም የውድድር ዘመኑን በመልካም ውጤት ማጠንቀቅ ይገባዋል።-ዎልቭስ ለዚህ ጨዋታ ያንሳል ብዬ ባልገምት ውጤት ወደ ኒውካስል የምታደላ ይመስለኛል።-ግምት፡ 2 - 1-የሊቨርፑል ታዳጊ ተጫዋቾች ከቼልሲ ጋር በነበረው ፍፃሜ ባሳዩት ብቃት ውዳሴ እየደረሳቸው ነው። በኤፍ ኤ ዋንጫም ሳውዝአምፕተንን ረትተዋል።-ሳምንቱ ለየርገን ክሎፕ ድንቅ ነው። የመጀመሪያውን ዋንጫ ከማግኘታቸው ባለፈ ሌላ ዋንጫ የማግኘት ተስፋቸውም ለምልሟል።-ሞሐመድ ሳላህ፣ ዶሞኒክ ስፖስዝላይ እና ዋታሩ ኤንዶ ወደ መልካም አቋማቸው ቢመለሱ ደግሞ ሊቨርፑልን ማቆም ከባድ ይሆናል ብዬ አስባለሁ።-ፎረስት ከመውረድ አደጋ ነፃ ቢሆኑም፣ ነጥብ ሊቀንስባቸው እንደሚችል እየተወራ ነው። ይህ ደግሞ ስጋት ላይ የሚጥል ነው።-በያዝነው ዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ድል የቀናው የኑኖ ኤስፔሪቶ ሳንቶ ቡድን ቅዳሜ ዕለት ድል ይቀናዋል የሚል ግምት የለኝም።-ግምት፡ 0 - 2-ቶተንሀም አሁንም በሚቀጥለው ዓመት በቻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ የሚያስፈልገውን ነጥብ እያሳደደ ነው።-አሠልጣኝ አንጅ ፖስቴኮግሉ በዚህ ፍጥነት እስከ አራተኛ ለመውጣት ይፋለማሉ ብዬ አልገመትኩም ነበር። ነገር ግን ቡድኑ በያዝነው የውድድር ዘመን ምርጥ ብቃቱን እያሳየን ነው።-አዲሱ የክሪስታል ፓላስ አሠልጣኝ ኦሊቨር ግላስነር፤ በርንሊን በመርታት ሥራውን በሦስት ነጥብ ጀምሯል። ነገር ግን ይህ ጨዋታ ይከብደዋል።-ምንም እንኳ ስፐርስ ባለፉት ሳምንታት ነጥብ ሲጥል ብንመለከትም ከፓላስ የተሻሉ ተጫዋቾችን ይዟል።-ግምት፡ 3 - 0-ሉተን ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ባሳየው ብቃት ውዳሴ ተችሮታል። ሉተን በፕሪሚዬር ሊጉ የሚቆይ ከሆነ አሠልጣኝ ሮብ ኤድዋርድስ የውድድር ዓመቱ ምርጥ አሠልጣኝ መባል አለበት ብዬ ከዚህ ቀደም ተናግሪያለሁ።-ነገር ግን ኤቨርተን የተቀነሰበትን ነጥብ መልሶ ማግኘቱ እና ሉተን ያለፉትን ተከታታይ ጨዋታዎች መሸነፉ ስጋት ላይ የሚጥል ነው።-የአስተን ቪላ ተጫዋቾች ወደ ተቃራኒ ቡድን ግብ አቅጣጫ ሲያመሩ ያስፈራሉ። ነገር ግን ይህ የራሱ ጉዳት አለው።-ሉተን ጎል ያስቆጥራል ብዬ ባምንም ቪላ ነጥቡን ያገኛል ነው ግምቴ።-ግምት፡ 1 - 3-በርንሊ ይህን ጨዋታ ማሸነፍ አለበት ማለት ከጀመርኩ ሳምንታት ተቆጥረዋል። ከወራጅ ቀጣናው ለመውጣት 11 ነጥብ ያስፈልገዋል። የቀረው ደግሞ 12 ጨዋታ ነው። በውድድር ዘመኑ ሦስት ጊዜ ብቻ ነው ድል የቀናቸው።-ከኋላ ኳስ መሥርተው ለመጫወት የሚያደርጉት መኩራ ኪሳራ እያመጣባቸው ነው።-ቦርንመዝም እንዲሁ ምርጥ አቋም ላይ አይደሉም። የዶሚኒክ ሶላንኬ መጎዳት ደግሞ ሌላ ደንቃራ ነው። ቢሆንም በበርንሊ ይረታሉ ብዬ አልገምትም።-ግምት፡ 1 - 1-ዩናይትድ በኤፍ ኤ ዋንጫ ከኖቲንግሀም ሲጫወት ያሳየው ብቃት ሲቲን የሚያስጨንቅ አይደለም። ምንም እንኳ ያገኙት ድል ለአሠልጣኝ ኤሪክ ቴን ሀግ አስፈላጊ ቢሆንም፣ የራስመስ ሆይለንድ መጎዳት ሌላ ራስ ምታት ሆኖባቸዋል።-ማርከስ ራሽፈርድ የቀደመ አቋሙን ካሳየን ቆይቷል። ነገር ግን ኤሪክ ቴን ሀግ ሲቲን ለመርታት የሚሆን የተለየ ታክቲክ ሊጠቀሙ ይችላሉ።-ሲቲ ይህን ጨዋታ እንደሚረታ ምንም ጥርጥር የለኝም። ጥያቄው በምን ያህል የጎል ልዩነት የሚለው ነው።-ግምት፡ 6 - 1-አርሰናል በፕሪሚዬር ሊጉ የሚያደርገውን ጨዋታ በጎል በመንበሽበሽ እየረታ ይገኛል። ልክ እንደ ሊቨርፑል እና ማንቸስተር ሲቲ ነጥብ መጣል የሚባል ነገር አአምሯቸው ላይ ሊመጣ አይገባም።-ባለፈው ሼፊልድ ወደ ኤሜሬትስ ስታድየም አቅንቶ 5 ለምንም ተረትቶ ተመልሷል። በወቅቱ ኤዲ ኒኬታህ ሦስት ጎል አስቆጥሮ ነበር።-ሼፊልድ ከአርሰናል ጋር አንገት ለአንገት ይተናነቃል ብዬ አላስብም። ባይሆን አርሰናል ጎል እንዳያገባ ለመከላከል ቆርጠው የሚገቡ ይመስለኛል።-መድፈኞቹ ቀድመው ጎል የሚያስቆጥሩ ከሆነ ለሼፊልድ አደጋ ነው የሚሆነው።-ግምት፡ 0 - 3
|
የፎቶው ባለመብት ethiopian/fb-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ እስያ አገራት ለሚያደርጋቸው በረራዎች ይጠቀምበት በነበረው የሶማሊያ የአየር ክልል በኩል መብረር ማቆሙን ዋና ሥራ አስፈጻሚው ለቢቢሲ ገለጹ።-አየር መንገዱ እዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ከሶማሊያ የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች “አስተማማኝ የአየር ትራፊክ አገልግሎት” ባለማግኘቱ እንደሆነ ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ መስፍን ጣሰው ለቢቢሲ አማርኛ አርብ ከሰዓት በኋላ የተናገሩ ቢሆንም፣ ድርጅቱ ምሽት ላይ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ ባሰራጨው መግለጫ የአቶ መስፍንን አስተያየት አስተባብሏል።-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ባወጣው መግለጫ “ሪፖርቱ ትክክል ያልሆነ እና የተዛባ ነው” ያለ ሲሆን፣ ዋና ሥራ አስፈጻሚው “የሶማሊያ አየር ክልል ደኅንነቱ አስተማማኝ አይደለም” አለማለታቸውን በመግለጽ፣ ቢቢሲ ማስተካከያ እንዲያደርግ ጠይቋል።-ቢቢሲ ዘገባውን ከዋና ሥራ አስፈጻሚው ጋር የተደረገን ቃለ ምልልስ መሠረት አድርጎ የሠራ ሲሆን፣ እንደተባለው አቶ መስፍን ከተናገሩት ውጪ የተካተተ ወይም የተዛባ አስተያየት እንደሌለ ያረጋግጣል።-ለዚህም ከዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ መስፍን ጣሰው ጋር የተደረገውን ቃለ ምልልስ እዚህ አያይዟል።-ኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ እስያ ለሚደርጋቸው በረራዎች “ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ” ይጠቀምበት በነበረው የሶማሊያ አየር ክልል መብረር ያቆመው፤ የአየር መንገዱ አውሮፕላን ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ የካቲት 16/2016 ዓ.ም. በአገሪቱ የአየር ክልል ውስጥ ካጋጠመው ክስተት ጋር በተያያዘ መሆኑን አቶ መስፍን አስታውሰዋል።-ኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን፤ “በዓለም አቀፍ አሠራር መሠረት እንደዚህ ዓይነት ነገር ሲያጋጥም ለሚመለከታቸው የሲቪል አቪየሽን ባለሥልጣናት ሪፖርት እናደርጋለን። [የቅዳሜውን ክስተት በተመለከተም] ለሶማሊያ እና ለኢትዮጵያ የሲቪል አቪየሽን ባለሥልጣናት ሪፖርት ተደርጓል” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል። ይሁንና እስካሁን ድረስ በጉዳዩ ላይ የተሰጠ ምላሽ አለመኖሩን አክለዋል።-የቅዳሜ ዕለቱ ክስተት የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሶማሊያ አየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች የሚሰጠውን አገልግሎት “አስተማማኝ ሆኖ እንዳያገኘው” ማድረጉን አቶ መስፍን ገልጸዋል።-በዚህም ምክንያት ይህ ክስተት ካጋጠመበት ማግስት እሁድ የካቲት 17/2016 ዓ.ም. አንስቶ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሶማሊያን አየር ክልል መጠቀም ለማቆም መወሰኑን አስታውቀዋል።-ቢቢሲ ፍላይትራዳር24 እና ፍላትአዌር የተባሉ ዓለም አቀፍ የበረራ መስመሮች መከታተያ ድረ ገጾች ላይ ባደረገው ማጣራት ባለፈው ሳምንት በሶማሊያ የአየር ክልል ውስጥ በኢትዮጵያ እና በኳታር አውሮፕላኖች መካከል ያጋጠመውን ክስተት ተከትሎ የበረራ መስመር ለውጥ እንዳለ ለመረዳት ችሏል።-በዚህም አየር መንገዱ ከዚህ ቀደም ወደ ባሕረ ሰላጤው አገራት የሚያደርጋቸው በረራዎች በሶማሊያ የአየር ክልል በኩል የነበሩ ሲሆን፣ ከዚህ ሳምንት መጀመሪያ አንስቶ ግን ጉዞዎቹ በጂቡቲ በኩል እንደሆኑ ድረገጾቹ ያመለክታሉ።-የበረራ መስመር ለውጥ ያደረገው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ብቻ ሳይሆን የኳታር አየር መንገድም ቀደም ሲል ከኡጋንዳ ኢንተቤ ወደ ዶሃ፣ በኢትዮጵያ እና ሶማሊያ በኩል ጉዞ ሲያደርግ የነበረ ሲሆን፣ ባለፉት ቀናት ግን በኢትዮጵያ እና በኤርትራ በኩል እየበረረ መሆኑን ለመረዳት ተችሏል።-አቶ መስፍን፤ ከክስተቱ በኋላ ካለው ቀን አንስቶ “አማራጭ ለመጠቀም ወስነናል። ለዚህም ዋናው ምክንያት [የቅዳሜ ዕለቱ ክስተት] ነው። እዚያ በነበረው ሁኔታ፤ የአየር ክልሉ አስተማማኝ የአየር ትራፊክ አገልግሎት ስላላገኘንበት ለደኅንነት ስንል አማራጭ መንገዶች እየተጠቀምን ነው” ሲሉ የአየር መንገዱን ውሳኔ አብራርተዋል።-አየር መንገዱ ወደ እስያ ለሚያደርጋቸው በረራዎች የሚጠቀመው የሶማሊያን የአየር ክልል እንደነበር ያስታወሱት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ በአሁኑ ሰዓት እነዚህ በራረዎች የሚደረጉት በጂቡቲ አየር ክልል በኩል መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የጂቡቲን የአየር ክልል እየተጠቀመ ያለው “ተጨማሪ ወጪ በማያመጣ መልኩ” እንደሆነም አክለዋል።-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሌለሎች አገራት ለሚደረጉ በራረዎች የሶማሊያን አየር ክልል መጠቀም ቢያቆምም ወደ ሞቃዲሾ እና ወደ የሶማሊላንድ ዋና ከተማ ሀርጌሳ ከተማዎች የሚያደርጋቸውን በራረዎች “ያለ ችግር” መቀጠሉን አብራርተዋል።-ባለፈው ሳምንት ከአዲስ አበባ ወደ ዱባይ ሲጓዝ የነበረው የአየር መንገዱ የበረራ ቁጥር 602 አውሮፕላን፤ የኳታር ኤር ዌይስ አውሮፕላን እየቀረበው እንደሆነ መረጃ መቀበሉን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለቢቢሲ ገልጾ ነበር።-በሶማሊያ የአየር ክልል ውስጥ እየበረረ የነበረው የኳታሩ አውሮፕላን የነበረበትን ከፍታ በመጨመር ወደ ኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን የቀረበው ከሞቃዲሾ የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች በተሰጠው ፈቃድ መሆኑን አየር መንገዱ ጠቅሶ ነበር።-የኢትዮጵያ አየር መንገድ በኢሜል ለቢቢሲ በሰጠው ምላሽ በሁለቱ አውሮፕላኖች መካከል የነበረው ርቀት 23 ኪሎ ሜትር እንደሆነ ገልጿል።-ይህንን ክስተት አስመልክቶ መግለጫ ያወጣው የሶማሊላንድ አቪየሽን እና ኤርፖርቶች ባለሥልጣን የኢትዮጵያ እና የኳታር አውሮፕላኖች “አደገኛ በሆነ ርቀት” ላይ እንደነበሩ እና “ሊጋጩ ተቃርበው” እንደነበር መግለጹ ይታወሳል። ይህም የሆነው በሞቃዲሾ የሚገኙት የሶማሊያ የአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች በሰጡት “የተሳሳተ መረጃ” እንደሆነ በመግለጽም ከስሶ ነበር።-ይሁንና የሶማሊያ አቪዬሽን ባለሥልጣን በበኩሉ በሁለቱ አውሮፕላን መካከል የነበረው ርቀት አደጋን የሚያስከትል ስጋት ላይ አልነበረም ሲል ጉዳዩን አስተባብሏል።
|
የፎቶው ባለመብት Getty Images-ማር በውስጡ የያዘው ከፍተኛ የካሎሪ መጠን በደም ውስጥ ያለውን የስኳር መጠን ስለሚጨምር የምንወስደው መጠን ትንሽ መሆን እንዳለበት ይመከራል።-ንቦች ከአበባ የሚገኝን ጣፋጭ ፈሳሽ [ኔክታር] ቀስመው የሚያዘጋጁት ማር ኢትዮጵያን ጨምሮ በበርካታ አገራት እንደ መድኃኒት ይቆጠራል።-ከቤት ውስጥ መጥፋት ከሌለባቸው ምግቦች ውስጥም ሲጠቀስ ይሰማል።-ጥንታውያን ግሪኮች ማርን “የፈጣሪ ምግብ” ሲሉ ነው የሚገልጹት። በቻይና ደግሞ መድኃኒት ተደርጎ ነው የሚታሰበው።-በአብዛኛው ወርቃማ ቀለም ያለው ይህ ጣፋጭ የተፈጥሮ ፈሳሽ ለምግብነት እና ለመድኃኒትነት የሚጠቅሙ ንጥረ ነገሮችን በውስጡ ይዟል።-እንደየ አካባቢው እና ንቦች እንደሚቀስሙት የአበባ ዓይነትም ቀለሙ የተለያየ ይሆናል።-ለመሆኑ ከስኳር የሚጣፍጠው የተፈጥሮ ማር ብቸኛው የስኳር አማራጭ ነው? ለሁሉም ሰውስ በእኩል ይጠቅማል? ሕጻናትን ለመመገብስ የዕድሜ ገደብ አለው? የምንወስደው መጠንስ ምን ያህል መሆን አለበት?-ለእነዚህ የበርካታ ሰዎች የዘውትር ጥያቄዎች የሥነ ምግብ ባለሙያ የሆኑት ጆ ልዊን ምላሽ አላቸው።-ንጹህ የተፈጥሮ ማር [ያልተቀነባበረ] በውስጡ አሚኖ አሲድ፣ አንታይኦክሲደንት፣ ቫይታሚኖች፣ ሚኒራሎች እና ስኳር ይዟል።-ማር ከፍተኛ የፍሩክቶስ ይዘት ያለው በመሆኑም ከስኳር በላይ ጣፋጭ ነው። ነገር ግን ግላይቼሚክ ኢንዴክስ (ጂአይ) ባወጣው ደረጃ መሠረት ማር ያለው ኃይል ሰጪ ንጥረ ነገር (ካርቦሃይድሬት) መካከለኛ ነው።-ጂአይ እያንዳንዱ የምንመገበው ምግብ ተፈጭቶ በምን ያህል ፍጥነት በደማችን ውስጥ የሚገኝ የስኳር (ግሉኮስ) መጠን ላይ ተፅእኖ እንደሚያደርስ የሚያሳይ የመለኪያ ሥርዓት ነው።-አንድ የሾርባ ማንኪያ (20 ግራም) ማር 58 ኪሎ ካሎሪ፣ 15.3 ግራም ካርቦሃይድሬት፣ 15.4 ግራም ስኳር፣ 0.1 ግራም ፕሮቲን እና 0 ግራም ስብን ይይዛል።-የፎቶው ባለመብት Getty Images-የማር የጤና ጥቅሞች በሚቀነባበርበት መንገድ እና ንቦች በሚቀስሙት የአበባ ጥራት ላይ ይወሰናል።-ንጹህ የተፈጥሮ ማር በማንኛውም መንገድ ያልቀለጠ፣ ያልተቀነባበረ፣ ያልተጣራ፣ ያልተጠለለ ወይም ሌላ ግብዓት ያልተጨመረበት ነው። እንዲህ ዓይነቱ ማር በማቀነባበር ሒደት ያልተወገዱ እና ለጤና የሚጠቅሙ ንጥረ ነገሮችን የያዘ ነው።-በሚይዛቸው ንጥረ ነገሮችም ማር ለበርካታ ዓመታት ረቂቅ ተህዋስያንን ለማጥፋት ጥቅም ላይ ሲውል ቆይቷል።-መጠነኛ የሆነ ቆዳ ላይ የሚያጋጥሙ ቁስሎችን፣ የብግነትን ( አልሰር) እና የቃጠሎ ጉዳቶችን የማገገም ሒደትን ማር ያፋጥናል ተብሎም ይታመናል።-ማር በውስጡ ግሉኮስ እና ፍሩክቶስ የተባሉ የስኳር ዓይነቶችን የያዘ ሲሆን፣ እነዚህ ስኳሮች ደግሞ ፈሳሽን የመምጠጥ ባህሪ አላቸው።-በመሆኑም በውስጡ እነዚህን የስኳር ዓይነቶች የያዘው ማር በቁስል ላይ ያለን ፈሳሽ የመምጠጥ እና የማድረቅ አቅም አለው። ይህም በተጎዳው አካል ላይ ያለውን የባክቴሪያ እና የፈንገስ እድገትን ይገታል።-ጠቆር የሚለው የማር ዓይነት ደግሞ ‘ፍላቮኖይድ’ በተባለ ኬሚካላዊ ውህድ የበለጸገ ነው።-ፍላቮኖይድ ፀረ ባክቴሪያ፣ ፀረ ቫይረስ፣ እንዲሁም አለርጂ እና የሰውነት መቆጣትን የሚከላከል ንጥረ ነገር አለው። ባለው የፍላቮኖይድ ንጥረ ነገር ምክንያትም በርካቶች ስኳርን እና አንታይኦክሲደንትን ለማግኘት ማርን እንደ ጤናማ የምግብ አማራጭ ይወስዱታል።-ሆኖም ግን አወሳሰዱ ላይ ጥንቃቄን ሲያደርጉ አይስተዋልም።-የሥነ ምግብ ባለሙያ የሆኑት ጆ ልዊን እንደሚሉት ማር ከአንድ የሾርባ ማንኪያ ስኳር ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ የካርቦሃይድሬት መጠን ነው ያለው። ሆኖም በውስጡ የያዘው ከፍተኛ የካሎሪ መጠን በደም ውስጥ ያለን የስኳር መጠን ስለሚጨመር በመጠኑ እንዲወሰድ ይመክራሉ።-የፎቶው ባለመብት Getty Images-ማር ከስኳር በላይ ጣፋጭ ስለሆነ የሚያስፈልገን ትንሽ ነው።-ማር ከስኳር ጋር ሲነጻጸር ዝቅተኛ የካርቦሃይድሬት መጠን ያለው። ይህ ማለት በደም ውስጥ ያለውን የስኳር መጠን እንደ ስኳር በፍጥነት አይጨምረውም ማለት ነው። ማር ከስኳር ይበልጥ ጣፋጭ በመሆኑም መመገብ የሚያስፈልገን ትንሽ ነው።-አንድ የሾርባ ማንኪያ ማር ብዙ ካሎሪ ስላለው በምንወስደው መጠን ላይ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል።-ማር ምርጫችን ከሆነና መመገብ የምንችል ከሆነ ከስኳር ይልቅ ብዙ ቫይታሚኖችን፣ ኤንዛይሞችን፣ አንታይኦክሲደንቶችን እና ሌሎች ንጥረ ነገሮችን በውስጡ የያዘውን ንጹህ የተፈጥሮ ማር መመገብ የጤና ጠቀሜታው የላቀ መሆኑን ባለሙያው አስረድተዋል።-በሚመከረው መጠን ልክ ከተወሰደ ማር ከስኳር ነጻ እንደሆነ ምግብ የሚቆጠር ነው። ለበርካታ አዋቂዎችም ጤና ጠቃሚ ሲሆን፣ የሚያስልጋቸውን ትክክለኛ መጠን ግን ማወቅ ይጠበቅባቸዋል።-ስኳር ላለባቸው ሰዎች አሊያም በደማቸው ውስጥ ያለውን የስኳር መጠን ለማስተካከል ጥረት እያደረጉ ያሉ ሰዎች ስኳርን በማር መተካታቸው “አልሸሹም ዞር አሉ” እንደማለት ነው። ምክንያቱም ሁለቱም በደም ውስጥ ያለን የስኳር መጠን ይጨምራሉ።-ከዚህም ባሻገር ከ12 ወር አሊያም ከአንድ ዓመት በታች ያሉ ሕጻናት ንጹህ [ያልተቀነባበረም] ሆነ የተቀነባበረ ማር መመገብ የለባቸውም። ምንያቱም የሰውነት የነርቭ ሥርዓት ላይ ጉዳት ለሚያደርስ ‘ቦቱሊዝም’ ለተባለ የምግብ መመረዝ ተጋላጭ ሊያደርጋቸው ስለሚችል ነው።-ምንም እንኳን አብዛኞቻችን ማርን በምግብ ዝርዝራችን ውስጥ ብናካትትም በሁሉም ሰው ዘንድ ተቀባይነት ላይኖረውም ይችላል።-የእንስሳት ተዋፅኦ ለማይመገቡ [ቪጋን] ለሆኑ ሰዎች ማር ተመራጭ አይደለም። ምክንያቱም ማር ምንም እንኳን ምንጩ አበባ [እፅዋት] ቢሆንም በክረምት ወራት የራሳቸውን ሕይወት ለማቆየት ሲሉ ታትረው ማር ከሚሰሩት ንቦች ጋር ስለሚያያዝ በቪጋኖች ዘንድ እንደ የእንስሳት ተዋፅኦ ይቆጠራል።
|
የፎቶው ባለመብት SOCIAL MEDIA-የተፈረደባቸው የአይኤስ አባላት በፍርድ ቤት-ለአይኤስ ለመዋጋት ወደ ሶማሊያ ገብተው ተይዘዋል የተባሉ ስድስት ሞሮኳውያን በሞት እንዲቀጡ ሲወሰንባቸው አንድ ኢትዮጵያዊ ደግሞ የ10 ዓመት እስር ተፈረደበት።-የተከሳሾቹን ጉዳይ የተመለከተው የሶማሊያ ወታደራዊ ፍርድ ቤት በአይኤስ አማካይነት በአገሪቱ ውስጥ ተሰማርተው ተገኝተዋል ብሎ ውሳኔ የሰጠባቸው ስድስት ሞሮኳውያን፣ አንድ ኢትዮጵያዊ እና ሁለት ሶማሊያውያን ናቸው።-ሞት የተፈረደባቸው የሰሜን አፍሪካዊቷ አገር ሞሮኮ ዜጎች በአንድ ወር ውስጥ ይግባኝ አቅርበው ተቀባይነት ካላገኙ በጥይት ተረሽነው ፍርዱ ተግባራዊ ይሆናል።-የወታደራዊው ፍርድ ቤት ምክትል ሊቀመንበር ኮሎኔል አሊ ኢብራሂም “ግለሰቦቹ ወደ ሶማሊያ የመጡት አይሲስ [ኤይኤስ] ደም እንዲያፈስ እና አገሪቱን እንዲያወድም ለማገዝ ነው” ማለታቸው ተዘግቧል።-ሞት የተፈረደባቸው ሞሮኳውያን አይኤስን እንዲቀላቀሉ መታለላቸውን እና ወደ አገራቸው እንዲመለሱ እንዲደረግ መጠየቃቸውን የተከሳሾቹ ጠበቃ ተናግረዋል።-የግለሰቦቹ ክስ የታየባት የከፊል ራስ ገዟ የፑንትላንድ ባለሥልጣናት ወደ አይኤስ ሊቀላቀሉ ነበር የተባሉ የውጭ ዜጎችን ሲከሱ እና ቅጣት ሲበይኑ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው ተብሏል።-ወታደራዊው ችሎት ሞት ከፈረደባቸው ስድስት ሞሮኳውያን ጋር የአንድ ኢትዮጵያዊ እና የሶማሊያዊ ጉዳይን ተመልክቶ በእያንዳንዳቸው ላይ የ10 ዓመት እስር ሲበይን፣ ሌላኛው ሶማሊያዊ ደግሞ በቂ ማስረጃ አልቀረበበትም በማለት በነጻ አሰናብቷል።-ክሱን ሲከታተሉ ከነበሩት ዓቃብያነ ህግ መካከል አንዱ ለቢቢሲ ሶማሊኛ እንደገለጹት፣ ታጣቂዎቹ የተያዙት የፑንትላንድ የንግድ ማዕከል ከሆነችው ቦሳሶ በስተምሥራቅ በሚገኝ ተራራማ ቦታ ላይ ነው።-ተራሮቹ አይኤስ ጠንካራ ይዞታ መሆናቸው የሚነገር ሲሆን፣ በስፍራውም ቡድኑ ወታደራዊ ሠፈር አለው።-በሶማሊያ የአይኤስ ቅርንጫፍ ከዘጠኝ ዓመት በፊት የተመሠረተው ከአልቃኢዳ ጋር ግንኙነት ካለው እና የአገሪቱ ዋነኛው ጂሃዲስት ቡድን ከሆነው ከአልሻባብ ተገንጥለው በወጡ ታጣቂዎች ነው።-በሶማሊያ ያለው የአይኤስ ቡድን ከነዋሪዎች ገንዘብ በማስገደድ የሚሰበስብ ሲሆን፣ አነስተኛ መጠን ያላቸው ጥቃቶችን አልፎ አልፎ የሚፈጽም መሆኑን የአሜሪካ ብሔራዊ መረጃ ጽህፈት ቤት አመልክቷል።-ነገር ግን የሞት ቅጣቶች እንዲቀሩ በርካታ የሶማሊያ እና ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ቡድኖች ጥሪ ሲያቀርቡ ቢቆዩም፣ ከሽብርተኝነት ጋር በሚገናኝ ወንጀል በሚዙ ሰዎች ላይ የሞት ቅጣት መበይን የተለመደ ነው።-የመብት ቡድኖች ባለፈው የካቲት ወር ባወጡት ሪፖርት መሠረት ባለፈው የአውሮፓውያን ዓመት በሶማሊያ በ55 ሰዎች ላይ የሞት ቅጣት ተፈጽሟል።-ከእነዚህም ውስጥ 23 የሞት ቅጣቶች የተፈጸሙት በፑንትላንድ እና በዋና ከተማዋ ሞቃዲሾ ውስጥ ነው።
|
የፎቶው ባለመብት Mayor Office/fb-በአዲስ አበባ እምብርት ፒያሳ፤ የሚኒሊክ ሀውልት እና የአራዳው ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የሚያዋስኑት ግዙፍ ፕሮጀክት ነው። በቅርቡ ከታደሰው እና የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ጽህፈት ቤት ከሚገኝበት ማዘጋጃ ቤት ጋር ደግሞ በድልድይ ተገናኝቷል።-እስከ ዛሬ ድረስ የራሱ መሰብሰቢያ አዳራሽ ሳይኖረው የቆየው የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤትም ቋሚ መሰብሰቢያ አዳራሽ የሚያገኘው በዚህ ፕሮጀክት ነው። እየተጠናቀቀ ያለው ይህ ፕሮጀክት ሁለት ሺህ ሰዎችን የሚይዝ የከተማ አዳራሽም በውስጡ ይዟል።-ከሁሉም በላይ ግን የዓድዋ ሙዚየም ፕሮጀክት ግዙፍነት የሚነሳው ሊዘክረው ካሰበው ታሪካዊ ሁነት ነው። ይህ ግዙፍ መንግሥታዊ ፕሮጀክት፤ ከሌሎች የአፍሪካ አገራት በተለየ የኢትዮጵያን ነጻነት ያስጠበቀው እና በተለያዩ አገራት የፀረ ቅኝ ግዛት እንቅስቃሴን ያነሳሳው የዓድዋ ድል መታሰቢያ ነው።-የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ መንግሥት ካስገነባቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች ውስጥ የሚጠቀሰው የዓድዋ ሙዚየም፤ ግንባታው የተጀመረው ሐምሌ 2011 ዓ.ም. ነበር። ሙዚየሙ የካቲት 3/2016 ዓ.ም. ተመርቆ ተከፍቷል።-የፒያሳ አዲስ ምልክት ይሆናል ተብሎ የሚጠበቀው የዚህ ሙዚየም ዋና አርክቴክት እስክንድር ውበቱ ነው።-የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአርክቴክቸር እና የከተማ ፕላን ምሩቁ እስክንድር፤ ህንጻዎችን ሲነድፍ 28 ዓመት ገደማ አሳልፏል። ከሥራዎቹ መካከል አዲስ አበባ ሰንጋ ተራ አካባቢ የሚገኘው ባለ 37 ወለሉን የሕብረት ባንክ ዋና መሥሪያ ቤት “ሕብር ታወር” ተጠቃሽ ነው።-ከእስከ ዛሬ ሥራዎቹ መካከል ትልቁ ደግሞ ፒያሳ ላይ የተዘረጋው የዓድዋ ሙዚየም ነው።-እንደ እስክንድር አገላለጽ ይህ ፕሮጀክት፤ እንደ ሌሎች ሥራዎች የደንበኛን ፍላጎት በህንጻ ንድፍ የመተርጎም ሥራ ብቻ አይደለም። “ከ1.5 ሄክታር በላይ በሆነ መሬት ላይ የሚቀመጥ ነገር ህንጻ ብቻ አይደለም” የሚለው እስክንድር፤ በትምህርት፣ በሙያ እና በንባብ ያሰባሰበውን የ“ኧርባን ዲዛይን” ጽንሰ ሀሳብ በትልቅ ደረጃ ሙከራ (experiment) ያደረገበት መሆኑን ይገልጻል።-የፎቶው ባለመብት Eskinder Woubtu-አርክቴክት እስክንድር ውበቱ በዓድዋ ሙዚየም-የዓድዋ ሙዚየምን የሚገነባው ተቋራጭ “ቻይና ጂያንግሱ ኢንተርናሽናል” ከእስክንድር ጋር ሲሠራ ይህ የመጀመሪያው አይደለም። እስክንድር የነደፈውን የሕብረት ባንክ ዋና መሥሪያ ቤት ህንጻን የገነባው ይህ ኩባንያ ነበር።-በ2011 ዓ.ም. የዓድዋ ሙዚየምን ለመገንባት ጨረታ የወጣው ከቤተ መንግሥት ፓርኪንግ እና ከአብርሆት ቤተ መጽሐፍት ፕሮጀክቶች ጋር በአንድ ላይ እንደነበር እስክንድር ያስታውሳል። እነዚህን ፕሮጀክቶች ለመገንባት የሚጫረቱ ተቋራጮች የህንጻውን ንድፍ የሚሠራ የአርክቴክት ድርጅት አብረው ማቅረብ ነበረባቸው።-በዚህ ጨረታ ላይ የሚወዳደረው ጂያንግሱ ኢንተርናሽናል ለኢትዮጵያዊው የአርክቴክቸር ድርጅት “እስክንድር አርክቴክትስ” የእንጣመር ጥያቄ አቀረበ።-“እነዚህን ፕሮጀክቶች ሲጫረቱ ከፕሮጀክቶቹ ውስጥ ‘የትኛው ውስጥ መሳተፍ ትፈልጋለህ?’ ተብሎ ነው [ጥያቄው] የመጣው። ከነበሩት ውስጥ ይበልጥ ሊፈትነኝ የሚችል እና ሀሳቡም በጣም ቅንጭብ ሆኖ የቀረበ ስለሆነ፤ ብዙ ዲዛይን የማድረግ ዕድል ስለሚኖረኝ ዓድዋን መርጬ ከቻይና ጂያንግሱ ግሩፕ ጋር ተጣማሪ ሆነን እዚህ ውስጥ ገባን” ይላል ሥራው የመጣበትን አጋጣሚ ሲያስታውስ።-ፕሮጀክቱን ያስጀመረው በቀድሞው የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ የሚመራው የከተማዋ አስተዳደር የሚገነባውን ህንጻ በተመለከተ ያስቀመጣቸው የመነሻ ሀሳቦች ነበሩ። ህንጻው የሚኒሊክ ሀውልት ከሚገኝበት መንገድ እኩል ሆኖ እንዲጀምር እና እጅጉን ከፍታ ያለው እንዳይሆን ማድረግ ከከተማ አስተዳደሩ መነሻዎች ውስጥ አንዱ ነው።-በሙዚየሙ ህንጻ ላይ የሰንሰለታማ ተራራ እና የነጋሪት ሀሳቦችን እንዲጸባረቁ ማድረግም የከተማ አስተዳደሩ መስፈርቶች ነበሩ። እነዚህ ሀሳቦች እንዴት ይካተቱ የሚለው ደግሞ የህንጻ ነዳፊው እስክንድር ፈጠራ ነው።-“የራሴን ሀሳቦች እንድጨምር ነጻነት ነበረኝ” የሚለው አርክቴክቱ፤ “ሁልጊዜ የሚጠየቀውን ኢትዮጵያዊ ኪነ ህንጻ” ለመሥራት ሙከራ ማድረጉን ይናገራል።-የፎቶው ባለመብት Eskinder Woubtu-ከሚኒሊክ ሀውልት ፊት ለፊት በሚገኘው የዓድዋ ሙዝየም መግቢያ ያለ የድል በዓል ማክበሪያ ስፍራ-በ3.3 ሄክታር ላይ ያረፈው የዓድዋ ሙዚየም ቁመቱን ከፍ ያደረገ አንድ ወጥ ህንጻ አይደለም። በተለያዩ መንገዶች የተሳሰሩ እና የአጠቃላይ ህንጻው አካል የሆኑ የተለያዩ ስብስቦችን (ሰብ ሴቶችን) የያዘ ነው።-ወደ ዓድዋ ሙዚየም የሚያስገቡት አራት ዋነኛ መግቢያዎች፤ የሚያደርሱት የተለያየ ገጽታ እና አገልግሎት ወዳላቸው የህንጻው ክፍሎች ነው። መግቢያዎቹ ስያሜያቸው የደቡብ ጀግኖች፣ የሰሜን ጀግኖች፣ የምሥራቅ ጀግኖች እና የምዕራብ ጀግኖች የሚል ነው።-እስክንድር፤ “ታሪክ እንደሚያሳየው ከሁሉም የኢትዮጵያ አቅጣጫ [ጦርነቱ ላይ] ተሳትፎ ተደርጓል ነው። ስለዚህ ሁሉም በአቅጣጫ ተወክለዋል። የበሮቹ ስያሜ ሲሰጥ ስሜቱም፣ ተመሳሌትነቱም እርሱ ነው” ይላል ከስያሜው ጀርባ ያለውን ምክንያት ሲያስረዳ።-ከዓድዋ ጦርነት ጋር የተያያዙ ቅርሶች የሚቀመጡበት ሙዚየም የሚገኘው በሚኒሊክ ሀውልት በኩል ባለው የሰሜን ጀግኖች መግቢያ ነው። ይህ መግቢያ ሀውልቱ ከሚገኝበት መንገድ እኩል (flat) ሆኖ የሚጀምር ሲሆን ለዓድዋ ድል በዓል ማክበሪያ የሚውል ሰፊ ፕላዛን ይዟል።-ከዚህ ዓመት ጀምሮ የዓድዋ ድል በዓል በዚህ ስፍራ ላይ እንደሚከበር የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አስታውቋል።-በዓድዋ ድል በዓል ማክበሪያው ስፍራ መሀል ላይ በአንድ ጎኑ ከፍ ያለ ባለመስታወት ክብ ቅርጽ ተቀምጧል። ከመስታወቱ ስር የሚገኘው፤ ምድር ቤት (basement) ውስጥ የተሠራው ባለ ሁለት ወለል ሙዚየም ነው።-መስታወቱ፤ አስፓልቱን ተሻግሮ ባለው የሚኒሊክን ሀውልት ላይ የምታርፈውን ፀሐይ ወደ ታች አውርዶ ምድር ቤት በሚገኘው ሙዚየሙ ውስጥ ተፈጥሯዊ ብርሃን ይፈነጥቃል። በክብ መስታወት (circular skylight) በኩል 20 ሜትር ቁልቁል የሚወረወረው የፀሐይ ብርሃን ማረፊያው ደግሞ በሙዚየሙ መሀል፣ ከመስታወቱ ትይዩ የተቀመጠ ነጋሪት ነው።-የፎቶው ባለመብት Eskinder Woubtu-በሙዚየሙ መሃል ላይ ከብርሃን ማስገቢያው መስታወት ትይዩ የሚገኘው ነጋሪት-እስክንድር የነጋሪቱን አቀማመጥ ሲገልጽ፤ “የሙዚየሙ መጀመሪያም፣ ማጠንጠኛም ነው” ይላል።-“ጦርነት ሲገባ፣ አዋጅ ሲነገር፣ ክተት ሲታወጅ የሚጎሰመው ነጋሪት ነው። ነጋሪቱ መሃል ላይ ሆኖ የሙዚየሙ የትኩረት ማዕከል (focal point) ነው፤ መነሻም ነው። ሙዚየም ውስጥ ስትገባ ጉብኝትህን ከአንድ ነገር ትጀምራለህ” ሲል ያብራራል።-“ሙዚየሙ ራሱ ሙሉ በሙሉ ከመሬት በታች ነው ያለውና ቀጥታ የሚመጣልህ ብርሃን ነው” የሚለው አርክቴክቱ፤ “ብርሃንን ቀርጾ ማስገባት እና በብርሃን መጫወትን” ሙከራ ያደረገበት የህንጻው ክፍል መሆኑን ያስረዳል።-እስንክድር፤ በህንጻው ንድፍ ላይ ደጋግሞ ያንጸባረቀው ሌላኛው ሀሳብ የዓድዋ ጦርነት የተካሄደበትን ምድረ ገጽ የሚወክለው ሰንሰለታማ ተራራ ነው። የህንጻው የውስጥ እና የውጭ ጎኖች፣ የደረጃ መደገፊያዎች ላይ በተቀመጡት ወጣ ገባ እያሉ አግድም በሚሄዱ መስመሮች እንዲሁም በደረጃ ፋንታ በተቀመጡት ተዳፋቶች (ramp) ላይ መንጸባረቁን እስክንድር ይናገራል።-ተራራ “በአርክቴክቸራል ቋንቋ” ከተገለጸባቸው የህንጻው ክፍሎች ውስጥ አንዱ በማዘጋጃ ቤት በኩል የሚገኘው መግቢያ ነው። በዚህ መግቢያ ላይ ከደረጃ ባሻገር የተቀመጠው ዚግ ዛግ የሚሄድ ተዳፋት (ramp) ከርቀት ሲታይ የተራራ ይመስላል።-በዚህ መግቢያ ወደ የሚዘልቁ ጎብኚዎች ደረጃውን እንደጨረሱ የሚያገኙት እቴጌ ጣይቱ በመቀለው ውጊያ የውሃ ምንጮችን በመያዝ የጣልያን ጦር እጅ እንዲሰጥ ለተጠቀሙት ስልት መታሰቢያነት የዋለ የውሃ ፋውንቴን ነው።-ተራራማ እና ድንጋያማ አካባቢን በዓድዋ ሙዚየም ላይ የማንጸባረቅ ሀሳብ፤ የህንጻው ቀለም ላይም ታይቷል። በተለይ በህንጻው የውጭ ክፍል ላይ ጎልቶ የሚታየው ቀለም “ሸክላ መሳይ” ነው።-ከህንጻው ትልቅነት አንጻር የተለያዩ ቀለማትን መጠቀም ይቻል እንደነበር የሚናገረው እስክንድር፤ ይበልጥ “ተፈጥሯዊ ነው” ብሎ ያሰበውን ይህንን ቀለም በብቸኝነት መጠቀሙን ይገልጻል። “ተራሮቹን የበለጠ የመግለጽ አቅም ያለው ቀለም ነው። ለህንጻውም የራሱ መገለጫ ሰጥቶታል” ይላል።-የፎቶው ባለመብት Mega Projects Office/fb-ከባህላዊው ልብስ 'ድንጉዛ' የተቀዳው የዓድዋ ሙዚየም የውጭ ገጽታ-እስክንድር፤ አንድ ህንጻ ሲሠራ ለአካባቢው እና ለነዋሪዎች የሚያስተላልፈው “ጥበብ” ሊኖረው ይገባል የሚል እምነት አለው።-በዓድዋ ሙዚየም ላይ “ሞክሬዋለሁ” የሚለው ዋነኛው ጉዳይ ኢትዮጵያዊ ምልክቶች እና መገለጫዎችን በህንጻ ዲዛይን ውስጥ የማካተት ሀሳብን ነው።-“ሌሎች አገራት ላይ ብዙ ፓተርኖች ላይ ኤክስፐርመንት ያደርጋሉ። እኛ አሁን ማየት ያለብን ወደ ውጭ ሳይሆን ወደ ውስጥ ነው። እነዚህን ነገሮች መሞከር እፈልግ ነበር” ሲል የህንጻን ገጽታ ከአገርኛ አውድ ጋር (local context) ጋር የማስተሳሰር ሙከራው በዚህ ፕሮጀክት መጀመሩን ያስረዳል።-በኢትዮጵያ ባህል ውስጥ “ያልታዩ ጥበቦች” መኖራቸውን የሚያነሳው እስክንድር፤ “ዘመናዊ ነገር እንሥራ ማለት አይደለም። በብዙ መልኩ እኛን የሚመስል ነገር [ወደ ማስቀመጥ] ነው መሄድ ያለብን” ይላል።-በዓድዋ ሙዚየም ላይ ያካተተው አንዱ አገርኛ ምልክት በደቡባዊ ኢትዮጵያ በጋሞ እና በወላይታ አካባቢዎች የሚለበሰው “ድንጉዛ” ነው። በደማቅ ቀይ፣ ቢጫ እና ጥቁር ቀለሞች ዐይን የሚገባው ድንጉዛ፤ በጥለቱ ላይ የሚቀመጡት ወጣ ገባ ያሉ መስመሮችም መለያዎቹ ናቸው።-ይህን የድንጉዛ ጥለት የመስመር አካሄድ ከ100 ሜትር በላይ በሚሄድ የህንጻው ክፍል ላይ ተንጸባርቋል። በህንጻው የውጪ ክፍል ላይ የሚገኙት የጦር እና ጋሻ ምልክቶች የተቀረጹት በድንጉዛ የመስመር አካሄድ በተቀመጡ ቅርጾች ላይ ነው።-ከአክሱም ሀውልት እና ከላሊበላ ኪነ ህንጻ የተወሰዱ ምልክቶችም በህንጻው የደረጃ ድጋፎች እና የኮሪደር ስፍራዎች ላይ ማንጸባረቁንም አርክቴክቱ ይናገራል።-የፎቶው ባለመብት Eskinder Woubtu-የሰባ ደረጃ ተምሳሌት በዓድዋ ሙዚየም የደቡብ ጀግኖች መግቢያ-የንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት፤ አዲስ አበባ አሉኝ የምትላቸው ኪነ ህንጻዊ ውበትን የተጎናጸፉ ህንጻዎች የተገነቡበት ነው። ብሔራዊ ቲያትር፣ ማዘጋጃ ቤት እና የንግድ ባንክ የቀድሞ ዋና መሥሪያ ቤት ከእነዚህ ህንጻዎች መካከል ናቸው።-እነዚህን ህንጻዎች የተነደፉት እንደ ፈረንሳዊው ሄንሪ ሾሜት እና ጣልያናዊው አርትሮ ሜዜዲሚ ባሉ የውጭ አርክቴክቶች ነው። እስክንድር፤ “የአካባቢውን ሁኔታ አጥንተው አካባቢያዊ አውዱን (local context) ለማምጣት የሚሞክሩ አርክቴክቶች ነበሩ” ሲል ያሞካሻቸዋል።-የእነዚህ ህንጻዎች አንድ መገለጫ ከፊታቸው አጭር ሆነው ለእግረኛ መረማመጃ ስፍራ መፍጠራቸው ነው። “የአራት ኪሎ መደዳው እና ዞሮ ወደ ፒያሳ ሲመጣ [ህንጻዎች] በደረጃዎች እተገናኙ አርኬድ (ታዛ) አላቸው። እግረኛ በምቾት፣ በጥላ እንዲሄድ ነው” የሚለው አርክቴክቱ፤ የፒያሳ ህንጻዎች ከመንገዱ ጋር “በጣም የተናበቡ” መሆናቸውን ያነሳል።-“ከፒያሳ የምወስደውን የበፊት (traditional) ፕላኒንግ ልበለው። አሁን ዘመናዊ ፕላኒንግ ደግሞ አለ። እኔ ወደዚያ [ወደበፊቱ] ነው መመለስ የምፈልገው። ያ ጥሩ ፕላኒንግ ነው” የሚለው አርክቴክቱ በዓድዋ ሙዚየም ላይ እግረኛ የሚራመድባቸው ታዛዎችን መፍጠሩን ያስረዳል።-በሙዚየሙ ህንጻ ውስጥ የሚገኙት መደብሮች ደጃፋቸው እንደ ፒያሳው መብራት ኃይል ህንጻ እግረኛን የሚያስተናግዱ ናቸው።-ከአራዳ ህንጻ ጋር አዋሳኝ በሆነው አቅጣጫ የሚገኘው የዓድዋ ሙዚየም ደግሞ ሌላኛው የፒያሳ ገጽታ ምሳሌ አድርጎ የተነደፈ ነው። በሙዚየሙ ሁለት ብሎኮች መካከል ረጅም ደረጃ የተዘረጋበት ይህ የደቡብ ጀግኖች መግቢያ፤ ከፒያሳው 70 ደረጃ ጋር ተመሳሳይነት አለው።-የፎቶው ባለመብት Adanech Abiebie/fb-የዓድዋ ተራሮች በሙዚየሙ ህንጻ ንድፍ ላይ የተገለጸበት አንድ ክፍል-የዓድዋ ሙዚየም የህንፃ ንድፍ ሲሠራ ከጦርነቱ ጋር የተያያዙ 40 ገደማ ቅርጾች እንደተካተቱበት እስክንድር ይናገራል። ከእነዚህ የሚቆሙ እና በግድግዳ ላይ የሚለጠፉ ቅርጾች ውስጥ ግማሾቹ መሠራታቸውን የሚገልጸው አርክቴክቱ፤ “የተወሰኑት ወደፊት ይሰራሉ” ተብሎ እንደሚጠበቅ ጠቅሷል።-በአሁኑ ጊዜ ተቀርጸው ከቆሙት ሀውልቶች መካከል የአጼ ሚኒሊክ እና የእቴጌ ጣይቱ እንዲሁም 12 የጦርነቱ አዝማቾች ይገኙበታል። የአጼ ሚኒሊክ እና እቴጌ ጣይቱ ሀውልት የውሃ ፋውንቴን በሚገኝበት ፕላዛ ላይ ጎን ለጎን ተቀምጠዋል። የጦር አዝማቾች ሀውልት ደግሞ በከተማ አዳራሽ የውጨኛ ክፍል ላይ በሚገኙት አምዶች ላይ ተቀምጠዋል።-እንደ እስክንድር ገለጻ የሀውልቶቹን አቀማመጥ በተመለከተ መጀመሪያ የሠራው ንድፍ ላይ ተጨማሪ ሀሳቦች ተካትተዋል። በንድፉ ላይ የ12ቱ የጦር አዛዦች ሀውልቶች በአንድ እልፍኝ ላይ እንዲቀመጥ ተደርጎ ነበር። የእቴጌ ጣይቱ ሀውልት ደግሞ በመቀለው ጦርነት ንግሥቲት ላመጡት የጦርነት ስልት መታሰቢያ በተሠራው የውሃ ፋውንቴን መሃል ላይ እንዲሰፍር ተነድፎ ነበር።-የእነዚህ ሀውልቶች ፎቶግራፍ በሶሻል ሚዲያ ገጾች ላይ ከተሰራጨ በኋላ የተለያዩ አስተያየቶች ሲሰጡ ተደምጠዋል። በቅሬታ መልክ ከተነሱት አስተያየቶች ውስጥ የሀውልቶቹን የቁመት መጠን እና ገጽታ እንዲሁም የተሰሩበት ቁስን የተመለከቱ ይገኙበታል። የሠዓሊያን እና የቀራፂያን ማኅበር በሙዚየሙ ቅርፃ ቅርፅ ሥራዎች ላይ “አልተሳተፍኩም” ማለቱም ሌላኛው አስተያየት ነበር።-የሀውልት እና ሌሎች የቅርፅ ሥራዎች የሚከናወኑት ከ20 እስከ 25 አባላት ባሉት የቀራፂያን ቡድን መሆኑን የሚናገረው እስክንድር፤ “በፎቶግራፍ የተደገፉ የታሪክ መጽሐፍትን ይዘው፤ ጊዜው በቂ እንኳን ባይሆን [የሀውልቶቹን] ገጽታ ከዚያ ላይ እያጠኑ ሠርተዋል። ይህንን አይቻለሁ” ይላል።-ይሁንና የቅርጽ ሥራዎቹ ቀድመው ተጀምረው ለጥናት ሰፊ ጊዜ መሰጠት እንደነበር ይገልጻል።-የፎቶው ባለመብት Adanech Abiebie/fb-የአጼ ሚኒሊክ እና የእቴጌ ጣይቱ ሀውልት በዓድዋ ሙዚየም-አርክቴክቱ እንደሚያስረዳው በዓድዋ ሙዚየም ውስጥ ከሚቀመጡት የቅርፃ ቅርፅ ሥራዎች መካከል “ወሳኝ” የሆኑት ከነሐስ እንዲሠሩ በህንጻው ንድፍ ላይ ሰፍሯል። ይሁንና በአሁኑ ሰዓት ለሀውልቶቹ ግንባታ ጥቅም ላይ የዋለው ቁስ ሌላ መሆኑን አመልክቷል።-“እኛ ስናስቀምጥ ወሳኝ ሥራዎች በነሐስ እንዲሠሩ ተቀምጧል። የተያዘላቸው የሥራ ዝርዝር እንደዚያ ነው። በዚህኛው ግን አሁን ለማስመረቂያ ስለማይደርሱ፤ በመቀጠል የነሐስ ሀውልቶች እንደሚሠሩ ነው የማውቀው” ሲል በህንጻው ንድፍ ላይ በተቀመጠው መሠረት ሀውልቶቹ በድጋሚ ይሠራሉ የሚል እምነቱን ገልጿል።-ሀውልቶቹ አሁን የተሠሩበት ቁስም ቢሆን ግን ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ ውስጥ የተለያዩ ቅርፆችን ለመሥራት ጥቅም ላይ የዋለ መሆኑን አስረድቷል።-ከቅርፅ ሥራዎች ጋር በተያያዘ የሚነሱትን አስተያየቶች እንደሚጋራ የሚናገረው እስክንድር፤ “የአርት ሥራን መልሶ አሻሽሎ መሥራት፣ መለወጥ ይቻላል” ይላል። በአሁኑ ሰዓት ያልተሠሩት የቅርፃ ቅርፅ ሥራዎች ሲከናወኑ “ከዚህ ልምድ ተወስዶ የሚቀጥለውን ሂደት በማሳተፍ፣ ጊዜ በመስጠት እና በጥናት ይበልጥ ቢኬድበት” የሚል ምክረ ሀሳቡን አስቀምጧል።-የሀውልቶቹን ሥራ ጨምሮ ከዋና ንድፍ ላይ ለውጥ የተደረገባቸው ነገሮች ቢኖሩም “90 በመቶ በሚባል ደረጃ” ያስቀመጠው አርክቴክቸር ወደ ተግባር መተርጎሙን እስክንድር ይናገራል። የዓድዋ ሙዚየም ግንባታ “በአስቸጋሪ” ሁኔታ ውስጥ የተከናወነ መሆኑን በመጥቀስም ጥሩ ሥራ መሠራቱን ያስረዳል።-ከሙዚየሙ ግንባታ ጋር የሜካኒካል፣ የኤሌክትሪካል እና የኦዲዮ ቪዥዋል ሥራዎችም “በጣም በከፍተኛ ሁኔታ” መከናወናቸውን በመግለጽ፣ በግንባታው ሂደት ጥቅም ላይ የዋሉት እቃዎችም ደረጃውን የጠበቁ እንደሆኑ አክሏል።-እስክንድር፤ “ለዓድዋ በሚመጥን መልኩ ያለንን ሁሉ ሰጥተን ሠርተነዋል። ለብዙ ጊዜ ሌሎች ሥራዎችን ሳንሠራ ሁልጊዜ እዚህ ጋር ነን። ማንኛውም እንደዚህ [ዓይነት] ኪነ ህንጻ ሲሠራ ፍጹም ሊሆን አይችልም፤ ብዙ ትችቶች እንደሚመጡ አውቃለሁ። ግን ባለን አቅም ሁሉ የምንችለውን ጥረት አድርገን [ሠርተነዋል]” ይላል።-እስክንድር ወደ ሦስት አስርት ዓመታት እየተጠጋ ባለው የሥራ ልምዱ ውስጥ ትልቁ ስለሆነው ፕሮጀክት ሲያነሳ፤ “በውጭም ዓለም ሙዚየምን የሚሠራ አርክቴክት ‘ዕድለኛ ነው’ ይባላል። በክፍለ ዘመን [አንዴ] የሚመጣ ዕድል ሊሆን ይችላል። እጅግ በጣም ዕድለኛ ነኝ” ሲል ስሜቱን ለቢቢሲ አጋርቷል።-የፎቶው ባለመብት Eskinder Woubtu
|
የፎቶው ባለመብት PA Media-ዩኬ ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ የምታዘዋውረው በትንንሽ ጀልባዎች ወደ ግዛቷ የሚገቡትን ለመከላከል በሚል ነው-ዩናይትድ ኪንግደም ጥገኝነት ጠያቂዎችን ከግዛቷ ወደ ሩዋንዳ ለሚሰፍሩት ካላት እቅድ ለተወሰነው 370 ሚሊዮን ፓውንድ እንደምትከፍል የመንግሥት ወጪዎችን የሚከታተለው ተቋም ይፋ አደረገ።-ዩናይትድ ኪንግደም (ዩኬ) በአምስት ዓመታት ውስጥ ወደ ምሥራቅ አፍሪካዊቷ አገር ለሚዘዋወሩ ለእያንዳንዳቸው ጥገኝነት ጠያቂዎች 150000 ፓውንድ ለሩዋንዳ መንግሥት ይከፍላል።-ሌበር ፓርቲ የኦሪት ጽህፈት ቤቱ ያወጣውን የገንዘቡን መጠን በተመለከተ “ብሔራዊ ቅሌት” ሲል የተቃወመው ሲሆን፣ የአገር ውስጥ ሚኒስቴር ግን “አንድ ነገር ለመሥራት ከፍተኛ ወጪ ይጠይቃል” ብሏል።-የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ “አሁን አንድ እርምጃ ካልወሰድን በ2026 ለጥገኝነት ጠያቂዎች መኖሪያ የሚወጣው ገንዘብ በየዓመቱ 11 ቢሊዮን ፓውንድ ይደርሳል” ሲሉ የውሳኔውን መነሻ አብራርተዋል።-የኦዲት ሪፖርቱ ይፋ የተደረገው የዩኬ ምክር ቤት አባላት ስደተኞችን ወደ ሌላ አገር የማዘዋወሩ ዕቅድን በተመለተ ከፍተኛ ግልጽነት እንዲኖር መጠየቃቸውን ተከትሎ ነው።-ለአምስት ዓመታት በተደረሰው ስምምነት መሠረት፣ ዩናይትድ ኪንግደም በሕገወጥ መንገድ ወደ ግዛቷ የሚገቡ ሰዎችን ወደ ሩዋንዳ በመላክ እዚያ ጥገኝነት እንዲጠይቁ ይደረጋል።-የዚህ ፖሊሲ ዓላማም በእንግሊዝ ቦይ በኩል በባሕር የሚገቡ ሰዎችን ለማስቆም ሲሆን፣ ይህ ዕቅድም ጠቅላይ ሚኒስትር ሪሺ ሱናክ ከቀዳሚ ዓላማዎቻቸው መካከል አንዱ ነው።-ቢሆንም ግን ዕቅዱ የሕጋዊነት እንቅፋት ስለገጠመው በእንጥልጥል ላይ ያለ ሲሆን፣ አስካሁን አንድም ሰው ወደ ሩዋንዳ አልተዘዋወረም።-ዕቅዱን ተግባራዊ ለማድረግ የተዘጋጀው ሕግ በፓርላማ አባላት የጸደቀ ሲሆን፣ በሚቀጥለው ሳምንት ክርክር ይደረግበታል። ነገር ግን አሁን ይፋ የሆነው የገንዘብ መጠን ጉዳይ እንቅፋት ሊሆን ይችላል ተብሏል።-በዚህ መርሃ ግብር አማካይነት የዩኬ የአገር ውስጥ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ለሩዋንዳ የምጣኔ ሃብት ድጋፍ እና ወደ አገሩ ለሚገቡት ሰዎች ሰዎች የሚውል ገንዘብ ይሰጣል።-ከአውሮፓውያኑ 2022 ጀምሮ አስካሁን ዩኬ 220 ሚሊዮን ፓውንድ ለሩዋንዳ የሰጠች ሲሆን በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታትም በየዓመቱ 50 ሚሊዮን ፓውንድ በመስጠት አጠቃላዩ 370 ሚሊዮን ፓውንድ ይሆናል።-ከ300 በላይ ጥገኝነት ጠያቂዎች ወደ ሩዋንዳ የሚላኩ ከሆነ፣ በአንድ ጊዜ 120 ሚሊዮን ፓውንድ እና ተጨማሪ በእያንዳንዳቸው ሰዎች 20 ሺህ ፓውንድ ተክፍላለች።-በተጨማሪም ወደ ሩዋንዳ ለሚዘዋወሩት ጥገኝነት ጠያቂዎች ለእያንዳንዳቸው የመኖሪያ፣ የምግብ እና የትምህርት ወጪ የሚሆን 150874 ፓውንድ መድቧል።-ነገር ግን ግለሰቦቹ ከሩዋንዳ ውጪ የሚሄዱ ከሆነ ገንዘቡ የሚቆም ሲሆን ለጉዟቸው የሚሆን 10 ሺህ ፓውንድ ብቻ ይሰጣቸዋል።-የኦዲት ተቋሙ ባወጣው መረጃ መሠረት ይህ ጥገኝነት ጠያቂዎችን ወደ ሩዋንዳ ለማዘዋወር የወጣው ዕቅድ በ370 ሚሊዮን ፓውንድ ላይ የሚቆም ሳይሆን ተጨማሪ ወጪዎች እንደሚኖሩት አሳውቋል።-ተቃዋሚው ሌበር ፓርቲ በሚቀጥለው ምርጫ የሚያሸንፍ ከሆነ ወደ ሩዋንዳ ስደተኞችን ለማዘዋወር የተያዘውን እቅድ እንደሚሰርዘው አስታውቋል።
|
የፎቶው ባለመብት Getty Images-የኢትዮጵያ መንግሥት እና የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ላለፉት አምስት ዓመታት ያደረጉትን ጦርነት በንግግር ለመፍታት በመወሰን በዛንዚባር ንግግር የጀመሩት ከወራት በፊት ነበር።-በመጀመሪያው ዙር ድርድር ማን ምን ይፈልጋል የሚለውን የለዩበት አንደነበር የሚናገሩት የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊትን ወክለው የተሳተፉት አቶ ጅሬኛ ጉደታ ይህም ለሁለተኛ ዙር ድርድር መንገድ የጠረገ እንደነበር ይጠቅሳሉ።-ይህ ለመጀመሪያ ጊዜ የተደረገው ንግግር በመልካም መግባባት ከተጠናቀቀ በኋላ፣ ለሁለተኛ ዙር ድርድር በታንዛኒያ ዋና ከተማ ዳሬ ሰላም ተገናኝተው ነበር።-የሁለተኛው ዙር ድርድር በሁለቱም ወገን ደጋፊዎች በኩል መግባባት ላይ ተደርሶ የሰላም ንግግሩ በፊርማ ይጠናቀቃል የሚል እምነት አሳድሮ ነበር።-ለዚህም ምክንያት የሆነው ከፍተኛ የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት መሪዎች እንዲሁም የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መኮንኖች በንግግሩ ላይ መሳተፋቸው ነበር።-ከዚህ በተጨማሪም የኢትዮጵያ መንግሥትም ከፍተኛ የፖለቲካ አመራሮቹ በቀጥታ በውይይቱ ላይ ተሳትፈው ነበር።-በኦሮሞ ነጻነት ግንባር በኩል ዋና አዛዡ መሮ ድሪባ፣ ምክትሉ ገመቹ አቦዬ እና ሌሎችም ሲሳተፉ በኢትዮጵያ መንግሥት ደግሞ በወቅቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የደኅንነት አማካሪ የነበሩት አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን እንዲሁም የፍትህ ሚኒስትሩ ጌድዮን ጢሞትዮስ (ዶ/ር) ተሳታፊ ነበሩ።-በአደራዳሪነት ደግሞ አሜሪካ፣ ኖርዌይ እንዲሁም የኢጋድ ተወካዮች ሲሳተፉ፣ የዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ድጋፍ መስጠቱን ቢቢሲ በወቅቱ ተሳታፊ ከነበሩ አካላት መረዳት አችሏል።-ይህ ከሳምንት በላይ በዝግ የተካሄደው ስብሰባ ባለመግባባት ተጠናቅቋል።-በወቅቱ ሁለቱ አካላት እንዳልተስማሙ ከመግለጻቸው በስተቀር ያላግባቧቸው ዝርዝር ጉዳዮች ላይ ምንም ዓይነት ማብራሪያ እስከ ዛሬ ድረስ አልሰጡም።-የኦሮሞ ነጻነተ ሠራዊት አዛዥ መሮ ድሪባ ዋና አማካሪ የሆኑት እና በድርድሩ ላይ ተሳታፊ የነበሩት አቶ ጅሬኛ ለቢቢሲ አፋን ኦሮሞ የዳሬሰላሙ ድርድር ለምን ሳይሳካ እንደቀረ ሲናገሩ “ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ” ጉዳዮች እንዳላግባቧቸው ተናግረዋል።-አቶ ጅሬኛ በዳሬሰላሙ ድርድር መጀመሪያ ላይ በሁለቱም ወገኖች በኩል ስምምነት ላይ ለመድረስ ቁርጠኝነት የነበረበት ነው ይላሉ።-“ለዚህ አንዱ ማሳያ ብዙ ጊዜ ተገድሏል ሲባል የነበረው መሮ ድሪባ እና ሌሎች የጦሩ አመራሮች መገኘታቸው ነው።”-አደራዳሪዎቹም ቢሆኑ እነ መሮ ይመጣሉ የሚል ሙሉ እምነት አንዳልነበራቸው የሚያስታውሱት አቶ ጅሬኛ “ሲመጣ ግን እኛንም አስደስቶናል” ሲሉ በወቅቱ የነበውን ስሜት ያስታውሳሉ።-እርሱን ከምዕራብ ኦሮሚያ ዳሬሰላም ለማምጣትም ቢሆን አደራዳሪዎቹ ከፍተኛ ኦፕሬሽን ማካሄዳቸውን ይናገራሉ።-“እንግዲህ ሁለተኛ ዙር ውይይት ላይ ብዙ ርዕሶችን አንስተን ተነጋግረናል። ግን ከእነዚህ ውስጥ ሁለት ዋና ዋና አከራካሪ ሀሳቦች አንዱ የአገሪቱ ወታደራዊ እና ደኅንነት እና የፖለቲካ ጉዳዮች" እንደነበሩ አቶ ጅሬኛ ጠቅሰዋል።-ዋና አከራካሪ የነበረው እና ያላስማማቸው ነጥብ በአገሪቱ የሚገኙ የፀጥታ አካላት አወቃቀር እና አመራርን በተመለከተ አካታች እንዲሆን የተነሳው ነጥብ ነው ይላሉ።-በዚህ ንግግር የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ከፌደራል እስከ ክልል ባሉ የፀጥታ አካላት አወቃቀር ላይ አካታች በሆነ መልኩ እንደገና እንዲዋቀሩ መጠየቁን አቶ ጅሬኛ ጠቅሰዋል።-“ሁሉንም ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ጨምሮ፣ አመራር ውስጥ ድርሻ ሊኖራቸው ይገባል የሚል አንስተናል። እነርሱ አልተቀበሉትም።”-ቢቢሲ የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት አመራር የአገሪቱ መከላከያ እና የፌደራል ፖሊስ ውስጥ እንዲካተት ስለመጠየቃቸው አቶ ጅሬኛን ጠይቆ ይኸው መከናወኑን አመልክተዋል።-“እዚህ ጉዳይ ላይ መነጋገር ያለባቸው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት እና መንግሥት ናቸው ብለን እናምናለን። በሌሎች ፖለቲካ ጉዳዮች ውስጥ ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲካተቱ አንስተናል” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።-በኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት በኩል በኢትዮጵያ ከፍተኛ ችግር ነው ብሎ የሚያነሳው የፖለቲካ ጉዳይ መሆኑን የሚናገሩት አቶ ጅሬኛ፣ “እርሱ መፍትሄ ስላላገኘ ነው ወደ ትጥቅ ትግል የገባነው” ይላሉ።-የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ሁሉንም የፖለቲካ ፓርቲዎች ባሳተፈ ሁኔታ የዜጎች መብት የሚከበርበት፣ የሚዲያ ነጻነት የሚረጋገጠበት፣ ነጻ ምርጫ ቦርድ የሚኖርበት፣ የፖለቲካ ምኅዳሩ የሰፋበት ሥርዓት እንዲገነባ፣ የፍትህ አካላት ነጻነት እንዲኖራቸው በወቅቱ መጠየቁን ይገልጻሉ።-አቶ ጅሬኛ “ይህ ጉዳይ ሲነሳ መንግሥትን የወከሉ ተደራዳሪዎች አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ የፖለቲካ ጥያቄ የለም። በሕዝብ የተመረጠ መንግሥት ነው ሥልጣን የያዘው። ሕገ መንግሥቱን በጠበቀ መልኩ ትጥቃችሁን ፈትታችሁ ግቡ” የሚል ምላሽ መስጠቱን ያነሳሉ።-የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት በበኩሉ “የሕዝብ ጥያቄ አለ፣ የአገሪቱን ወታደር እና የፖሊስ ኃይልን መንግሥት ይዞ ሕዝቡን እያፈነ እና ነጻነቱን እያሳጣ መሆኑን በመጥቀስ የራሱን ዕድል በራሱ አንዳይወስን እያደረገ መሆኑን” በመጥቀስ መከራከራቸውን ይናገራሉ።-“የአገር ጦር ሠራዊት ፖለቲካ ውስጥ መግባት የለበትም፣ ለፓርቲም ተገዢ አይሁን” ሲሉ መከራከራቸውንም አክለው ተናግረዋል።-“መንግሥት የራሱን ሥልጣን ለመከላከል የአገሪቱን ፖሊስ እና ወታደር እየተጠቀመበት ነው” የሚሉት አቶ ጅሬኛ፣ የፀጥታ ኃይሉ የተቃዋሚውም ሆነ የገዢው ፓርቲም መከታ መሆን አለበት ብለው ቢከራከሩም ከመንግሥት ወገን ይህ ተቀባይነት አለማግኘቱን አቶ ጅሬኛ ይናገራሉ።-መንግሥት የአገሪቱን ሕገ መንግሥት በተከተለ እና ባከበረ ሁኔታ እየሠራ መሆኑን በመጥቀስ መከራከራሩን ጨምረው አስረድተዋል።-ሌሎች ከተነሱ ጥያቄዎች መካከል ደግሞ የኦሮሚያ ክልል ወሰንን በተመለከተ በወሎ፣ በአዲስ አበባ፣ በድሬዳዋ የብሔር ብሔረሰቦችን መብት ባከበረ እና ባለቤትነት በተረጋገጠ መልኩ እንዲሆን መጠየቃቸውን ገልጸዋል።-መንግሥት ይህንን ጥያቄ ሕገ መንግሥቱን በጠበቀ መንገድን እንመልሳለን የሚል መልስ መስጠቱን እና መግባባት ላይ መድረሳቸውን ያስረዳሉ።-ሌላው መግባባት ላይ የደረሱበት ኦሮምኛ የፌደራል የሥራ ቋንቋ እንዲሆን የሚለው ጥያቄ መሆኑን ያነሱት አቶ ጅሬኛ፣ ይህም በሕገ መንግሥቱ መሠረት ተፈጻሚ አንደሚሆን መግባባታቸውን አመልክተዋል።-ድርድሩ ከተጠናቀቀ በኋላ በተለያዩ ማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን በኩል መንግሥት መሮ ድሪባን ጨምሮ ለኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት አመራሮች ሥልጣን ለመስጠት ፈቃደኛ መሆኑን ተጠይቀው ይህንን አረጋግጠዋል።-“ለሺህ ሰው የሚሆን ከፌደራል እስከ ክልል የታችኛው መዋቅር ድረስ ሥልጣን የመስጠት ጥያቄ ለማቅረብ አስበው ነበር” በማለት አለመቀበላቸውን ተናግረዋል።-“እኛ እንደ ግል የጠየቅነው ሥልጣን የለም ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚሠራ ሥርዓት እንዲገነባ ነው የጠየቅነው። ያ ሥርዓተ ሲኖር በጦርነት እና በጉልበት ሕዝቡንም አታስቸግርም። . . . ሥልጣን የመጨረሻ ግባችን አይደለም። ጠንካራ ሥርዓትን መገንባት ነው። እነርሱ ደግሞ ሥልጣን የመጨረሻ ግባችን እንደሆነ አድርገው ነው ለግለሰቦች ሥልጣን ለመስጠት ያሰቡት።”-መንግሥት እና የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ከሳምንት በላይ በዳሬ ሰላም ያደረጉት ድርድር ባለመስማማት መጠናቀቁን ተከትሎ የመንግሥት ተወካዮቸ አዳራሹን ጥለው መውጣታቸውን አቶ ጅሬኛ ይናገራሉ።-ለአቶ ጅሬኛ ሦስተኛ ዙር ድርድር ይኖራል ተብለው ተጠይቀው “የሁለተኛው ዙር ድርድር አጨራረስ ጥሩ ስላልነበረ ከአደራዳሪዎቹ ጋር ሳንነጋገር ቆይተናል” ይላሉ።-አደራዳሪዎቹ ሰሞኑን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት አመራሮችን ስለ ሦስተኛ ዙር ድርድር ማነጋገራቸውን የተናገሩት አቶ ጅሬኛ “በተጨባጭ ግን መቼ እና የት ይካሄዳል የሚል ስምምነት የለም” ብለዋል።-የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ዋና አዛዥ ይገኝበታል ከሚባለው የምዕራብ ኦሮሚያ ድርድሩ ወደ ሚካሄድበት ዳሬሰላም ማን ወሰደው? ለሚለው ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል አቶ ጅሬኛ።-“ከመንግሥት ጋር አንድም ቀን መተማመን የለንም” ካሉ በኋላ፣ ነገር ግን አደራዳሪዎቹ ከመንግሥት ጋር መግባባት ላይ የደረሱበት ነገር መኖሩን ያነሳሉ።-መሮን ከነበረበት በሂሊኮፕተር አንስቶ ወደ ደምቢዶሎ ከተማ የወሰደው የዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ድርጅት መሆኑን ጠቅሰዋል።-ከደምቢዶሎም በአውሮፕላን ናይሮቢ፣ ከናይሮቢ ዳሬሰላም እንደሄደ አቶ ጅሬኛ ጨምረው ተናግረዋል።-ከድርድሩ በኋላስ የአማጺው ቡድን መሪ ወደ ምዕራብ ኦሮሚያ ለመመለስ ግን ያጋጠመ ችግር ነበር ይላሉ አቶ ጅሬኛ።-“የኢትዮጵያ መንግሥት ቃሉን አልጠበቀም። ቀይ መስቀል እና ሌሎቹ መካከላችን የነበሩ አካላት ወዳመጡበት የመመለስ ኃላፊነት ቢኖርባቸውም የኢትዮጵያ መንግሥት ባለመፍቀዱ መመለስ አንዳልቻሉ ነገሩን።”-“እኛ በራሳችን መንገድ ወደ መጡበት አንዲመለሱ አድርገናል፤ ዝርዝሩን ሌላ ጊዜ” በማለት የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት አመራሮች ወደ አገር ውስጥ ገብተዋል ሲሉ ተናገረዋል።
|
የፎቶው ባለመብት Bahirdar Communication-በአማራ ክልል ዋና ከተማ ባሕር ዳር በመንግሥት ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የተኩስ ልውውጥ መካሄዱን ነዋሪዎች ለቢቢሲ ተናገሩ።-በከተማዋ ሦስት ቀበሌዎች ዛሬ አርብ የካቲት 22/2016 ዓ.ም. ማለዳ 12፡00 ሰዓት ላይ ውጊያው መጀመሩን የተናገሩት አራት ነዋሪዎች፤ የከባድ መሳሪያ ድምጾችንም መስማታቸውን ተናግረዋል።-የክልሉ መንግሥት ረፋድ ላይ ባወጣው መግለጫ በባሕር ዳር ዙሪያ የመከላከያ ሠራዊት እና የክልሉ የፀጥታ ኃይል በጋራ በመሆን ሰርጎ ገብቷል ያለውን “ጽንፈኛ ቡድን በየቤቱ የማሰስ እና የማጽዳት ሥራ እየሠራ ይገኛል” ይገኛል ብሏል።-ለደኅንነታቸው ሲሉ ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ ቢቢሲ ያናገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች በቀበሌ 14 አቡነ ሃራ እና ልደታ በሚባሉ የመኖሪያ ሰፈሮች፤ እንዲሁም ቀበሌ 11 አባይ ማዶ እየተባለ በሚጠራ ሰፈር እና ቀበሌ 13 በዓታ ቤተ ክርስቲያን ወይም ወራሚት አካባቢ ውጊያ መደረጉን ተናግረዋል።-አንድ የከተማዋ ነዋሪ “...ከጠዋቱ 12፡20 ጀምሮ ውጊያ ነበር። ቅርብ ለቅርብ የሚመስል የክላሽ ድምጽ ነበር። ይህም እስከ 1፡40 አካባቢ ድረስ የቀጠለ ነበር። በማስከተል ድግሞ የከባድ መሳሪያ፤ ትልልቅ መሳሪያዎች ድምጽ ይሰሙ ነበር” ብለዋል።-አባይ ማዶ በተባለው አካባቢ ከሦስት ቀናት በፊት ጀምሮ የተኩስ ልውውጦች እንደነበሩ የተናገሩት ሌላ ነዋሪ፤ አየር ጤና በተባለው ሰፈር “ሌሊቱን ሙሉ” በመከላከያ እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ውጊያ እንደነበር ተናግረዋል።-በመኖሪያ ሰፈሮች አካባቢ ተደርጓል የተባለው የዛሬው ውጊያ ለአንድ ሰዓት ያህል ተጋግሎ መደረጉንና ረፋድ 3፡00 ሰዓት አካባቢ ጋብ ማለቱን ነዋሪዎች ገልጸዋል። ከዚያም በኋላ ረፋድ ላይ አልፎ አልፎ የተኩስ ድምጾች ይሰሙ ነበር ብለዋል።-ትናንት ሐሙስ የካቲት 21/2016 ዓ.ም. ምሽት ላይ “ውጊያ ሊኖር ይችላል ተጠንቀቁ” የሚል መረጃ እንደሰሙ የተናገሩት አንድ የመንግሥት ሠራተኛ ጥዋት 12፡00 ሰዓት አካባቢ የተኩስ ድምጽ መስማታቸውን ተናግረዋል።-ግለሰቡ የተኩስ ልውውጡ በተደረገበት አንደኛው ቀበሌ ውስጥ ነዋሪ ሲሆኑ፤ ይሰማ የነበረው “የተኩስ ልውውጥም በከባድ መሳሪያ የታገዘ ነበር” ብለዋል።-ውጊያ የመኖሪያ ሰፈሮች አካባቢ ላይ ቢደረግም እስካሁን ሰላማዊ ሠዎች ላይ ጉዳት ስለመድረሱ ለማወቅ እንዳልቻሉ የተናገሩት ነዋሪዎች፤ ከባድ የተኩስ ልውውጥ ከተሰማ በኋላ በከተማዋ “ምንም አይነት እንቅስቃሴ የለም” ብለዋል።-“ትምህርት ቤት የሚሄዱ ልጆች ነበሩ። ምግባቸውን አዘጋጅተን ነበር [ትምህርት ቤት] ለመላክ። ነገር ግን 12፡00 ሰዓት አካባቢ ተኩሱ ሲጀመር . . . አስቀረናቸው። እኛም ሥራ አልሄድንም” ሲሉ በከተማዋን አርብ ጠዋት ላይ የነበረውን ሁኔታ ገልጸዋል።-የፋኖ ታጣቂዎች ሳይሆኑ አይቀሩም ያሏቸው “ታጣቂዎች” በሰፈራቸው በኩል ከተማዋን ለቀው መውጣታቸውን መመልከታቸውንም ጠቅሰው ውጊያው የረገበው “ለዚህ ይመስላል” ብለዋል።-“ከተማዋ ጸጥ ረጭ ብላለች” ያሉት ሌላ ነዋሪ፤ ከቤታቸው መውጣት ስላልቻሉ “ምን እንደተፈጠረ ማወቅ አልቻልንም” ሲሉ እንቅስቃሴ እንደሌለ ተናግረዋል።-“ምንም አይነት የትራንስፖርት እንቅስቃሴ የለም። ሱቆች እና ሆቴሎች ሁሉም ተዘግተዋል። ሰው በመኖሪያ ሰፈሩ አካባቢ በር ላይ ብቻ ነው ቆሞ የሚታየው” ብለዋል።-የልጆች አባት እንደሆኑ የተናገሩ አንድ ነዋሪ ስጋት ውስጥ መሆናቸውን ተናግረው፤ “የንጹሃን እልቂት” ይደርሳል የሚል ፍርሃት እንዳላቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል።-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከአዲስ አበባ ወደ ባሕር ዳር እና ከባሕር ዳር አዲስ አበባ ተይዘው የነበሩ በረራዎችን ለመሰረዝ መገደዱን ቢቢሲ አረጋግጧል።-ለዛሬ አርብ የተያዙ ስድስት የሚደርሱ በረራዎች መሰረዛቸው የታወቀ ሲሆን፤ በረራው መቼ ሊጀመር እንደሚችል “ማወቅ አይቻልም” ተብሏል።-ዛሬ ረፋድ ላይ መግለጫ ያወጣው የአማራ ክልል መንግሥት በባሕር ዳሩ ዙሪያ “ሰርጎ ገቦችን” መዋጋቱን ገልጾ፤ በውጊያ የበላይነትን መቀናጀቱን ጠቁሟል።-በአሁኑ ሰዓት ሙሉ በሙሉ የባሕር ዳር ከተማ እና አካባቢው “ጽንፈኛ” ሲል ከጠራው ቡድን እንደጸዳ እና በተጨማሪም የፋኖ አባላትን እያሰሰ መሆኑንም አስታውቋል።-የክልሉ መስተዳደር በመግለጫው “ሕግ ማስከበር” ላለው እርምጃ ሕዝቡ ከጎኑ በመቆም “ለሰላም ዘብ ሊሆን ይገባል” በማለት ጥሪ አቅርቧል።-በባሕር ዳር ከተማ በመንግሥት እና በፋኖ ኃይሎች መካከል ውጊያ ሲደረግ የዛሬው የመጀመሪያ አይደለም። ግጭቱ በተቀሰቀሰበት ጊዜ የፋኖ ታጣቂዎች ወደ በርካታ የክልሉ ከተሞች ገብተው የነበረ ሲሆን፣ በባሕር ዳር እና በዙሪያዋ ውጊያዎች መካሄዳቸው ይታወሳል።-በወቅቱም የመንግሥት ኃይሎች በወሰዱት እርምጃ በከተማዋ የተለያዩ ክፍሎች ከሕግ ውጪ ሰላማዊ ሠዎችን መግደላቸውን አምነስቲ ኢንተርናሽናል በምርመራው ማረጋገጡን ከሰሞኑን ይፋ አድርጓል።-ይህኑ ግድያ በማስታወስ አንድ የከተማዋ ነዋሪ “ባለፈውም እንደሆነው ንጹሃን ያልቃሉ ብለን እንሰጋለን፤ የሚያሳስበን ነገር እሱ ነው” ሲል ተናግረዋል።-“...[የመንግሥት ኃይሎች] ‘እናንተ የፋኖ መደበቂያ ናችሁ፤ እናንተ ናችሁ እንደዚህ እንዲሆን የምታደርጉት’ ስለሚሉ ሠው ይፈራል። ለዚህ ይመስለኛል ሁሉም ነገር ጸጥ ያለው” በማለት ከዚህ ቀደም እንደሆነው ግድያ ይፈጸማል የሚል ስጋት እንዳለ ጠቁመዋል።-ሌላ ነዋሪም “የመንግሥት ኃይሎች “ፋኖን ትደግፋላችሁ” በሚል ሌላ አካባቢ እርምጃ ስለወሰዱ እኛ ላይም ይከሰታል የሚል ስጋት ሕዝቡ ላይ አለ” ሲሉ ስጋታቸውን ተናግረዋል።-ካለፈው ሳምንት መገባደጃ ጀምሮ በአማራ ክልል በመንግሥት ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ውጊያ ማገርሸቱ ታውቋል።-በተለይም በጎጃም እና በሸዋ አካባቢዎች “ከባድ ውጊያዎች” እተደረጉ መሆኑን ነዋሪዎች ለቢቢሲ ተናግረዋል።-ከዚህም ጋር ተያይዞ ከደብረ ብርሃን ወደ ደሴ የሚወስደው መንገድ ከቅዳሜ፣ የካቲት 16/2016 ዓ.ም. ጀምሮ ላልተወሰነ ጊዜ መዘጋቱን የማዕከላዊ ሸዋ ኮማንድ ፖስት መወሰኑን ማስታወቁ ይታወሳል።-ካለፈው ዓመት አጋማሽ በኋላ የክልሉን ልዩ ኃይል ለመበተን እና ታጣቂዎችን ትጥቅ ለማስፈታት የተላለፈውን ውሳኔ ተከትሎ በተለያዩ የአማራ ክልል አካባቢዎች የሚንቀሳቀሱት የፋኖ ታጣቂዎች ከፀጥታ ኃይሎች ጋር ግጭት ውስጥ መግባታቸው ይታወሳል።-የክልሉ መስተዳደርም ሁኔታው ከአቅሙ በላይ መሆኑን በመግለጽ የፌደራል መንግሥቱ ጣልቃ እንዲገባ በመጠየቁ በክልሉ እና እንዳስፈላጊነቱ በመላው አገሪቱ ተግባራዊ የሚሆን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተጥሎ የፌደራሉ መንግሥት ሠራዊት ወደ ክልሉ ተሰማርቶ ይገኛል።-ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ በተካሄዱ ወታደራዊ ግጭቶች በበርካታ የክልሉ አካባቢዎች ውስጥ መደበኛ እንቅስቃሴዎች የተስተጓጎሉ መሆናቸውነ ነዋሪዎች ሲናገሩ ቆይተዋል።-በተጨማሪም በመከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ኃይሎች መካከል በሚካሄዱ ውጊያዎች እና በሚፈጸሙ ጥቃቶች ምክንያት በርካታ ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውነ እና የንብረት ውድመት ማጋጠሙ እየተዘገበ ነው።
|
የፎቶው ባለመብት GoFundMe-በአሜሪካ መንገድ ተሳስታ በገጠር የመኪና ጥርጊያ መንገድ ላይ መኪናዋን ያስገባችውን የ20 ዓመት ወጣት ተኩሶ የገደለው ግለሰብ በ25 ዓመት እስር ተቀጣ።-ሟቿ ኬይሊን ጊሊስ እና ጓደኞቿ ከጥቂት ወራት በፊት በኒውዮርክ ግዛት የሚሄዱበትን ድግስ (ፓርቲ) አድራሻ እየፈለጉ በነበረበት ወቅት ነው ወደ ግለሰቡ የጥርጊያ መንገድ በስህተት የገቡት።-ኬቨን ሞናሃን የተባለው ይህ ግለሰብ ጊሊስን አንገቷ ላይ በጥይት ከመታት በኋላም ሕይወቷ አልፏል።-የ66 ዓመቱ ግለሰብ በሁለተኛ ደረጃ የግድያ ወንጀል ጥፋተኛ ሆኖ የተገኘው በጥር ወር ሲሆን፣ ዐቃቤ ሕግ ከፍተኛው የተባለውን የ25 ዓመት እስራትም እንዲቀጣ ጠይቋል።-ዳኞቹም ግለሰቡን በግድያ ወንጀል እንዲሁም በግዴለሽነት የሰዎችን ሕይወት አደጋ ውስጥ በመክተት እና ማስረጃዎችን በማበላሸት ጥፋተኛ ሆኖ አግኝተውታል።-አርብ ዕለት ውሳኔው የተላለፈበት ሞናሃን በችሎቱ ላይ ለመናገር የተሰጠውን ዕድል ውድቅ አድርጓል።-ከፍርድ ቤቱም ሲወጣ አንድ ሰው “ፈሪ” በማለትም እንደዘለፈው የኤፒ የዜና ወኪል ዘግቧል።-“በመኪና መንገድዎ ላይ ስላዞሩ ሰዎች ላይ በጥይት መተኮስ እንዲሁም መግደል እንደማይቻል ሊገነዘቡ ያስፈልጋል ብዬ አስባለሁ” ሲሉም ዳኛው አዳም ሚሼሊኒ መናገራቸውን የቢቢሲ የአሜሪካ አጋር የሆነው ሲቢኤስ ዘግቧል።-ጊሊስ እና ጓደኞቿ ከጥቂት ወራት በፊት ከአልባኒ በስተሰሜን ምሥራቅ 88 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ኬብሮን በተሰኘች ትንሽ ከተማ ወደ ሞናሃን ረጅም እና ጠመዝማዛ የመኪና መንገድ የገቡት የድግስ አድራሻ ፍለጋ ነበሩ።-ይህች ገጠራማ ቦታም ደካማ የሞባይል አገልግሎት ያላት ናት ተብሏል።-ጊልስና ጓደኞቿን በዙሪያው ያገኘው ግለሰቡ “በወራሪዎች ተከብቤያለሁ” ብሎ እንዳሰበም ተናግሯል።-ሟቿ እና ጓደኞቿ የተሳሳተ ስፍራ ውስጥ እንደገቡ ሲያውቁ መኪናቸውን ሲያዞሩ ግለሰቡ ከቤቱ ወጥቶ ከበረንዳ ላይ ሁለት ጥይቶችን ተኩሷል።-ሁለተኛውም ጥይት መኪናውን ሲያሽከረክር ከነበረው የወንድ ጓደኛዋ አጠገብ የተቀመጠችውን ጊሊስን ያገኛት ሲሆን ሕይወቷም አልፏል።-የወንድ ጓደኛዋ ገዳዩን ሞናሃን “በፍጹም ይቅር ሊለው እንደማይችልም” ተናግሯል።-የሞናሃን ጎረቤት እንደተናገሩት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሞናሃን ተሳስተው በመንገዱ በሚያዞሩ ሰዎች በጣም እየተበሳጨ እንደነበር ተናግረዋል።-የጊሊስ ጓደኞች በመኪና መንገዱ ላይ የነበረውን የግል የሚለውን ምልክት እንዳላስተዋሉ በችሎቱ መስክረዋል።
|
የፎቶው ባለመብት Ethiopian Federal Police-በእሳት ከተቃጠሉ ንብረቶች አንዱ የሆነው ተሽከርካሪ-በስድስት ወራት ከደረሱት የእሳት ቃጠሎዎች 16 ያህሉ ሆን ተብለው የተፈጸሙ መሆናቸውን እና ከእነዚህም መካከል 15ቱ በአዲስ አበባ መከሰታቸውን የፌደራል ፖሊስ በፎረንሲክ ምርመራ ማረጋገጡን አስታወቀ።-በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በመላው አገሪቱ ከደረሱት የእሳት አደጋዎች መካከል 90 በመቶ በላይ የሚሆኑት የደረሱት በዋና ከተማዋ ውስጥ እንደሆነ ፖሊስ ተገልጿል።-በ2016 የበጀት ዓመት የመጀመሪያ ስድስት ወራት ውስጥ በአገር አቀፍ ደረጃ 139 የእሳት ቃጠሎዎች መድረሳቸውን የፌዴራል ፖሊስ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጄይላን አብዲ ለቢቢሲ ተናግረዋል።-ከእነዚህ የእሳት አደጋዎች ውስጥ 130 ያህሉ የተከሰቱት በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ መሆኑን ኃላፊው አመልክተው፣ ቀሪዎቹ ዘጠኝ ቃጠሎዎች የተከሰቱት በአፋር፣ በደቡብ ኢትዮጵያ እና በሐረሪ ክልሎች መሆኑንም አክለዋል።-የፌደራል ፖሊስ የእሳት ቃጠሎዎቹን መንስኤ ለማወቅ የፎረንሲክ ምርመራ ማድረጉን የሚገልጹት አቶ ጄይላን፤ በተደረገው ምርመራ ከስምንቱ ውጪ የሌሎቹ ቃጠሎዎች ምክንያት መለየቱን አስረድተዋል። ባለፉት ስድስት ወራት ለተከሰቱ የእሳት ቃጠሎዎች በቀዳሚነት የተጠቀሰው ምክንያት በኤሌክትሪክ የቴክኒክ ችግር መሆኑንም ጠቅሰዋል።-በዚህ ምክንያት የደረሱ የእሳት አደጋዎች ብዛት 76 መሆናቸውን የተናገሩት አቶ ጄይላን፤ ይህ ቁጥር ከአምናው ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር ተመሳሳይ መሆኑን ገልጸዋል። ለ24 የእሳት አደጋዎች መነሻ በመሆን በሁለተኛነት የተቀመጠው ጉዳይ በተለያዩ ምክንያቶች የሚፈጠር የመካኒካል ችግር እንደሆነ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው አንስተዋል።-የፌደራል ፖሊስ የፎረንሲክ ምርመራ እንደሚያመለክተው ሆን ብሎ የእሳት ቃጠሎ እንዲከሰት ማድረግ በስድስቱ ወራት ውስጥ ለተከሰቱት ቃጠሎዎች ሌላ ምክንያት ነው። በዚህ መልኩ በአዲስ አበባ ከተማ 15 እና በአፋር ክልል ደግሞ አንድ የእሳት ቃጠሎዎች ሆን ተብለው መከሰታቸውን አቶ ጄይላን ጠቅሰዋል።-ግለሰቦች የኢንሹራንስ ካሳ ለማግኘት፣ የራስን ጥቅም ለማስጠበቅ ወይም ሌላ ሰው ላይ ጉዳት ለማድረስ ሲሉ ሆነ ብለው የእሳት ቃጠሎ እንደሚያስነሱ እንደተሰደረበትም ገልጸዋል።-አቶ ጄይላን፤ “ኢንሹራንስ ለማግኘት ያረጀ ወይም አልሸጥ ያለ መኪና አቃጥለው ‘በእሳት አደጋ ነው’ ብለው ኢንሹራንስ [ጉዳቱን] እንዲሸፍንላቸው የሚፈልጉ አሉ” ሲሉ አንዱን ምክንያት ለቢቢሲ ጠቅሰዋል።-ይህ ዓይነቱ ቃጠሎ በብዛት በተሽከርካሪዎች ላይ እንደሚደርስ እና ቤቶችም እንደሚገኙበት አንስተዋል። ሆነ ብሎ የእሳት ቃጠሎ ከማስነሳት ጋር በተያያዘ በቁጥጥር ስር የዋሉ ሰዎች መኖራቸውን የጠቀሱት አቶ ጄይላን፤ ምን ያህል ሰዎች እንደተያዙ እና የደረሰውን አደጋ መጠን ከመግለጽ ተቆጥበዋል።-የፌዴራል ፖሊስ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው እንደሚያስረዱት በስድስት ወራቱ ውስጥ በዚህ ዓይነቱ ምክንያት የደረሱት የእሳት አደጋዎች ብዛት ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ ጋር ሲነጻጸር በስድስት ቀንሷል።-በአጠቃላይ ከደረሱት የእሳት ቃጠሎዎች መካከል 15 ያህሉ በቸልተኝነት እና በጥንቃቄ ጉድለት ምክንያት የተከሰቱ መሆናቸውን አቶ ጄይላን ተናግረዋል።-በስድስት ወራት ውስጥ በተከሰቱት የእሳት ቃጠሎዎች ምክንያት በሰው ላይ ስለደረሰው ጉዳት እና በንብረት ላይ የደረሰውን የውድመት መጠንን በተመለከተ የተሰጠ አሃዝ የለም።
|
-በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ ጉዳት የደረሰባቸው ድሃ አገራትን ለመደጎም አዲስ በጀት ጸድቋል። ነገር ግን ለደረሰው ውድመት የላቀ ድርሻ ማዋጣት ያለበት ማን ነው? በሚለው ዙሪያ ክርክሮች አሉ።-በሌላ በኩል አዲስ በመበልጸግ ላይ የሚገኙ እንደ ቻይና እና ህንድ የመሳሰሉ አገራት ደግሞ ከምዕራባውያን ጋር እኩል ማዋጣት የለብንም የሚል ሃሳብ ያነሳሉ። ለመሆኑ በጀቱ ምንድን ነው? ለማንስ ነው የሚሰጠው?
|
የፎቶው ባለመብት REUTERS-ባለፉት ሳምንታት በቀይ ባሕር በኩል በመርከቦች ጭነት ማጓጓዝ ፈታኝ ሆኗል። በኢራን የሚደገፉት የየመን ሁቲ አማጽያን በሰው አልባ አውሮፕላን እና በሚሳኤል መርከቦች ላይ ጥቃት እየፈጸሙ ነው።-ታጣቂዎቹ በተጨማሪም በጀልባ እና በሄሊኮፕተርም ጥቃት አድርሰዋል።-አብዛኛውን የመን የሚቆጣጠሩት ሁቲዎች “በጋዛ እና በዌስት ባንክ ላሉ ፍልስጤማውያን ወንድሞች” ድጋፍ እንደሚሰጡ ገልጸዋል።-ወደ እስራኤል የሚጓዙ የንግድ መርከቦችን ዒላማ እንዳደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል።-ቢቢሲ ባጣራው መረጃ መሠረት ሁቲዎች ጥቃት የሰነዘሩት በደቡባዊ ቀይ ባሕር ነው። ይህም በየመን ባሕር ዳርቻ በባብ ኤል-ማንዳብ መተላለፊያ ላይ ነው።-ወደ ኤደን ባሕረ ሰላጤ የሚጓዙ መርከቦች ላይም ጥቃት ተሰንዝሯል።-ነገር ግን በጥቃቱ ዒላማቸውን የመቱት የተወሰኑት ብቻ ናቸው። ከእነዚህም መካከል እአአ ጥር 17 የተፈጸመው ጥቃት ይገኝበታል።-በዚህም በአሜሪካ መርከብ ላይ ነበር ጥቃቱ የተቃጣው። ነገር ግን መርከቡ በሁቲዎች ድሮን ጎኑ ላይ ቢመታም ጉዞውን ቀጥሏል።-ጥቃቱን የሚያሳይ ምሥል ያነሳው የሕንድ የባሕር ተዋጊ መርከብ ነበር። ይህም የሁቲዎችን ጥቃት ለመመከት ያለውን ትብብር ማሳያም ነው።-የተለያዩ የጦር መሣሪያዎችን ነው ሁቲዎች የሚጠቀሙት።-በተለይ ደግሞ ሚሳኤሎች እና ድሮኖችን ይጠቀማሉ።-ቃስፍ-1 እና ቃስፍ-2 ድሮኖች አሏቸው። እነዚህም እስከ 200 ኪሎ ሜትር የሚወነጨፉ ናቸው። እስከ 1800 ኪሎ ሜትር የሚምዘገዘጉ መሣሪያዎችም አሏቸው። በ800 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ያለ መርከብን ማጥቃት ይችላሉ ማለት ነው።-ሁቲዎች ትናንሽ ጀልባዎችን በመጠቀም መርከቦች ላይ ጥቃት ሰንዝረዋል።-ሄሊኮፕተር በመጠቀም መርከብ ላይ ጥቃት የሰነዘሩበትም ወቅት ነበር።-በሄሊኮፕተር መርከብ ላይ የወረዱት ጥቃት አድራሾች አንድ መርከብን አግተዋል። ጋላክሲ ሊደር የተባለው መርከብ አሁንም በየመን ባሕር ዳርቻ እንደተያዘ ነው።-የየመን የእርስ በእርስ ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ ከአገሪቱ መንግሥት የተወሰዱ መሣሪያዎች በሁቲዎች እጅ ናቸው።-የተባበሩት መንግሥታት እንደሚለው፣ ከምሥራቅ እስያ በሲቪሎች አማካይነት የተገኙም መሣሪያዎች አሏቸው።-አብዛኞቹ ዘመናዊ ድሮኖች እና ሚሳኤሎች ግን ከኢራን እንደተገኙ በስፋት ይነገራል።-አሜሪካ እንዳለችው፣ ከየመን ወደ ኢራን በዓሣ ማስገሪያ ጀልባ ተጭኖ እየተጓዘ የነበረ የሚሳኤል እና የአየር መቃወሚያ ይዛለች።-ወታደራዊ ተንታኞች እንዳሉት ኤምቪ ቤሻድ የተባለ የኢራን መርከብ ሁቲዎች ዒላማ እንዲመቱ እያገዘ ነው።-ቀድሞ ማጓጓዣ የነበረው መርከብ አሁን የደኅንነት መቆጣጠሪያ መሆኑን ያስረዳሉ።-ቢቢሲ ከኢራን መንግሥት ምላሽ ለማግኘት ቢጠይቅም ምላሽ አላገኘም።-የፎቶው ባለመብት INDIAN NAVY-በቀጠናው የደኅንነት ቡድን የመሩት ክሪስ ፋረል እንደሚሉት፣ የተለያየ ቁሳቁስ የጫኑ መርከቦች ጥበቃ የሚደረግላቸው ቢሆንም ከአየር የሚደረግ ጥቃትን መከላከል የሚያስችል መሣሪያ ግን የላቸውም።-ይህ በቀይ ባሕር በኩል የሚያቋርጡ “የንግድ መርከቦች ከረዥም ጊዜ በኋላ የገጠማቸው ከባድ ችግር ነው” ይላሉ።-ዓለም አቀፍ ምላሽ ከመጠናከሩ ጋር በተያያዘ አሜሪካ እና ዩናይትድ ኪንግደም በጋራ በየመን የሁቲ አማጽያን ይዞታዎች ላይ የአየር ጥቃት ፈጽመዋል።-በዚህም ሁለቱ አገራት የአማጽያኑን ወታደራዊ አቅም ለማዳከም ያለመ ጥቃት ነበር የሰነዘሩት።-ሆኖም ግን የየመንን ሰፊ ተራራማ አካባቢዎች ሁቲዎች ይቆጣጠራሉ።-መደበቅ የሚችሉትም በዚህ ምክንያት እንደሆነ ወታደራዊ ተንታኞች ይናገራሉ።-ባለፈው ታኅሣሥ በአሜሪካ የሚመራ ወታደራዊ ጥምረት የንግድ መርከቦችን ለመጠበቅ እንደሚሠራ ተገልጿል።-በዚህም ቀይ ባሕርን የመቆጣጠር ሥራ የሚሠሩ ሲሆን ዩናይትድ ኪንግደም ለዚህ ተግባር መርከብ እንደምታቀርብ አስታውቃለች።-ከአሜሪካ ጥምረት ውጪ እንደ ፈረንሳይ ያሉ አገራትም በቀጠናው መቆጣጠሪያ ጣቢያ አላቸው።-የአሜሪካ የባሕር ኃይል ካፕቴን ብራድሊ ማርቲን እንደሚሉት የተለያዩ ዓለም አቀፍ አጋሮችን ማስተባበር ፈታኝ ነው።-ባሕሩ ላይ የሚከናወነውን ጥበቃ የሚያካሂዱትን መርከቦቹ ነዳጅ ሞልቶ መሣሪያ ማስታጠቅም ከፍተኛ ወጪን ይጠይቃል።-ከሁቲዎች የሚተኮሱትን እንደ ሲ ቫይፐር ያሉ ሚሳኤሎችን መከላከል በሚሊዮን ዶላር የሚያስወጣ ነው።-በተቃራኒው ሁቲዎች የድሮን ጥቃት ለመፈጸም የሚያወጡት በሺዎች የሚቆጠር ዶላር ነው።-የፎቶው ባለመብት EPA-በርካታ ተቋማት መርከባቸው በቀይ ባሕር እንዳይጓዝ እያደረጉ ነው።-ይህ ማለት ደግሞ ኬፕ ኦፍ ጉድ ሆፕ በተባለው የአፍሪካ ዳርቻ መንገድ ለመጓዝ ከፍተኛ ወጪን ያወጣሉ ማለት ነው።-ለጅሙን የውቅያኖስ ላይ ዙሪያ ጥምጥም መንገድ በማስቀረት በቀይ ባሕር ለመጓዝ የመረጡ ደኅንነታቸውን ለመጠበቅ አማራጮች እየተጠቀሙ ነው።-አንደኛው መንገድ የመርከቦችን አቅጣጫ የሚጠቁም መከታተያ ሥርዓት መዘርጋት ነው። ይህም ኤአይኤስ ትራኪንግ ይባላለል።-የመከታተያ ሥርዓቱ የሁቲ አማጽያን መርከቦቹን እንዳያገኙ የሚያግዝ ነው።-አንዳንድ መርከቦች ደግሞ “ከእስራኤል ጋር ግንኙነት የለንም” ብለው መርከባቸው ላይ ይጽፋሉ።-መርከቡ ላይ “ታጣቂዎች አሉ” ወይም “ሠራተኞቹ ቻይናውያን ብቻ ናቸው” ብለው የሚጽፉም አሉ።-አሜሪካና ዩናይትድ ኪንግደም በቅርቡ ጥቃት ቢፈጽሙም ሁቲዎች ጉዳት የማድረስ አቅማቸው እንዳለ መሆኑን ወታደራዊ ተንታኙ ያስረዳሉ።-“ጥቃቱን መቀነስ ይቻላል። ነገር ግን ችግሩ የሚፈታው ለጋዛ ግጭት ፖለቲካዊ መፍትሄ ሲሰጥ ነው። መርከቦችን በመከላከል ብቻ ጥቃቱን ማቆም አይቻልም” ይላሉ።
|
የፎቶው ባለመብት Getty Images-የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን በጋዛ እስከ ሰኞ ድረስ የተኩስ አቁም እንደሚኖር ተስፋ አደርጋለሁ ሲሉ ገለጹ።-አስተያየቱን የሰጡት የእስራኤል እና የሐማስ ባለስልጣናትን አሳትፏል የተባባለ ቀጥተኛ ያልሆነ ድርድር ላይ መጠነኛ መሻሻል እንዳለ በተዘገበበት ወቅት ነው።-ይህም እስራኤል በሙሉ ከበባ ውስጥ ባስገባቻት ጋዛ እርዳታ እንዲገባ እና መስከረም 26 የተፈጸመውን የሐማስ ጥቃት ተከትሎ የተወሰዱ ታጋቾችን መልቀቅን ያካትታል።-እስራኤል በጉዳዩ ላይ አስተያየት ባትሰጥም የሐማስ ባለስልጣናት ግን ባይደን እንደጠቆሙት ሁለቱ ወገኖች የተኩስ አቁም ስምምነት ለመድረስ ጫፍ ላይ እንዳልደረሱ ጠቁመዋል።-ከግብጽ ጋር ድርድሩን በማካሄድ ላይ የምትገኘው ኳታር ይፋ ሊደረግ የሚችል ምንም አይነት ስምምነት እንደሌለ ተናግራለች።-የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ማጅድ አል-አንሷሪ እንዳሉት ዶሃ "የረመዳን ጾም ከመጀመሩ በፊት ጦርነቱ እንዲቆም ታበረታታለች። ሂደቱ ተስፋ ቢኖረውም ብሩህ አይደለም" ብለዋል።-በደቡብ እስራኤል የሐማስ ታጣቂዎች ወደ አንድ ሺህ 200 የሚጠጉ ሰዎችን ከገደሉ በኋላ እስራኤል በጋዛ መጠነ ሰፊ እና የማያባራ ጥቃት መጀመሯ ይታወሳል።-ጥቃት አድራሾቹ 253 ሰዎችን አግተው የወሰዱ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ የተወሰኑት ተለቀዋል።-በጋዛ እስራኤል እያደረገችው ባለው የተቀናጀ የአየር፣ የምድር እና የውሃ ላይ ጥቃት ቢያንስ 97 ሺህ 878 ሰዎች ሲገደሉ፤ 70 ሺህ 215 መቁሰላቸውን የጋዛ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል። በሐማስ አስተዳደር ስር ባለው የጋዛ ጤና ሚኒስቴር መሰረት ባለፉት 24 ሰዓታት ብቻ 96 ሰዎች መገደላቸውን ገልጿል።-ሮይተርስ የዜና ወኪል ለድርድሩ ቅርብ የሆኑ ስማቸውን ያልገለጸው ምንጭን ጠቅሶ እንደዘገበው ሐማስ በፈረንሣይ የተቀረፀውን ረቂቅ የድርድር ማዕቀፍ በማጥናት ላይ ይገኛል።-ማዕቀፉ ሁሉም ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች ለ40 ቀናት እንዲቋረጡ እና በእስራኤል እስር ቤቶች ውስጥ የሚገኙ ፍልስጤማውያን 1 ለ 10 ስምምነት ከእስራኤላውያን ታጋቾች መለዋወጥን ያካትታል።-ፕሬዝዳንት ባይደን ሰኞ ዕለት በኒውዮርክ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት “ከጫፍ ደርሰናል። እስካሁን ግን አልተጠናቀቀም። ተስፋዬ እስከሚቀጥለው ሰኞ ድረስ የተኩስ አቁም እናደርጋለን የሚል ነው" ብለዋል።-በኋላም በኤንቢሲ ላይ የቀረቡት ፕሬዚዳንቱ ስምምነቱ ከተደረሰ እስራኤል በረመዳን ጥቃቷን ለማቆም ፈቃደኛ ትሆናለች ብለዋል።-የረመዳን ጾም ከአስር ቀን በኋላ ይጀመራል።-“ረመዳን እየደረሰ ነው። ታጋቾቹን በሙሉ ለማውጣት እስራኤል ጊዜ ለመስጠት በረመዳንም እንቅስቃሴ እንደማይያደርጉ ስምምነት ተደርሷል" ብለዋል ባይደን።-የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ማቲው ሚለር በበኩላቸው “ንግግሮች ይቀጥላሉ። ከእነዚህ መካከል የአንዳንዶቹ የመጨረሻው ለሐማስ የሚተዉ ይሆናል” ብለዋል ።-ሚለር አክለውም ስለ ድርድሩ ወይም ስለሚሳካበት ጊዜ ተጨማሪ አስተያየት ለመስጠት ፈቃደኛ ባይሆኑም “በዚህ ሳምንት መጨረሻ ከሆነ እሰየው… ይህንን ስምምነት እንዲደረስ እየሞከርን ነው። የሚሳካም ይመስለናል” ብለዋል።-አንድ የሐማስ ባለስልጣን ቀደም ሲል ለቢቢሲ እንደተናገሩት “ሐማስ ቅድሚያ የሚሰጠው እስረኞችን መለዋወጥ ሳይሆን ጦርነቱን ማቆም ነው።”-"ከዚህ ሁሉ የህይወት እና የንብረት ውድመት በኋላ ወደ ሙሉ የተኩስ ማቆም፤ የተፈናቀሉትን መመለስ እና የጋዛን መልሶ ግንባታ የማያመጣ ማንኛውንም ሐሳብ መቀበል ምክንያታዊ አይደለም።"-የእስራኤል ዋና አጋር የሆነችው አሜሪካ ባለፈው ሳምንት የተባበሩት መንግስታት የፀጥታው ምክር ቤት በጋዛ አፋጣኝ የተኩስ አቁም እንዲቆም የሚጠይቀውን ውሳኔ በመቃወሟ ከፍተኛ ትችት አስተናግዳለች።-"በተቻለ ፍጥነት" ጊዜያዊ የተኩስ አቁም እንዲደረስም የራሷን የውሳኔ ሃሳብ አቅርባለች። እስራኤል የደቡብ ጋዛዋ ራፋህ ከተማን "አሁን ባለው ሁኔታ" እንዳትወር አስጠንቅቃለች።-እስራኤል 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን የሚጠጉ ፍልስጤማውያን በተጠለሉባት ራፋህ ላይ ጥቃት እንዳትሰነዝር ከፍተኛ የሆነ ዓለም አቀፍ ጫና ገጥሟታል። አብዛኞቹ በግዛቱ ያሉ ሰዎች በስተሰሜን ያለውን ጦርነት ሸሽተው የተጠለሉ ናቸው።-ባይደን በቃለ ምልልሱ ወቅት “በጣም ብዙ ንፁሀን ሰዎች እየተገደሉ ነው። እስራኤል በራፋህ የምታደርሰው ጥቃት ቀንሷል። ራፋህን ከሐማስ ነጻ ከማድረጋቸው በፊት አብዛኛውን ነዋሪ ለማውጣት ለእኔ ቃል ገብተውልኛል” ብለዋል።-እሑድ ዕለት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ራፋህን ጨምሮ ከሌሎች አካባቢዎች ንፁሀን ዜጎችን ለማስወጣት ያለመውን የአገሪቱን ጦር ዕቅዶች ተቀብያለሁ ብሏል።-ኔታንያሁ እሑድ ዕለት ከሲቢኤስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የእስራኤል ኃይሎች ጊዜያዊ የተኩስ አቁም ስምምነት ቢደረስም በራፋህ ላይ ወረራ እንደሚጀምሩ በመግለጽ “የመጨረሻውን የሐማስ ምሽግ ሳንሰባብር መልቀቅ አንችልም” ሲሉ አስረግጠው ተናግረዋል።-"ስምምነት ከደረሰን በተወሰነ መልኩ ይዘገያል እንጂ ይከናወናል። ስምምነት ካልተደረሰ ግን እናደርገዋለን” ሲሉም አክለዋል።-ሰኞ ዕለት ደግሞ የፍልስጤም አስተዳደር ጠቅላይ ሚኒስትር መሐመድ ሽታይህ ዌስት ባንክን በከፊል ከሚመራው መንግሥታቸው ጋር ስልጣናቸውን ለቀዋል።-ፕሬዝዳንት ማህሙድ አባስ ለአዲስ መንግስት መንገድ ይከፍታል የተባለውን የጠቅላይ ሚንስትሩን ውሳኔ ተቀብለዋል።-የእስራኤል እና የሐማስ ጦርነት ካበቃ በኋላ ጋዛን ለማስተዳደር የፍልስጤም አስተዳደር ማሻሻያዎችን እንዲያደርግ አሜሪካ አባስ ላይ ግፊት እያደረገች ነው።-ኔታንያሁ ባለፈው ሳምንት ለለግዛቲቱ የወደፊት ዕጣ ፈንታ ሲገልጹ ስለ አስተዳደሩ ሚና ምንም አልጠቀሱም።
|
የፎቶው ባለመብት AFP-በቤት ላሂያ የሚገኘው ካማል አድዋን ሆስፒታል ከምዕራባዊቷ የጋዛ ከተማ አስክሬኖችንና የተጎዱ ሰዎችን መቀበሉን ገልጿል።-በጋዛ እርዳታ ለማግኘት በተሽከርካሪዎች ዙሪያ ተሰባስበው የነበሩ ቢያንስ 112 ፍልስጤማውያን ሲገደሉ፣ 760 የሚሆኑት ላይ ጉዳት መድረሱ ተገለጸ።-ሐሙስ ዕለት በርካቶች የተገደሉበት ክስተት ያጋጠመው በምግብ እጦት የተሰቃዩት ሰዎች በጋዛ በስተደቡብ ምዕራብ በሚገኘው የባህር ዳርቻ መንገድ ላይ በእስራኤል ታንኮች ታጅበው እየተጓዙ ከነበሩ ተሽከርካሪዎች እርዳታ ለማውረድ ሲሞክሩ ነበር።-የእስራኤል ጦር፣ታንክ የተተኮሰው ለማስጠንቀቂያ እንደሆነና የእርዳታ ተሽከርካሪዎቹን እንዳልመታ ገልጿል።-ሆኖም አንዳንድ ፍልስጤማውያን የእስራኤል ወታደሮች ቀጥታ ወደ እነሱ እንደተኮሱባቸው ተናግረዋል።-አንድ ፍልስጤማዊ የዓይን እማኝ ለቢቢሲ እንደተናገሩት አብዛኞቹ ሰዎች የሞቱት እርዳታ የጫኑት መኪኖች አሽከርካሪዎች ወደ ፊት ለመጓዝ በሚሞክሩበት ወቅት ተገጭተው ነው።-የግብፅን እርዳታ የጫኑ 30 ተሽከርካሪዎች በሰላማዊ ሰዎች የተከበቡት የእስራኤል መከላከያ ኃይል “የእርዳታ ማስተላለፊያ ኮሪደር” ባለው ቦታ እየተጓዙ ሳለ ነበር።-ይህ ክስተት ያጋጠመው የጋዛ ጤና ሚኒስቴር በእስራኤል እና ሐማስ መካከል ግጭት ከተከሰተ አንስቶ 21 ሺህ ሕጻናትና ሴቶችን ጨምሮ ከ30 ሺህ በላይ ሰዎች መገደላቸውን ካስታወቀ ከሰዓታት በኋላ ነው።-ሚኒስቴሩ ሰባት ሺህ የሚሆኑ ሰዎች እንደጠፉ እና 70 ሺህ 450 የሚሆኑት ላይ ጉዳት እንደደረሰባቸውም አክሏል።-የፎቶው ባለመብት ISRAEL DEFENSE FORCES-የእስራኤል ጦር በመቶዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን በእርዳታ ተሽከርካሪዎቹ ዙሪያ ተሰባስበው የሚያሳይ ተንቀሳቃሽ ምስል አውጥቷል።-ከላይ ሆነው የተነሱ የእስራኤል ምስሎች በተሽከርካሪዎቹ ዙሪያ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተሰባስበው ያሳያሉ። በማኅበራዊ ሚዲያ የተጋሩ ምስሎች ደግሞ ባዶ የእርዳታ መኪናዎች እና የአህያ ጋሪዎች ላይ የተጫኑ አስክሬኖችን አሳይተዋል።-በዚህ ክስተት 112 ሰዎች መገደላቸውንና 760 መጎዳታቸውን የገለጸው በሐማስ የሚተዳደረው የጋዛ ጤና ሚኒስቴር እስራኤልን “ በጅምላ ጭፍጨፋ” ከሷል።-የተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤትም በዚህ ጉዳይ ላይ ለመነጋገር አስቸኳይ ዝግ ስብሰባ ለማካሄድ እቅድ ይዟል።-ፈረንሳይም የእስራኤል ወታደሮች ምግብ ለማግኘት የተሰባሰቡ ሰላማዊ ሰዎች ላይ መተኮሳቸው ፍትሐዊ አይደለም ብላለች።-የአሜሪካው ፕሬዚደንት ጆ ባይደን በበኩላቸው ይህ ክስተት በእስራኤል እና ሐማስ መካከል ጊዜያዊ የተኩስ አቁም እንዲደረግ በአደራዳሪዎች እየተደረገ ያለውን ጥረት ያወሳስባል ብለዋል።-ግብረ ሰናይ ድርጅቱ ድንበር የለሽ የሐኪሞች ቡድን (ኤምኤስኤፍ) ክስተቱን “ አሰቃቂ” ያለው ሲሆን አስቸኳይ እና ዘላቂነት ያለው የተኩስ አቁም እንዲደረግ ጥሪ አቅርቧል።-የፍልስጤም ፕሬዚደንት ሞሃሙድ አባስም “አስከፊ ጭፍጨፋ” በመፈፀም የእስራኤልን ኃይሎች ከሰዋል።-የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ድርጊቱን አውግዘው አስቸኳይ ሰብዓዊ የተኩስ አቁም እንዲደረግ እና ያለቅድመ ሁኔታ የእስራኤል ታጋቾች እንዲለቀቁ በድጋሜ ጥሪ አቅርበዋል።-ሰሜን ጋዛ እስራኤል በመጀመሪያው ምዕራፍ ባካሄደችው መጠነ ሰፊ የምድር ጥቃት ውድመት የደረሰበት ሲሆን ሰብዓዊ እርዳታ ወደ ሥፍራው መድረስ ከቆመ በርካታ ወራት ተቆጥረዋል።-ባለፈው ሳምንት የዓለም ምግብ ፕሮግራም እርዳታ የጫኑ ተሽከርካሪዎቹ በእስራኤል ፍተሻ ጣቢያ አቅራቢያ በተራቡ ሰዎች በመከበቡ ወደ አካባቢው የሚያደርሰውን እርዳታ ለማቋረጥ መገደዱን ገልጿል።-ማክሰኞ ዕለት የተባበሩት መንግሥታት የእርዳታ ባለሥልጣን በጋዛ ሰርጥ ካለው ሕዝብ ሩብ የሚያህለው [576 ሺህ ሰዎች] አስከፊ ለሆነ የምግብ እጥረት መዳረጋቸውን እና ከሁለት ዓመት በታች ከሆኑ ስድስት ሕጻናት አንዱ በከፍተኛ የምግብ እጥረት መጋለጡን በመግለጽ አስጠንቅቀዋል።-በቅርብ ቀናትም በሰሜን ጋዛ በሚገኝ ሆስፒታል አስር ሕጻናት በምግብ እጥረት መሞታቸውን የጋዛ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።-ተመድ ወደ 300 ሺህ የሚገመቱ ሰዎች በተጠለሉባትና በቂ ምግብ እና ንጹህ ውሃ በሌለባት የጋዛ ሰሜናዊ ግዛት ረሃብ እያንዣበበ እንደሆነ አስጠንቅቋል።-የእስራኤል ጦር ሐማስን ለማጥፋት በሚል በምድር እና በአየር መጠነ ሰፊ ጥቃት የከፈተው ባለፈው ጥቅምት ወር የሐማስ ታጣቂዎች የእስራኤልን ድንበር ዘልቀው በመግባት 1 ሺህ 200 የሚሆኑ ሰዎችን ከገደሉ እና 250 ሰዎችን አግተው ከወሰዱ በኋላ ነበር።
|
የፎቶው ባለመብት Getty Images-የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ከቀድሞው ፕሬዚዳንት ትራምፕ ይልቅ የባይደንን ፕሬዚዳንትነት እንደሚመርጡ ተናገሩ።-ባይደን የበለጠ ልምድ ያላቸው እና ሊገመት የሚችል ባህርይ ያላቸው ሰው ናቸው ሲሉም መናገራቸው በርካቶችን አስደንቋል።-ዶናልድ ትራምፕ ለመጀመሪያ ጊዜ ለፕሬዚዳንትነት ከመወዳደራቸው በፊት ፑቲን “ታላቅ እና ጎበዝ” ሲሉም በአውሮፓውያኑ 2016 አሞካሽተዋቸው ነበር።-ባይደን የሩሲያውን ፕሬዚዳንት ፑቲንን ለዓመታት በሰላ ሁኔታ በመተቸት የሚታወቁ ሲሆን ከዩክሬን ወረራ በፊትም በአንድ ወቅት “ነፍሰ ገዳይ” ሲሉ ወርፈዋቸው ነበር።-ፑቲን በቅርቡ ከአሜሪካዊው ጋዜጠኛ ታከር ካልርሰን ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ላይም አስተያየት የሰጡ ሲሆን ጥያቄዎቹ የሰሉ እና የተስተካከሉ ስላልነበሩ እንዳሳዘናቸውም ተናግረዋል።-ረቡዕ ዕለት ከሩሲያ ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የባይደን አመራር ለሩሲያ የተሻለ እንደሚሆን የተናገሩት ፑቲን ምክንያቱንም ሲጠቅሱ “የበለጠ ልምድ ያለው፣ ሊገመት የሚችል ባሕርይ፣ ፖለቲከኛ እና መሰረት ያለው ሰው ነው” ብለዋል።-ከባይደን ዕድሜ እና የአዕምሮ ብቃት ጋር ተያይዞ የሚነሱ ጥያቄዎችን ውድቅ ያደረጉት ፕሬዚዳንት ፑቲን ከሶስት ዓመታት በፊት ለመጨረሻ ጊዜ ሲገናኙም የተለየ ነገር አለማስተዋላቸውን ተናግረዋል።-“በዚያን ጊዜም [ከሦስት ዓመታት በፊት] ሰዎች አቅም እንደሚያንሰው ይናገሩ ነበር እኔ ግን እንዲህ አይነት ነገር አላየሁም” ሲሉም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።-አክለውም “አዎ የያዘውን ወረቀት እየተመለከተ ነበር እኔም እውነቱን ለመናገር የያዝኩትን ወረቀት እያማተርኩ ነበር። ስለዚህ ምንም የተለየ ነገር አልነበረም” ሲሉም ነው ያስረዱት።-ፐቲን አገራቸው “የአሜሪካን ህዝብ አመኔታ ካገኘ” እና የፕሬዚዳንትነቱን ቦታ ካሸነፈ ከማንኛውም መሪ ጋር እንደምትሰራም በዚሁ ወቅት አብራርተዋል።-ባይደንን ከትራምፕ ይልቅ ቢመርጧቸውም የዩክሬንን ጦርነት ያወገዙበትን መንገድ “እጅግ ጎጂ” እና “ስህተት የተሞላው” ነው ሲሉ ፑቲን ገልጸውታል።-በአውሮፓውያኑ 2016 የአሜሪካ ምርጫ ወቅር ትራምፕ ከፑቲን ጋር “በጥሩ ሁኔታ እንደሚግባቡ ጠቁመው” ነበር።-በመጪው የአሜሪካ ምርጫ የሪፐብሊካኑ ቀዳሚ እጩ የሆኑት ዶናልድ ትራምፕ የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) አባል አገራት የሚጠበቅባቸውን መዋጮ ባለመክፈላቸው አገራቸው ከየትኛውም ወረራ እንደማትከላከልላቸው ለአንድ መሪ መንገራቸውን አስረድተዋል።-በአወዛጋቢ ንግግሮቻቸው የሚታወቁት ትራምፕ በነዚህ አገራት ላይ ሩሲያ ጥቃት እንድትፈጽም “እንደሚያበረታቱም” አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።-የኔቶ ዋና አዛዥ ጄንስ ስቶልተንበርግ በምላሹ ትራምፕ የህብረቱን የጋራ ደህንነት ዋስትና “እንዳያዳክሙ” ጠይቀዋል።
|
የፎቶው ባለመብት Reuters-አውሮፓ ሙሉ በሙሉ ራሷን የመከላከል አቅም ለማዳበር አስር ዓመት እንደሚያስፈልጋት ግዙፉ የጀርመን የመከላከያ ኩባንያ የሆነው ርሄይንሜታል ኃላፊ ለቢቢሲ ተናገሩ።-የአህጉሪቱ የጦር መሳሪያ ክምችት “መመናመኑንም” ነው አርሚን ፓፐርገር የተናገሩት።-ኃላፊው ይህንን አስተያየት የሰጡት የጀርመኑ ቻንስለር ኦላፍ ሾልዝ ግዙፍ የተባለውን የጦር መሳሪያ ማምረቻ ኩባንያ የመሰረት ድንጋይ ለመጣል ሎወር ሳክሶኒ በተባለችው ግዛት በተገኙበት ወቅት ነው።-በዚህ ዝግጅት ላይ የጀርመን የመከላከያ ሚኒስትር ቦሪስ ፒስቶሪየስ እና የሆላንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ሜቴ ፍሬደሪክሰንም ተገኝተው ነበር።-ለዚህ ሁሉ የጦር መሳሪያ ክምችት “መመናመን” ስጋት መነሻ የሆነው የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከቀናት በፊት የሰጡት አስተያየት ነው።-በመጪው የአሜሪካ ምርጫ የሪፐብሊካኑ ቀዳሚ እጩ የሆኑት ዶናልድ ትራምፕ የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት (ኔቶ) አባል አገራት የሚጠበቅባቸውን መዋጮ ባለመክፈላቸው አገራቸው ከየትኛውም ወረራ እንደማትከላከልላቸው ለአንድ መሪ መንገራቸውን አስረድተዋል።-በአወዛጋቢ ንግግሮቻቸው የሚታወቁት ትራምፕ በነዚህ አገራት ላይ ወራሪዎች የፈለጉትንም እንዲያደርጉ “እንደሚያበረታቱም” አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።-ርሄይንሜታል በአዲሱ የጦር መሳሪያ ማምረቻ ላይ ከ300 ሚሊዮን ዶላር በላይ መዋዕለ ንዋይ እንደሚያፈስም አስታውቋል።-ማምረቻው በየዓመቱ 200 ሺህ የሚሆኑ የከባድ መሳሪያ ጥይቶችን እንደሚያመርትም ተነግሯል።-ሆኖም “ኔቶን መዋጋት የሚፈልግ ወራሪ ከመጣ” ለጦር ዝግጅት ረዘም ያለ ጊዜ እንደሚያስፈልግ ነው የገለጹት።-“በሦስት፣ አራት ዓመታት ጥሩ እንሆናል። ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ለመዘጋጀት አስር ዓመት ያስፈልገናል” ብለዋል።-“በአውሮፓ በየዓመቱ 1.5 ሚሊዮን ጥይቶች ማምረት ይጠበቅብናል” ሲሉም ነው ኃላፊው ያስረዱት።-አውሮፓ የነበራት የጦር መሳሪያ ክምችት ዩክሬንን ለማገዝ የሄደ ሲሆን “ይህም የአገሪቱን ክምችት አመንምኖታል” ብለዋል።-“ጦርነት እስከቀጠለ ድረስ ዩክሬንን ልናግዝ ይገባል፤ ነገር ግን የሚያስፈልገንን የጦር መሳሪያ ክምችት ለመሙላት ቢያንስ አምስት ዓመት ሙሉ ለሙሉ ለመዘጋጀት ደግሞ አስር ዓመት ያስፈልገናል” ሲሉም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።-የጀርመኑ ቻንስለር ሾልዝ የትራምፕ አስተያየት ስጋት ፈጥሮባቸው እንደሆነ ቢጠየቁም ምላሽ ለመስጠት ባይፈልጉም የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት ለካናዳ፣ ለአሜሪካም ሆነ ለአውሮፓ አገራት “ፍጹም አስፈላጊ ነው” ሲሉ አስረድተዋል።
|
ዳረን ፍራንኪሽ ለ17 ዓመታት ያክል ከባድ የራስ ምታት ሲያሰቃየው ኖሯል።-ይህ ራስ ምታት ከባድ ከመሆኑ የተነሳ ጭንቅላቱን ከግድግዳ እያላተመ እና እየጮኸ ነው ስቃዩን የሚወጣው።-የ53 ዓመቱ እንግሊዛዊ ራስ ምታቱ ሲነሳ አንዳች ቅቤ የጠገበ ዱላ ጭንቅላቱን የመታው ያህል ይሰማዋለ። ይህ አልበቃ ብሎ ዓይኑን በጩቤ የተወጋ ያክል ያመዋል።-በእንግሊዝኛው ክላስተር ሄድኤክ የተሰኘ ስም ያለው ይህ ራስ ምታት እጅግ በጣም ስቃዩ የበዛ ነው።-“በኮቪድ ወቅት ወደ ሆስፒታል ስሄድ ትዝ ይለኛል። አውቶቡስ ሲመታ ዘለህ ግባ ግባ ይለኛል። ራስ ማጥፋት የሚያስመኝ ራስ ምታት ነው ቢሉ አይገርምም” ሲል ለቢቢሲ ይናገራል።-የሆርቲካልቸር ኢንጂነር የሆነው ዳረን “መች እንደሚጀምረኝ ስለማላውቅት በፍርሀት ነው የምኖረው” ይላል።-“ይህ ስነ-ልቡናዊ ስቃይ ነው። በየትኛውም ሰዓት ሊጀምረኝ ይችላል። በጣም ያስፈራኛል።”-ይህ ዓይነቱ ራስ ምታት ከ15 ደቂቃ ጀምሮ እስከ 3 ሰዓታት ሊቆይ የሚችል ሲሆን በቀን ሰባት አሊያም ስምንት ጊዜ ይነሳል።-ነገር ግን ዳረን ለ12 ሰዓታት የቆየ ራስ ምታት እንዳጋጠመው ያስታውሳል።-የፎቶው ባለመብት DOUG ARMAND/ GETTY IMAGES-ራስ ምታቱ ሲጀምረው በግራ ጭንቅላቱ በኩል ከግራ ዓይኑ ከፍ ብሎ ባለው ክፍል ነው።-ግራ ዓይኑ መቅላት ሲጀምር እና ውሀ ሲሞላው እንዲሁም አፍንጫው ሲደፈን እና ጭንቅላቱ በአንዳች ስቃይ ሲሞላ ራስ ምታቱ ጀመረ ማለት ነው።-“የማደርገው ይጠፋኛል። በትራስ ታፍኜ እጮኃለሁ። ጭንቅላቴን ወስጄ ከግድግዳ አሊያም ከአንዳች ጠንካራ ነገር ጋር አላትመዋለሁ። ብርሀን ካየሁ ስለሚብስኝ ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ እቀመጣለሁ።”-ዳረን አንዳንድ ጊዜ ውሀ የሚሞላውን ግራ ዓይኑን ሸፍኖ የእግር ጉዞ ለማድረግ እንደሚወጣ ይናገራል።-“ራስ ምታቱ ሲመጣብኝ ከማንም ጋር መነጋገር አልችልም” ይላል።-እሱ እንደሚለው ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ራስ ምታቱ በተደጋጋሚ እየጎበኘው መሆኑ ሳያንስ ከተለመደው ጊዜ በላይ እየቆየ ነው።-ባለፈው ግንቦት ሁለት ጊዜ ወደ ሕክምና መስጫ እንዲሄድ ያደረጉት ሁለት ራስ ምታቶች እያንዳንዳቸው ለ12 ሰዓታት የቆዩ ናቸው።-ክላስተር ሄድኤክ የተሰኘው የራስ ምታት ዓይነት ከ1000 ሰዎች መካከል አንድ ሰው ነው የሚያጠቃው።-ይህ ማለት በዩናይትድ ኪንግደም 65 ሺህ ሰዎች በዚህ ራስ ምታት ይሰቃያሉ ማለት ነው።-“ይህ ከራስ ምታት በላይ ነው” ይላሉ የብሬይን ሪሰርች ዩኬ የጥናት ባለሙያዋ ኬቲ ማርቲን።-“ዳረን እንደገለጠው ይህ ራስ ምታት እጅግ ከባድ ነው። መሸከም የሚችሉት አይደለም። ሰዎች በስቃይ እንዲጮሁ የሚያደርግና ከራስ ምታቱ ለመገላገል ከግድግዳ የሚያላትም ነው።”-በዚህ ራስ ምታት የሚሰቃዩ አብዛኛዎቹ ሰዎች ዕድሜያቸው ከ30 በላይ ሰዎች ናቸው።-ይህ ራስ ምታት ብዙውን ጊዜ ከሴቶች በላይ በወንዶች ላይ ይስተዋላል።-አንዳንድ ጊዜ ይህ ራስ ምታት በጥቂት ቀናት እየቆየ ይመጣል፤ በሌላው ጊዜ ደግሞ ተጠቂዎችን በቀን በተደጋጋሚ ሊጎበኝ ይችላል።-ይህ ራስ ምታት ያለባቸው ሰዎች በተደጋጋሚ ሆስፒታል ሊጎበኙ ግድ ይላቸዋል።-የሕይወት ዘይቤን የሚያመሰቃቅለው ይህ ራስ ምታት ተጠቂዎችን ሥራ አልባ ሊያደርጋቸው ይችላል።-አልፎም ይህ ራስምታት ተጠቂዎችን ድባቴ ሊጥልና የራስ ማጥፋት አዝማሚያቸውን በሶስት እጥፍ ሊጨምረው እንደሚችል ጥናቶች ይጠቁማሉ።-በሽታው መድኃኒት የለውም።-ዳረን ለመጀመሪያ ጊዜ ይህ ራስ ምታት የጀመረው በ37 ዓመቱ ነው።-“ከቤተሰቦቼ ጋር ልዝናና ወደ ፕራግ አቅንቼ ነበር። በጣም ኃይለኛ ራስ ምታት ሲጀምረኝ መጀመሪያ የመሰለኝ የጭንቅላቴ ዕጢ ነበር” ይላል የሁለት ልጆች አባት የሆነው ዳረን።-ይህ ራስ ምታት ከጀመረው ወዲህ እንደ ስቴሮይድ፣ ሊቲየም፣ የልብ ሕክምና እና የሚጥል በሽታ [ኤፒለፕሲ] መድኃኒቶችን ወስዷል።-“የሚጥል በሽታ የለብኝም። ነገር ግን ምናልባት ከሠራ በሚል መድኃኒት ሰጡኝ። ነገር ግን የትኛውም መድኃኒት ሊሠራ አልቻለም። አንዳንዴ የሚሠራልኝ በመርፌ የሚሰጥ መድኃኒት ነው።”-ዳረን ሕመሙን ለማስታገስ የሚውል ኦክሲጂን የሚያመነጭ ብልቃጥ ቤቱ አይጠፋም።-ሕመሙ እንዲቀልለት በሚል የተለያዩ ምግቦች ሞክሯል፤ ከአልኮል መጠጦችና ትምባሆ ማጨስ አቁሟል። ነገር ግን ሕመሙ ሊቆም አልቻለም።-“ቀጣዩ እርምጃ ወደ ጭንቅላቴ የሚሄደውን ነርቭ የሚከላከል መድኃኒት መወጋት ነው” ይላል።-ይህ ሕክምና በሽታውን ለጥቂት ጊዜም ቢሆን የሚያስታግስ ነው። ስቴሮይዱ ለአንድ ዓመት ያክል ራስ ምታቱ የሚመጣበት ጊዜ ሊቀንስለት ይችላል።-“ትዳሬ ላይ ተፅዕኖ አሳድሯል። ለፍቺዬ ምክንያት ከሆኑ ነገሮች አንዱ ነው። ልጆቼ የኔን ጩኸት እየሰሙ ማደጋቸው ያሳዝነኛል።”-ዳረን ለጊዜው ከዚህ ራስ ምታት ጋር ከመኖር ውጭ ሌላ አማራጭ የለውም።
|
የፎቶው ባለመብት Getty Images-የአል-ናስር አጥቂው ክሪስቲያኖ ሮናልዶ ሜዳ ላይ ባሳየው ድርጊት ምክንያት የአንድ ጨዋታ ቅጣት ተላለፈበት።-በሳዑዲ ፕሮ ሊግ የሚጫወተው ሮናልዶ “ደጋፊዎችን በመቀስቀስ” በሚል ነው የተቀጣው።-ሮናልዶ ቡድኑ አል-ናስር ከአል-ሸባብ ጋር ሲጫወት የሸባብ ደጋፊዎችን ለማበሳጨት ባሳየው ምልክት ምክንያት አንድ ጨዋታ ያመልጠዋል።-የአል ሸባብ ደጋፊዎች “ሜሲ፤ ሜሲ” እያሉ የሮናልዶን የረዥም ጊዜ ተፎካካሪ ለማብሸቅ ሞክረዋል።-መዲናዋ ሪያድ የተደረገውን ጨዋታ አል-ናስር 3-2 አሸንፏል።-የ39 ዓመቱ የፖርቹጋል አጥቂ ክሪስቲያኖ ሮናልዶ እጁን ተጠቅሞ ለደጋፊዎች ባሳየው ምልክት አሳይቷል።-በተጨማሪ የሳዑዲ አረቢያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ተጫዋቹ 30 ሺህ የሳዑዲ ሪያል እንዲከፍል ፈርዶበታል።-ገንዘቡ ወደ ፓውንድ ሲመነዘር 6300 ገደማ ይሆናል።-የፌዴሬሽኑ የዲስፕሊን እና ሥነ-ምግብር ኮሚቲ እንዳለው ሮናልዶ የተወሰነበት ውሳኔ አሜን ብሎ ከመቀበል ባለፈ ይግባኝ መጠየቅ አይችልም።-በጨዋታው ሮናልዶ የመጀመሪያዋን ጎል በማስቆጠር ቢጀምር አል-ሸባብ ሁለት ጊዜ ከመመራት ተነስተው 2 አቻ ሆነዋል። ነገር ግብ በ87ኛው ደቂቃ ታሊስካ ባስቆጠራት ጎል አል-ናስር ባለድል ሆኗል።-ሮናልዶ፤ በነፃ ዝውውር ከማንቸስተር ዩናይትድ አል-ናስርን የተቀላቀለው በአውሮፓውያኑ ታኅሣሥ 2022 ነው።-ተጫዋቹ በዓለማችን እጅግ ከፍተኛውን ደሞዝ የሚያገኝ እግር ኳስ ተጫዋች እንደሆነ ይታመናል።-በያዝነው የውድድር ዘመን በ22 የሊግ ጨዋታዎች 20 ጎሎች ለቡድኑ ያስቆጠረ ሲሆን፤ አል-ናስር በሳዑዲ ፕሮ ሊግ ከአል-ሂላል ቀጥሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።-ሮናልዶ አል-ናስርን ከተቀላቀለ በኋላ በሁሉም ውድድሮች በ48 ጨዋታዎች 42 ጎሎች አስቆጥሯል።
|
የፎቶው ባለመብት Office of the Prime Minister-Ethiopia-የኢትዮጵያ መንግሥት ከሶማሊያ ጋር ጦርነት ውስጥ የመግባት ፍላጎት እንደሌለው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ገለጹ።-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ይህንን ያሉት ዛሬ ማክሰኞ ጥር 28/2016 ዓ.ም ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ እና ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ነው።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዛሬው ውሏቸው ከሶማሊላንድ ፕሬዚዳንት ሙሴ ቤሂ ጋር ከአንድ ወር በፊት የተፈራረሙት የባሕር በር ለማግኘት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ላይ የሚነሱ ጥያቄዎችን በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል።-ኢትዮጵያ እራሷን እንደ ነጻ አገር ካወጀችው እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ካላገኘችው ሶማሊላንድ ጋር 20 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የባሕር ጠረፍ ለማግኘት የፈረመችው የመግባቢያ ሰነድ ሶማሊያን በእጅጉ አስቆጥቶ በቀጠናው ከፍተኛ ውጥረትን ያስከተለ ሆኗል።-ይህ ከሆነ ከ36 ቀናት በኋላ ለተወካዮች ምክር ቤት ገለጻ ያደረጉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አገራቸው ከሶማሊያ ጋር የመዋጋት ፍላጎት እንደሌላት ተናግረው፤ በስም ያልጠቀሷቸው “ኃይሎች” ኢትዮጵያን ከሶማሊያ ጋር ለማጋጨት እየሰሩ ነው ሲሉ ከሰዋል።-“የሶማሊያ መንግሥት ከኢትዮጵያ ጋር የመጋጨት ፍላጎት ያለው አይመስለኝም - ስገምት። ግን ፍላጎት ያላቸው ኃይሎች ሶማሊያን በእጅ አዙር መጠቀም ይፈልጋሉ። ለዚያ ደሞ’ እኛ አንመችም። ምንም አይነት የከፋ ነገር ለመናገርም፣ ለማደረግም ዝግጁ አይደለንም” ብለዋል።-አክለውም “ [ይህንን] የሚመኙ ኃይሎች ለአንዳንድ ዲያስፖራ ወንድሞቻችን ሚዲያ እንደከፈቱ ሁሉ ለአንዳንድ ሶማሌ ወንድሞቻችን የተወሰነ ነገር ሊያደርጉላቸው ይችላሉ፤ ሊያዋጉን ግን አይችሉም። ቢያንስ በእኛ በኩል አንዋጋም” ብለዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግሥታቸው ለሶማሊያ ሰላም እና አንድነት በመሥራት የሚወዳደረው አካልም እንደሌለም ጠቅሰዋል።-“ለሶማሊያ አንድነት እንደዚህ መንግሥት የሠራ የለም። ሶማሊላንድ እና ሶማሊያን ለማገናኘት ጥረት አድርገናል። ነገም ሶማሊያ እና ሶማሊላንድ ቢስማሙ የመጀመሪያ ተደሳች አገር ኢትዮጵያ ነች” ብለዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ “ከማንም መቀማት አንፈልግም። የማንንም ሉዓላዊነት መንካት አንፈልግም” በማለትም የመንግሥታቸውን አቋም አንጸባርቀዋል።-ሆኖም ኢትዮጵያ ለሶማሊላንድ የአገርነት እውቅና ስለመስጠት እና ስለቀጣዩ እርምጃ ምንም አይነት አስተያየት አልሰጡም።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ማብራሪያ አገራቸው “ከወራሪ” ይልቅ “የሰፈር ጎረምሳ” እንዳስቸገራት አንስተው የውጪ ኃይልን ለመመከት የሚያስችል በቂ አቅም እንዳላት ተናግረዋል።-“ኢትዮጵያ ማንም ወርራ አታውቅም፣ [ሌላ አገር] ወርሯት ደግሞ አሸንፏት አያውቅም። ሦስት አይደለም አስር ቢደመር ኢትዮጵያን ማሸነፍ አይችልም። እኛ አንዋጋም። አንፈልግም። ወደዚህ ከመጣ ደግሞ አይችልም። በቂ የሆነ አቅም አለን . . . ወደማንም አንሄድም፣ ማንም ከመጣብን ግን ራሳችንን እንከላከላለን። በሱ ስጋት አይደርባችሁ” ብለዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሶማሌላንድ ከተፈራረሙት የባሕር በር ስምምነት በተጨማሪ ጨምሮ አገሪቷን እየናጧት እያሉ ግጭቶች እንዲሁም ድርቅ እና የኑሮ ውድነት እና የአገር ሀብት ምዝበራን አስመልክቶ ምላሾችን ሰጥተዋል።-በዛሬው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውሏቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ረዘም ያለ ጊዜ ወስደው ምላሽ የሰጡት በአገሪቷ እየተነሱ ባሉ ግጭቶች ላይ ሲሆን፣ እነዚህም አንዳንድ ጅምሮችን አደናቅፏል ብለዋል።-በአማራ እና በትግራይ ክልል ያለውን የግዛት ይገባኛል ጥያቄ በሕዝበ ውሳኔ ለመመለስ የተጀመረው ጥረት በግጭቶች ምክንያት መደናቀፉን፣ በጉዳይ ላይ ሁለቱ ክልሎች መረጃ ከተሰጣቸው በኋላ ወደ ተግባር ለመግባት የተደረገው ጥረት አለመሳካቱን ጠቅሰዋል።-“በምሁራን፣ በሃይማኖት አባቶች፣ በሽማግሌዎች፣ በወጣቶች ወይይት እያደረግን በሕዝበ ውሳኔ፣ ሕዝቡ ወደ ፈለገበት እንዲመለስ እናድርግ ይህንን ካደረግን ዘላቂ ሰላም ልናመጣለን እንችላለን” ሲሉም ተደምጠዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ “ከዚህ ውጪ ያለው አማራጭ ግን ጊዜያዊ ድል ዘላቂ ሰላም አያረጋግጥም የሚል አቋም ወስደን ለሁለቱም ክልሎች ነግረን ሥራ ልንጀምር ስንዘጋጅ ግጭቶች አጋጠሙን” ብለዋል።-በወሰን ይገባኛል ጥያቄ በሚነሳባቸው አካባቢዎች ሕዝበ ውሳኔ እና ውይይት እስኪካሄድ ድረስ የተፈናቀሉ ሰዎች ወደቀያቸው እንዲመለሱ፣ እንዲሁም የራሳቸውን ተወካዮች መርጠው እንዲተዳደሩም መንግሥታቸው ይሠራል ብለዋል።-በመጨረሻም በሕዝበ ውሳኔ ህዝቡ በሚፈልገው መንገድ በአንደኛው ክልል በሚጠቃለልበት ሁኔታ ላይም መንግሥታቸው እንደሚሠራ ጠቅሰዋል።-በትግራይ እና በአማራ ክልል የሚነሱ የግዛት ይገባኛል ጥያቄዎች ዘላቂ ሰላምን በሚያረጋግጥ መልኩ ሊፈታ እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል።-“የወሰን ጥያቄዎችን በተመለከተ የፌዴራል መንግሥት 'እከሌን ገፍተህ የኔን ጥያቄ መልስ' የሚለውን መንገድ ሳይሆን ለሁሉም ክልሎች እኩል መፍትሔ የሚሰጠውን መንገድ ይከተላል” ብለዋል።-ቀጥለውም ከሕዝበ ውሳኔ ወጪ ያሉ ሌሎች አማራጮች ካሉ መንግሥት እንደሚቀበልም አንስተዋል።-“ከጦርነት መለስ ያለ ሌላ አማራጭ ካለ የፌደራል መንግስት ተባባሪ ነው” ሲሉም ተደምጧል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ከማለታቸው አንድ ቀን ቀድም ብሎ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ከአማራ ክልል ጋር በይገባኛል እያወዛገቡ ያሉትን አካባቢዎች ጉዳይ በሕዝብ ውሳኔ መፍትሄ ለመስጠት ከስምምነት ተደርሷል መባሉን አስተባብሎ ነበር።-ጊዜያዊ አስተዳደሩ ባለፈው ሳምንት በመንግሥት ኮሚዩኒኬሽን የወጣወን መግለጫ መነሻ አድርጎ የአከራካሪ ቦታዎችን ሁኔታ በዘላቂነት ለመፍታት “ሕዝበ ውሳኔ እንዲደረግ ከአማራ እና ከትግራይ ክልሎች ጋር መግባባት ላይ ተደርሶ ነበር” ማለቱን በመጥቀስ ነው፤ “ፍጹም የተሳሳተ [ነው]” ሲል አስተባብሏል።-ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ለአገሪቱ ሕግ አውጪ አካል በሰጡት ማብራሪያ ላይ ጉዳዩ ለሁለቱም ክልሎች “መነገሩን” ገልጸዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአማራ ክልል የተለያዩ ማኅበረሰቦች ጋር ባደረጓቸው ቀደምት ውይይቶች የወሰን ይገባኛል ጥያቄ ከሦሰቱ መሠረታዊ ጥያቄዎች አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል።-ከወሰን በተጨማሪም ሕዝቡ የሚያነሳቸው መሠረታዊ ጥያቄዎች ልማት፣ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ እንደሆነ ጠቅሰው እነዚህንም ጥያቄዎች ለመመለስ መንግሥታቸው እየሠራም እንደሆነ ተናግረዋል።-መንግሥት የልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ በሚል ባለፉት አምስት ዓመታት ሥራዎችን እየሠራ እንደሆነ አመልክተው፣ ከእነዚህም ውስጥ 3200 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው፣ 53 የመንገድ ፕሮጀክቶች ሥራን በዋቢነት አንስተዋል። ከዚህም ውስጥ 1300 ኪሎ ሜትር መጠናቀቁን ጠቅሰዋል።-ሌላኛው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የጠቀሱት በ2.4 ቢሊዮን ብር በባሕር ዳር እየተገነባ ያለውን የዓባይ ወንዝ ድልድይን በአባሪነት አንስተዋል።-ድልድዩ በኢትዮጵያ ደረጃም በጥራቱም ሆነ በወጪው ተወዳዳሪ የለውም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህም መንግሥታቸው እየሄደበት ያለውን ርቀት አመላካች ነው ብለዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሌላው ያነሱት በቱሪዝም ዘርፍ ከፍተኛ እመርታ አለው ያሉትን የጎርጎራ ፕሮጀክት ነው። ቀጥለውም የፋሲል ቤተ መንግሥት እድሳት ተደርጎለት በአዲስ አበባ እንዳሉ ፕሮጅክቶች ገቢ እንዲያመጣ ሥራ ለመጀመር ቢታቀደም አለመሳካቱን አንስተዋል።-በክልሉ ውስጥ ታሪካዊ የሆነውን የፋሲል ቤተ መንግሥት የፈረሰው አካል እድሳት ቢታሰብም በተለያዩ አሉባልታዎች እና ሴራዎች ሥራው መቆሙን ነው የተናገሩት።-“[የፋሲል ቤተ መንግሥት እድሳት] በተለያዩ አሉባልታዎች እና ሴራዎች ሥራው እንዳይከናወን አስቁመውታል” ካሉ በኋላ “ጦርነትም” ሌላው ምክንያት እንደሆነ አስቀምጠዋል።-ጥገናውን ለማካሄድ ያላስቻሉትን “አሉባልታዎች” ያልጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የመደመር መጽሐፍን ሽያጭ በመጠቀም ለመጠገን ታቅዶም እንደነበር አመልከተዋል።-የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን ለማደስ ከፈረንሳይ መንግሥት ጋር በመተባበር እየተሠሰራ መሆኑን እንደ አንድ የመንግሥታቸውን ቁርጠኝነት ማሳያነት ያወሱት ዐቢይ፣ በጦርነቱ ምክንያት መስተጓጎል እየገጠመው እንደሆነም አልደበቁም።-በተጨማሪም በቱሪዝም፣ በመንገድ፣ በግብርና እና ኢንደስትሪ ዘርፎች ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል።-ዐቢይ በክልሉ ላሉ ታጣቂ ኃይሎች በድጋሚ የሰላም ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፣ አገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ አማራ ክልልን ጨምሮ በክልሎች ድጋፍ ከተደረገለት “እገረ መንገዱን የአማራ ክልል [የሕገ መንግሥት] ጥያቄ ይመልሳል” ብለዋል።-መሠረታዊ ባሉት የሕገ መንግሥት የማሻሻያ ጥያቄም ከዚህ ቀደም ባልነበረ መልኩ መስተናገድ የሚችልበትን ማዕቀፍ በመፍጠር በሕዝቦች ውይይት እና ምክክር አገሪቷ ዘላቂ ሕገ መንግሥት እንዲኖራት የሚያስችል ሥራ የምክክር ኮሚሽኑ እየሠራ ነው ብለዋል።-“ሕገ መንግሥት ከነገሥታት ጋር የሚቀየር ሁኔታ መሆን የለበትም። በውይይት ዘላቂ ሕገ መንግሥትም ለመቅረጽ እየተሠራ ነው” ብለዋል።-በሌላ በኩል “ሕገ ማስከበር አጠናክረን እንቀጥላለን። እጃችሁን አጣጥፋችሁ ተቀመጡ የሚለንን አንስማም፣ አንቀበልም፣ አናደርግም። መንግሥት ነን አቅም በፈቀደ መጠን እንሠራለን። ሕግ ለማስከበር ሰንሠራ በእያንዳንዷ ሰከንድ ለሰላም ዝግጁ የሆነ ኃይል ካለ ለሰላም ዝግጁ ነን” ብለዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መንግሥታቸው ሸኔ እያለ ከሚጠራው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ጋር በቅርቡ ለሁለተኛ ጊዜ በታንዛንያ ተደርጎ ስላልተሳካው የሰላም ድርድር ለምክር ቤቱ ማብራሪያ ሰጥተዋል።-ከኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ጋር የተደረገው የሰላም ውይይት ግልጽነት የጎደለው ነው የሚሉ ኃይሎች እንዳሉ የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ንግግር ሲጀመር ለሕዝቡ መንግሥታችው ቀድሞ ማሳወቁን ጠቅሰዋል።-ንግግሩ ከተጠናቀቀ በኋላ ይህ ነው የሚባል ፍሬ ሃሳብ ላይ ባለመደረሱ መናገር ባይቻልም የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት የአገሪቱን ሕግ እና ሥርዓት ባከበረ መልኩ ውይይት አድርጎ ተጨባጭ ነገር ላይ መድረስ ከተቻለ ለሕዝቡ ይፋ ይሆናል ሲሉ የመንግሥታቸውን አቋም አስታውቀዋል።-የኦሮሞ ነጻነት ግንባርን ጨምሮ በርካታ ተፋላሚ ወገኖች ወደ አገሪቱ ገብተው በሰላም እንዲታገሉ መንግሥታቸው ጥሪ ማድረጉን ያስታወሱት ዐቢይ፣ ኦብነግ፣ ኦነግ፣ ግንቦት ሰባት፣ ኢህአፓ በአገሪቱ ውስጥ እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ ብለዋል።-እነዚህ ወገኖች በተለያዩ ደረጃዎች በሚንቀሳቀሱበት ወቅት ከ“ሸኔ ጋር” ምን ዓይነት መግባባት ተደርሶ ነበር? ምንስ ቃል ተገብቶላቸው ነው የሚሉ ጥያቄዎችን አጣጥለዋል።-ኦነግን ወክለው በአመራ ደረጃ አስመራ ላይ ከመንግሥት ጋር የተደራደሩ ሰዎች አብዛኛዎቹ አዲስ አበባ መሆናቸውን የተወሰኑትም በመንግሥት ኃላፊነት ላይ ናቸው ብለዋል።-“የተለየ የሰላም ውይይት ካለ ግማሹ እዚህ ገብተው የሚሠሩበት ከፊሎቹ ደግሞ ጫካ ገብተው ሕዝብ የሚያሰቃዩበት ምንም ምክንያት አይኖርም። ለሁሉም የቀረቡት ጥሪዎች ተመሳሳይ ናቸው” ብለዋል።-ሸኔ ሲሉ የጠሩት ኃይል በአሥመራ በተደረገው ድርድር ከመንግሥት የተገባለት ቃል ሳይሳካ ከሆነ ጫካ የገባው “ሕዝብን እየገደሉ፣ እየዘረፉ፣ እታገላለሁ ማለት ተቀባይነት የለውም” ሲሉም ተደምጠዋል።-ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሁለት ዓመታት የዘለቀውን ደም አፋሳሽ ጦርነት የቋጨውን የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት የፌደራል መንግሥት እና የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተደዳር በትብብር ትላልቅ ድሎችን ማስመዝገብ የቻሉበት ነው ብለዋል።-አክለውም ለእነዚህ ሥራዎች የፌዴራል መንግሥት እና የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በጋራ መሥራታቸውን ተናግረው ጊዜያዊ አስተዳደሩን አሞካሽተዋል።-እነዚህን ውጤቶች በአየር መንገድ፣ በቴሌኮም፣ በኢንደስትሪ፣ ትምህርት እና ጤና ዘርፎች በማብራራት፤ በመቀለ፣ በሽረ እና በአክሱም አየር መንገድ ሥራ መጀመራቸው የሰላም ስምምነቱ ውጤት ነው ብለዋል።-በቴሌኮም ከ20 ሺህ በላይ የቤት ስልክ መስመሮች መጠገናቸው፤ በትግራይ 600 የባንክ ቅርንጫፎች በብሔራዊ ባንክ 10 ቢሊዮን ብር ጥሬ ገንዘብ መለቀቁን፣ በኢንዱስትሪ 217 ፋብሪካ ሥራ መጀመራቸው እንዲሁም በግብርና 630 ሺህ ሄክታር መሬት መታረሱ ትልቅ ውጤት ነው ሲሉ አንስተዋል።-በክልሉ ያለውን የግብርና ዘርፍ ለማገዝ እንዲሁ 500 የሚሆኑ ትራክተሮች ለክልሉ ተገዝተው ጂቡቲ ወደብ መድረሳቸውን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተለያዩ ዘርፎች ድጋፍ ቢደረግም በቂ እንዳልሆነም ነው የጠቀሱት።-ሆኖም ይህ ውጤት “በቂ አይደለም። የኢትዮጵያ አቅም ውስን ስለሆነ ነው እንጂ ከዚህ በላይ መታገዝ አለባቸው” ብለዋል።-ተፈናቃዮችን በመመለስ እንዲሁም የይገባኛል የግዛት ጥያቄዎች ሊመለሱ እንደሚገባ ጠቅሰው፣ መንግሥታቸው ከትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ጋር እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ ሥራዎችን አብሮ ያከናውናል ብለዋል።-በርካታ የረድዔት ተቋማት ኢትዮጵያ የከፋ ረሃብ ሊያጋጥማት እንደሚችል እያስጠነቀቁ ባለበት ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ድርቁን እንደ ፖለቲካ መሳሪያ መጠቀም አግባብ አይደለም ሲሉ በዛሬው ውሏቸው ተደምጠዋል፡፡-በዘንድሮው ዓመት በትግራይ፣ በአማራ አና በኦሮሚያ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች ድርቅ መከሰቱን ገልጸው የዚህንም ታሪካዊ ዳራ ጠቅሰዋል።-“ድርቅ መንግሥት አላመጣውም፣ ችግኝ እንተከል ሲባል ምን ያደርጋል ስንል፣ ስንዴ እናምርት ስንል ምን ያደርጋል ብለን ድርቅ መጣ ብለን ብንጮህ ትርጉም የለውም” ሲሉ ተናግረዋል፡፡-“በረሃብ ምክንያት የሚሞት ሰው የለም” ብለውም የተከሰተው ድርቅ የሰው ሕይወት እንዳይቀጥፍ መተባበር እንደሚገባ አሳስበዋል።-አንዱ ክልል ተርቦ አንዱ በልቶ ሊያድር አይችልም ሲሉም ገልጸው ባለፉት ጥቂት ወራት በትግራይ ክልል 5 መቶ ሺህ ኩንታል እህል በመንግሥት እና በሌሎች አካላት ትብብር ወደ ክልሉ ማድረስ መቻሉን አስረድተዋል።-መንግሥታቸው አንድም ቦታ በረሃብ የሚሞት ሰው አይቶ ዝም አይልም በማለትም በመተባበር ይህንንም ጊዜ እንዲሻገር እንደሚሠሩም አስረድተዋል።
|
End of preview. Expand
in Data Studio
No dataset card yet
- Downloads last month
- 2