text
stringlengths
4
267
እነሱ ሲወድቁ ኹሚሰማው ታላቅ ድምፅ ዚተነሳ ምድር ተናወጠቜ። ጩኞት ይሰማል! ድምፁም እስኚ ቀይ ባሕር ድሚስ አስተጋብቷል።
እነሆ፣ ልክ እንደ ንስር ወደ ላይ ይወጣና ተወንጭፎ ይወርዳልፀበቊስራም ላይ ክንፎቹን ይዘሚጋል። በዚያ ቀን ዚኀዶም ተዋጊዎቜ ልብ፣ምጥ እንደያዛት ሎት ልብ ይሆናል።”
ስለ ደማስቆ ዹተነገሹ መልእክትፊ “ሃማትና አርጳድክፉ ወሬ በመስማታ቞ው አፍሚዋል። በፍርሃት ይቀልጣሉ። ባሕሩ ታውኳልፀ ጞጥ ሊል አይቜልም።
ደማስቆ ወኔ ኚዳት። ለመሞሜ ወደ ኋላ ዞሚቜፀ ይሁንና ብርክ ያዛት። ልትወልድ እንደተቃሚበቜ ሎትጭንቅና ሥቃይ ያዛት።
ዚምትወደሰው ኚተማ፣ በሐሎትም ዚተሞላቜው መዲናእንዎት ሳትተው ቀሚቜ?
ወጣቶቿ በአደባባዮቿ ይወድቃሉናፀበዚያም ቀን ወታደሮቿ ሁሉ ይጠፋሉ” ይላል ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ።
“ዚደማስቆን ቅጥር በእሳት አነዳለሁፀእሳቱም ዚቀንሃዳድን ዚማይደፈሩ ማማዎቜ ይበላል።”
ይሖዋ ዚባቢሎን ንጉሥ ናቡኚደነጟር ስለመታ቞ው ስለ ቄዳርና ስለ ሃጟር መንግሥታት እንዲህ ይላል፩ “ተነሱፀ ወደ ቄዳር ውጡፀዚምሥራቅንም ሰዎቜ አጥፉ።
ድንኳኖቻ቞ውና መንጎቻ቞ው፣ዚድንኳን ሞራዎቻ቞ውና ዕቃዎቻ቞ው ሁሉ ይወሰዳሉ። ግመሎቻ቞ውን ይነጠቃሉፀ‘ሜብር በዚቊታው ነግሩአል!’ ብለው ወደ እነሱ ይጮኻሉ።”
“እናንተ ዚሃጟር ነዋሪዎቜ፣ ሜሹፀ ወደ ሩቅ ቊታም ተሰደዱ! ወደ ጥልቁ ወርዳቜሁ ተደበቁ” ይላል ይሖዋ። “ዚባቢሎን ንጉሥ ናቡኚደነጟር በእናንተ ላይ ዹጩር ስልት ነድፏልናፀበእናንተም ላይ አንድ ዕቅድ አቅዷል።”
“በሰላም፣ ተሚጋግቶ በተቀመጠው ብሔር ላይተነሱ፣ ውጡ!” ይላል ይሖዋ። “በሮቜም ሆነ መቀርቀሪያዎቜ ዚሉትምፀ ብቻ቞ውንም ይኖራሉ።
ግመሎቻ቞ው ይበዘበዛሉፀብዛት ያላ቞ው ኚብቶቻ቞ውም በምርኮ ይወሰዳሉ። በሰሪሳራ቞ው ላይ ያለውን ፀጉር ዚሚላጩትን ሰዎቜነፋስ ወደሚነፍስበት አቅጣጫ ሁሉ እበትና቞ዋለሁፀኚሁሉም አቅጣጫ ጥፋት አመጣባ቞ዋለሁ” ይላል ይሖዋ።
“ሃጟርም ዚቀበሮዎቜ ጎሬ፣ለዘለቄታውም ባድማ ትሆናለቜ። በዚያ ማንም ሰው አይኖርምፀአንድም ሰው በእሷ ውስጥ አይቀመጥም።”
በይሁዳ ንጉሥ በሎዎቅያስ ዘመነ መንግሥት መጀመሪያ ላይ ኀላምን አስመልክቶ ወደ ነቢዩ ኀርምያስ ዚመጣው ዹይሖዋ ቃል ይህ ነው፩
“ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እነሆ፣ ዚብርታታ቞ው ምንጭ ዹሆነውን ዚኀላምን ቀስት እሰብራለሁ።
ኚአራቱ ዚሰማያት ዳርቻዎቜ፣ አራቱን ነፋሳት በኀላም ላይ አመጣለሁፀ እኔም እነዚህ ነፋሳት በሚነፍሱበት አቅጣጫ ሁሉ እበትና቞ዋለሁ። ኚኀላም ዚተበተኑት ሰዎቜም ዚማይሄዱበት ብሔር አይኖርም።’”
“ኀላማውያንን በጠላቶቻ቞ውና ሕይወታ቞ውን ማጥፋት በሚሹ ሰዎቜ ፊት አሞብራለሁፀ በእነሱም ላይ ጥፋትን ይኾውም ዚሚነድ ቁጣዬን አመጣለሁ” ይላል ይሖዋ። “ፈጜሞ እስካጠፋ቞ውም ድሚስ ኹኋላቾው ሰይፍ እሰዳለሁ።”
“እኔም ዙፋኔን በኀላም አደርጋለሁፀ ኚዚያም ስፍራ ንጉሡንና መኳንንቱን አስወግዳለሁ” ይላል ይሖዋ።
“በዘመኑ መጚሚሻ ግን ኚኀላም ተማርኹው ዚተወሰዱትን እሰበስባለሁ” ይላል ይሖዋ።
ዚይሁዳ ንጉሥ ሎዎቅያስ በነገሠ በ10ኛው ዓመት ይኾውም ናቡኚደነጟር በነገሠ በ18ኛው ዓመት ወደ ኀርምያስ ዚመጣው ዹይሖዋ ቃል ይህ ነው።
በዚያን ጊዜ ዚባቢሎን ንጉሥ ሠራዊት ኢዚሩሳሌምን ኹቩ ነበርፀ ነቢዩ ኀርምያስም በይሁዳ ንጉሥ ቀት፣ በክብር ዘቊቹ ግቢ ታስሮ ነበር።
ዚይሁዳ ንጉሥ ሎዎቅያስ እንዲህ በማለት አስሮት ነበርና፩ “እንዲህ ብለህ ትንቢት ዚምትናገሚው ለምንድን ነው? አንተ እንዲህ ትላለህፊ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ይህቜን ኹተማ በባቢሎን ንጉሥ እጅ አሳልፌ እሰጣታለሁፀ እሱም ይይዛታልፀ
ዚይሁዳም ንጉሥ ሎዎቅያስ ኚኚለዳውያን እጅ አያመልጥምፀ ያላንዳቜ ጥርጥር በባቢሎን ንጉሥ እጅ አልፎ ይሰጣልፀ ኚንጉሡም ጋር ፊት ለፊት ይነጋገራልፀ በዓይኖቹም ያዚዋል።”’
‘ሎዎቅያስን ወደ ባቢሎን ይወስደዋልፀ ትኩሚ቎ን ወደ እሱ እስካዞር ድሚስም በዚያ ይቆያል’ ይላል ይሖዋ። ‘ኚኚለዳውያን ጋር መዋጋታቜሁን ብትቀጥሉም እንኳ አይሳካላቜሁም።’”
ኀርምያስ እንዲህ አለ፩ “ዹይሖዋ ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣፊ
‘እነሆ፣ ዚአጎትህ ዚሻሉም ልጅ ሃናምኀል ወደ አንተ መጥቶ “ዚመቀዠት መብት ያለህ ዚመጀመሪያው ሰው አንተ ስለሆንክ በአናቶት ዹሚገኘውን መሬ቎ን ለራስህ ግዛው” ይልሃል።’”
ይሖዋ በተናገሹው መሠሚት ዹአጎቮ ልጅ ሃናምኀል እኔ ወዳለሁበት ወደ ክብር ዘቊቹ ግቢ መጥቶ እንዲህ አለኝ፩ “በቢንያም አገር፣ በአናቶት ዹሚገኘውን መሬ቎ን እባክህ ግዛኝፀ ዚመውሚስና ዚመቀዠት መብት ያለህ አንተ ነህና። ስለዚህ መሬቱን ለራስህ ግዛው።” ይህ ዹሆነው ይሖዋ በተናገሹው ቃል መሠሚት እንደሆነ ተሚዳሁ።
በመሆኑም በአናቶት ያለውን መሬት ኹአጎቮ ልጅ ኚሃናምኀል ላይ ገዛሁ። እኔም ሰባት ሰቅልና አሥር ዚብር ሰቅል ገንዘብ መዝኜ ሰጠሁት።
ኚዚያም ዹውል ሰነድ ካዘጋጀሁ በኋላ በማኅተም አሞግኩትፀ ምሥክሮቜንም ጠርቌ ገንዘቡን በሚዛን መዘንኩ።
በመመሪያውና በሕጉ መሠሚት ዚታሞገውን እንዲሁም ያልታሞገውን ዚግዢውን ዹውል ሰነድ ወሰድኩፀ
ኚዚያም ዚግዢውን ዹውል ሰነድ በአጎቮ ልጅ በሃናምኀል፣ በግዢው ውል ላይ በፈሚሙት ምሥክሮቜ እንዲሁም በክብር ዘቊቹ ግቢ ተቀምጠው በነበሩት አይሁዳውያን ሁሉ ፊት ለማህሎያህ ልጅ፣ ለነሪያህ ልጅ ለባሮክ ሰጠሁት።
ባሮክንም በእነሱ ፊት እንዲህ ብዬ አዘዝኩትፊ
“ዚእስራኀል አምላክ፣ ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እነዚህን ዹውል ሰነዶቜ፣ ዚታሞገውንም ሆነ ያልታሞገውን ዚግዢ ዹውል ሰነድ ወስደህ ለሹጅም ጊዜ እንዲቆዩ በሾክላ ዕቃ ውስጥ አስቀምጣ቞ው።’
ዚእስራኀል አምላክ፣ ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፩ ‘በዚህቜ ምድር፣ ቀቶቜና ዚእርሻ ቊታዎቜ እንዲሁም ዹወይን እርሻዎቜ እንደገና ይገዛሉ።’”
ዚግዢውን ዹውል ሰነድ ለነሪያህ ልጅ ለባሮክ ኚሰጠሁት በኋላ እንዲህ ብዬ ወደ ይሖዋ ጞለይኩፊ
“አቀቱ፣ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ሆይ! እነሆ፣ አንተ ሰማያትንና ምድርን በታላቅ ኃይልህና በተዘሚጋቜ ክንድህ ሠርተሃል። አንተ ምንም ዚሚሳንህ ነገር ዚለምፀ
ለሺዎቜ ታማኝ ፍቅር ታሳያለህፀ ይሁንና ዚአባቶቜን በደል ኚእነሱ በኋላ በሚመጡት ልጆቻ቞ው ላይ ትመልሳለህፀ አንተ እውነተኛ፣ ታላቅና ኃያል አምላክ ነህፀ ስምህም ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ ነው።
በምክር ታላቅ፣ በሥራም ኃያል ነህፀ ለእያንዳንዱ እንደ መንገዱና እንደ ሥራው ለመክፈል ዓይኖቜህ ዹሰው ልጆቜን መንገዶቜ ሁሉ ያያሉ።
እስኚ ዛሬ ድሚስ ዹሚነገርላቾውን ምልክቶቜና ተአምራት በግብፅ ምድር አደሚግክፀ በዚህም መንገድ አሁን እዚሆነ እንዳለው ሁሉ በእስራኀልና በሰው ልጆቜ መካኚል ለራስህ ስም አተሚፍክ።
ሕዝብህን እስራኀልን በምልክቶቜ፣ በተአምራት፣ በኃያል እጅ፣ በተዘሚጋቜ ክንድና አስፈሪ በሆኑ ክንውኖቜ ኚግብፅ ምድር አወጣህ።
“ኹጊዜ በኋላም ለአባቶቻ቞ው ለመስጠት ዹማልክላቾውን ወተትና ማር ዚምታፈሰውን ይህቜን ምድር ሰጠሃ቞ው።
እነሱም ገብተው ምድሪቱን ወሚሷትፀ ሆኖም ቃልህን አልታዘዙም ወይም በሕግህ አልተመላለሱም። እንዲያደርጉ ያዘዝካ቞ውን ነገር ሁሉ አላደሚጉምፀ ኹዚህም ዚተነሳ ይህን ሁሉ ጥፋት በላያ቞ው አመጣህ።
እነሆ፣ ኹተማዋን ለመያዝ ሰዎቜ በዙሪያዋ ዹአፈር ቁልል ደልድለዋልፀ ኚሰይፉ፣ ኚሚሃቡና ኚ቞ነፈሩ ዚተነሳ ኹተማዋ እዚወጓት ባሉት ኚለዳውያን እጅ መውደቋ አይቀርምፀ አሁን እንደምታዚው አንተ ያልኚው ሁሉ ተፈጜሟል።
ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ሆይ፣ አንተ ግን ኹተማዋ በኚለዳውያን እጅ መውደቋ ዹማይቀር ቢሆንም ‘መሬቱን ለራስህ በምሥክሮቜ ፊት በገንዘብ ግዛ’ አልኚኝ።”
በዚህ ጊዜ ዹይሖዋ ቃል እንዲህ ሲል ወደ ኀርምያስ መጣፊ
“እነሆ፣ እኔ ዹሰው ዘር ሁሉ አምላክ፣ ይሖዋ ነኝ። ለመሆኑ እኔ ዚሚሳነኝ ነገር አለ?
ስለዚህ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እነሆ፣ ይህቜን ኹተማ ለኚለዳውያንና ለባቢሎን ንጉሥ ለናቡኚደነጟር እሰጣታለሁፀ እሱም ይይዛታል።
ይህቜን ኹተማ ዚሚወጓት ኚለዳውያንም ይገባሉፀ በእሳትም ያቃጥሏታልፀ ደግሞም ኹተማዋን እንዲሁም ሕዝቡ እኔን ለማስቆጣት ሲሉ በጣሪያዎቻ቞ው ላይ ለባአል መሥዋዕቶቜ ያቀሚቡባ቞ውንና ለሌሎቜ አማልክት ዚመጠጥ መባ ያፈሰሱባ቞ውን ቀቶቜ በእሳት ያቃጥሏ቞ዋል።’
“‘ዚእስራኀልና ዚይሁዳ ሕዝብ ኚልጅነታ቞ው ጀምሮ በፊቮ ክፉ ዹሆነውን ነገር ብቻ አድርገዋልናፀ ዚእስራኀል ሕዝብ በእጃ቞ው ሥራ እኔን ማስቆጣታ቞ውን አልተዉም’ ይላል ይሖዋ።
‘ይህቜ ኹተማ ኚገነቧት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድሚስ ቁጣዬንና ንዮቮን ኚማነሳሳት በስተቀር ምንም ዚፈዚደቜው ነገር ዚለምፀ በመሆኑም ኹፊቮ አስወግዳታለሁፀ
ይህም ዹሆነው ዚእስራኀልና ዚይሁዳ ሕዝብ ይኾውም እነሱ፣ ነገሥታታ቞ው፣ መኳንንታ቞ው፣ ካህናታ቞ው፣ ነቢያታ቞ው፣ ዚይሁዳ ሰዎቜና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ እኔን ለማስቆጣት በሠሩት ክፉ ነገር ሁሉ ዚተነሳ ነው።
ለእኔ ፊታ቞ውን ሳይሆን ጀርባ቞ውን ሰጡፀ ደግሜ ደጋግሜ ላስተምራ቞ው ብሞክርም፣ አንዳ቞ውም ተግሣጌን ለመቀበል ፈቃደኛ አይደሉም።
ስሜ ዚተጠራበትንም ቀት ለማርኚስ አስጞያፊ ጣዖቶቻ቞ውን በዚያ አስቀመጡ።
በተጚማሪም ወንዶቜና ሎቶቜ ልጆቻ቞ውን ለሞሎክ በእሳት አሳልፈው ለመስጠት በሂኖም ልጅ ሾለቆ ያሉትን ዚባአልን ኹፍ ያሉ ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ሠርተዋልፀ ይሁዳን ኃጢአት ለማሠራት ይህን አስጞያፊ ነገር እንዲፈጜሙ እኔ አላዘዝኩምፀ ፈጜሞም በልቀ አላሰብኩም።’
“ስለዚህ እናንተ በሰይፍ፣ በሚሃብና በቾነፈር ለባቢሎን ንጉሥ አልፋ ትሰጣለቜ ስለምትሏት ስለዚህቜ ኹተማ ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩
‘እነሆ፣ እነሱን በመዓቮና በታላቅ ቁጣዬ ኚበተንኩባ቞ው አገሮቜ ሁሉ አንድ ላይ እሰበስባ቞ዋለሁፀ ወደዚህም ቊታ መልሌ አመጣ቞ዋለሁፀ ያለስጋት እንዲኖሩም አደርጋለሁ።
እነሱም ሕዝቀ ይሆናሉፀ እኔም አምላካ቞ው እሆናለሁ።
ለእነሱም ሆነ ኚእነሱ በኋላ ለሚመጡት ልጆቻ቞ው መልካም ይሆንላቾው ዘንድ ዘወትር እኔን እንዲፈሩ አንድ ልብና አንድ መንገድ እሰጣ቞ዋለሁ።
ደግሞም ለእነሱ መልካም ነገር ኚማድሚግ እንዳልቆጠብ ኚእነሱ ጋር ዘላለማዊ ቃል ኪዳን እገባለሁፀ ኚእኔም እንዳይርቁ በልባ቞ው ውስጥ እኔን ዚመፍራት መንፈስ አሳድራለሁ።
ለእነሱ መልካም በማድሚግ እጅግ ደስ እሰኛለሁፀ በሙሉ ልቀና በሙሉ ነፍሮም በዚህቜ ምድር ላይ አጜንቌ እተክላ቞ዋለሁ።’”
“ይሖዋ እንዲህ ይላልና፩ ‘በዚህ ሕዝብ ላይ ይህን ሁሉ ታላቅ ጥፋት እንዳመጣሁ፣ ልክ እንዲሁ ቃል ዚገባሁላ቞ውን መልካም ነገር ሁሉ አመጣላ቞ዋለሁ።
እናንተ “ሰውም ሆነ እንስሳ ዚማይኖርባት ጠፍ መሬት ናትፀ ለኚለዳውያንም ተሰጥታለቜ” ብትሉም በዚህቜ ምድር ላይ እንደገና መሬት ይገዛል።’
“‘ተማርኹው ዚተወሰዱባ቞ውን ሰዎቜ መልሌ ስለማመጣ቞ው፣ በቢንያም አገር፣ በኢዚሩሳሌም ዙሪያ ባሉ ቊታዎቜ፣ በይሁዳ ኚተሞቜ፣ በተራራማው ምድር ባሉ ኚተሞቜ፣ በዝቅተኛው ስፍራ ባሉ ኚተሞቜና በደቡብ በሚገኙ ኚተሞቜ መሬት በገንዘብ ይገዛልፀ ዚግዢ ውል ተዘጋጅቶ በማኅተም ይታሞጋልፀ ምሥክሮቜም ይጠራሉ’ ይላል ይሖዋ።”
“እስራኀል ሆይ፣ ብትመለስ” ይላል ይሖዋ፣“ወደ እኔ ብትመለስ፣አስጞያፊ ጣዖቶቜህን ኹፊቮ ብታስወግድተንኚራታቜ አትሆንም።
‘በእውነት፣ በፍትሕና በጜድቅሕያው ይሖዋን!’ ብለህ ብትምል፣ብሔራት በእሱ አማካኝነት በሚኚት ያገኛሉፀበእሱም ይኮራሉ።”
ይሖዋ ለይሁዳ ሰዎቜና ለኢዚሩሳሌም እንዲህ ይላልና፩ “ያልለማውን መሬት እሚሱፀበእሟህ መካኚልም አትዝሩ።
እናንተ ዚይሁዳ ሰዎቜና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ፣ለይሖዋ ተገሚዙፀዚልባቜሁንም ሞለፈት አስወግዱፀአለዚያ በክፉ ሥራቜሁ ዚተነሳቁጣዬ እንደ እሳት ይነድዳልፀማንም ሊያጠፋው አይቜልም።”
ይህን በይሁዳ ተናገሩፀ በኢዚሩሳሌምም አውጁ። ጩኹፀ በምድሪቱም ሁሉ ላይ ቀንደ መለኚት ንፉ። ድምፃቜሁን ኹፍ አድርጋቜሁ እንዲህ በሉ፩ “አንድ ላይ ተሰብሰቡፀወደተመሞጉት ኚተሞቜም እንሜሜ።
ወደ ጜዮን ዹሚጠቁም ምልክት አቁሙ። መጠለያ ፈልጉፀ ዝም ብላቜሁም አትቁሙ።” ኹሰሜን ጥፋት ብሎም ታላቅ መዓት አመጣለሁና።
ጠላት እንደ አንበሳ ኚጥሻው ውስጥ ወጥቷልፀብሔራትንም ዚሚያጠፋው ተነስቷል። ምድርሜን አስፈሪ ቊታ ሊያደርግ ኚቊታው ወጥቷል። ኚተሞቜሜ አንድም ሰው ዚማይኖርባ቞ው ዚፍርስራሜ ክምር ይሆናሉ።
ስለዚህ ማቅ ልበሱፀእዘኑፀ ዋይ ዋይም በሉፀምክንያቱም ዹሚነደው ዹይሖዋ ቁጣ ኚእኛ አልተመለሰም።
“በዚያ ቀን” ይላል ይሖዋ፣ “ዚንጉሡ ልብናዚመኳንንቱ ልብ ይቀልጣልፀካህናቱም ይሞበራሉፀ ነቢያቱም ይገሚማሉ።”
ኚዚያም እንዲህ አልኩፊ “ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ሆይ፣ ወዮ! ሰይፍ አንገታቜን ላይ ተጋድሞ እያለ ‘ሰላም ታገኛላቜሁ’ ብለህ ይህን ሕዝብና ኢዚሩሳሌምን ፈጜሞ አታለሃል።”
በዚያን ጊዜ ለዚህ ሕዝብና ለኢዚሩሳሌም እንዲህ ይባላልፊ “ዚሚለበልብ ነፋስ በበሹሃ ኹሚገኙ ጠፍ ኮሚብቶቜ ተነስቶወደ ሕዝቀ ሎት ልጅ በፍጥነት ይነፍሳልፀነፋሱ ዹሚነፍሰው እህል ለማዝራትም ሆነ ለማጥራት አይደለም።
በእኔ ትእዛዝ ኃይለኛው ነፋስ ኚእነዚህ ስፍራዎቜ ይመጣል። አሁን በእነሱ ላይ ፍርድ አስተላልፋለሁ።
እነሆ፣ እሱ ዝናብ እንዳዘሉ ደመናት ይመጣልፀሠሚገሎቹም እንደ አውሎ ነፋስ ና቞ው። ፈሚሶቹ ኚንስር ይበልጥ ፈጣኖቜ ና቞ው። ጠፍተናልና ወዮልን!
ኢዚሩሳሌም ሆይ፣ እንድትድኚ ልብሜን ኚክፋት ሁሉ አጥሪ። እስኚ መቌ በውስጥሜ ክፉ ሐሳብ ይዘሜ ትኖሪያለሜ?
አንድ ድምፅ ኚዳን ዜናውን ይናገራልናፀኚኀፍሬም ተራሮቜም ጥፋትን ያውጃል።
ይህን አሳውቁፀ አዎ ለብሔራት ተናገሩፀበኢዚሩሳሌም ላይ አውጁ።” “ጠባቂዎቜ ኚሩቅ አገር እዚመጡ ነውፀበይሁዳ ኚተሞቜም ላይ ይጮኻሉ።
ማሳ እንደሚጠብቁ ሰዎቜ ኹሁሉም አቅጣጫ ይመጡባታልፀምክንያቱም እሷ በእኔ ላይ ዓምፃለቜ” ይላል ይሖዋ።
“ለተኚተልሜው መንገድና ለፈጞምሜው ተግባር ዋጋሜን ትቀበያለሜ። ዚሚደርስብሜ ጥፋት ምንኛ መራራ ነውፀወደ ልብሜ ዘልቆ ይገባልና!”
ወይ አበሳዬ! ወይ አበሳዬ! ልቀን ሥቃይ ቀስፎታል። ልቀ በውስጀ በኃይል ይመታል። ዝም ማለት አልቜልምፀዚቀንደ መለኚት ድምፅ፣ዚጊርነት ማስጠንቀቂያ ድምፅ ሰምቻለሁና።
በጥፋት ላይ ጥፋት መድሚሱ ተወርቷልፀምድሪቱ በሙሉ ወድማለቜና። ዹገዛ ድንኳኖቌ በድንገት፣ዚድንኳን ሞራዎቌም በቅጜበት ጠፍተዋል።
ምልክቱን ዹማዹውናዹቀንደ መለኚቱን ድምፅ ዹምሰማው እስኚ መቌ ድሚስ ነው?
“ሕዝቀ ሞኝ ነውናፀእነሱ ለእኔ ትኩሚት አይሰጡም። ማስተዋል ዹሌላቾው ቂል ልጆቜ ና቞ው። ክፉ ነገር ለማድሚግ ብልሃተኞቜ ና቞ውፀመልካም ነገር ማድሚግ ግን አያውቁም።”
ምድሪቱን አዚሁፀ እነሆም፣ ባዶና ወና ነበሚቜ። ወደ ሰማያት ተመለኚትኩፀ ብርሃና቞ው ጠፍቶ ነበር።
ተራሮቹን አዚሁፀ እነሆ፣ ይናወጡ ነበርፀኮሚብቶቹም ይንቀጠቀጡ ነበር።
እኔም ተመለኚትኩፀ እነሆ፣ በዚያ አንድም ሰው አልነበሚምፀዚሰማይ ወፎቜም ሁሉ ሞሜተው ነበር።
እኔም አዚሁፀ እነሆ፣ ዚፍራፍሬ እርሻው ምድሚ በዳ ሆኖ ነበርፀኚተሞቹም ሁሉ ፈራርሰው ነበር። ይህም ዹሆነው በይሖዋ፣በሚነደውም ቁጣው ዚተነሳ ነው።
ይሖዋ እንዲህ ይላልና፩ “ምድሪቱ በሙሉ ባድማ ትሆናለቜፀሆኖም ፈጜሜ አላጠፋትም።
ኹዚህ ዚተነሳ ምድሪቱ ታዝናለቜፀበላይ ያሉት ሰማያትም ይጚልማሉ። ምክንያቱም እኔ ተናግሬአለሁፀ ደግሞም ወስኛለሁፀሐሳቀንም አለውጥምፀ ወደ ኋላም አልመለስም።
ኚፈሚሰኞቹና ኚቀስተኞቹ ድምፅ ዚተነሳኚተማዋ በሙሉ ትሞሻለቜ። ጥሻ ውስጥ ይገባሉፀዓለቶቹም ላይ ይወጣሉ። ኚተሞቹ ሁሉ ተትተዋልፀዚሚኖርባ቞ውም ሰው ዚለም።”
ለጥፋት ተዳርገሻልፀ ታዲያ ምን ታደርጊ ይሆን? ደማቅ ቀይ ልብስ ትጎናጞፊ፣በወርቅ ጌጣጌጊቜ ታጌጪናዓይኖቜሜን ትኳዪ ነበር። ይሁንና ትዋቢ ዹነበሹው እንዲያው በኚንቱ ነውፀበፍትወት ስሜት ይኚተሉሜ ዚነበሩት ትተውሻልናፀአሁን ሕይወትሜን ይሿታል።
እንደታመመቜ ሎት ድምፅ፣ዚመጀመሪያ ልጇንም ለመውለድ እንደምታምጥ ሎት ያለ ዹጭንቅ ድምፅ፣ደግሞም ትንፋሜ አጥሯት ቁና ቁና ዚምትተነፍሰውን ዚጜዮን ሎት ልጅ ድምፅ ሰምቻለሁና። እሷም እጆቿን ዘርግታ “ወዮልኝ! ኚገዳዮቜ ዚተነሳ ዝያለሁና” ትላለቜ።
ዚይሁዳ ንጉሥ ሎዎቅያስ በነገሠ በዘጠነኛው ዓመት፣ በአሥሚኛው ወር፣ ዚባቢሎን ንጉሥ ናቡኚደነጟርና መላው ሠራዊቱ መጥተው ኢዚሩሳሌምን ኚበቧት።
በሎዎቅያስ ዘመነ መንግሥት በ11ኛው ዓመት፣ በአራተኛው ወር፣ ኚወሩም በዘጠነኛው ቀን ዚኚተማዋን ቅጥር ነደሉ።
ዚባቢሎን ንጉሥ መኳንንት ሁሉ ይኾውም ሳምጋሩ ኔርጋልሻሬጞር፣ ራብሳሪስ ዹሆነው ነቊሳርሰኪም፣ ራብማግ ዹሆነው ኔርጋልሻሬጞርና ዚቀሩት ዚባቢሎን ንጉሥ መኳንንት ሁሉ ገብተው በመካኚለኛው በር አጠገብ ተቀመጡ።
ዚይሁዳ ንጉሥ ሎዎቅያስና ወታደሮቹ ሁሉ ባዩአ቞ው ጊዜ፣ በንጉሡ ዚአትክልት ቊታ ባለው መንገድ፣ በሁለቱ ቅጥሮቜ መካኚል በሚገኘው በር በኩል በሌሊት ኹኹተማዋ ወጥተው ሞሹፀ ወደ አሚባ ዚሚወስደውንም መንገድ ተኚትለው ሄዱ።
ዚኚለዳውያን ሠራዊት ግን አሳደዳ቞ውፀ ሎዎቅያስንም በኢያሪኮ በሹሃማ ሜዳ ላይ ደሚሱበት። ኚያዙት በኋላ በሃማት ምድር በሪብላ ወደነበሹው ወደ ባቢሎን ንጉሥ ወደ ናቡኚደነጟር አመጡትፀ እሱም በዚያ ፈሚደበት።
ዚባቢሎን ንጉሥ በሪብላ ዚሎዎቅያስን ወንዶቜ ልጆቜ ዓይኑ እያዚ አሳሚዳ቞ውፀ በተጚማሪም ዚባቢሎን ንጉሥ ዚይሁዳን ታላላቅ ሰዎቜ ሁሉ አሳሚደ።