text
stringlengths
4
267
እኔም እያዚሁ ሳለ በኪሩቊቹ አጠገብ አራት መንኮራኩሮቜ ተመለኚትኩፀ በእያንዳንዱ ኪሩብ አጠገብ አንድ መንኮራኩር ነበርፀ መንኮራኩሮቹም እንደ ክርስቲሎቀ ድንጋይ ዚሚያብሚቀርቅ መልክ ነበራ቞ው።
ዚአራቱም መልክ ይመሳሰል ነበርፀ በአንድ መንኮራኩር ውስጥ በጎን በኩል ሌላ መንኮራኩር ዚተሰካ ይመስል ነበር።
በሚንቀሳቀሱበት ጊዜ መዞር ሳያስፈልጋ቞ው በአራቱም አቅጣጫ መሄድ ይቜሉ ነበርፀ ምክንያቱም መዞር ሳያስፈልጋ቞ው ፊታ቞ው ወደሚያይበት አቅጣጫ ሁሉ ይሄዱ ነበር።
ሰውነታ቞ው ሁሉ፣ ጀርባ቞ው፣ እጃ቞ው፣ ክንፋቾው እንዲሁም መንኮራኩሮቹ ይኾውም ዚአራቱም መንኮራኩሮቜ ሁለመና በዓይን ዹተሞላ ነበር።
አንድ ድምፅ መንኮራኩሮቹን “ተሜኚርካሪ መንኮራኩሮቜ!” ብሎ ሲጠራ቞ው ሰማሁ።
እያንዳንዳ቞ው አራት አራት ፊት ነበራ቞ው። ዚመጀመሪያው ፊት ዚኪሩብ ፊት፣ ሁለተኛው ፊት ዹሰው ፊት፣ ሊስተኛውም ዚአንበሳ ፊት፣ አራተኛው ደግሞ ዚንስር ፊት ነበር።
ኪሩቊቹም ወደ ላይ ተነሱፀ በኬባር ወንዝ ያዚኋ቞ው ሕያዋን ፍጥሚታት እነዚሁ ነበሩፀ
ኪሩቊቹ ሲንቀሳቀሱ፣ መንኮራኩሮቹም አጠገባ቞ው ሆነው ይንቀሳቀሱ ነበርፀ ኪሩቊቹ ኚምድር በላይ ኹፍ ኹፍ ለማለት ክንፎቻ቞ውን ወደ ላይ ሲዘሚጉ መንኮራኩሮቹ ኚአጠገባ቞ው አይለዩም ወይም አይርቁም ነበር።
እነሱ ሲቆሙ፣ መንኮራኩሮቹም ይቆማሉፀ እነሱ ኹፍ ኹፍ ሲሉ መንኮራኩሮቹም አብሚዋ቞ው ኹፍ ኹፍ ይሉ ነበርፀ በሕያዋን ፍጥሚታቱ ላይ ዚሚሠራው መንፈስ በውስጣ቞ው ነበርና።
ኚዚያም ዹይሖዋ ክብር ኚቀተ መቅደሱ በር ደጃፍ ተነስቶ በመሄድ ኚኪሩቊቹ በላይ ቆመ።
ኪሩቊቹ እኔ እያዚኋ቞ው ክንፎቻ቞ውን ወደ ላይ ዘርግተው ኚምድር ተነሱ። እነሱ ሲሄዱ መንኮራኩሮቹም አብሚዋ቞ው ነበሩ። በይሖዋ ቀት በስተ ምሥራቅ በሚገኘው በር መግቢያም ላይ ቆሙፀ ዚእስራኀል አምላክ ክብርም በላያ቞ው ነበር።
እነዚህ በኬባር ወንዝ አቅራቢያ ኚእስራኀል አምላክ በታቜ ያዚኋ቞ው ሕያዋን ፍጥሚታት ና቞ውፀ በመሆኑም ኪሩቊቜ መሆናቾውን አወቅኩ።
አራቱም፣ አራት አራት ፊትና አራት አራት ክንፍ ነበራ቞ውፀ ኚክንፎቻ቞ውም ሥር ዹሰው እጆቜ ዚሚመስሉ ነገሮቜ ነበሯ቞ው።
ዚፊታ቞ውም መልክ በኬባር ወንዝ አቅራቢያ እንዳዚኋ቞ው ፊቶቜ ነበር። እያንዳንዳ቞ው ቀጥ ብለው ወደ ፊት ይሄዱ ነበር።
ዹይሖዋ ቃል ዳግመኛ እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣፊ
“ዹሰው ልጅ ሆይ፣ ለኢዚሩሳሌም አስጞያፊ ልማዶቿን አሳውቃት።
እንዲህ በል፩ ‘ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ለኢዚሩሳሌም እንዲህ ይላል፩ “መገኛሜና ትውልድሜ በኚነአናውያን ምድር ነው። አባትሜ አሞራዊ፣ እናትሜም ሂታዊት ነበሩ።
አወላለድሜንም በተመለኚተ፣ በተወለድሜበት ቀን እትብትሜ አልተቆሚጠምፀ ንጹሕም እንድትሆኚ በውኃ አልታጠብሜምፀ በጹውም አልታሞሜምፀ ደግሞም በጹርቅ አልተጠቀለልሜም።
ለአንቺ አዝኖ ኚእነዚህ ነገሮቜ አንዱንም እንኳ ያደሚገልሜ ዚለም። ዚራራልሜም ዚለም። ይልቁንም በተወለድሜበት ቀን ስለተጠላሜ አውላላ ሜዳ ላይ ተጣልሜ።
“‘“በአጠገብሜ ሳልፍ በደምሜ ላይ ስትንፈራገጪ አዚሁሜፀ ደግሞም በደምሜ ላይ ተኝተሜ ሳለ ‘በሕይወት ኑሪ!’ አልኩሜ። አዎ፣ በደምሜ ላይ ተኝተሜ ሳለ ‘በሕይወት ኑሪ!’ አልኩሜ።
በሜዳ ላይ እንደሚበቅሉ ዕፀዋት እጅግ እንድትበዢ አደሚግኩፀ አንቺም አደግሜፀ ደግሞም ሙሉ ሰው ሆንሜፀ እጅግ ያማሚ ጌጥም አደሚግሜ። ጡቶቜሜ አጎጠጎጡፀ ፀጉርሜም አደገፀ ይሁንና በዚህ ጊዜም እርቃንሜንና ራቁትሜን ነበርሜ።”’
“‘በአጠገብሜ ሳልፍ አዚሁሜፀ ዹፍቅር ግንኙነት ለመጀመር ዕድሜሜ እንደደሚሰ አስተዋልኩ። ስለዚህ ልብሎን በአንቺ ላይ ዘርግቌ እርቃንሜን ሞፈንኩፀ ደግሞም ማልኩልሜፀ ኚአንቺም ጋር ቃል ኪዳን አደሚግኩ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋፀ ‘አንቺም ዚእኔ ሆንሜ።
በተጚማሪም በውኃ አጠብኩሜፀ ኚደምሜም አነጻሁሜፀ ዘይትም ቀባሁሜ።
ኚዚያም ዹተጠለፈ ሾማ አለበስኩሜፀ ኚጥሩ ቆዳ ዚተሠራ ጫማም ሰጠሁሜፀ በጥሩ በፍታም ጠቀለልኩሜፀ እጅግ ውድ ዹሆነ ልብስም አለበስኩሜ።
በጌጣጌጥ አንቆጠቆጥኩሜፀ በእጆቜሜ አምባር፣ በአንገትሜም ሐብል አጠለቅኩልሜ።
በተጚማሪም በአፍንጫሜ ቀለበት፣ በጆሮዎቜሜ ጉትቻ፣ በራስሜም ላይ ዚሚያምር አክሊል አደሚግኩልሜ።
ራስሜን በወርቅና በብር አስጌጥሜፀ ልብስሜም ጥሩ በፍታ፣ እጅግ ውድ በሆነ ጹርቅ ዚተሠራና ዹተጠለፈ ሾማ ነበር። ምግብሜም ዹላመ ዱቄት፣ ማርና ዘይት ነበርፀ እጅግ ውብ ሆንሜፀ ንግሥት ለመሆንም በቃሜ።’”
“‘ኚውበትሜ ዚተነሳ ዝናሜ በብሔራት መካኚል ገነነፀ ውበትሜ በአንቺ ላይ ካኖርኩት ግርማዬ ዚተነሳ ፍጹም ሆኖ ነበርና’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።”
“‘ሆኖም አንቺ በውበትሜ መመካት ጀመርሜፀ ዝናሜንም ለዝሙት አዳሪነት ተጠቀምሜበት። ኹአላፊ አግዳሚው ጋር ያለገደብ አመነዘርሜፀ ውበትሜንም ለማንም አሳልፈሜ ሰጠሜ።
ዚተለያዩ ቀለማት ካሏ቞ው ልብሶቜሜ አንዳንዶቹን ወስደሜ ዚምታመነዝሪባ቞ውን ኹፍ ያሉ ዚማምለኪያ ቊታዎቜሜን አስጌጥሜባ቞ውፀ እነዚህ ነገሮቜ መሆን ዚለባ቞ውምፀ ጚርሶ ሊፈጾሙም አይገባም።
ደግሞም በሰጠሁሜ ወርቅና ብር ዚተሠሩትን ያማሩ ጌጣጌጊቜሜን ወስደሜ ለራስሜ ዚወንድ ምስሎቜ ሠራሜፀ ኚእነሱም ጋር አመነዘርሜ።
ዹተጠለፉ ሞማዎቜሜንም ወስደሜ አለበስሻ቞ውፀ ዘይቮንና ዕጣኔንም አቀሚብሜላ቞ው።
ደግሞም እንድትበዪው ዚሰጠሁሜን ኹላመ ዱቄት፣ ኚዘይትና ኹማር ዹተዘጋጀ ምግብ ደስ ዚሚያሰኝ መዓዛ አድርገሜ አቀሚብሜላ቞ው። ዹተፈጾመው ነገር ይኾው ነው’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።”
“‘ለእኔ ዚወለድሻ቞ውን ወንዶቜና ሎቶቜ ልጆቜሜን ወስደሜ መብል ይሆኑ ዘንድ ለጣዖቶቹ ሠዋሜላ቞ውፀ ዚምትፈጜሚው ምንዝር እጅግ አልበዛም?
ወንዶቜ ልጆቌን አሚድሜፀ በእሳትም አሳልፈሜ መሥዋዕት አድርገሜ አቀሚብሻ቞ው።
አስጞያፊ ልማዶቜሜንና ምንዝርሜን ሁሉ ስትፈጜሚ እርቃንሜንና ራቁትሜን ሆነሜ በገዛ ደምሜ ላይ ስትንፈራገጪ ዚነበርሜበትን ዚልጅነትሜን ጊዜ አላስታወስሜም።
ይህን ሁሉ ክፋት ኚፈጞምሜ በኋላ ወዮ፣ ወዮልሜ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።
‘ለራስሜ ጉብታ አበጀሜፀ በዚአደባባዩም ኹፍ ያለ ቊታ ሠራሜ።
በዚመንገዱ ላይ በሚገኝ ዚታወቀ ስፍራ ሁሉ ኹፍ ያለ ቊታ ሠራሜፀ ለአላፊ አግዳሚው ሁሉ ራስሜን በመስጠት ውበትሜን ወደ አስጞያፊ ነገር ለወጥሜፀ ዚምትፈጜሚውንም ምንዝር አበዛሜ።
በፍትወት ኹተቃጠሉ ጎሚቀቶቜሜ ይኾውም ኚግብፅ ወንዶቜ ልጆቜ ጋር አመነዘርሜፀ ገደብ በሌለው ምንዝርሜ አስቆጣሜኝ።
አሁን እጄን በአንቺ ላይ እዘሚጋለሁፀ ቀለብሜንም እቀንሳለሁፀ በጞያፍ ተግባርሜ ዚተነሳ ዚሚሞማቀቁትና ዚሚጠሉሜ ሎቶቜ ይኾውም ዚፍልስጀም ሎቶቜ ልጆቜ ያሻ቞ውን እንዲያደርጉብሜ አሳልፌ እሰጥሻለሁ።
“‘እርካታ ባለማግኘትሜ ኹአሩር ወንዶቜ ልጆቜ ጋር ደግሞ አመነዘርሜፀ ሆኖም ኚእነሱ ጋር ካመነዘርሜ በኋላም እንኳ አልሚካሜም።
ስለዚህ ምንዝርሜን በነጋዎዎቜ ምድርና በኚለዳውያን ምድር አበዛሜፀ ያም ሆኖ እንኳ አልሚካሜም።
ዓይን አውጣ እንደሆነቜ ዝሙት አዳሪ ይህን ሁሉ ነገር ዚፈጞምሜው ልብሜ ምንኛ ታማሚ ቢሆን ነው!’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።
‘ይሁንና በዚመንገዱ ላይ በሚገኝ ዚታወቀ ስፍራ ሁሉ ጉብታሜን ስታበጂና በዚአደባባዩ ለራስሜ ኹፍ ያለ ቊታ ስትሠሪ እንደ ዝሙት አዳሪ አልሆንሜምፀ ምክንያቱም ምንም ዓይነት ክፍያ አትቀበዪም።
አንቺ በባሏ ፋንታ እንግዳ ዹሆኑ ሰዎቜን ዚምታስተናግድ አመንዝራ ሚስት ነሜ!
ሰዎቜ ለዝሙት አዳሪዎቜ ሁሉ ስጊታ ይሰጣሉፀ በፍትወት ለሚመኙሜ ሁሉ ስጊታ ዚሰጠሜው ግን አንቺ ነሜፀ ደግሞም ኚዚቊታው መጥተው ኚአንቺ ጋር እንዲያመነዝሩ ጉቩ ትሰጫ቞ዋለሜ።
አንቺ ኚሌሎቜ ዝሙት አዳሪ ሎቶቜ ፈጜሞ ዚተለዚሜ ነሜ። አንቺ ዚፈጞምሜው ዓይነት ምንዝር ዹፈጾመ ሰው ታይቶ አይታወቅም! አንቺ ትኚፍያ቞ዋለሜ እንጂ እነሱ አይኚፍሉሜም። ዚአንቺ አድራጎት ተቃራኒ ነው።’
“በመሆኑም አንቺ ዝሙት አዳሪ፣ ዹይሖዋን ቃል ስሚ።
ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ኚፍቅሚኞቜሜና ዚወንዶቜ ልጆቜሜን ደም መሥዋዕት አድርገሜ ካቀሚብሜላ቞ው አስጞያፊና ቀፋፊ ጣዖቶቜሜ ሁሉ ጋር ባመነዘርሜ ጊዜ ኹልክ በላይ በፍትወት ስለተቃጠልሜና እርቃንሜ ስለተገለጠ፣
እኔ ደስ ያሰኘሻ቞ውን ፍቅሚኞቜሜን ሁሉ፣ ዚወደድሻ቞ውንም ሆነ ዚጠላሻ቞ውን ሁሉ አንድ ላይ እሰበስባለሁ። እነሱን ኚዚቊታው በአንቺ ላይ እሰበስባ቞ዋለሁፀ እርቃንሜን ለእነሱ እገልጣለሁፀ እነሱም ሙሉ በሙሉ እርቃንሜን ሆነሜ ያዩሻል።
“‘አመንዝሮቜና ደም ዚሚያፈሱ ሎቶቜ ሊፈሚድባ቞ው በሚገባው ፍርድ እቀጣሻለሁፀ ደግሞም በቁጣና በቅናት ደምሜ ይፈስሳል።
በእጃ቞ው አሳልፌ እሰጥሻለሁፀ እነሱም ጉብታዎቜሜን ያፈርሳሉፀ ኹፍ ያሉ ቊታዎቜሜንም ያወድማሉፀ ልብሶቜሜንም ይገፉሻልፀ ያማሩ ጌጣጌጊቜሜንም ይወስዳሉፀ እርቃንሜንና ራቁትሜንም ያስቀሩሻል።
ብዙ ሰዎቜን ያነሳሱብሻልፀ በድንጋይም ይወግሩሻልፀ በሰይፋቾውም ያርዱሻል።
ቀቶቜሜን በእሳት ያቃጥላሉፀ በብዙ ሎቶቜም ፊት በአንቺ ላይ ፍርዮን ይፈጜማሉፀ ምንዝርሜንም አስተውሻለሁፀ ኚእንግዲህም ወዲህ ዋጋ አትኚፍዪም።
በአንቺ ላይ ዹነበሹው ቁጣዬ ይበርዳልፀ ንዮቮም ኚአንቺ ይርቃል። እኔም እሚጋጋለሁፀ ኚእንግዲህም አልቆጣም።’
“‘ዚልጅነት ጊዜሜን ስላላስታወስሜና እነዚህን ነገሮቜ ሁሉ በማድሚግ ስላስቆጣሜኝ እኔም ዚተኚተልሜው መንገድ ዚሚያስኚትለውን መዘዝ በራስሜ ላይ አመጣብሻለሁ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋፀ ‘አንቺም ኚእንግዲህ ወዲህ አስነዋሪ ምግባርሜንና አስጞያፊ ዹሆኑ ልማዶቜሜን ሁሉ አትፈጜሚም።
“‘እነሆ፣ ምሳሌያዊ አባባል ዹሚጠቀም ሁሉ “ልጅቷም በእናቷ ወጣቜ!” እያለ ይተርትብሻል።
አንቺ ዚእናትሜ ልጅ ነሜፀ እሷ ባሏንና ልጆቿን ትንቃለቜ። ደግሞም ባሎቻ቞ውንና ልጆቻ቞ውን ዚናቁት ዚእህቶቜሜ እህት ነሜ። እናታቜሁ ሂታዊት፣ አባታቜሁ ደግሞ አሞራዊ ነበሩ።’”
“‘ታላቅ እህትሜ ኚሎቶቜ ልጆቿ ጋር ኚአንቺ በስተ ሰሜን ዚምትኖሚው ሰማርያ ናትፀ ታናሜ እህትሜም ኚሎቶቜ ልጆቿ ጋር ኚአንቺ በስተ ደቡብ ዚምትኖሚው ሰዶም ናት።
በእነሱ መንገድ መሄድና ዚእነሱን አስጞያፊ ልማዶቜ መኹተል ብቻ ሳይሆን በጥቂት ጊዜ ውስጥ በምግባርሜ ሁሉ ኚእነሱ ይበልጥ ብልሹ ሆንሜ።
በሕያውነ቎ እምላለሁ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፣ ‘አንቺና ሎቶቜ ልጆቜሜ ያደሚጋቜሁትን እህትሜ ሰዶምና ሎቶቜ ልጆቿ አላደሚጉትም።
እነሆ፣ ዚእህትሜ ዚሰዶም በደል ይህ ነበር፩ እሷና ሎቶቜ ልጆቿ ኩራተኞቜ ነበሩፀ ዚተትሚፈሚፈ ምግብ ዚነበራ቞ው ሲሆን ያለጭንቀት ተሹጋግተው ይኖሩ ነበርፀ ይሁንና ጎስቋላውንና ድሃውን አልደገፉም።
እነሱም ትዕቢታ቞ውን አላስወገዱምፀ በፊቮም አስጞያፊ ዹሆኑ ልማዶቜን መፈጾማቾውን ቀጠሉፀ በመሆኑም እነሱን ማስወገድ ተገቢ ሆኖ አገኘሁት።
“‘ሰማርያም ብትሆን አንቺ ዚሠራሜውን ኃጢአት ግማሹን እንኳ አልሠራቜም። አንቺ ኚምትፈጜሚያ቞ው አስጞያፊ ልማዶቜ ሁሉ ዚተነሳ እህቶቜሜ ጻድቃን መስለው እስኪታዩ ድሚስ ኚእነሱ ይበልጥ ብዙ አስጞያፊ ልማዶቜ መፈጞምሜን ቀጠልሜ።
ዚእህቶቜሜ ምግባር ተገቢ መስሎ እንዲታይ ስላደሚግሜ አሁን ኀፍሚትሜን ተኚናነቢ። ኚእነሱ ይበልጥ አስጞያፊ በሆነ መንገድ ኚፈጞምሜው ኃጢአት ዚተነሳ እነሱ ኚአንቺ ይልቅ ጻድቃን ሆነዋል። እንግዲህ እህቶቜሜን ጻድቃን ስላስመሰልሻ቞ው ኀፍሚት ተኚናነቢፀ ውርደትሜንም ተሞኚሚ።’
“‘በምርኮ ዚተወሰዱባ቞ውን ይኾውም ኚሰዶምና ኚሎቶቜ ልጆቿ ዚተማሚኩትን እንዲሁም ኚሰማርያና ኚሎቶቜ ልጆቿ ዚተማሚኩትን እሰበስባለሁፀ በተጚማሪም ኚአንቺ ዚተማሚኩትን ኚእነሱ ጋር እሰበስባለሁፀ
ይህም ዹሚሆነው ውርደትሜን እንድትሞኚሚ ነውፀ ደግሞም እነሱን በማጜናናት ባደሚግሜው ነገር ዚተነሳ ውርደት ትኚናነቢያለሜ።
ዹገዛ እህቶቜሜ፣ ሰዶምና ሎቶቜ ልጆቿ ወደ ቀድሞ ሁኔታ቞ው ይመለሳሉፀ እንዲሁም ሰማርያና ሎቶቜ ልጆቿ ወደ ቀድሞ ሁኔታ቞ው ይመለሳሉፀ አንቺና ሎቶቜ ልጆቜሜም ቀድሞ ወደነበራቜሁበት ሁኔታ ትመለሳላቜሁ።
ኩሩ በነበርሜበት ቀን እህትሜ ሰዶም በአንደበትሜ ለመጠራት እንኳ ዚምትበቃ አልነበሚቜምፀ
ይህም ዹሆነው ክፋትሜ ኚመጋለጡ በፊት ነበር። አሁን ግን ዚሶርያ ሎቶቜ ልጆቜና ጎሚቀቶቿ በአንቺ ላይ ነቀፋ ይሰነዝራሉፀ እንዲሁም ዚፍልስጀማውያን ሎቶቜ ልጆቜ፣ በዙሪያሜም ያሉ ሁሉ በንቀት ያዩሻል።
አስነዋሪ ምግባርሜና አስጞያፊ ልማዶቜሜ ዚሚያስኚትሉብሜን መዘዝ ትቀበያለሜ’ ይላል ይሖዋ።”
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፩ ‘እንግዲህ ቃል ኪዳኔን በማፍሚስ መሐላውን ስለናቅሜ እኔም እንዳደሚግሜው አደርግብሻለሁ።
ይሁንና እኔ ራሎ በልጅነትሜ ጊዜ ኚአንቺ ጋር ዚገባሁትን ቃል ኪዳን አስታውሳለሁፀ ደግሞም ኚአንቺ ጋር ዘላቂ ቃል ኪዳን አደርጋለሁ።
ታላላቆቜሜና ታናናሟቜሜ ዚሆኑትን እህቶቜሜን ስትቀበዪ ምግባርሜን ታስታውሻለሜፀ ደግሞም ታፍሪያለሜፀ እኔም እነሱን ሎቶቜ ልጆቜ አድርጌ እሰጥሻለሁፀ ይህን ዹማደርገው ግን ኚአንቺ ጋር በገባሁት ቃል ኪዳን ዚተነሳ አይደለም።’
“‘እኔ ራሎም ኚአንቺ ጋር ዚገባሁትን ቃል ኪዳን አጞናለሁፀ አንቺም እኔ ይሖዋ እንደሆንኩ ታውቂያለሜ።
ኚዚያም፣ ያን ሁሉ ነገር ብታደርጊም እንኳ ለአንቺ ባስተሰሚይኩልሜ ጊዜ ሥራሜን ታስታውሻለሜፀ ኚደሚሰብሜም ውርደት ዚተነሳ አፍሜን ለመክፈት እጅግ ታፍሪያለሜ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ።”
“አንተም ዹሰው ልጅ ሆይ፣ እንደ ፀጉር አስተካካይ ምላጭ ዚምትጠቀምበት ስለታም ሰይፍ ውሰድ። ዚራስህን ፀጉርና ጢምህን ተላጭፀ ኚዚያም ሚዛን ወስደህ ፀጉሩን መዝነውና ኚፋፍለው።
ዚኚበባው ጊዜ ሲፈጞም አንድ ሊስተኛውን በኹተማዋ ውስጥ በእሳት ታቃጥለዋለህ። ኚዚያም ሌላ አንድ ሊስተኛ ወስደህ በኹተማዋ ዙሪያ በሰይፍ ትመታዋለህፀ ዚመጚሚሻውንም አንድ ሊስተኛ ለነፋስ ትበትነዋለህፀ እኔም እነሱን ለማሳደድ ሰይፍ እመዛለሁ።
“ደግሞም ኚፀጉሮቹ ላይ ጥቂት ወስደህ በልብስህ እጥፋት ቋጥራ቞ው።
ዹተወሰነውን ደግሞ ወስደህ እሳት ውስጥ ጚምሚውፀ ሙሉ በሙሉም በእሳት አቃጥለው። ይህ እሳት ወጥቶ በእስራኀል ቀት ሁሉ ይሰራጫል።
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ይህቜ ኢዚሩሳሌም ናት። አገሮቜን በዙሪያዋ አድርጌ፣ በብሔራት መካኚል አስቀምጫታለሁ።
እሷ ግን ኚብሔራትና በዙሪያዋ ካሉ አገሮቜ ሁሉ ዚባሰ ክፋት በመሥራት በድንጋጌዎቌና ባወጣኋ቞ው ደንቊቜ ላይ ዓምፃለቜ። ሕዝቡ ድንጋጌዎቌን ወደ ጎን ገሞሜ አድርጓልናፀ ደንቊቌንም አክብሮ አልተመላለሰም።’
“ስለዚህ ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘በዙሪያቜሁ ካሉት ብሔራት ይበልጥ አስ቞ጋሪ በመሆናቜሁ፣ ደንቊቌን አክብራቜሁ ባለመመላለሳቜሁ ወይም ድንጋጌዎቌን ባለመጠበቃቜሁ፣ ይልቁንም በዙሪያቜሁ ያሉትን ብሔራት ድንጋጌዎቜ በመኚተላቜሁ፣
ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “አንቺ ኹተማ ሆይ፣ በአንቺ ላይ ተነስቻለሁፀ ደግሞም እኔ ራሎ በብሔራት ፊት በመካኚልሜ ፍርዮን አስፈጜማለሁ።
በአስጞያፊ ድርጊቶቜሜ ሁሉ ዚተነሳ ኹዚህ በፊት ፈጜሞ ያላደሚግኩትን፣ ኹዚህም በኋላ ዹማልደግመውን በአንቺ ላይ አደርጋለሁ።
“‘“ስለዚህ በመካኚልሜ አባቶቜ ልጆቻ቞ውን ይበላሉፀ ልጆቜም አባቶቻ቞ውን ይበላሉፀ በመካኚልሜ ፍርዮን አስፈጜማለሁፀ ኚአንቺ ዚቀሩትንም በሙሉ በዚአቅጣጫው እበትና቞ዋለሁ።”’
“‘ስለዚህ በሕያውነ቎ እምላለሁ’ ይላል ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ፣ ‘በአስጞያፊ ጣዖቶቜሜ ሁሉና ጞያፍ በሆኑ ድርጊቶቜሜ ሁሉ መቅደሮን ስላሚኚስሜ፣ እኔ ራሎ እተውሻለሁፀ ዓይኔ አያዝንም ደግሞም አልራራም።
ኚአንቺም አንድ ሊስተኛው በቾነፈር ይሞታል ወይም በመካኚልሜ በሚሃብ ያልቃል። ሌላ አንድ ሊስተኛ ደግሞ በዙሪያሜ በሰይፍ ይወድቃል። ዚመጚሚሻውን አንድ ሊስተኛ ደግሞ በዚአቅጣጫው እበትነዋለሁፀ እነሱንም ለማሳደድ ሰይፍ እመዛለሁ።
ኚዚያም ቁጣዬ ይፈጞማልፀ በእነሱም ላይ ዹነደደው ቁጣዬ ይበርዳልፀ እኔም እሚካለሁ። በእነሱም ላይ ቁጣዬን ፈጜሜ ባወሚድኩ ጊዜ፣ እኔ ብቻ መመለክ ዚምፈልገው፣ እኔ ይሖዋ ይህን እንደተናገርኩ ያውቃሉ።
“‘በዙሪያሜ ባሉ ብሔራት መካኚል እንዲሁም በአጠገብሜ በሚያልፉ ሁሉ ፊት ባድማና መሳለቂያ አደርግሻለሁ።
በቁጣ፣ በንዎትና በኃይለኛ ቅጣት ዚፍርድ እርምጃ ስወስድብሜ በዙሪያሜ ባሉ ብሔራት ዘንድ መሳለቂያና መዘባበቻ ደግሞም ዚማስጠንቀቂያ ምሳሌና ማስፈራሪያ ትሆኛለሜ። እኔ ይሖዋ ይህን ተናግሬአለሁ።
“‘እነሱን ለማጥፋት ገዳይ ዹሆኑ ዚሚሃብ ፍላጻዎቜን እሰድባ቞ዋለሁ። ዚምሰዳ቞ው ዚሚሃብ ፍላጻዎቜ ያጠፏቜኋል። ዚምግብ አቅርቊታቜሁ እንዲቋሚጥ በማድሚግ ሚሃቡን አባብሳለሁ።
በእናንተ ላይ ሚሃብንና አደገኛ ዚዱር አራዊትን እሰዳለሁፀ እነሱም ዚወላድ መሃን ያደርጓቜኋል። ቾነፈርና ደም መፋሰስ ያጥለቀልቋቜኋልፀ ሰይፍም አመጣባቜኋለሁ። እኔ ይሖዋ ይህን ተናግሬአለሁ።’”
“ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ኚምሥራቅ ትይዩ ዹሆነው ዚውስጠኛው ግቢ በር በስድስቱ ዚሥራ ቀናት ዝግ እንደሆነ ይቆይፀ ሆኖም በሰንበት ቀንና አዲስ ጹሹቃ በምትወጣበት ቀን ይኚፈት።
አለቃው ኹውጭ በኩል በበሩ በሚንዳ ገብቶ በበሩ መቃን አጠገብ ይቆማል። ካህናቱ ዚእሱን ሙሉ በሙሉ ዹሚቃጠል መባና ዚኅብሚት መሥዋዕት ያቀርባሉፀ እሱም በበሩ ደፍ ላይ ይሰግዳልፀ ኚዚያም ይወጣል። በሩ ግን እስኚ ምሜት ድሚስ አይዘጋ።
ዚምድሪቱም ነዋሪዎቜ በዚሰንበቱና አዲስ ጹሹቃ በምትወጣበት ቀን በበሩ መግቢያ ላይ በይሖዋ ፊት ይሰግዳሉ።
“‘አለቃው በሰንበት ቀን እንኚን ዚሌለባ቞ው ስድስት ተባዕት ዹበግ ጠቊቶቜና እንኚን ዚሌለበት አንድ አውራ በግ ለይሖዋ ሙሉ በሙሉ ዹሚቃጠል መባ አድርጎ ማቅሚብ ይኖርበታል።
ለአውራ በጉ አንድ ኢፍ ዚእህል መባ፣ ለተባዕት ዹበግ ጠቊቶቹም መስጠት ዚሚቜለውን ያህል ዚእህል መባ እንዲሁም ለእያንዳንዱ ኢፍ አንድ ሂን ዘይት ያቀርባል።
አዲስ ጹሹቃ በምትወጣበት ቀን ኚኚብቶቹ መካኚል እንኚን ዚሌለበት አንድ ወይፈን፣ ስድስት ተባዕት ዹበግ ጠቊቶቜና አንድ አውራ በግ ያቀርባልፀ ሁሉም እንኚን ዚሌለባ቞ው ይሁኑ።