text
stringlengths
4
267
ወዲያውም፣ ትንሽ ልጇ በርኩስ መንፈስ የተያዘችባት አንዲት ሴት ስለ እሱ ሰምታ መጣችና እግሩ ላይ ወደቀች።
ሴትየዋ ግሪካዊት፣ በዜግነት ደግሞ ሲሮፊንቃዊት ነበረች፤ እሷም ጋኔኑን ከልጇ እንዲያስወጣላት ወተወተችው።
እሱ ግን “የልጆችን ዳቦ ወስዶ ለቡችሎች መጣል ተገቢ ስላልሆነ መጀመሪያ ልጆቹ ይጥገቡ” አላት።
ሆኖም ሴትየዋ መልሳ “አዎ ጌታዬ፣ ቡችሎችም እኮ ከገበታ በታች ሆነው ከልጆች የሚወድቀውን ፍርፋሪ ይበላሉ” አለችው።
በዚህ ጊዜ “ሂጂ፤ እንዲህ ስላልሽ ጋኔኑ ከልጅሽ ወጥቷል” አላት።
እሷም ወደ ቤቷ ስትመለስ ልጇ አልጋ ላይ ተኝታ፣ ጋኔኑም ወጥቶላት አገኘቻት።
ኢየሱስ ከጢሮስ ክልል ሲመለስ በሲዶና በኩል አድርጎ ዲካፖሊስ በተባለው ክልል በማለፍ ወደ ገሊላ ባሕር ሄደ።
በዚያም ሰዎች መስማት የተሳነውና የመናገር እክል ያለበት አንድ ሰው ወደ እሱ አምጥተው እጁን እንዲጭንበት ተማጸኑት።
እሱም ከሕዝቡ ለይቶ ለብቻው ወሰደው። ከዚያም ጣቶቹን በሰውየው ጆሮዎች ውስጥ አስገባ፤ እንትፍ ካለ በኋላም የሰውየውን ምላስ ዳሰሰ።
ወደ ሰማይ እየተመለከተም በረጅሙ ተንፍሶ “ኤፈታ” አለው፤ ይህም “ተከፈት” ማለት ነው።
በዚህ ጊዜ ጆሮዎቹ ተከፈቱ፤ ምላሱም ተፈቶ አጥርቶ መናገር ጀመረ።
ይህን ለማንም እንዳይናገሩ አዘዛቸው፤ እነሱ ግን ይበልጥ ባስጠነቀቃቸው መጠን የዚያኑ ያህል ነገሩን በስፋት ያወሩ ነበር።
እንዲያውም ከመጠን በላይ ከመደነቃቸው የተነሳ “ያደረገው ነገር ሁሉ መልካም ነው። ሌላው ቀርቶ መስማት የተሳናቸው ሰዎች እንዲሰሙ፣ ዱዳዎችም እንዲናገሩ ያደርጋል” አሉ።
ከቤተ መቅደስ እየወጣ ሳለ ከደቀ መዛሙርቱ አንዱ “መምህር፣ እንዴት ያሉ ግሩም ድንጋዮችና ሕንጻዎች እንደሆኑ ተመልከት!” አለው።
ኢየሱስ ግን “እነዚህን ታላላቅ ሕንጻዎች ታያለህ? ይህ ሁሉ ሳይፈርስ እንዲህ ድንጋይ በድንጋይ ላይ እንደተነባበረ ከቶ አይኖርም” አለው።
በቤተ መቅደሱ ትይዩ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ተቀምጦ ሳለ ጴጥሮስ፣ ያዕቆብ፣ ዮሐንስና እንድርያስ ብቻቸውን ሆነው እንዲህ በማለት ጠየቁት፦
“እስቲ ንገረን፣ እነዚህ ነገሮች የሚፈጸሙት መቼ ነው? የእነዚህ ነገሮች ሁሉ መደምደሚያ መቅረቡን የሚያሳየው ምልክትስ ምንድን ነው?”
ኢየሱስም እንዲህ ይላቸው ጀመር፦ “ማንም እንዳያሳስታችሁ ተጠንቀቁ።
ብዙዎች ‘እኔ እሱ ነኝ’ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ ብዙዎችንም ያሳስታሉ።
ከዚህም ሌላ ጦርነትና የጦርነት ወሬ ስትሰሙ አትደናገጡ፤ እነዚህ ነገሮች መፈጸማቸው የግድ ነው፤ ሆኖም ፍጻሜው ገና ነው።
“ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሳልና፤ በተለያየ ስፍራ የምድር ነውጥ ይከሰታል፤ በተጨማሪም የምግብ እጥረት ይኖራል። እነዚህ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው።
“እናንተ ግን ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። ሰዎች ለፍርድ ሸንጎ አሳልፈው ይሰጧችኋል፤ በምኩራብም ትገረፋላችሁ፤ በእኔ ምክንያት በገዢዎችና በነገሥታት ፊት ያቀርቧችኋል፤ በዚያ ጊዜ ለእነሱ መመሥከር ትችላላችሁ።
አስቀድሞም ምሥራቹ ለብሔራት ሁሉ መሰበክ አለበት።
አሳልፈው ለመስጠት በሚወስዷችሁ ጊዜም ምን እንላለን በማለት አስቀድማችሁ አትጨነቁ፤ ከዚህ ይልቅ በዚያች ሰዓት የሚሰጣችሁን ተናገሩ፤ የሚናገረው መንፈስ ቅዱስ እንጂ እናንተ አይደላችሁምና።
በተጨማሪም ወንድም ወንድሙን፣ አባትም ልጁን ለሞት አሳልፎ ይሰጣል፤ ልጆችም በወላጆቻቸው ላይ ይነሳሉ፤ ደግሞም ያስገድሏቸዋል።
በስሜ የተነሳም ሰዎች ሁሉ ይጠሏችኋል። እስከ መጨረሻው የጸና ግን ይድናል።
“ይሁንና ጥፋት የሚያመጣው ‘ርኩስ ነገር’ በማይገባው ስፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል፤ በዚህ ጊዜ በይሁዳ ያሉ ወደ ተራሮች ይሽሹ።
በጣሪያ ላይ ያለ ሰው አይውረድ፤ አንዳችም ነገር ለመውሰድ ወደ ቤቱ አይግባ፤
በእርሻም ያለ መደረቢያውን ለመውሰድ ወደ ኋላ አይመለስ።
በእነዚያ ቀናት ለነፍሰ ጡሮችና ለሚያጠቡ ወዮላቸው!
ይህ በክረምት እንዳይሆን ዘወትር ጸልዩ፤
ምክንያቱም በእነዚያ ቀናት ከአምላክ የፍጥረት ሥራ መጀመሪያ አንስቶ እስከዚያ ጊዜ ድረስ ሆኖ የማያውቅ ዳግመኛም የማይሆን መከራ ይከሰታል።
እንዲያውም ይሖዋ ቀኖቹን ባያሳጥራቸው ኖሮ ሥጋ ሁሉ ባልዳነ ነበር። ሆኖም እሱ ለመረጣቸው ምርጦች ሲል ቀኖቹን አሳጥሯል።
“በዚያን ጊዜም ማንም ‘እነሆ፣ ክርስቶስ ይኸውላችሁ’ ወይም ‘እነሆ፣ ያውላችሁ’ ቢላችሁ አትመኑ።
ምክንያቱም ሐሰተኛ ክርስቶሶችና ሐሰተኛ ነቢያት ይነሳሉ፤ ቢቻላቸው የተመረጡትን እንኳ እስኪያስቱ ድረስ ምልክቶችና አስደናቂ ነገሮች ያደርጋሉ።
ስለዚህ ተጠንቀቁ። ሁሉን ነገር አስቀድሜ ነግሬአችኋለሁ።
“ሆኖም በእነዚያ ቀናት፣ ከዚያ መከራ በኋላ ፀሐይ ትጨልማለች፤ ጨረቃም ብርሃኗን አትሰጥም፤
ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፤ በሰማያት ያሉ ኃይላትም ይናወጣሉ።
ከዚያም የሰው ልጅ በታላቅ ኃይልና ክብር በደመና ሲመጣ ያዩታል።
እሱም መላእክቱን ልኮ ከአራቱ ነፋሳት፣ ከምድር ዳርቻ እስከ ሰማይ ዳርቻ ለእሱ የተመረጡትን ይሰበስባል።
“እንግዲያው ይህን ምሳሌ ከበለስ ዛፍ ተማሩ፦ ቅርንጫፎቿ ሲለመልሙና ቅጠሎቿ ሲያቆጠቁጡ በጋ እንደቀረበ ታውቃላችሁ።
በተመሳሳይ እናንተም እነዚህ ነገሮች ሲፈጸሙ ስታዩ የሰው ልጅ ደጃፍ ላይ እንደደረሰ እርግጠኞች ሁኑ።
እውነት እላችኋለሁ፣ እነዚህ ነገሮች ሁሉ እስኪፈጸሙ ድረስ ይህ ትውልድ ፈጽሞ አያልፍም።
ሰማይና ምድር ያልፋሉ፤ ቃሌ ግን ፈጽሞ አያልፍም።
“ስለዚያ ቀን ወይም ሰዓት ከአብ በቀር በሰማይ ያሉ መላእክትም ሆኑ ወልድ፣ ማንም አያውቅም።
ስለዚህ የተወሰነው ጊዜ መቼ እንደሆነ ስለማታውቁ ምንጊዜም በንቃት ተከታተሉ፤ ዘወትር ነቅታችሁ ጠብቁ።
ይህም ለባሪያዎቹ ሥልጣን ከሰጠና ለእያንዳንዱ የሥራ ድርሻውን ከመደበ በኋላ በር ጠባቂውን ነቅቶ እንዲጠብቅ በማዘዝ ቤቱን ትቶ ወደ ሌላ አገር እንደሄደ ሰው ነው።
ስለዚህ የቤቱ ጌታ፣ በምሽት ይሁን በእኩለ ሌሊት ወይም ዶሮ ሲጮኽ ይሁን ከመንጋቱ በፊት፣ መቼ እንደሚመጣ ስለማታውቁ ምንጊዜም ነቅታችሁ ጠብቁ፤
አለዚያ ድንገት ሲመጣ ተኝታችሁ ያገኛችኋል።
ይሁንና ለእናንተ የምነግራችሁን ለሁሉም እናገራለሁ፤ ምንጊዜም ነቅታችሁ ጠብቁ።”
ዳግመኛ ወደ ምኩራብ ገባ፤ በዚያም እጁ የሰለለ አንድ ሰው ነበር።
ኢየሱስን ሊከሱት ይፈልጉ ስለነበር ሰውየውን በሰንበት ይፈውሰው እንደሆነ ለማየት በትኩረት ይከታተሉት ነበር።
እሱም እጁ የሰለለበትን ሰው “ተነሳና ወደ መሃል ና” አለው።
ከዚያም “በሰንበት ቀን የተፈቀደው መልካም ማድረግ ነው ወይስ ክፉ? ሕይወት ማዳን ነው ወይስ ማጥፋት?” አላቸው። እነሱ ግን ዝም አሉ።
በልባቸው ደንዳናነት በጣም አዝኖ በዙሪያው ያሉትን በብስጭት ከተመለከተ በኋላ ሰውየውን “እጅህን ዘርጋ” አለው። እሱም በዘረጋ ጊዜ እጁ ዳነለት።
ፈሪሳውያኑ ወጥተው ከሄዱ በኋላ ወዲያው ከሄሮድስ ሥርወ መንግሥት ደጋፊዎች ጋር በመሰብሰብ እንዴት እንደሚገድሉት መመካከር ጀመሩ።
ኢየሱስ ግን ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወደ ባሕሩ ሄደ፤ ከገሊላና ከይሁዳ የመጣ ብዙ ሕዝብም ተከተለው።
ያከናወናቸውን በርካታ ነገሮች የሰሙ ብዙ ሰዎች ከኢየሩሳሌም፣ ከኤዶምያስና ከዮርዳኖስ ማዶ እንዲሁም ከጢሮስና ከሲዶና አካባቢ እንኳ ሳይቀር ወደ እሱ መጡ።
ኢየሱስም ሕዝቡ እንዳያጨናንቀው አንዲት ትንሽ ጀልባ እንዲያዘጋጁለት ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው።
ብዙ ሰዎችን ፈውሶ ስለነበር ከባድ በሽታ የያዛቸው ሁሉ እሱን ለመንካት በዙሪያው ይጋፉ ነበር።
ርኩሳን መናፍስት እንኳ ሳይቀሩ ባዩት ቁጥር በፊቱ ወድቀው “አንተ የአምላክ ልጅ ነህ” በማለት ይጮኹ ነበር።
ሆኖም የእሱን ማንነት ለሌሎች እንዳይገልጹ በተደጋጋሚ አጥብቆ አዘዛቸው።
ኢየሱስም ወደ ተራራ ወጥቶ የሚፈልጋቸውን ሰዎች ጠራ፤ እነሱም ወደ እሱ መጡ።
ከዚያም 12 ሰዎች መርጦ ሐዋርያት ብሎ ሰየማቸው፤ እነዚህ አብረውት የሚሆኑ ከመሆኑም ሌላ ከጊዜ በኋላ ለስብከት ሥራ የሚልካቸውና
አጋንንትን የማስወጣት ሥልጣን የሚሰጣቸው ናቸው።
የመረጣቸውም 12 ሐዋርያት እነዚህ ናቸው፦ ጴጥሮስ ብሎ የሰየመው ስምዖን፣
የዘብዴዎስ ልጅ ያዕቆብና የያዕቆብ ወንድም ዮሐንስ (እነዚህን ቦአኔርጌስ ብሎ የሰየማቸው ሲሆን ትርጉሙም “የነጎድጓድ ልጆች” ማለት ነው)፣
እንድርያስ፣ ፊልጶስ፣ በርቶሎሜዎስ፣ ማቴዎስ፣ ቶማስ፣ የእልፍዮስ ልጅ ያዕቆብ፣ ታዴዎስ፣ ቀነናዊው ስምዖን
እንዲሁም በኋላ ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው የአስቆሮቱ ይሁዳ። ከዚያ በኋላ ወደ አንድ ቤት ሄደ፤
ዳግመኛም ብዙ ሕዝብ ተሰበሰበ፤ ከዚህም የተነሳ እህል እንኳ መቅመስ አልቻሉም።
ዘመዶቹ ግን ይህን በሰሙ ጊዜ “አእምሮውን ስቷል” በማለት ሊይዙት መጡ።
ከኢየሩሳሌም የመጡ ጸሐፍትም “ብዔልዜቡል አለበት፤ አጋንንትን የሚያስወጣው በአጋንንት አለቃ ነው” ይሉ ነበር።
በመሆኑም ወደ እሱ ከጠራቸው በኋላ በምሳሌ እንዲህ አላቸው፦ “ሰይጣን እንዴት ሰይጣንን ሊያስወጣ ይችላል?
አንድ መንግሥት እርስ በርሱ ከተከፋፈለ ያ መንግሥት ጸንቶ ሊቆም አይችልም፤
አንድ ቤትም እርስ በርሱ ከተለያየ ያ ቤት ጸንቶ ሊቆም አይችልም።
በተመሳሳይም ሰይጣን በራሱ ላይ የሚነሳና የሚከፋፈል ከሆነ ያከትምለታል እንጂ ሊጸና አይችልም።
ደግሞም ወደ አንድ ብርቱ ሰው ቤት የገባ ሰው በቅድሚያ ብርቱውን ሰው ሳያስር ንብረቱን ሊሰርቅ አይችልም። ቤቱን መዝረፍ የሚችለው እንዲህ ካደረገ ብቻ ነው።
እውነት እላችኋለሁ፣ የሰው ልጆች ምንም ዓይነት ኃጢአት ቢሠሩ ወይም ምንም ዓይነት የስድብ ቃል ቢናገሩ ሁሉም ይቅር ይባልላቸዋል።
ይሁን እንጂ መንፈስ ቅዱስን የሚሳደብ ሁሉ ለዘላለም ይቅር አይባልም፤ ከዚህ ይልቅ ለዘላለም የሚጠየቅበት ኃጢአት ይሆንበታል።”
ይህን ያለው “ርኩስ መንፈስ አለበት” ይሉ ስለነበር ነው።
በዚህ ጊዜ እናቱና ወንድሞቹ መጡ፤ ውጭ ቆመውም ሰው ልከው አስጠሩት።
በዙሪያውም ብዙ ሰዎች ተቀምጠው ስለነበር “እነሆ፣ እናትህና ወንድሞችህ ውጭ ሆነው እየጠሩህ ነው” አሉት።
እሱ ግን መልሶ “እናቴና ወንድሞቼ እነማን ናቸው?” አላቸው።
ከዚያም ዙሪያውን ከበው ወደተቀመጡት ሰዎች ተመልክቶ እንዲህ አለ፦ “እናቴና ወንድሞቼ እነዚህ ናቸው!
የአምላክን ፈቃድ የሚያደርግ ሁሉ ለእኔ ወንድሜ፣ እህቴና እናቴ ነው።”
ቀጥሎም “እውነት እላችኋለሁ፣ እዚህ ከቆሙት መካከል አንዳንዶች የአምላክ መንግሥት በታላቅ ኃይል መምጣቱን እስኪያዩ ድረስ ፈጽሞ ሞትን አይቀምሱም” አላቸው።
ኢየሱስ ከስድስት ቀን በኋላ ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ብቻ ይዞ ወደ አንድ ረጅም ተራራ ወጣ። በፊታቸውም ተለወጠ፤
ልብሱ በምድር ላይ ያለ ማንኛውም ልብስ አጣቢ አጥቦ ሊያነጣው ከሚችለው በላይ እጅግ ነጭ ሆኖ ያንጸባርቅ ጀመር።
ደግሞም ኤልያስና ሙሴ ታዩአቸው፤ ከኢየሱስም ጋር እየተነጋገሩ ነበር።
በዚህ ጊዜ ጴጥሮስ ኢየሱስን “ረቢ፣ እዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው። ስለዚህ አንድ ለአንተ፣ አንድ ለሙሴና አንድ ለኤልያስ ሦስት ድንኳኖች እንትከል” አለው።
እርግጥ፣ በጣም ስለፈሩ ምን ማለት እንዳለበት አላወቀም ነበር።
ከዚያም ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፤ ከደመናውም “የምወደው ልጄ ይህ ነው። እሱን ስሙት” የሚል ድምፅ መጣ።
ከዚያም ድንገት ዙሪያቸውን ሲመለከቱ ከኢየሱስ በቀር ማንም አብሯቸው አልነበረም።
ከተራራው እየወረዱ ሳሉ የሰው ልጅ ከሞት እስኪነሳ ድረስ ያዩትን ለማንም እንዳይናገሩ በጥብቅ አዘዛቸው።
እነሱም ቃሉን በልባቸው አኖሩ፤ ነገር ግን ከሞት መነሳት ሲል ምን ማለቱ እንደሆነ እርስ በርሳቸው ተነጋገሩ።
ከዚያም “ጸሐፍት፣ ኤልያስ በመጀመሪያ መምጣት አለበት የሚሉት ለምንድን ነው?” ሲሉ ጠየቁት።
እሱም እንዲህ አላቸው፦ “በእርግጥ ኤልያስ መጀመሪያ መጥቶ ሁሉንም ነገር ወደ ቀድሞ ሁኔታው ይመልሳል፤ ይሁንና የሰው ልጅ ብዙ መከራ መቀበልና መናቅ እንዳለበት የተጻፈው ለምን ይመስላችኋል?
ነገር ግን እላችኋለሁ፣ ኤልያስ ስለ እሱ በተጻፈው መሠረት በእርግጥ መጥቷል፤ እነሱም የፈለጉትን ሁሉ አድርገውበታል።”
ወደቀሩት ደቀ መዛሙርት በመጡም ጊዜ ብዙ ሕዝብ ከቧቸው አዩ፤ ጸሐፍትም ከእነሱ ጋር እየተከራከሩ ነበር።
ሆኖም የተሰበሰቡት ሰዎች ሁሉ ኢየሱስን እንዳዩት በጣም ተገረሙ፤ ከዚያም ሰላም ሊሉት ወደ እሱ ሮጡ።