text
stringlengths
4
267
ኚዚያም ዹይሖዋ መንፈስ ለሳምሶን ኃይል ሰጠውፀ እሱም ወደ አስቀሎን ወርዶ ኚሰዎቻ቞ው መካኚል 30ውን ገደለፀ ልብሳ቞ውንም ገፎ እንቆቅልሹን ለፈቱት ሰዎቜ ሰጣ቞ው። ቁጣው እንደነደደም ወደ አባቱ ቀት ወጣ።
ዚሳምሶንም ሚስት አብሚውት ኚነበሩት ሚዜዎቜ ለአንዱ ተዳሚቜ።
ኹተወሰነ ጊዜ በኋላ በስንዎ መኹር ወቅት ሳምሶን አንድ ዹፍዹል ጠቊት ይዞ ሚስቱን ሊጠይቅ ሄደ። እሱም “ሚስ቎ ወዳለቜበት መኝታ ቀት መግባት እፈልጋለሁ” አለ። አባቷ ግን እንዲገባ አልፈቀደለትም።
ኚዚያም አባትዚው እንዲህ አለው፩ “እኔ እኮ ‘ፈጜሞ ጠልተሃታል’ ብዬ አስቀ ነበር። ስለሆነም ለሚዜህ ዳርኳት። ታናሜ እህቷ ኚእሷ ይልቅ ቆንጆ አይደለቜም? እባክህ በዚያቜኛዋ ፋንታ ይህቜኛዋን አግባት።”
ሳምሶን ግን “ኚእንግዲህ ፍልስጀማውያን ለማደርስባ቞ው ጉዳት ተጠያቂ ሊያደርጉኝ አይቜሉም” አላ቞ው።
ሳምሶንም ሄዶ 300 ቀበሮዎቜን ያዘ። ኚዚያም ቜቊዎቜ አመጣፀ ቀበሮዎቹንም ፊታ቞ውን አዙሮ ጭራና ጭራ቞ውን አንድ ላይ ካሰሚ በኋላ በጭራ቞ው መሃል አንድ አንድ ቜቊ አደሚገ።
በመቀጠልም ቜቊዎቹን በእሳት በመለኮስ ቀበሮዎቹን በፍልስጀማውያን እርሻ ላይ ባለው ያልታጚደ እህል ውስጥ ለቀቃ቞ው። ኚነዶው አንስቶ እስካልታጚደው እህል ድሚስ እንዲሁም ዹወይን እርሻዎቜንና ዚወይራ ዛፎቜን አቃጠለ።
ፍልስጀማውያኑም “ይህን ያደሚገው ማን ነው?” ብለው ጠዚቁ። እነሱም “ዚቲምናዊው አማቜ ሳምሶን ነውፀ ይህን ያደሚገውም ሚስቱን ወስዶ ለሚዜው ስለሰጠበት ነው” ተብሎ ተነገራ቞ው። በዚህ ጊዜ ፍልስጀማውያን ሄደው እሷንና አባቷን በእሳት አቃጠሉ።
ሳምሶንም “እንግዲህ እናንተ ይህን ካደሚጋቜሁ እኔ ደግሞ እናንተን ሳልበቀል አርፌ አልቀመጥም” አላ቞ው።
ኚዚያም አንድ በአንድ እዚመታ ሚፈሚፋ቞ውፀ ኹዚህ በኋላ ወርዶ በኀጣም በሚገኝ አንድ ዚዓለት ዋሻ ውስጥ ተቀመጠ።
በኋላም ፍልስጀማውያን ወጥተው በይሁዳ ሰፈሩፀ ዹሊሃይንም አካባቢ ያስሱ ጀመር።
ዚይሁዳም ሰዎቜ “እኛን ልትወጉ ዚመጣቜሁት ለምንድን ነው?” አሏ቞ውፀ እነሱም መልሰው “እኛ ዚመጣነው ሳምሶንን ለመያዝና እሱ እንዳደሚገብን ሁሉ እኛም እንድናደርግበት ነው” አሉ።
በመሆኑም 3,000 ዚይሁዳ ሰዎቜ በኀጣም ወደሚገኘው ዚዓለት ዋሻ ወርደው ሳምሶንን “ፍልስጀማውያን ገዢዎቻቜን መሆናቾውን አታውቅም? ታዲያ እንዲህ ያለ ነገር ዚፈጞምክብን ለምንድን ነው?” አሉት። እሱም “እነሱ እንዳደሚጉብኝ እኔም አደሚግኩባ቞ው” አላ቞ው።
እነሱ ግን “አሁን ዚመጣነው ይዘን ለፍልስጀማውያን ልናስሚክብህ ነው” አሉት። ኚዚያም ሳምሶን “እናንተ ራሳቜሁ ምንም ጥቃት እንደማታደርሱብኝ ማሉልኝ” አላ቞ው።
እነሱም “አስሚን ብቻ ለእነሱ እናስሚክብሃለን እንጂ አንገድልህም” አሉት። በመሆኑም በሁለት አዳዲስ ገመዶቜ አስሚው ኚዓለቱ ውስጥ አወጡት።
እሱም ሊሃይ ሲደርስ ፍልስጀማውያኑ እሱን በማግኘታ቞ው በድል አድራጊነት ጮኹ። በዚህ ጊዜ ዹይሖዋ መንፈስ ኃይል ሰጠውፀ እጆቹ ዚታሰሩባ቞ውም ገመዶቜ እሳት እንደበላው ዚበፍታ ክር ሆኑፀ ማሰሪያዎቹም ኚእጆቹ ላይ ቀልጠው ወደቁ።
እሱም በቅርቡ ዹሞተ ዚአንድ አህያ መንጋጋ አገኘፀ መንጋጋውንም አንስቶ በእሱ 1,000 ሰው ገደለ።
ኚዚያም ሳምሶን እንዲህ አለ፩ “በአህያ መንጋጋ በክምር ላይ ክምር አነባባሪፀ በአህያ መንጋጋ 1,000 ሰው ዘራሪ!”
እሱም ይህን ተናግሮ ሲጚርስ ዚአህያውን መንጋጋ ወሚወሚውፀ ያንንም ቊታ ራማትሊሃይ ብሎ ጠራው።
ኚዚያም በጣም ተጠማፀ ወደ ይሖዋም እንዲህ ሲል ጮኞፊ “ይህ ታላቅ መዳን በአገልጋይህ እጅ እንዲፈጞም ያደሚግኚው አንተ ነበርክ። ታዲያ አሁን በውኃ ጥም ልሙት? በእነዚህ ባልተገሚዙ ሰዎቜ እጅስ ልውደቅ?”
በመሆኑም አምላክ በሊሃይ ዹሚገኝ አንድ ዓለት ነደለፀ ውኃም ኚዓለቱ መውጣት ጀመሚ። እሱም በጠጣ ጊዜ መንፈሱ ተመለሰፀ ብርታትም አገኘ። እስኚ ዛሬ ድሚስ በሊሃይ ዹሚገኘውን ያንን ቊታ ኀንሃቆሬ ሲል ዚጠራው ለዚህ ነው።
እሱም በፍልስጀማውያን ዘመን ለ20 ዓመት በእስራኀል ውስጥ ፈራጅ ሆኖ አገለገለ።
ሆኖም ኀሁድ ኹሞተ በኋላ እስራኀላውያን እንደገና በይሖዋ ፊት መጥፎ ነገር አደሚጉ።
በመሆኑም ይሖዋ በሃጟር ሆኖ ይገዛ ለነበሹው ለኹነአን ንጉሥ ለያቢን አሳልፎ ሞጣ቞ው። ዚሠራዊቱም አለቃ በሃሮሌትጎይም ዹሚኖሹው ሲሳራ ነበር።
ያቢን ዚብሚት ማጭድ ዹተገጠመላቾው 900 ዹጩር ሠሚገሎቜ ስለነበሩትና ለ20 ዓመት ክፉኛ ስለጚቆና቞ው እስራኀላውያን ወደ ይሖዋ ጮኹ።
በዚያን ጊዜ ዚላጲዶት ሚስት ነቢዪቱ ዲቊራ በእስራኀል ውስጥ ፈራጅ ሆና ታገለግል ነበር።
እሷም በኀፍሬም ተራራማ አካባቢ፣ በራማና በቀ቎ል መካኚል ባለው ዚዲቊራ ዘንባባ ዛፍ ሥር ትቀመጥ ነበርፀ እስራኀላውያንም ለፍርድ ወደ እሷ ይወጡ ነበር።
እሷም ዚአቢኖዓምን ልጅ ባርቅን ኚቃዎሜንፍታሌም አስጠርታ እንዲህ አለቜውፊ “ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ዹሚል ትእዛዝ ሰጥቶ ዹለም? ‘ሂድና ወደ ታቊር ተራራ ዝመትፀ ኹአንተም ጋር ኚንፍታሌምና ኚዛብሎን 10,000 ወንዶቜን ውሰድ።
እኔም ዚያቢን ሠራዊት አለቃ ዹሆነውን ሲሳራን ኹጩር ሠሚገሎቹና ኚሠራዊቱ ጋር ወደ ቂሟን ጅሚት ወደ አንተ አመጣዋለሁፀ እሱንም በእጅህ አሳልፌ እሰጥሃለሁ።’”
በዚህ ጊዜ ባርቅ “አብሚሜኝ ዚምትሄጂ ኹሆነ እሄዳለሁፀ አብሚሜኝ ዚማትሄጂ ኹሆነ ግን አልሄድም” አላት።
እሷም እንዲህ አለቜውፊ “በእርግጥ አብሬህ እሄዳለሁ። ይሁንና ይሖዋ ሲሳራን በሎት እጅ አሳልፎ ስለሚሰጠው ዚምታካሂደው ዘመቻ ለአንተ ክብር አያስገኝልህም።” ኚዚያም ዲቊራ ተነስታ ኚባርቅ ጋር ወደ ቃዎሜ ሄደቜ።
ባርቅም ዛብሎንንና ንፍታሌምን ወደ ቃዎሜ ጠራ቞ውፀ 10,000 ሰዎቜም ዚእሱን ዱካ ተኚተሉ። ዲቊራም አብራው ወጣቜ።
እንደ አጋጣሚ ሆኖ ቄናዊው ሄቀር፣ ዹሙሮ አማት ዚሆባብ ዘሮቜ ኚሆኑት ኚቄናውያን ተለይቶ በቃዎሜ በሚገኘው በጻናኒም ትልቅ ዛፍ አጠገብ ድንኳኑን ተክሎ ነበር።
ኚዚያም ዚአቢኖዓም ልጅ ባርቅ ወደ ታቊር ተራራ እንደወጣ ለሲሳራ ነገሩት።
ሲሳራም ወደ ቂሟን ጅሚት ለመሄድ ወዲያውኑ ዹጩር ሠሚገሎቹን በሙሉ ይኾውም ዚብሚት ማጭድ ዹተገጠመላቾውን 900 ዹጩር ሠሚገሎቜ እንዲሁም ኚእሱ ጋር ዹነበሹውን ሠራዊት ሁሉ ኚሃሮሌትጎይም አሰባሰበ።
በዚህ ጊዜ ዲቊራ ባርቅን እንዲህ አለቜውፊ “ይሖዋ ሲሳራን በእጅህ አሳልፎ ዚሚሰጥበት ቀን ይህ ስለሆነ ተነስ! ይሖዋ በፊትህ ቀድሞ ይወጣ ዹለም?” ባርቅም 10,000 ሰዎቜን አስኚትሎ ኚታቊር ተራራ ወሚደ።
ይሖዋም ሲሳራንና ዹጩር ሠሚገሎቹን በሙሉ እንዲሁም ሠራዊቱን ሁሉ ግራ እንዲጋቡ አደሚጋ቞ውፀ በባርቅም ሰይፍ አጠፋ቞ው። በመጚሚሻም ሲሳራ ኹሠሹገላው ላይ ወርዶ በእግሩ መሞሜ ጀመሚ።
ባርቅም ዹጩር ሠሚገሎቹንና ሠራዊቱን እስኚ ሃሮሌትጎይም ድሚስ አሳደዳ቞ው። በመሆኑም ዚሲሳራ ሠራዊት በሙሉ በሰይፍ ወደቀፀ አንድም ዹተሹፈ ሰው አልነበሚም።
ሆኖም ሲሳራ ዹቄናዊው ዚሄቀር ሚስት ወደሆነቜው ወደ ኢያዔል ድንኳን በእግሩ ሞሞፀ ምክንያቱም በሃጟር ንጉሥ በያቢንና በቄናዊው በሄቀር ቀት መካኚል ሰላማዊ ግንኙነት ነበር።
ኢያዔልም ሲሳራን ልትቀበለው ወጣቜፀ ኚዚያም “ጌታዬ ናፀ ወደዚህ ግባ። አትፍራ” አለቜው። በመሆኑም ወደ እሷ ድንኳን ገባ። እሷም ብርድ ልብስ አለበሰቜው።
ኚዚያም “እባክሜ ስለጠማኝ ዚምጠጣው ትንሜ ውኃ ስጪኝ” አላት። እሷም ዚወተት አቁማዳውን ፈትታ ዚሚጠጣውን ሰጠቜውፀ ኚዚያም በድጋሚ ሞፈነቜው።
እሱም “ድንኳኑ በር ላይ ቁሚፀ ማንም ሰው መጥቶ ‘እዚህ ሰው አለ?’ ብሎ ቢጠይቅሜ ‘ዹለም!’ በይ” አላት።
ዚሄቀር ሚስት ኢያዔል ግን ዚድንኳን ካስማና መዶሻ ወሰደቜ። ኚዚያም ሲሳራ ደክሞት ድብን ያለ እንቅልፍ ወስዶት ሳለ በቀስታ ወደ እሱ ሄዳ ካስማውን ሰሪሳራዎቹ ላይ በመቾንኹር ኚመሬት ጋር አጣበቀቜው። እሱም ሞተ።
ባርቅ ሲሳራን እያሳደደ ወደዚያ አካባቢ ሄደፀ ኢያዔልም እሱን ለማግኘት ወጣቜፀ ኚዚያም “ና፣ ዚምትፈልገውን ሰው አሳይሃለሁ” አለቜው። እሱም ኚእሷ ጋር ወደ ውስጥ ገባፀ ሲሳራንም ካስማው ሰሪሳራዎቹ ላይ እንደተ቞ነኚሚ ሞቶ አገኘው።
በመሆኑም አምላክ በዚያን ዕለት ዹኹነአን ንጉሥ ያቢን ለእስራኀላውያን እንዲንበሚኚክ አደሚገ።
እስራኀላውያን ዹኹነአንን ንጉሥ ያቢንን እስኪያጠፉት ድሚስ እጃ቞ው በኹነአን ንጉሥ በያቢን ላይ ይበልጥ እዚበሚታ ሄደ።
በመሆኑም ኚዳን አንስቶ እስኚ ቀርሳቀህ ድሚስ እንዲሁም በጊልያድ ምድር ያሉ እስራኀላውያን በሙሉ አንድ ላይ በመውጣት በምጜጳ በይሖዋ ፊት ተሰበሰቡ።
ዚሕዝቡና ዚእስራኀል ነገዶቜ አለቆቜ ሁሉ በእውነተኛው አምላክ ሕዝብ ጉባኀ መካኚል ቊታ ቊታ቞ውን ይዘው ቆሙፀ ሰይፍ ዚታጠቁት እግሚኛ ወታደሮቜ 400,000 ነበሩ።
ቢንያማውያንም ዚእስራኀል ሰዎቜ ወደ ምጜጳ መውጣታ቞ውን ሰሙ። ኚዚያም ዚእስራኀል ሰዎቜ “ይህ ክፉ ነገር እንዎት ሊፈጾም እንደቻለ እስቲ ንገሩን?” አሏ቞ው።
በዚህ ጊዜ ዚተገደለቜው ሎት ባል ዹሆነው ሌዋዊ እንዲህ ሲል መለሰ፩ “እኔና ቁባ቎ ዚቢንያም በሆነቜው በጊብዓ ለማደር ወደዚያ መጥተን ነበር።
ዚጊብዓ ነዋሪዎቜም በእኔ ላይ ተነሱብኝፀ በሌሊት መጥተውም ቀቱን ኚበቡ። ለመግደል ያሰቡት እኔን ነበርፀ ሆኖም ቁባ቎ን ደፈሯትፀ እሷም ሞተቜ።
እኔም ዚቁባ቎ን አስኚሬን ወስጄ ቆራሚጥኩትፀ ኚዚያም ወደ እያንዳንዱ ዚእስራኀል ርስት ላክሁትፀ ምክንያቱም እነሱ በእስራኀል ውስጥ አሳፋሪና አስነዋሪ ድርጊት ፈጜመዋል።
እንግዲህ እናንተ እስራኀላውያን ሁሉ ይህን ጉዳይ በተመለኹተ ያላቜሁን ሐሳብና አስተያዚት ስጡ።”
ኚዚያም ሕዝቡ ሁሉ አንድ ላይ ሆኖ በመነሳት እንዲህ አለ፩ “ኚመካኚላቜን ማንም ሰው ወደ ድንኳኑ አይሄድም ወይም ወደ ቀቱ አይመለስም።
እንግዲህ በጊብዓ ላይ ዹምናደርገው ይህ ነው፩ ዕጣ እናወጣና እንዘምትባታለን።
ዚቢንያም ግዛት ዚሆነቜው ዚጊብዓ ነዋሪዎቜ በእስራኀል ውስጥ በፈጞሙት አሳፋሪ ድርጊት ዚተነሳ በእሷ ላይ ዘምቶ ተገቢውን እርምጃ ለሚወስደው ሠራዊት ስንቅ እንዲያዘጋጁ ኚእስራኀል ነገዶቜ ሁሉ መካኚል ኹ100ው 10፣ ኹ1,000ው 100፣ ኹ10,000ው ደግሞ 1,000 ሰዎቜን እንወስዳለን።”
በዚህ መንገድ ዚእስራኀል ሰዎቜ በሙሉ ግንባር በመፍጠር በኹተማዋ ላይ በአንድነት ወጡ።
ኚዚያም ዚእስራኀል ነገዶቜ ወደ ቢንያም ነገድ መሪዎቜ ሁሉ እንዲህ በማለት መልእክተኞቜን ላኩፊ “በመካኚላቜሁ ዹተፈጾመው ይህ ዘግናኝ ድርጊት ምንድን ነው?
በሉ አሁን በጊብዓ ያሉትን እነዚያን ጋጠወጥ ሰዎቜ እንድንገድላ቞ውና ክፉ ዹሆነውን ኚእስራኀል መካኚል እንድናስወግድ ሰዎቹን አሳልፋቜሁ ስጡን።” ቢንያማውያን ግን ወንድሞቻ቞ውን እስራኀላውያንን ለመስማት ፈቃደኞቜ አልሆኑም።
ኚዚያም ቢንያማውያን ኚእስራኀል ሰዎቜ ጋር ለመዋጋት ኚዚኚተሞቹ ወጥተው በጊብዓ ተሰባሰቡ።
ኚተመሚጡት 700 ዚጊብዓ ሰዎቜ በተጚማሪ በዚያ ቀን ሰይፍ ዚታጠቁ 26,000 ቢንያማውያን ኚዚኚተሞቻ቞ው ተሰባሰቡ።
በሠራዊቱም መካኚል ዚተመሚጡ 700 ግራኞቜ ነበሩ። እያንዳንዳ቞ውም ድንጋይ ወንጭፈው ፀጉር እንኳ ዚማይስቱ ነበሩ።
ዚእስራኀል ሰዎቜ ደግሞ ቢንያምን ሳይጚምር ሰይፍ ዚታጠቁ 400,000 ሰዎቜ አሰባሰቡፀ እያንዳንዳ቞ውም ልምድ ያላ቞ው ተዋጊዎቜ ነበሩ።
እነሱም አምላክን ለመጠዹቅ ተነስተው ወደ ቀ቎ል ወጡ። ኚዚያም ዚእስራኀል ሰዎቜ “ኚቢንያማውያን ጋር ለሚደሹገው ውጊያ ኚመካኚላቜን ማን ቀድሞ ይውጣ?” ሲሉ ጠዚቁ። ይሖዋም “ይሁዳ ቀድሞ ይውጣ” ሲል መለሰ።
ኚዚያም እስራኀላውያን በማለዳ ተነስተው ጊብዓን ኚበቡ።
ዚእስራኀል ሰዎቜም ቢንያምን ለመውጋት ወጡፀ ዚእስራኀል ሰዎቜ እነሱን ጊብዓ ላይ ለመውጋት ዚጊርነት አሰላለፍ ይዘው ቆሙ።
ቢንያማውያንም ኚጊብዓ በመውጣት በዚያን ቀን ኚእስራኀላውያን መካኚል 22,000 ሰዎቜን ገደሉ።
ሆኖም ዚእስራኀላውያን ሠራዊት ልክ እንደ መጀመሪያው ቀን ዚጊርነት አሰላለፍ ይዞ አሁንም እዚያው ቊታ ላይ በድፍሚት ቆመ።
ኚዚያም እስራኀላውያን ወጥተው እስኪመሜ ድሚስ በይሖዋ ፊት አለቀሱፀ ይሖዋንም “ኚወንድሞቻቜን ኚቢንያም ሰዎቜ ጋር ለመዋጋት እንደገና እንውጣ?” በማለት ጠዚቁ። ይሖዋም “አዎ፣ በእነሱ ላይ ውጡ” አላ቞ው።
በመሆኑም እስራኀላውያን በሁለተኛው ቀን ወደ ቢንያማውያን ተጠጉ።
ቢንያማውያንም በሁለተኛው ቀን እነሱን ለመግጠም ኚጊብዓ ወጡፀ ኚእስራኀላውያንም መካኚል ሰይፍ ዚታጠቁ ተጚማሪ 18,000 ሰዎቜን ገደሉ።
በዚህ ጊዜ ዚእስራኀል ሰዎቜ በሙሉ ወደ ቀ቎ል ወጡ። በዚያም እያለቀሱ በይሖዋ ፊት ተቀመጡፀ እንዲሁም በዚያ ቀን እስኪመሜ ድሚስ ጟሙፀ በይሖዋም ፊት ዹሚቃጠሉ መባዎቜንና ዚኅብሚት መባዎቜን አቀሚቡ።
ኚዚያም ዚእስራኀል ሰዎቜ ይሖዋን ጠዚቁፀ ምክንያቱም በዚያ ዘመን ዚእውነተኛው አምላክ ዹቃል ኪዳን ታቊት ዹሚገኘው እዚያ ነበር።
ዚአሮን ልጅ፣ ዹአልዓዛር ልጅ ፊንሃስም በዚያ ዘመን በታቊቱ ፊት ያገለግል ነበር። እነሱም “ወንድሞቻቜንን ዚቢንያምን ሰዎቜ ለመውጋት እንደገና እንውጣ ወይስ እንቅር?” ሲሉ ጠዚቁ። ይሖዋም “በነገው ዕለት እነሱን በእጃቜሁ አሳልፌ ስለምሰጣቜሁ ውጡ” በማለት መለሰላ቞ው።
ኚዚያም እስራኀላውያን በጊብዓ ዙሪያ አድፍጠው ዚሚጠባበቁ ሰዎቜ አስቀመጡ።
በሊስተኛውም ቀን እስራኀላውያን ቢንያማውያንን ለመውጋት ወጡፀ እንደ ሌሎቹ ጊዜያት ሁሉ ጊብዓን ለመውጋት ዚጊርነት አሰላለፍ ይዘው ቆሙ።
ቢንያማውያንም ሠራዊቱን ለመግጠም በወጡ ጊዜ ኹኹተማዋ ራቁ። ኚዚያም እንደ ሌሎቹ ጊዜያት ሁሉ በአውራ ጎዳናዎቹ ማለትም ወደ ቀ቎ልና ወደ ጊብዓ በሚወስዱት አውራ ጎዳናዎቜ ላይ በነበሩት ሰዎቜ ላይ ጥቃት በመሰንዘር ዹተወሰኑ ሰዎቜን ገደሉፀ ወደ 30 ገደማ ዹሚሆኑ ዚእስራኀል ሰዎቜን በሜዳው ላይ ገደሉ።
በመሆኑም ቢንያማውያን “እንደ በፊቱ ሁሉ አሁንም ድል እያደሚግና቞ው ነው” አሉ። እስራኀላውያን ግን “እዚሞሞን ኹኹተማው ርቀው ወደ አውራ ጎዳናዎቹ እንዲመጡ እናድርጋ቞ው” አሉ።
ስለሆነም ዚእስራኀል ሰዎቜ ሁሉ ኚነበሩበት ተነስተው በመሄድ በዓልታማር ላይ ዚጊርነት አሰላለፍ ይዘው ቆሙፀ በዚህ ጊዜ አድፍጠው ዚነበሩት እስራኀላውያን ተደብቀውበት ኹነበሹው ኚጊብዓ አቅራቢያ ተንደርድሚው ወጡ።
በዚህ መንገድ ኹመላው እስራኀል ዚተውጣጡ 10,000 ዚተመሚጡ ወንዶቜ ወደ ጊብዓ ፊት ለፊት መጡፀ ኚባድ ውጊያም ተካሄደ። ሆኖም ቢንያማውያን ጥፋት እያንዣበበባ቞ው መሆኑን አላወቁም ነበር።
ይሖዋ ቢንያምን በእስራኀል ፊት ድል አደሚገውፀ በዚያም ቀን እስራኀላውያን ሰይፍ ዚታጠቁ 25,100 ቢንያማውያንን ገደሉ።
ይሁንና ቢንያማውያን ዚእስራኀል ሰዎቜ ኚእነሱ ሲያፈገፍጉ ድል እያደሚጓ቞ው ያሉ መስሏ቞ው ነበርፀ ሆኖም እስራኀላውያን ያፈገፈጉት በጊብዓ ላይ ባደፈጡት ሰዎቜ ተማምነው ነበር።
አድፍጠው ዚነበሩትም ሰዎቜ በፍጥነት እዚተንደሚደሩ ወደ ጊብዓ ሄዱ። ኚዚያም በዚቊታው ተሰራጭተው ኹተማዋን በሙሉ በሰይፍ መቱ።
ዚእስራኀልም ሰዎቜ አድፍጠው በኹተማዋ ላይ ጥቃት ዚሚሰነዝሩት ተዋጊዎቜ ኹኹተማዋ ጭስ እንዲወጣ በማድሚግ ምልክት እንዲያሳዩአ቞ው ተስማምተው ነበር።
እስራኀላውያንም ኚውጊያው ሲያፈገፍጉ ዚቢንያም ሰዎቜ ጥቃት በመሰንዘር ኚእስራኀላውያን መካኚል ወደ 30 ገደማ ዹሚሆኑ ሰዎቜን ገደሉፀ እነሱም “ልክ እንደ መጀመሪያው ውጊያ ሁሉ አሁንም ድል እያደሚግና቞ው መሆኑ ግልጜ ነው” ይሉ ነበር።
ሆኖም ምልክት ሆኖ ዚሚያገለግለው ጭስ እንደ ዓምድ በመሆን ኹኹተማዋ ይወጣ ጀመር። ዚቢንያምም ሰዎቜ ዞር ብለው ሲመለኚቱ ዹመላ ኹተማዋ ነበልባል ወደ ሰማይ ሲንቀለቀል አዩ።
ኚዚያም ዚእስራኀል ሰዎቜ ወደ ኋላ ተመለሱፀ ዚቢንያምም ሰዎቜ መጥፊያ቞ው እንደቀሚበ ስላወቁ ተደናገጡ።
በመሆኑም ኚእስራኀል ሰዎቜ በመሞሜ ወደ ምድሚ በዳው ሄዱፀ ሆኖም ኚኚተሞቹ ዚወጡትም ሰዎቜ በእነሱ ላይ ጥቃት መሰንዘር ስለጀመሩ ኚውጊያው ማምለጥ አልቻሉም።
እነሱም ቢንያማውያኑን ኚበቧ቞ውፀ ያለእሚፍትም አሳደዷ቞ው። ኚዚያም ጊብዓ ፊት ለፊት በስተ ምሥራቅ አቅጣጫ ባለው ስፍራ ደመሰሷ቞ው።
በመጚሚሻም 18,000 ዚቢንያም ሰዎቜ ሚገፉፀ ሁሉም ኃያል ተዋጊዎቜ ነበሩ።
ዚቢንያም ሰዎቜም ዞሹው በምድሚ በዳው ወደሚገኘው ዚሪሞን ዓለት ሞሹፀ እስራኀላውያንም 5,000 ሰዎቜን በአውራ ጎዳናዎቹ ላይ ገደሉባ቞ውፀ እስኚ ጊድኊምም ድሚስ አሳደዷ቞ውፀ በመሆኑም ተጚማሪ 2,000 ሰዎቜን ገደሉ።
በዚያ ቀን ዚተገደሉት ሰይፍ ዚታጠቁ ቢንያማውያን ቁጥር በአጠቃላይ 25,000 ደሚሰፀ ሁሉም ኃያል ተዋጊዎቜ ነበሩ።
ሆኖም 600 ሰዎቜ በምድሚ በዳው ወደሚገኘው ዚሪሞን ዓለት ሞሹፀ በሪሞን ዓለትም ለአራት ወር ተቀመጡ።
ዚእስራኀልም ሰዎቜ በቢንያማውያን ላይ ተመልሰው በመምጣት ኹሰው አንስቶ እስኚ እንስሳ ድሚስ በኹተማዋ ውስጥ ዹቀሹውን ሁሉ በሰይፍ መቱ። በተጚማሪም በመንገዳ቞ው ላይ ያገኟ቞ውን ኚተሞቜ በሙሉ በእሳት አቃጠሉ።
ኚዚያም ዚኀፍሬም ሰዎቜ አንድ ላይ ተሰባስበው ወደ ጻፎን በመሻገር ዮፍታሔን “አሞናውያንን ለመውጋት ስትሻገር አብሚንህ እንድንሄድ ያልጠራኞን ለምንድን ነው? ቀትህን በላይህ ላይ በእሳት እናቃጥለዋለን” አሉት።
ዮፍታሔ ግን እንዲህ አላቾው፩ “እኔና ሕዝቀ ኚአሞናውያን ጋር በኹፍተኛ ሁኔታ ተጋጭተን ነበር። እኔም እንድትሚዱኝ ጠርቻቜሁ ነበርፀ እናንተ ግን ኚእጃ቞ው አላዳናቜሁኝም።
እኔም እንደማታድኑኝ ስመለኚት ሕይወቮን አደጋ ላይ ጥዬ በአሞናውያን ላይ ለመዝመት ወሰንኩፀ ይሖዋም እነሱን በእጄ አሳልፎ ሰጣ቞ው። ታዲያ ዛሬ ልትወጉኝ ዚወጣቜሁት ለምንድን ነው?”
ኚዚያም ዮፍታሔ ዚጊልያድን ሰዎቜ ሁሉ አሰባስቊ ኚኀፍሬም ጋር ተዋጋፀ ዚጊልያድም ሰዎቜ ኀፍሬማውያንን ድል አደሚጓ቞ውፀ ኀፍሬማውያን ዚጊልያድን ሰዎቜ “በኀፍሬምና በምናሮ ዚምትኖሩ እናንተ ዚጊልያድ ሰዎቜ፣ እናንተ እኮ ኚኀፍሬም ሞሜታቜሁ ያመለጣቜሁ ስደተኞቜ ናቜሁ” ይሏቾው ነበር።
ጊልያዳውያንም ኚኀፍሬማውያን ፊት ለፊት ዹሚገኘውን ዚዮርዳኖስን መልካ ተቆጣጠሩፀ ዚኀፍሬምም ሰዎቜ ለማምለጥ በሚሞክሩበት ጊዜ “እንድሻገር ፍቀዱልኝ” ይላሉፀ በዚህ ጊዜ ዚጊልያድ ሰዎቜ እያንዳንዱን ሰው “አንተ ኀፍሬማዊ ነህ?” ብለው ይጠይቁታልፀ እሱም “አይ፣ አይደለሁም” ብሎ ሲመልስላ቞ው
“እስቲ ሺቊሌት በል” ይሉታል። እሱ ግን ቃሉን በትክክል መጥራት ስለማይቜል “ሲቊሌት” ይላል። እነሱም ይዘው እዚያው ዮርዳኖስ መልካ ላይ ይገድሉታል። በመሆኑም በዚያን ጊዜ 42,000 ኀፍሬማውያን አለቁ።