text
stringlengths
4
267
ዚንጉሡ አገልጋዮቜም ንጉሡን “እኛ አገልጋዮቜህ ጌታዬ ንጉሡ ዹወሰነውን ሁሉ ለማድሚግ ዝግጁ ነን” አሉት።
በመሆኑም ንጉሡ ቀተሰቡን ሁሉ አስኚትሎ ወጣፀ ሆኖም ቀቱን እንዲጠብቁ አሥር ቁባቶቹን እዚያው አስቀሚ።
ንጉሡም ሕዝቡን ሁሉ አስኚትሎ ተጓዘፀ እነሱም ቀትሜርሃቅ ሲደርሱ ቆሙ።
ኚዚያም አብሚውት ዚሄዱት አገልጋዮቹ በሙሉ፣ ኚሪታውያን በሙሉ፣ ጎሌታውያን በሙሉ እንዲሁም ኚጌት ተኚትለውት ዚመጡት 600 ጌታውያን ንጉሡ እያያ቞ው አለፉ።
ንጉሡም ጌታዊውን ኢታይን እንዲህ አለው፩ “ኚእኛ ጋር ዚምትሄደው ለምንድን ነው? በል ተመለስና ኚአዲሱ ንጉሥ ጋር ተቀመጥፀ አንተ ለራስህ ኹአገርህ ተሰደህ ዚመጣህ ዚባዕድ አገር ሰው ነህ።
ዚመጣኞው ገና ትናንት ነውፀ ታዲያ ዛሬ እኔ ወደምሄድበት ቊታ ሁሉ አብሚህ እንድትሄድ በማድሚግ ኚእኛ ጋር እንድትንኚራተት ላድርግ? በል አሁን ወንድሞቜህን ይዘህ ተመለስፀ ይሖዋም ታማኝ ፍቅርና ታማኝነት ያሳይህ!”
ኢታይ ግን ለንጉሡ “ሕያው በሆነው በይሖዋና ሕያው በሆነው በጌታዬ በንጉሡ እምላለሁ፣ በሕይወት ብኖርም ሆነ ብሞት ጌታዬ ንጉሡ በሚገኝበት በማንኛውም ቊታ ሁሉ እኔ አገልጋይህም በዚያ እሆናለሁ!” ሲል መለሰ።
በዚህ ጊዜ ዳዊት ኢታይን “እሺ፣ እለፍ” አለው። በመሆኑም ጌታዊው ኢታይ ኚሰዎቹና ኚልጆቹ ሁሉ ጋር አለፈ።
እነዚህ ሁሉ ሰዎቜ በሚያልፉበት ጊዜ በአካባቢው ያሉ ሰዎቜ በሙሉ ድምፃ቞ውን ኹፍ አድርገው ያለቅሱ ነበርፀ ንጉሡም በቄድሮን ሾለቆ አጠገብ ቆሞ ነበርፀ ሕዝቡም ሁሉ ወደ ምድሚ በዳው ወደሚወስደው መንገድ ተሻገሚ።
ሳዶቅም በዚያ ነበርፀ ዚእውነተኛውን አምላክ ዹቃል ኪዳን ታቊት ዚተሞኚሙት ሌዋውያንም በሙሉ ኚእሱ ጋር ነበሩፀ እነሱም ዚእውነተኛውን አምላክ ታቊት አስቀመጡትፀ ሕዝቡ ሁሉ ኹተማዋን ለቆ ኚተሻገሚም በኋላ አብያታር ወጣ።
ሆኖም ንጉሡ ሳዶቅን እንዲህ አለው፩ “ዚእውነተኛውን አምላክ ታቊት ወደ ኹተማዋ መልሱት። በይሖዋ ፊት ሞገስ ካገኘሁ እንድመለስና ታቊቱንም ሆነ ማደሪያ ስፍራውን እንዳይ ያደርገኝ ይሆናል።
ይሁንና እሱ ‘በአንተ አልተደሰትኩም’ ካለኝ መልካም መስሎ ዚታዚውን ያድርግብኝ።”
ንጉሡም ካህኑን ሳዶቅን እንዲህ አለው፩ “አንተ ባለ ራእይ አይደለህም? በል እንግዲህ ወደ ኹተማዋ በሰላም ተመለስፀ ሁለቱን ልጆቻቜሁን ማለትም ዹገዛ ልጅህን አኪማዓስንና ዚአብያታርን ልጅ ዮናታንን ይዘህ ተመለስ።
እኔም ኚእናንተ አንድ መልእክት እስኪመጣልኝ ድሚስ በምድሚ በዳው በሚገኙት መልካዎቜ አጠገብ እቆያለሁ።”
ስለዚህ ሳዶቅና አብያታር ዚእውነተኛውን አምላክ ታቊት ይዘው ወደ ኢዚሩሳሌም ተመለሱፀ እነሱም በዚያ ተቀመጡ።
ዳዊት ዚደብሚ ዘይትን ተራራ ሜቅብ ሲወጣ እያለቀሰ ነበርፀ እሱም ራሱን ተኹናንቩ ባዶ እግሩን ይሄድ ነበር። አብሚውት ዚነበሩት ሰዎቜም ሁሉ ራሳ቞ውን ተኚናንበው እያለቀሱ ሜቅብ ወጡ።
ኚዚያም ዳዊት “ኚአቢሎሎም ጋር ካሎሩት ሰዎቜ አንዱ እኮ አኪጊፌል ነው” ተብሎ ተነገሚው። በዚህ ጊዜ ዳዊት “ይሖዋ ሆይ፣ እባክህ ዚአኪጊፌልን ምክር ዹሞኝ ምክር አድርገው!” አለ።
ዳዊት ሕዝቡ ለአምላክ ይሰግድበት ወደነበሹው ዚተራራ ጫፍ ሲደርስ አርካዊው ኩሲ ልብሱን ቀዶና በራሱ ላይ አቧራ ነስንሶ እሱን ለማግኘት በዚያ ይጠባበቅ ነበር።
ዳዊት ግን እንዲህ አለው፩ “አብሚኞኝ ዚምትሻገር ኹሆነ ሾክም ትሆንብኛለህ።
ኹዚህ ይልቅ ወደ ኹተማዋ ተመልሰህ አቢሎሎምን ‘ንጉሥ ሆይ፣ እኔ ዹአንተ አገልጋይ ነኝ። ቀደም ሲል ዚአባትህ አገልጋይ ነበርኩፀ አሁን ግን ዹአንተ አገልጋይ ነኝ’ ብትለው ዚአኪጊፌልን ምክር ታኚሜፍልኛለህ።
ካህናት ዚሆኑት ሳዶቅና አብያታር እዚያው ኹአንተ ጋር አይደሉም? ኚንጉሡ ቀት ዚምትሰማውን ነገር ሁሉ ካህናት ለሆኑት ለሳዶቅና ለአብያታር ንገራ቞ው።
ኚእነሱም ጋር ሁለቱ ልጆቻ቞ው ማለትም ዚሳዶቅ ልጅ አኪማዓስና ዚአብያታር ልጅ ዮናታን አሉፀ እናንተም ዚምትሰሙትን ማንኛውንም ነገር በእነሱ በኩል ልካቜሁ አሳውቁኝ።”
በመሆኑም አቢሎሎም ወደ ኢዚሩሳሌም ሲገባ ዚዳዊት ወዳጅ ዹሆነው ኩሲ ወደ ኹተማዋ ሄደ።
ዚሳኊል ልጅ ኢያቡስ቎፣ አበኔር በኬብሮን መሞቱን ሲሰማ ወኔ ኚዳውፀ እስራኀላውያንም በሙሉ ተሚበሹ።
ዚሳኊል ልጅ ዚሚመራ቞ው ወራሪ ቡድኖቜ አለቃ ዹሆኑ ሁለት ሰዎቜ ነበሩፀ ዹአንደኛው ስም ባአናህ ሲሆን ዹሌላኛው ስም ደግሞ ሬካብ ነበር። እነሱም ኚቢንያም ነገድ ዹሆነው ዚበኀሮታዊው ዚሪሞን ልጆቜ ነበሩ። (ምክንያቱም በኀሮት ኚቢንያም ወገን እንደሆነ ተደርጎ ይቆጠር ነበር።
በኀሮታውያን ወደ ጊታይም ሞሹፀ እስኚ ዛሬም ድሚስ በዚያ ዚባዕድ አገር ሰው ሆነው ይኖራሉ።)
ዚሳኊል ልጅ ዮናታን እግሮቹ ሜባ ዹሆኑ አንድ ልጅ ነበሚው። እሱም ስለ ሳኊልና ስለ ዮናታን ዹሚገልጾው ወሬ ኚኢይዝራኀል በመጣ ጊዜ ዚአምስት ዓመት ልጅ ነበርፀ ሞግዚቱም አንስታው መሞሜ ጀመሚቜፀ ሆኖም በድንጋጀ ሞሜታ ስትሮጥ ኚእጇ ላይ ወድቆ ሜባ ሆነ። ስሙም ሜፊቊስ቎ ነበር።
ዚበኀሮታዊው ዚሪሞን ልጆቜ ሬካብ እና ባአናህ ሞቃታማ በሆነው ዹቀኑ ክፍለ ጊዜ ወደ ኢያቡስ቎ ቀት ሄዱፀ እሱም ቀትር ላይ አሹፍ ብሎ ነበር።
እነሱም ስንዎ ዚሚወስዱ ሰዎቜ መስለው ወደ ቀቱ ውስጥ ዘልቀው ገቡፀ ኢያቡስ቎ንም ሆዱ ላይ ወጉትፀ ኚዚያም ሬካብ እና ወንድሙ ባአናህ ሞሜተው አመለጡ።
ወደ ቀት ሲገቡ ኢያቡስ቎ መኝታ ቀቱ ውስጥ አልጋው ላይ ጋደም ብሎ ነበርፀ እነሱም መትተው ገደሉትፀ ኚዚያም ራሱን ቆርጠው በመውሰድ ወደ አሚባ በሚወስደው መንገድ ሌሊቱን ሙሉ ሲጓዙ አደሩ።
ዚኢያቡስ቎ንም ራስ በኬብሮን ወዳለው ወደ ዳዊት አምጥተው ንጉሡን “ሕይወትህን ሲፈልጋት ዹነበሹው ዚጠላትህ ዚሳኊል ልጅ ዚኢያቡስ቎ ራስ ይኞውልህ። ይሖዋ በዛሬው ዕለት ሳኊልንና ዘሮቹን ለጌታዬ ለንጉሡ ተበቀለለት” አሉት።
ሆኖም ዳዊት ለበኀሮታዊው ለሪሞን ልጆቜ ለሬካብ እና ለወንድሙ ለባአናህ እንዲህ ሲል መለሰላቾው፩ “ሕይወቮን ኚመኚራ ሁሉ በታደገልኝ ሕያው በሆነው በይሖዋ እምላለሁ፣
አንድ ሰው ምሥራቜ ያበሰሚኝ መስሎት ‘ሳኊል እኮ ሞተ’ ብሎ በነገሹኝ ጊዜ ጺቅላግ ላይ ገደልኩት። መልእክተኛው ኚእኔ ያገኘው ሜልማት ይህ ነበር!
ታዲያ በገዛ ቀቱ አልጋው ላይ ተኝቶ ዹነበሹውን ጻድቅ ሰው ዹገደሉ ክፉ ሰዎቜማ እንዎት ኹዚህ ዚባሰ ነገር አይጠብቃ቞ው! እና አሁን ደሙን ኚእጃቜሁ መጠዹቅም ሆነ እናንተን ኚምድር ገጜ ማጥፋት አይገባኝም?”
ኚዚያም ዳዊት እንዲገድሏ቞ው ለወጣቶቹ ትእዛዝ ሰጠ። እነሱም እጆቻ቞ውንና እግሮቻ቞ውን ቆርጠው በኬብሮን በሚገኘው ኩሬ አጠገብ ሰቀሏ቞ው። ዚኢያቡስ቎ን ራስ ግን ወስደው በኬብሮን ባለው በአበኔር ዚመቃብር ቊታ ቀበሩት።
በዚህ ጊዜ ዚቢንያማዊው ዚቢክሪ ልጅ ዹሆነ ሳባ ዚሚባል አንድ አስ቞ጋሪ ሰው ነበር። እሱም ቀንደ መለኚት በመንፋት “እኛ ኚዳዊት ጋር ምንም ድርሻ ዚለንምፀ ኚእሎይም ልጅ ጋር ምንም ውርሻ ዚለንም። እስራኀል ሆይ፣ እያንዳንድህ ወደ አማልክትህ ተመለስ!” አለ።
ስለዚህ ዚእስራኀል ሰዎቜ በሙሉ ዳዊትን መኹተል ትተው ዚቢክሪን ልጅ ሳባን መኹተል ጀመሩፀ ዚይሁዳ ሰዎቜ ግን ኚዮርዳኖስ አንስቶ እስኚ ኢዚሩሳሌም ድሚስ ኚንጉሣ቞ው አልተለዩም።
ዳዊት በኢዚሩሳሌም ወደሚገኘው ቀቱ ሲመጣ ንጉሡ ቀቱን እንዲጠብቁ ትቷ቞ው ሄዶ ዚነበሩትን አሥሩን ቁባቶቹን ወስዶ በዘብ በሚጠበቅ አንድ ቀት ውስጥ አስገባ቞ው። በዹጊዜው ቀለብ ይሰጣ቞ው ዹነበሹ ቢሆንም ኚእነሱ ጋር ምንም ግንኙነት አልፈጞመም። እነሱም ባላ቞ው በሕይወት ያለ ቢሆንም እስኚ ዕለተ ሞታ቞ው ድሚስ እንደ መበለት ሆነው ኖሩ።
ንጉሡም አሜሳይን “ዚይሁዳን ሰዎቜ በሊስት ቀን ውስጥ ጠርተህ ወደ እኔ ሰብስብልኝፀ አንተም እዚህ መገኘት ይኖርብሃል” አለው።
ስለዚህ አሜሳይ ዚይሁዳን ሕዝብ ለመሰብሰብ ሄደፀ ሆኖም ንጉሡ ኚቀጠሚለት ጊዜ ዘገዚ።
ኚዚያም ዳዊት አቢሳን “ኚአቢሎሎም ይልቅ ዚቢክሪ ልጅ ሳባ ዹኹፋ ጉዳት ሊያደርስብን ይቜላል። ስለሆነም ዹተመሾጉ ኚተሞቜ አግኝቶ እንዳያመልጠን ዚጌታህን አገልጋዮቜ ይዘህ አሳደው” አለው።
በመሆኑም ዚኢዮዓብ ሰዎቜ፣ ኚሪታውያን፣ ጎሌታውያን እና ኃያላን ዚሆኑት ሰዎቜ በሙሉ ተኚትለውት ሄዱፀ ዚቢክሪን ልጅ ሳባን ለማሳደድም ኚኢዚሩሳሌም ወጡ።
እነሱም በገባኊን በሚገኘው ትልቅ ድንጋይ አጠገብ ሲደርሱ አሜሳይ ሊገናኛቾው መጣ። ኢዮዓብ ዹጩር ልብሱን ለብሶ፣ ወገቡም ላይ ሰይፉን ኚነሰገባው ታጥቆ ነበር። ወደ ፊት ራመድ ሲልም ሰይፉ ኚሰገባው ወደቀ።
ኢዮዓብም አሜሳይን “ወንድሜ ሆይ፣ ደህና ነህ?” አለው። ኚዚያም ኢዮዓብ ዚሚስመው አስመስሎ በቀኝ እጁ ዚአሜሳይን ጢም ያዘ።
አሜሳይ፣ በኢዮዓብ እጅ ኹነበሹው ሰይፍ ራሱን አልጠበቀምፀ ኢዮዓብም በሰይፉ ሆዱ ላይ ወጋውፀ አንጀቱም መሬት ላይ ተዘሚገፈ። ዳግመኛ መውጋት እንኳ ሳያስፈልገው አንዮ ብቻ ወግቶ ገደለው። ኚዚያም ኢዮዓብና ወንድሙ አቢሳ ዚቢክሪን ልጅ ሳባን ማሳደዳ቞ውን ቀጠሉ።
ኚኢዮዓብ ወጣቶቜ መካኚል አንዱ አሜሳይ አጠገብ ቆሞ “ኚኢዮዓብ ጎን ዹሚቆምና ዚዳዊት ዹሆነ ማንኛውም ሰው ኢዮዓብን ይኹተል!” ይል ነበር።
በዚህ ጊዜ አሜሳይ መንገዱ መሃል ላይ በደም ተጹማልቆ ይንፈራገጥ ነበር። ሰውዹውም ሰዉ ሁሉ እዚያ ሲደርስ እንደሚቆም ሲያይ አሜሳይን ኚመንገዱ ላይ ወደ ሜዳው ገለል አደሚገው። ይሁንና ሰዉ ሁሉ አሁንም እሱ ጋ ሲደርስ እንደሚቆም ሲያይ ልብስ ጣል አደሚገበት።
አሜሳይን ኚመንገዱ ላይ ካነሳው በኋላ ሰዉ ሁሉ ዚቢክሪን ልጅ ሳባን ለማሳደድ ኢዮዓብን ተኚትሎ ሄደ።
ሳባም ዚእስራኀልን ነገዶቜ በሙሉ አልፎ ወደ ቀትማዓካዋ አቀል ሄደ። ቢክሪያውያንም ተሰብስበው ተኚተሉት።
ኢዮዓብና ሰዎቹም መጥተው ሳባን በቀትማዓካዋ አቀል እንዳለ ኚበቡትፀ በኹተማዋም ዙሪያ ዹአፈር ቁልል ደለደሉፀ ኹተማዋም በአፈር ቁልሉ መሃል ነበሚቜ። ኚኢዮዓብም ጋር ዚነበሩት ሰዎቜ ሁሉ ዹኹተማዋን ቅጥር ለመጣል ኚሥሩ ይሰሚስሩ ነበር።
ኹኹተማዋም ውስጥ አንዲት ብልህ ሎት ድምፅዋን ኹፍ አድርጋ “ስሙ፣ እናንተ ሰዎቜ ስሙ! እባካቜሁ ኢዮዓብን ‘ወደዚህ ቅሚብና ላነጋግርህ’ በሉት” አለቜ።
እሱም ወደ እሷ ቀሚበፀ ኚዚያም ሎትዚዋ “ኢዮዓብ አንተ ነህ?” አለቜውፀ እሱም “አዎ፣ እኔ ነኝ” አላት። በዚህ ጊዜ “አገልጋይህ ዚምትልህን ስማ” አለቜው። እሱም መልሶ “እሺ እዚሰማሁ ነው” አላት።
እሷም እንዲህ አለቜፊ “ቀደም ባሉት ጊዜያት ሰዎቜ ‘በአቀል ኹተማ ይጠይቁፀ ጉዳያ቞ውም እልባት ያገኛል’ ይሉ ነበር።
እኔ ዚእስራኀልን ሰላማዊና ታማኝ ሰዎቜ እወክላለሁ። አንተ በእስራኀል ውስጥ እንደ እናት ዚሆነቜን ኹተማ ልትደመስስ ትፈልጋለህ። ዹይሖዋን ውርሻ ዚምታጠፋው ለምንድን ነው?”
ኢዮዓብም መልሶ እንዲህ አላትፊ “ኹተማዋን ማጥፋትም ሆነ መደምሰስ ፈጜሞ ዚማላስበው ነገር ነው።
ነገሩ እንደዚያ አይደለም። ሆኖም ኚኀፍሬም ተራራማ አካባቢ ዚመጣውና ዚቢክሪ ልጅ ዹሆነው ሳባ በንጉሥ ዳዊት ላይ ዓምፆአል። ይህን ሰው አሳልፋቜሁ ኚሰጣቜሁኝ ኹተማዋን ትቌ እሄዳለሁ።” ኚዚያም ሎትዚዋ ኢዮዓብን “እንግዲህ ዹሰውዹው ራስ በቅጥሩ ላይ ይወሹወርልሃል!” አለቜው።
ብልህ ዚሆነቜው ሎትም ወዲያውኑ ወደ ሕዝቡ ሄደቜፀ እነሱም ዚቢክሪን ልጅ ዚሳባን ራስ ቆርጠው ለኢዮዓብ ወሚወሩለት። በዚህ ጊዜ ኢዮዓብ ቀንደ መለኚት ነፋፀ እነሱም ኹተማዋን ትተው በዚአቅጣጫው ተበታተኑፀ እያንዳንዱም ሰው ወደቀቱ ሄደፀ ኢዮዓብም ወደ ኢዚሩሳሌም ወደ ንጉሡ ተመለሰ።
ኢዮዓብ ዹመላው ዚእስራኀል ሠራዊት አዛዥ ነበርፀ ዚዮዳሄ ልጅ በናያህ ደግሞ በኚሪታውያንና በጎሌታውያን ላይ ዹበላይ ነበር።
አዶራም ዚግዳጅ ሥራ እንዲሠሩ በተመለመሉት ላይ ዹበላይ ነበርፀ ዚአሂሉድ ልጅ ኢዮሳፍጥ ደግሞ ታሪክ ጾሐፊ ነበር።
ሻዌ ጾሐፊ ነበርፀ ሳዶቅና አብያታር ደግሞ ካህናት ነበሩ።
በተጚማሪም ያኢራዊው ኢራ ዋና ኃላፊ ሆኖ ዳዊትን ያገለግል ነበር።
በመሆኑም ይሖዋ ናታንን ወደ ዳዊት ላኚው። እሱም ወደ ዳዊት መጥቶ እንዲህ አለው፩ “በአንዲት ኹተማ ውስጥ ዚሚኖሩ ሁለት ሰዎቜ ነበሩፀ አንደኛው ሀብታም ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ድሃ ነበር።
ሀብታሙ ሰው እጅግ ብዙ በጎቜና ኚብቶቜ ነበሩትፀ
ድሃው ሰው ግን ኚገዛት አንዲት ትንሜ ዹበግ ጠቊት ሌላ ምንም አልነበሚውም። እሱም ይንኚባኚባት ነበርፀ እሷም ኚእሱና ኚወንዶቜ ልጆቹ ጋር አብራ እዚኖሚቜ አደገቜ። ያለቜውን ጥቂት ምግብ አብራ ትበላ፣ ኚጜዋውም ትጠጣ እንዲሁም በእቅፉ ትተኛ ነበር። ለእሱም እንደ ሎት ልጁ ነበሚቜ።
አንድ ቀን ሀብታሙ ሰው እንግዳ መጣበትፀ ሆኖም ይህ ሰው ወደ እሱ ለመጣው መንገደኛ ዹሚበላ ነገር ለማዘጋጀት ኚራሱ በጎቜና ኚብቶቜ ላይ አልወሰደም። ኹዚህ ይልቅ ዚድሃውን ሰው ዹበግ ጠቊት ወስዶ ወደ እሱ ለመጣው እንግዳ አዘጋጅቶ አቀሚበለት።”
በዚህ ጊዜ ዳዊት በሰውዹው ላይ እጅግ ተቆጥቶ ናታንን እንዲህ አለውፊ “ሕያው በሆነው በይሖዋ እምላለሁ፣ ይህን ያደሚገው ሰው ሞት ይገባዋል!
ይህ ሰው እንዲህ ያለውን ነገር ስላደሚገና ርኅራኄ ስላላሳዚ በበግ ጠቊቷ ምትክ አራት እጥፍ መክፈል አለበት።”
ኚዚያም ናታን ዳዊትን እንዲህ አለው፩ “ያ ሰው አንተ ነህ! ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘በእስራኀል ላይ ንጉሥ እንድትሆን እኔ ራሎ ቀባሁህፀ ኚሳኊልም እጅ ታደግኩህ።
ዚጌታህን ቀት ልሰጥህ፣ ዚጌታህንም ሚስቶቜ በእቅፍህ ላደርግልህ ፈቃደኛ ነበርኩፀ ዚእስራኀልንና ዚይሁዳንም ቀት ሰጠሁህ። ይህም ሁሉ አንሶህ ቢሆን ኖሮ ኹዚህ ዹበለጠ ነገር ላደርግልህ ፈቃደኛ ነበርኩ።
ታዲያ በፊቱ መጥፎ ነገር በመሥራት ዹይሖዋን ቃል ያቃለልኚው ለምንድን ነው? ሂታዊውን ኊርዮን በሰይፍ መታኞው! በአሞናውያን ሰይፍ ኹገደልኹውም በኋላ ሚስቱን ወስደህ ሚስትህ አደሚግካት።
ስለዚህ ዚሂታዊውን ዚኊርዮን ሚስት ወስደህ ሚስትህ በማድሚግ እኔን ስለናቅክ ሰይፍ ኚቀትህ ፈጜሞ አይለይም።’
ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ኹገዛ ቀትህ መኚራ አመጣብሃለሁፀ ዓይንህ እያዚም ሚስቶቜህን ወስጄ ለሌላ ሰው እሰጣ቞ዋለሁፀ እሱም በቀን ብርሃን ኚሚስቶቜህ ጋር ይተኛል።
አንተ ይህን በድብቅ ብታደርገውም እኔ ግን በመላው እስራኀል ፊት በቀን ብርሃን አደርገዋለሁ።’”
ኚዚያም ዳዊት ናታንን “በይሖዋ ላይ ኃጢአት ሠርቻለሁ” አለው። ናታንም ዳዊትን እንዲህ አለው፩ “ይሖዋም ኃጢአትህን ይቅር ይላል። አትሞትም።
ይሁንና ይህን ድርጊት በመፈጾም ይሖዋን እጅግ ስለናቅክ አሁን ዹተወለደልህ ልጅ ይሞታል።”
ኚዚያም ናታን ወደ ቀቱ ሄደ። ይሖዋም ዚኊርዮ ሚስት ለዳዊት ዚወለደቜለትን ልጅ በመቅሰፍት መታውፀ ልጁም ታመመ።
ዳዊትም ስለ ልጁ እውነተኛውን አምላክ ተማጞነ። ምንም ነገር ሳይቀምስም ጟመፀ ወደ ክፍሉ ገብቶም ሌሊቱን ሙሉ መሬት ላይ ተኝቶ አደሚ።
በቀቱ ያሉ ሜማግሌዎቜም መጥተው አጠገቡ ቆሙፀ ኚመሬት ሊያነሱትም ሞኚሩ። እሱ ግን ፈቃደኛ አልሆነምፀ አብሯ቞ውም ምግብ አልበላም።
በሰባተኛው ቀን ልጁ ሞተፀ ዚዳዊት አገልጋዮቜ ግን ዹልጁን መሞት ለእሱ መንገር ፈሩ። እነሱም እንዲህ አሉ፩ “ልጁ በሕይወት ሳለ ዳዊትን አነጋግሹነው ነበርፀ እሱ ግን ሊሰማን ፈቃደኛ አልሆነም። ታዲያ አሁን ልጁ መሞቱን እንዎት እንነግሚዋለን? መቌም ይህን ብንነግሚው መጥፎ ነገር ሊያደርግ ይቜላል።”
ዳዊት አገልጋዮቹ በሹክሹክታ ሲነጋገሩ ሲያይ ልጁ እንደሞተ ገባው። በመሆኑም አገልጋዮቹን “ልጁ ሞተ?” አላ቞ው። እነሱም “አዎ፣ ሞቷል” ብለው መለሱለት።
በዚህ ጊዜ ዳዊት ኚመሬት ተነሳ። ኚታጠበ፣ ዘይት ኚተቀባና ልብሱን ኹቀዹሹ በኋላም ወደ ይሖዋ ቀት ሄዶ ሰገደ። ወደ ቀቱም ሄዶ ምግብ እንዲያቀርቡለት ጠዚቀፀ ኚዚያም በላ።
አገልጋዮቹም “እንዲህ ያደሚግኚው ለምንድን ነው? ልጁ በሕይወት ሳለ ስትጟምና ስታለቅስ ነበርፀ ልጁ ሲሞት ግን ወዲያውኑ ተነሳህፀ ምግብም በላህ” አሉት።
እሱም እንዲህ አለ፩ “ልጁ በሕይወት ሳለ ‘ማን ያውቃል፣ ይሖዋ ይራራልኝና ልጁን በሕይወት ያኖርልኝ ይሆናል’ ብዬ ስላሰብኩ ጟምኩፀ እንዲሁም አለቀስኩ።
አሁን ግን ልጁ ሞቷልፀ ታዲያ ዚምጟመው ለምንድን ነው? መልሌ ላመጣው እቜላለሁ? እኔ ወደ እሱ እሄዳለሁ እንጂ እሱ ወደ እኔ አይመለስም።”
ኚዚያም ዳዊት ሚስቱን ቀርሳቀህን አጜናናት። ወደ እሷም ገብቶ አብሯት ተኛ። ኹጊዜ በኋላም ወንድ ልጅ ወለደቜፀ ስሙም ሰለሞን ተባለ። ይሖዋም ወደደውፀ
በነቢዩ ናታን በኩል መልእክት ልኮም ለይሖዋ ሲል ስሙን ይዲድያህ አለው።
ኢዮአብ ዚአሞናውያን ኹተማ ዚሆነቜውን ራባን መውጋቱን ቀጠለፀ ዚነገሥታቱንም ኹተማ ተቆጣጠሚ።
በመሆኑም ኢዮአብ እንዲህ ብለው እንዲነግሩት መልእክተኞቜን ወደ ዳዊት ላኹ፩ “ኚራባ ጋር ተዋግቌ ዚውኃዎቜን ኹተማ ይዣለሁ።
በል አሁን ዹቀሹውን ሠራዊት ሰብስብና ኹተማዋን ኹበህ በቁጥጥርህ ሥር አድርጋት። አለዚያ ኹተማዋን እይዛትና ክብሩ ለእኔ ይሆናል።”
በመሆኑም ዳዊት ሠራዊቱን ሁሉ ሰብስቊ ወደ ራባ ሄደፀ ኹተማዋንም ወግቶ በቁጥጥር ሥር አደሚጋት።
ኚዚያም ዚማልካምን ዘውድ ኚራሱ ላይ ወሰደ። ዚዘውዱም ክብደት አንድ ታላንት ወርቅ ነበርፀ በላዩም ላይ ዚኚበሩ ድንጋዮቜ ነበሩፀ ዘውዱም በዳዊት ራስ ላይ ተደሚገ። በተጚማሪም ኹኹተማዋ በጣም ብዙ ምርኮ ወሰደ።
ነዋሪዎቿንም አውጥቶ ድንጋይ እንዲቆርጡ፣ ስለት ባላ቞ው ዚብሚት መሣሪያዎቜና በብሚት መጥሚቢያዎቜ እንዲሠሩ እንዲሁም ጡብ እንዲያመርቱ አደሚጋ቞ው። በአሞናውያን ኚተሞቜ ሁሉ እንዲሁ አደሚገ። በመጚሚሻም ዳዊትና ሠራዊቱ ሁሉ ወደ ኢዚሩሳሌም ተመለሱ።
ኚዚያም ዳዊት አብሚውት ዚነበሩትን ሰዎቜ ቆጠሚፀ በእነሱም ላይ ዚሺህ አለቆቜና ዚመቶ አለቆቜ ሟመ።
በተጚማሪም ዳዊት ኚሰዎቹ መካኚል አንድ ሊስተኛውን በኢዮዓብ አመራር ሥር፣ አንድ ሊስተኛውን ደግሞ ዚኢዮዓብ ወንድም በሆነው በጜሩያ ልጅ በአቢሳ አመራር ሥር እንዲሁም አንድ ሊስተኛውን በጌታዊው በኢታይ አመራር ሥር አድርጎ ላኚ። ንጉሡም ሰዎቹን “እኔም አብሬያቜሁ እወጣለሁ” አላ቞ው።
እነሱ ግን እንዲህ አሉትፊ “አንተማ መውጣት ዚለብህምፀ ለመሞሜ ብንገደድ እንኳ እነሱ ስለ እኛ ደንታ አይሰጣ቞ውምፀ ግማሟቻቜን ብንሞትም ግድ ዚላ቞ውምፀ ምክንያቱም አንተ ኚእኛ ኚአሥሩ ሺህ ትበልጣለህ። ስለዚህ ኹተማው ውስጥ ሆነህ ድጋፍ ብትሰጠን ይሻላል።”
ንጉሡም “እሺ፣ እናንተ ዚተሻለ ነው ያላቜሁትን አደርጋለሁ” አላ቞ው። በመሆኑም ንጉሡ በኹተማዋ በር አጠገብ ቆመፀ ሰዎቹም ሁሉ በመቶዎቜና በሺዎቜ እዚሆኑ ወጡ።
ንጉሡም ኢዮዓብን፣ አቢሳንና ኢታይን “ለእኔ ስትሉ በወጣቱ በአቢሎሎም ላይ አትጚክኑበት” ሲል አዘዛ቞ው። ንጉሡ አቢሎሎምን አስመልክቶ ለአለቆቹ በሙሉ ትእዛዝ ሲሰጥ ሰዎቹ ሁሉ ሰሙ።
ሰዎቹም ኚእስራኀላውያን ጋር ለመዋጋት ወደ ሜዳው ወጡፀ ውጊያውም በኀፍሬም ጫካ ውስጥ ተካሄደ።
በዚያም ዚእስራኀል ሰዎቜ በዳዊት አገልጋዮቜ ድል ተመቱፀ በዚያም ቀን ታላቅ እልቂት ሆነፀ ኚመካኚላ቞ውም 20,000 ሰው ተገደለ።
ውጊያውም በአካባቢው ሁሉ ተዛመተ። በዚያን ቀን ሰይፍ ኹበላው ይልቅ ጫካ ዹበላው ሰው በለጠ።