text
stringlengths
4
267
ሆኖም ካህኑ ሳዶቅ፣ ዚዮዳሄ ልጅ በናያህ፣ ነቢዩ ናታን፣ ሺምአይ፣ ሹአይና ዚዳዊት ኃያላን ተዋጊዎቜ አዶንያስን አልደገፉትም።
በኋላም አዶንያስ በኀንሮጌል አቅራቢያ በሚገኘው በጟሃለት ድንጋይ አጠገብ በጎቜን፣ ኚብቶቜንና ዚሰቡ እንስሳትን መሥዋዕት አድርጎ አቀሚበፀ ዚንጉሡ ልጆቜ ዚሆኑትን ወንድሞቹን በሙሉ እንዲሁም ዚንጉሡ አገልጋዮቜ ዚሆኑትን ዚይሁዳን ሰዎቜ ሁሉ ጠራ።
ይሁን እንጂ ነቢዩ ናታንን፣ በናያህን፣ ዚዳዊትን ኃያላን ተዋጊዎቜ ወይም ወንድሙን ሰለሞንን አልጠራም።
ኚዚያም ናታን ዹሰለሞንን እናት ቀርሳቀህን እንዲህ አላትፊ “ዚሃጊት ልጅ አዶንያስ ንጉሥ እንደሆነና ጌታቜን ዳዊት ደግሞ ስለ ጉዳዩ ምንም ዚሚያውቀው ነገር እንደሌለ አልሰማሜም?
ስለዚህ አሁን ነይ፣ ዚራስሜንም ሆነ ዚልጅሜን ዹሰለሞንን ሕይወት ማዳን እንድትቜይ አንድ ነገር ልምኚርሜ።
ወደ ንጉሥ ዳዊት ገብተሜ እንዲህ በዪውፊ ‘“ልጅሜ ሰለሞን ኚእኔ በኋላ ንጉሥ ይሆናልፀ በዙፋኔም ላይ ዹሚቀመጠው እሱ ነው” በማለት ለአገልጋይህ ዚማልክላት አንተ ንጉሡ ጌታዬ አልነበርክም? ታዲያ አዶንያስ ንጉሥ ዹሆነው ለምንድን ነው?’
አንቺም እዚያው ገና ኚንጉሡ ጋር እዚተነጋገርሜ ሳለ እኔ ተኚትዬሜ እገባና ያልሜው ትክክል መሆኑን እናገራለሁ።”
በመሆኑም ቀርሳቀህ ንጉሡ ወዳለበት ወደ ውስጠኛው ክፍል ገባቜ። ንጉሡ በጣም አርጅቶ ነበርፀ ሹነማዊቷ አቢሻግም ንጉሡን እዚተንኚባኚበቜ ነበር።
ኚዚያም ቀርሳቀህ በንጉሡ ፊት ተደፍታ ሰገደቜፀ ንጉሡም “ጥያቄሜ ምንድን ነው?” አላት።
እሷም እንዲህ ስትል መለሰቜፊ “ጌታዬ ሆይ፣ ‘ልጅሜ ሰለሞን ኚእኔ በኋላ ንጉሥ ይሆናልፀ በዙፋኔም ላይ ዹሚቀመጠው እሱ ነው’ በማለት ለአገልጋይህ በአምላክህ በይሖዋ ዚማልክላት አንተ ነበርክ።
ይኾው አሁን ግን አዶንያስ ንጉሥ ሆኗልፀ ጌታዬ ንጉሡም ስለዚህ ጉዳይ ምንም ዚሚያውቀው ነገር ዚለም።
እሱም በጣም ብዙ በሬዎቜን፣ ዚሰቡ እንስሳትንና በጎቜን መሥዋዕት አድርጓልፀ ዚንጉሡን ልጆቜ በሙሉ፣ ካህኑን አብያታርንና ዚሠራዊቱን አለቃ ኢዮዓብን ጠርቷልፀ አገልጋይህን ሰለሞንን ግን አልጠራውም።
አሁንም ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፣ እስራኀላውያን በሙሉ ኚጌታዬ ኚንጉሡ በኋላ በዙፋኑ ላይ ዹሚቀመጠው ማን እንደሆነ እንድታሳውቃ቞ው ዓይኖቻ቞ው አንተ ላይ ና቞ው።
አለዚያ ግን ጌታዬ ንጉሡ ኚአባቶቹ ጋር በሚያንቀላፋበት ጊዜ እኔና ልጄ ሰለሞን እንደ ኚዳተኞቜ ተደርገን እንቆጠራለን።”
እሷም ገና ኚንጉሡ ጋር እዚተነጋገሚቜ ሳለ ነቢዩ ናታን ገባ።
ወዲያውም ለንጉሡ “ነቢዩ ናታን መጥቷል!” ብለው ነገሩት። ናታንም ንጉሡ ፊት ቀርቩ በግንባሩ መሬት ላይ በመደፋት ሰገደ።
ኚዚያም ናታን እንዲህ አለ፩ “ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፣ ‘አዶንያስ ኚእኔ በኋላ ንጉሥ ይሆናልፀ በዙፋኔ ላይ ዹሚቀመጠውም እሱ ነው’ ብለህ ተናግሹሃል እንዎ?
ይኾው ዛሬ በጣም ብዙ በሬዎቜን፣ ዚሰቡ እንስሳትንና በጎቜን ለመሠዋት ወርዷልፀ እንዲሁም ዚንጉሡን ልጆቜ በሙሉ፣ ዚሠራዊቱን አለቆቜና ካህኑን አብያታርን ጠርቷል። እነሱም በዚያ ኚእሱ ጋር እዚበሉና እዚጠጡ ‘ንጉሥ አዶንያስ ለዘላለም ይኑር!’ እያሉ ነው።
ሆኖም እኔን አገልጋይህን ወይም ካህኑን ሳዶቅን አሊያም ዚዮዳሄን ልጅ በናያህን ወይም አገልጋይህን ሰለሞንን አልጠራም።
ጌታዬ ንጉሡ ኚእሱ በኋላ በጌታዬ በንጉሡ ዙፋን ላይ ዹሚቀመጠው ማን እንደሆነ ለአገልጋዩ ሳይነግሚው ይህ እንዲደሚግ ፈቅዷል?”
በዚህ ጊዜ ንጉሥ ዳዊት “ቀርሳቀህን ጥሩልኝ” አለ። እሷም ገብታ ንጉሡ ፊት ቆመቜ።
ንጉሡም እንዲህ ሲል ማለ፩ “ኚመኚራ ሁሉ ባዳነኝ ሕያው በሆነው በይሖዋ እምላለሁ፣
‘ልጅሜ ሰለሞን ኚእኔ በኋላ ንጉሥ ይሆናልፀ በእኔ ምትክ በዙፋኔ ላይ ዹሚቀመጠውም እሱ ነው!’ በማለት በእስራኀል አምላክ በይሖዋ በማልኩልሜ መሠሚት ዛሬም ይህ እንዲፈጞም አደርጋለሁ።”
ኚዚያም ቀርሳቀህ በግንባሯ መሬት ላይ ተደፍታ ለንጉሡ በመስገድ “ጌታዬ ንጉሥ ዳዊት ለዘላለም ይኑር!” አለቜ።
ንጉሥ ዳዊትም ወዲያውኑ “በሉ አሁን ካህኑን ሳዶቅን፣ ነቢዩን ናታንንና ዚዮዳሄን ልጅ በናያህን ጥሩልኝ” አለ። እነሱም ገብተው ንጉሡ ፊት ቀሚቡ።
ንጉሡም እንዲህ አላቾው፩ “ዚጌታቜሁን አገልጋዮቜ ውሰዱና ልጄን ሰለሞንን በበቅሎዬ ላይ አስቀምጣቜሁ ወደ ግዮን ይዛቜሁት ውሚዱ።
በዚያም ካህኑ ሳዶቅና ነቢዩ ናታን በእስራኀል ላይ ንጉሥ አድርገው ይቀቡታልፀ ኚዚያም ቀንደ መለኚት እዚነፋቜሁ ‘ንጉሥ ሰለሞን ለዘላለም ይኑር!’ በሉ።
አጅባቜሁትም ተመለሱፀ እሱም መጥቶ በዙፋኔ ላይ ይቀመጣልፀ በእኔም ምትክ ንጉሥ ይሆናልፀ እኔም በእስራኀልና በይሁዳ ላይ መሪ አድርጌ እሟመዋለሁ።”
ዚዮዳሄ ልጅ በናያህም ወዲያውኑ ንጉሡን እንዲህ አለው፩ “አሜን! ዚጌታዬ ዚንጉሡ አምላክ ይሖዋ ይህን ያጜናው።
ይሖዋ ኚጌታዬ ኚንጉሡ ጋር እንደነበሚ ሁሉ ኹሰለሞንም ጋር ይሁንፀ ዙፋኑንም ኚጌታዬ ኚንጉሥ ዳዊት ዙፋን ዹበለጠ ያድርገው።”
ኚዚያም ካህኑ ሳዶቅ፣ ነቢዩ ናታን፣ ዚዮዳሄ ልጅ በናያህ፣ ኚሪታውያንና ጎሌታውያን ወርደው ሰለሞንን በንጉሥ ዳዊት በቅሎ ላይ አስቀመጡትፀ ወደ ግዮንም አመጡት።
ካህኑ ሳዶቅም ኚድንኳኑ ውስጥ ዚዘይቱን ቀንድ ወስዶ ሰለሞንን ቀባውፀ እነሱም ቀንደ መለኚት መንፋት ጀመሩፀ ሕዝቡም ሁሉ “ንጉሥ ሰለሞን ለዘላለም ይኑር!” እያለ ይጮኜ ጀመር።
ኚዚያም ሕዝቡ በሙሉ ዋሜንት እዚነፋና በደስታ እዚፈነደቀ ተኚትሎት ወጣፀ ኚጩኞታ቞ውም ዚተነሳ ምድሪቱ ተሰነጠቀቜ።
አዶንያስና ዹጋበዛቾው ሰዎቜ ሁሉ በልተው ሲጚርሱ ይህን ድምፅ ሰሙ። ኢዮዓብ ዹቀንደ መለኚቱን ድምፅ ሲሰማ “በኹተማዋ ውስጥ ዹሚሰማው ይህ ሁሉ ሁካታ ምንድን ነው?” አለ።
እሱም ገና እዚተናገሚ ሳለ ዚካህኑ ዚአብያታር ልጅ ዮናታን መጣ። ኚዚያም አዶንያስ “መቌም አንተ ጥሩ ሰው ስለሆንክ ምሥራቜ ሳትይዝ አትመጣምና ግባ” አለው።
ዮናታን ግን ለአዶንያስ እንዲህ ሲል መለሰለትፊ “ምሥራቜ ይዀስ አልመጣሁም! ጌታቜን ንጉሥ ዳዊት ሰለሞንን አንግሊታል።
ንጉሡም ካህኑ ሳዶቅ፣ ነቢዩ ናታን፣ ዚዮዳሄ ልጅ በናያህ፣ ኚሪታውያንና ጎሌታውያን አብሚውት እንዲሄዱ አደሚገፀ እነሱም በንጉሡ በቅሎ ላይ አስቀመጡት።
ኚዚያም ካህኑ ሳዶቅና ነቢዩ ናታን በግዮን ንጉሥ አድርገው ቀቡት። እነሱም ኚዚያ እዚተደሰቱ መጡፀ ኹተማዋ በጩኞት እዚተናወጠቜ ነው። እናንተም ዚሰማቜሁት ይህን ድምፅ ነው።
ኹዚህም በላይ ሰለሞን በነገሥታቱ ዙፋን ላይ ተቀምጧል።
ዚንጉሡ አገልጋዮቜም ‘አምላክህ ዹሰለሞንን ስም ኹአንተ ስም በላይ ታላቅ ያድርገውፀ ዙፋኑንም ኹአንተ ዙፋን ዹበለጠ ያድርገው’ በማለት ለጌታቜን ለንጉሥ ዳዊት ደስታ቞ውን ለመግለጜ መጥተዋል። በዚህ ጊዜ ንጉሡ አልጋው ላይ ሰገደ።
ኚዚያም ንጉሡ ‘ዛሬ በዙፋኔ ላይ ዚሚቀመጥ ሰው ዹሰጠኝና ዓይኖቌም ይህን እንዲያዩ ያደሚገው ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ ይወደስ!’ አለ።”
አዶንያስ ዹጋበዛቾው ሰዎቜም ሁሉ ተሞበሩፀ እያንዳንዳ቞ውም ተነስተው በዹፊናቾው ሄዱ።
አዶንያስም ሰለሞንን ስለፈራው ተነስቶ በመሄድ ዚመሠዊያውን ቀንዶቜ ያዘ።
በኋላም ሰለሞን “አዶንያስ ንጉሥ ሰለሞንን ፈርቶታልፀ ‘በመጀመሪያ ንጉሥ ሰለሞን አገልጋዩን በሰይፍ እንደማይገድል ይማልልኝ’ በማለት ዚመሠዊያውን ቀንዶቜ ይዟል” ተብሎ ተነገሚው።
በዚህ ጊዜ ሰለሞን “ጞባዩን ካሳመሚ ኚራስ ፀጉሩ አንዲቷም እንኳ መሬት ላይ አትወድቅምፀ መጥፎ ነገር ኚተገኘበት ግን ይሞታል” አለ።
በመሆኑም ንጉሥ ሰለሞን አዶንያስን ኚመሠዊያው ላይ እንዲያወርዱት ሰዎቜ ላኚ። ኚዚያም አዶንያስ መጥቶ ለንጉሥ ሰለሞን ሰገደፀ ሰለሞንም “ወደ ቀትህ ሂድ” አለው።
ሰለሞንም ዚራሱን ቀት ሙሉ በሙሉ ሠርቶ ለማጠናቀቅ 13 ዓመት ፈጀበት።
እሱም ዚሊባኖስ ደን ዚተባለውን ርዝመቱ 100 ክንድ፣ ወርዱ 50 ክንድ፣ ቁመቱ ደግሞ 30 ክንድ ዹሆነ ቀት በአራት ሚድፍ በተደሚደሩ ዹአርዘ ሊባኖስ ዓምዶቜ ገነባፀ በዓምዶቹም ላይ ዹአርዘ ሊባኖስ ወራጆቜ ነበሩ።
ቀቱም በዓምዶቹ ላይ ባሚፉት አግዳሚዎቜ ላይ ዚተሚበሚቡ ዹአርዘ ሊባኖስ ሳንቃዎቜ ነበሩትፀ ዓምዶቹም 45 ሲሆኑ በአንዱ ሚድፍ ላይ 15 ነበሩ።
በሊስት ሚድፍ ዚተሠሩ ባለ ክፈፍ መስኮቶቜ ነበሩፀ በሊስቱም ደርቊቜ ላይ እያንዳንዱ መስኮት ኹሌላኛው መስኮት ጋር ትይዩ ነበር።
በሊስቱ ደርቊቜ ላይ ያሉት ትይዩ ዹሆኑ መስኮቶቜ ኚፊት ለፊት ሲታዩ አራት ማዕዘን እንደሆኑ ሁሉ መግቢያዎቹና መቃኖቹም በሙሉ እንዲሁ ነበሩ።
እሱም ርዝመቱ 50 ክንድ፣ ወርዱ ደግሞ 30 ክንድ ዹሆነ ዚዓምዶቜ መተላለፊያ ሠራፀ ኚፊት ለፊቱም ዓምዶቜና ታዛ ያለው በሚንዳ ነበር።
በተጚማሪም ፍርድ ዚሚሰጥበትን ዹዙፋን አዳራሜ ይኾውም ዚፍርድ አዳራሹን ሠራፀ አዳራሹንም ኹወለሉ አንስቶ እስኚ ወራጆቹ ድሚስ በአርዘ ሊባኖስ ለበጡት።
በሌላኛው ግቢ ያለው ራሱ ዚሚኖርበት ቀት ዹሚገኘው ኚአዳራሹ ጀርባ ሲሆን አሠራራ቞ውም ተመሳሳይ ነበር። በተጚማሪም ሰለሞን ላገባት ለፈርዖን ልጅ ኹዚህ አዳራሜ ጋር ዚሚመሳሰል ቀት ሠርቶላት ነበር።
እነዚህ ሁሉ ኹውጭ አንስቶ እስኚ ትልቁ ግቢ ድሚስ፣ ኚመሠሚቱ እስኚ ድምድማቱ፣ በውስጥም በውጭም ተለክተው በተጠሚቡና በድንጋይ መጋዝ በተቆሚጡ ውድ ድንጋዮቜ ዚተሠሩ ነበሩ።
መሠሚቱ ዚተጣለው ውድ በሆኑ ትላልቅ ድንጋዮቜ ነበርፀ አንዳንዶቹ ድንጋዮቜ ባለ አሥር ክንድ ሲሆኑ ሌሎቹ ደግሞ ባለ ስምንት ክንድ ነበሩ።
በእነዚህም ላይ ተለክተው ዚተጠሚቡ ውድ ድንጋዮቜና ዹአርዘ ሊባኖስ እንጚቶቜ ነበሩ።
ለይሖዋ ቀት ውስጠኛ ግቢና ለቀቱ በሚንዳ እንደተደሚገው ሁሉ ዚትልቁ ግቢ አጥር ዚተሠራው በሊስት ሚድፍ ጥርብ ድንጋይና በአንድ ሚድፍ ዹአርዘ ሊባኖስ ሳንቃ ነበር።
ንጉሥ ሰለሞን መልእክተኛ ልኮ ኪራምን ኚጢሮስ አስመጣው።
ኪራም ኚንፍታሌም ነገድ ዚሆነቜ ዚአንዲት መበለት ልጅ ነበርፀ አባቱ ዚጢሮስ ሰው ሲሆን ዚመዳብ ሥራ ባለሙያ ነበርፀ ኪራም ኹማንኛውም ዚመዳብ ሥራ ጋር በተያያዘ ኹፍተኛ ቜሎታ፣ ማስተዋልና ልምድ ነበሚው። በመሆኑም ወደ ንጉሥ ሰለሞን መጥቶ ሥራዎቹን ሁሉ አኚናወነለት።
እሱም ሁለቱን ዓምዶቜ ኹቀለጠ መዳብ ሠራፀ እያንዳንዱም ዓምድ ቁመቱ 18 ክንድ ነበርፀ ሁለቱ ዓምዶቜ እያንዳንዳ቞ው በመለኪያ ገመድ ሲለኩ መጠነ ዙሪያ቞ው 12 ክንድ ነበር።
እንዲሁም በዓምዶቹ አናት ላይ ዹሚሆኑ ሁለት ዚዓምድ ራሶቜን ኚመዳብ ሠራ። ዹአንደኛው ዚዓምድ ራስ ቁመት አምስት ክንድ ዹሌላኛው ዚዓምድ ራስ ቁመትም አምስት ክንድ ነበር።
በእያንዳንዱ ዓምድ አናት ላይ ያለው ዚዓምድ ራስ በሰንሰለት ጉንጉን ዚተሠሩ መሚቊቜ ነበሩትፀ በአንደኛው ዚዓምድ ራስ ላይ ሰባት በሌላኛው ዚዓምድ ራስ ላይም ሰባት ነበሩ።
በዓምዶቹ አናት ላይ ያሉትን ዚዓምድ ራሶቜ ለማስጌጥ በአንደኛው መሚብ ዙሪያ ሮማኖቜን በሁለት ሚድፍ ሠራፀ በሁለቱም ዚዓምድ ራሶቜ ላይ እንዲሁ አደሚገ።
በሚንዳው አጠገብ በሚገኙት ዓምዶቜ አናት ላይ ያሉት ዚዓምድ ራሶቜ አራት ክንድ ቁመት ያለው ዚአበባ ቅርጜ ነበራ቞ው።
ዚዓምድ ራሶቹ በሁለቱ ዓምዶቜ ላይ፣ ልክ ኚመሚብ ሥራው ቀጥሎ ካለው ኚሆዱ በላይ ነበሩፀ በእያንዳንዱ ዚዓምድ ራስ ዙሪያ 200 ሮማኖቜ በሚድፍ ተደርድሚው ነበር።
እሱም ዚቀተ መቅደሱን በሚንዳ ዓምዶቜ አቆመ። በስተ ቀኝ ያለውን ዓምድ አቁሞ ያኪን ብሎ ሰዚመውፀ ኚዚያም በስተ ግራ ያለውን ዓምድ አቁሞ ቩዔዝ ብሎ ሰዚመው።
ዚዓምዶቹም አናቶቜ ዚአበባ ቅርጜ ነበራ቞ው። በዚህ መንገድ ዚዓምዶቹ ሥራ ተጠናቀቀ።
ኚዚያም ባሕሩን በቀለጠ ብሚት ሠራ። ባሕሩ ክብ ቅርጜ ዚነበሚው ሲሆን ኚአንዱ ጠርዝ እስኚ ሌላኛው ጠርዝ 10 ክንድ፣ ኚፍታው ደግሞ 5 ክንድ ነበርፀ መጠነ ዙሪያውም በመለኪያ ገመድ ሲለካ 30 ክንድ ሆነ።
በባሕሩም ዙሪያ ኹጠርዙ ዝቅ ብሎ በእያንዳንዱ ክንድ ላይ በቅል ቅርጜ ዚተሠሩ አሥር ጌጊቜ ነበሩፀ ቅሎቹም በሁለት ሚድፍ ኚባሕሩ ጋር አንድ ወጥ ሆነው ተሠርተው ነበር።
ባሕሩ 3ቱ ወደ ሰሜን፣ 3ቱ ወደ ምዕራብ፣ 3ቱ ወደ ደቡብ እንዲሁም 3ቱ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ ፊታ቞ውን ባደሚጉ 12 በሬዎቜ ላይ ተቀምጩ ነበርፀ ባሕሩም ላያ቞ው ላይ ነበርፀ ዹሁሉም ሜንጥ ወደ መሃል ገባ ያለ ነበር።
ዹውኃ ማጠራቀሚያው ውፍሚት አንድ ጋት ነበርፀ ጠርዙ ዚጜዋ ኹንፈር ይመስል ዹነበሹ ሲሆን በአበባ ቅርጜ ዚተሠራ ነበር። ዹውኃ ማጠራቀሚያውም 2,000 ዚባዶስ መስፈሪያ ይይዝ ነበር።
ኚዚያም አሥር ዹዕቃ ማጓጓዣ ጋሪዎቜን ኚመዳብ ሠራ። እያንዳንዱ ጋሪ ርዝመቱ አራት ክንድ፣ ወርዱ አራት ክንድ፣ ቁመቱ ደግሞ ሊስት ክንድ ነበር።
ዚጋሪዎቹ አሠራር እንዲህ ነበር፩ ጋሪዎቹ ዹጎን መኚለያ ነበራ቞ውፀ ዹጎን መኚለያዎቹም በፍርግርግ መካኚል ነበሩ።
በፍርግርጎቹ መሃል በነበሩት ዹጎን መኚለያዎቜ ላይ ዚአንበሶቜ፣ ዚበሬዎቜና ዚኪሩቊቜ ምስል ነበርፀ በፍርግርጎቹም ላይ እንዲሁ ዓይነት ምስል ነበር። ኚአንበሶቹና ኚበሬዎቹ በላይና በታቜ፣ ዹተንጠለጠሉ ዚአበባ ጉንጉኖቜ ዚሚመስሉ ቅርጟቜ ነበሩ።
እያንዳንዱ ዹዕቃ ማጓጓዣ ጋሪ አራት ዚመዳብ መንኮራኩሮቜና ዚመዳብ ዘንጎቜ ነበሩትፀ በአራቱ ማዕዘኖቜ ላይ ያሉት ቋሚዎቜ ደግሞ ድጋፍ ይሆኗቾው ነበር። ድጋፎቹ ኚገንዳው በታቜ ነበሩፀ እያንዳንዳ቞ውም በጎናቾው ወጥ ሆኖ ዚተሠራ ዚአበባ ጉንጉን ዚሚመስል ቅርጜ ነበራ቞ው።
ዚገንዳው አፍ ያለው በጋሪው አናት ውስጥ ሲሆን አንድ ክንድ ኚፍታ ነበሚውፀ ዚጋሪው አፍ ክብ ነበርፀ በአፉ ላይ ያለው ማስቀመጫ አንድ ክንድ ተኩል ኚፍታ ነበሚውፀ በአፉም ላይ ዚተቀሚጹ ምስሎቜ ነበሩ። ዹጎን መኚለያዎቹም አራት ማዕዘን እንጂ ክብ አልነበሩም።
አራቱ መንኮራኩሮቜ ኹጎን መኚለያዎቹ በታቜ ነበሩፀ ዚመንኮራኩሮቹ ድጋፎቜ ኚጋሪው ጋር ተያይዘው ነበርፀ ዚእያንዳንዱ መንኮራኩር ቁመት አንድ ክንድ ተኩል ነበር።
ዚመንኮራኩሮቹ አሠራር ኹሠሹገላ መንኮራኩር አሠራር ጋር ተመሳሳይ ነበር። ዚመንኮራኩሮቹ ድጋፎቜ፣ ክፈፎቜ፣ ራጂዎቜና አቃፊዎቜ ሁሉ ኹቀለጠ ብሚት ዚተሠሩ ነበሩ።
በእያንዳንዱ ጋሪ አራት ማዕዘኖቜ ላይ አራት ድጋፎቜ ነበሩፀ ድጋፎቹም ዚጋሪው ክፍል ሆነው ዚተሠሩ ነበሩ።
በጋሪው አናት ላይ ቁመቱ ግማሜ ክንድ ዹሆነ ክብ ክፈፍ ነበርፀ እንዲሁም በጋሪው አናት ላይ ዚሚገኙት ፍርግርጎቜና ዹጎን መኚለያዎቜ ዚጋሪው ክፍል ሆነው ዚተሠሩ ነበሩ።
በፍርግርጎቹና በጎን መኚለያዎቹም ላይ እንደ ስፋታ቞ው ኪሩቊቜን፣ አንበሶቜንና ዚዘንባባ ዛፍ ምስሎቜን ቀሚጞባ቞ውፀ ዙሪያውንም ዚአበባ ጉንጉን ምስል ሠራበት።
አሥሩን ጋሪዎቜ ዚሠራው በዚህ መንገድ ነበርፀ ሁሉም አንድ ዓይነት መጠንና ቅርጜ እንዲኖራ቞ው ተደርገው በተመሳሳይ መንገድ ቀልጠው ዚተሠሩ ነበሩ።
እሱም አሥር ዚመዳብ ገንዳዎቜን ሠራፀ እያንዳንዱ ገንዳ 40 ዚባዶስ መስፈሪያ ይይዝ ነበር። እያንዳንዱ ገንዳ አራት ክንድ ነበር። በአሥሩም ጋሪዎቜ ላይ አንድ አንድ ገንዳ ነበር።
ኚዚያም አምስቱን ጋሪዎቜ ኚቀቱ በስተ ቀኝ በኩል አምስቱን ጋሪዎቜ ደግሞ ኚቀቱ በስተ ግራ በኩል አደሚጋ቞ውፀ ባሕሩንም ኚቀቱ በስተ ቀኝ በኩል፣ በስተ ደቡብ ምሥራቅ አቅጣጫ አስቀመጠው።
በተጚማሪም ኪራም ገንዳዎቹን፣ አካፋዎቹንና ጎድጓዳ ሳህኖቹን ሠራ። ኪራምም በይሖዋ ቀት ለንጉሥ ሰለሞን ያኚናውን ዹነበሹውን ሥራ ሁሉ ጚሚሰ። ዚሠራ቞ውም ነገሮቜ እነዚህ ነበሩፊ
ሁለቱ ዓምዶቜ፣ በሁለቱ ዓምዶቜ አናት ላይ ዚነበሩት ዚጎድጓዳ ሳህን ቅርጜ ያላ቞ው ዚዓምድ ራሶቜ፣ በዓምዶቹ አናት ላይ ዚነበሩትን ዚጎድጓዳ ሳህን ቅርጜ ያላ቞ውን ሁለቱን ክብ ዚዓምድ ራሶቜ ዚሚያስጌጡት ሁለት መሚቊቜ፣
ለሁለቱ መሚቊቜ ዚተሠሩት 400 ሮማኖቜ ማለትም በሁለቱ ዓምዶቜ አናት ላይ ዚነበሩትን ዚጎድጓዳ ሳህን ቅርጜ ያላ቞ው ዚዓምድ ራሶቜ ለማስጌጥ ዚተሠሩት በእያንዳንዱ መሚብ ላይ በሁለት ሚድፍ ዚተደሚደሩት ሮማኖቜ፣
አሥሩ ጋሪዎቜና በጋሪዎቹ ላይ ዚነበሩት አሥር ዹውኃ ገንዳዎቜ፣
ባሕሩና ኚሥሩ ዚነበሩት 12 በሬዎቜ፣
አመድ ማጠራቀሚያዎቹ፣ አካፋዎቹ፣ ጎድጓዳ ሳህኖቹና ኪራም ለይሖዋ ቀት እንዲሆኑ ለንጉሥ ሰለሞን ኹተወለወለ መዳብ ዚሠራ቞ው ዕቃዎቜ በሙሉ።
ንጉሡ እነዚህ ነገሮቜ በዮርዳኖስ አውራጃ በሱኮትና በጻሚታን መካኚል በሚገኝ ስፍራ ኹሾክላ በተሠሩ ቅርጜ ማውጫዎቜ ውስጥ ቀልጠው እንዲሠሩ አደሚገ።
ሰለሞን ዕቃዎቹ ሁሉ እንዲመዘኑ አላደሚገምፀ ምክንያቱም ዕቃዎቹ እጅግ ብዙ ነበሩ። ዚመዳቡ ክብደት ምን ያህል እንደሆነ አልታወቀም።
ሰለሞንም ለይሖዋ ቀት መገልገያ ዚሚሆኑትን ዚሚኚተሉትን ነገሮቜ ሠራፊ ዹወርቅ መሠዊያውን፣ ገጾ ኅብስት ዚሚቀመጥበትን ዹወርቅ ጠሚጎዛ፣
በውስጠኛው ክፍል ፊት በቀኝና በግራ ዚሚቀመጡትን ኚንጹሕ ወርቅ ዚተሠሩ አምስት አምስት መቅሚዞቜ፣ ኹወርቅ ዚተሠሩትን ዚፈኩ አበቊቜ፣ መብራቶቜና መቆንጠጫዎቜ፣
ኚንጹሕ ወርቅ ዚተሠሩትን ሳህኖቜ፣ ዚእሳት ማጥፊያዎቜ፣ ጎድጓዳ ሳህኖቜ፣ ጜዋዎቜና መኮስተሪያዎቜ እንዲሁም ኹወርቅ ዚተሠሩትን ዚውስጠኛው ክፍል ማለትም ዚቅድስተ ቅዱሳኑ በሮቜና ዚመቅደሱ በሮቜ ዚሚሜኚሚኚሩባ቞ውን መቆሚያዎቜ።
በዚህ ሁኔታ ንጉሥ ሰለሞን ኹይሖዋ ቀት ጋር በተያያዘ መሥራት ዚሚገባውን ሥራ በሙሉ አጠናቀቀ። ኚዚያም ሰለሞን አባቱ ዳዊት ዚቀደሳ቞ውን ነገሮቜ ወደዚያ አስገባፀ ብሩን፣ ወርቁንና ዕቃዎቹን በይሖዋ ቀት ግምጃ ቀቶቜ ውስጥ አስቀመጠ።
ኢዮርብዓም በመሠዊያው አጠገብ ዚሚጚስ መሥዋዕት ለማቅሚብ ቆሞ ሳለ አንድ ዹአምላክ ሰው በይሖዋ ቃል በታዘዘው መሠሚት ኚይሁዳ ወደ ቀ቎ል መጣ።
ኚዚያም በይሖዋ ቃል በታዘዘው መሠሚት መሠዊያውን በመቃወም እንዲህ ሲል ተጣራፊ “መሠዊያ ሆይ! መሠዊያ ሆይ! ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እነሆ፣ ኢዮስያስ ዚተባለ ልጅ ለዳዊት ቀት ይወለዳል! እሱም በአንተ ላይ ዚሚጚስ መሥዋዕት እያቀሚቡ ያሉትን ኹፍ ያሉ ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ካህናት በላይህ ይሠዋ቞ዋልፀ በአንተም ላይ ዚሰዎቜን አጥንት ያቃጥላል።’”
እሱም በዚያ ቀን እንዲህ በማለት ምልክት ሰጠ፩ “ይሖዋ ዹሰጠው ምልክት ይህ ነው፩ እነሆ፣ መሠዊያው ይሰነጠቃልፀ በላዩም ላይ ያለው አመድ ይፈስሳል።”