text
stringlengths
4
267
እንዲህም በሏቾው፩ ‘ንጉሡ “በሰላም ተመልሌ እስክመጣ ድሚስ ይህን ሰው እስር ቀት አቆዩትፀ ጥቂት ምግብና ውኃ ብቻ ስጡት” ብሏል።’”
ሚካያህ ግን “እውነት አንተ በሰላም ኚተመለስክ ይሖዋ በእኔ አልተናገሹም ማለት ነው!” አለ። ኚዚያም “እናንተ ሰዎቜ፣ ሁላቜሁም ልብ በሉ” አለ።
በመሆኑም ዚእስራኀል ንጉሥና ዚይሁዳ ንጉሥ ኢዮሳፍጥ ወደ ራሞትጊልያድ ወጡ።
ዚእስራኀልም ንጉሥ ኢዮሳፍጥን “እኔ ማንነቮ እንዳይታወቅ ራሎን ለውጬ ወደ ውጊያው እገባለሁፀ አንተ ግን ንጉሣዊ ልብስህን ልበስ” አለው። ስለዚህ ዚእስራኀል ንጉሥ ማንነቱ እንዳይታወቅ ራሱን ለውጩ ወደ ውጊያው ገባ።
በዚህ ጊዜ ዚሶርያ ንጉሥ 32ቱን ዹሠሹገላ አዛዊቜ “ኚእስራኀል ንጉሥ በስተቀር ኚትንሹም ሆነ ኚትልቁ፣ ኹማንም ጋር እንዳትዋጉ” በማለት አዟቾው ነበር።
ዚሠሚገሎቹ አዛዊቜም ኢዮሳፍጥን ባዩት ጊዜ “ያለጥርጥር ይህ ዚእስራኀል ንጉሥ ነው” ብለው አሰቡ። በመሆኑም ሊወጉት ወደ እሱ ዞሩፀ በዚህ ጊዜ ኢዮሳፍጥ እርዳታ ለማግኘት ጮኞ።
ዚሠሚገሎቹ አዛዊቜም ዚእስራኀል ንጉሥ አለመሆኑን ሲያዩ ወዲያውኑ እሱን ማሳደዳ቞ውን ትተው ተመለሱ።
ይሁንና አንድ ሰው በነሲብ ቀስቱን ሲያስወነጭፍ ዚእስራኀልን ንጉሥ ዚጥሩሩ መጋጠሚያ ላይ ወጋው። ስለሆነም ንጉሡ ሠሹገላ ነጂውን “ክፉኛ ስለቆሰልኩ ሠሹገላውን አዙሹህ ኚጊርነቱ ይዘኾኝ ውጣ” አለው።
ያን ቀን ሙሉ ዹተፋፋመ ውጊያ ተካሄደፀ ንጉሡንም ሠሹገላው ውስጥ እንዳለ ፊቱን ወደ ሶርያውያን አዙሹው ደግፈው አቆሙት። ኚቁስሉ ዚሚወጣውም ደም በጩር ሠሹገላው ውስጥ ይፈስ ነበርፀ አመሻሹም ላይ ሞተ።
ፀሐይ ልትጠልቅም ስትል በሰፈሩ መካኚል “እያንዳንዱ ሰው ወደ ኚተማው፣ እያንዳንዱም ሰው ወደ ምድሩ ይመለስ!” ዹሚል ጥሪ አስተጋባ።
በዚህ መንገድ ንጉሡ ሞተፀ ወደ ሰማርያም ተወሰደፀ ንጉሡንም በሰማርያ ቀበሩት።
እነሱም ዹጩር ሠሹገላውን በሰማርያ ኩሬ ባጠቡት ጊዜ ይሖዋ በተናገሹው መሠሚት ውሟቜ ደሙን ላሱትፀ ዝሙት አዳሪዎቜም በዚያ ገላቾውን እዚታጠቡ ነበር።
ስለቀሚው ዚአክዓብ ታሪክ፣ ስላደሚጋ቞ው ነገሮቜ ሁሉ፣ በዝሆን ጥርስ ስለሠራው ቀትና ስለገነባ቞ው ኚተሞቜ ሁሉ በእስራኀል ነገሥታት ዘመን ስለተፈጞሙት ነገሮቜ በሚተርኹው ዚታሪክ መጜሐፍ ውስጥ ተጜፎ ይገኝ ዹለም?
በመጚሚሻም አክዓብ ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ በእሱም ምትክ ልጁ አካዝያስ ነገሠ።
ዚእስራኀል ንጉሥ አክዓብ በነገሠ በአራተኛው ዓመት ዚአሳ ልጅ ኢዮሳፍጥ በይሁዳ ላይ ነገሠ።
ኢዮሳፍጥ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 35 ዓመት ዹነበሹ ሲሆን በኢዚሩሳሌም 25 ዓመት ገዛ። እናቱ ዚሺልሂ ልጅ አዙባ ነበሚቜ።
እሱም በአባቱ በአሳ መንገድ ሁሉ ሄደ። ኚዚያ ፈቀቅ አላለምፀ በይሖዋም ፊት ትክክል ዹሆነውን ነገር አደሚገ። ይሁን እንጂ ኹፍ ያሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ አልተወገዱም ነበርፀ ሕዝቡም ኹፍ ባሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ላይ መሠዋቱንና ዚሚጚስ መሥዋዕት ማቅሚቡን አልተወም ነበር።
ኢዮሳፍጥ ኚእስራኀል ንጉሥ ጋር ሰላማዊ ግንኙነት ነበሚው።
ዹቀሹው ዚኢዮሳፍጥ ታሪክ፣ በኃያልነቱ ዹፈጾማቾው ጀብዱዎቜና ያደሚጋ቞ው ውጊያዎቜ በይሁዳ ነገሥታት ዘመን ስለተፈጞሙት ነገሮቜ በሚተርኹው ዚታሪክ መጜሐፍ ውስጥ ተጜፈው ይገኙ ዹለም?
ኢዮሳፍጥ ኚአባቱ ኚአሳ ዘመን ዚተሚፉትን ዚቀተ መቅደስ ቀላጮቜ ኚምድሪቱ ላይ አስወግዶ ነበር።
በዚያ ዘመን በኀዶም ንጉሥ አልነበሚምፀ እንደ ንጉሥ ሆኖ ዹሚገዛው አስተዳዳሪው ነበር።
በተጚማሪም ኢዮሳፍጥ ወርቅ ለማምጣት ወደ ኩፊር ዚሚሄዱ ዚተርሎስ መርኚቊቜ ሠርቶ ነበርፀ ሆኖም መርኚቊቹ በዔጜዮንጋብር ስለተሰበሩ ወደዚያ አልሄዱም።
ዚአክዓብ ልጅ አካዝያስ ኢዮሳፍጥን “አገልጋዮቌ ኚአገልጋዮቜህ ጋር በመርኚቊቹ ይሂዱ” ያለው በዚህ ጊዜ ነበርፀ ኢዮሳፍጥ ግን በዚህ አልተስማማም።
በመጚሚሻም ኢዮሳፍጥ ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ በአባቱ በዳዊት ኹተማም ኚአባቶቹ ጋር ተቀበሚፀ በእሱም ምትክ ልጁ ኢዮራም ነገሠ።
ዚይሁዳ ንጉሥ ኢዮሳፍጥ በነገሠ በ17ኛው ዓመት ዚአክዓብ ልጅ አካዝያስ በሰማርያ ሆኖ በእስራኀል ላይ ነገሠፀ በእስራኀልም ላይ ሁለት ዓመት ገዛ።
እሱም በይሖዋ ፊት መጥፎ ዹሆነውን ነገር ማድሚጉን ቀጠለፀ በአባቱና በእናቱ መንገድ እንዲሁም እስራኀላውያን ኃጢአት እንዲፈጜሙ ባደሚጋ቞ው በናባጥ ልጅ በኢዮርብዓም መንገድ ሄደ።
ባአልን ማገልገሉንና ለእሱ መስገዱን ቀጠለፀ አባቱም እንዳደሚገው ሁሉ ዚእስራኀልን አምላክ ይሖዋን አስቆጣ።
ዚናባጥ ልጅ ንጉሥ ኢዮርብዓም በነገሠ በ18ኛው ዓመት አብያም በይሁዳ ላይ ነገሠ።
እሱም በኢዚሩሳሌም ለሊስት ዓመት ገዛ። ዚእናቱ ስም ማአካ ሲሆን እሷም ዚአቢሎሎም ዹልጅ ልጅ ነበሚቜ።
እሱም አባቱ ኚእሱ በፊት በሠራው ኃጢአት ሁሉ መመላለሱን ቀጠለፀ ልቡ እንደቀድሞ አባቱ እንደ ዳዊት ልብ በአምላኩ በይሖዋ ዘንድ ሙሉ አልነበሚም።
ሆኖም በዳዊት ዚተነሳ አምላኩ ይሖዋ ኚእሱ በኋላ ልጁን በማስነሳትና ኢዚሩሳሌም ጞንታ እንድትኖር በማድሚግ በኢዚሩሳሌም መብራት ሰጠው።
ምክንያቱም ዳዊት በይሖዋ ፊት ትክክል ዹሆነውን ነገር አድርጓልፀ እንዲሁም ኚሂታዊው ኚኊርዮ ጋር በተያያዘ ኹፈጾመው ነገር በስተቀር በሕይወት ዘመኑ ሁሉ እሱ ኹሰጠው ኚዚትኛውም ትእዛዝ ፈቀቅ አላለም።
በሕይወት ዘመኑ ሁሉ በሮብዓምና በኢዮርብዓም መካኚል ጊርነት ነበር።
ዹቀሹው ዚአብያም ታሪክ፣ ያደሚጋ቞ው ነገሮቜ በሙሉ በይሁዳ ነገሥታት ዘመን ስለተፈጞሙት ነገሮቜ በሚተርኹው ዚታሪክ መጜሐፍ ውስጥ ተጜፈው ይገኙ ዹለም? በአብያምና በኢዮርብዓም መካኚልም ጊርነት ነበር።
በመጚሚሻም አብያም ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ በዳዊት ኹተማም ቀበሩትፀ በእሱም ምትክ ልጁ አሳ ነገሠ።
ዚእስራኀል ንጉሥ ኢዮርብዓም በነገሠ በ20ኛው ዓመት አሳ በይሁዳ ላይ መግዛት ጀመሚ።
እሱም በኢዚሩሳሌም ለ41 ዓመት ገዛ። ዚአያቱም ስም ማአካ ሲሆን እሷም ዚአቢሎሎም ዹልጅ ልጅ ነበሚቜ።
አሳ እንደ አባቱ እንደ ዳዊት በይሖዋ ፊት ትክክል ዹሆነውን ነገር አደሚገ።
እሱም ዚቀተ መቅደስ ቀላጮቜን ኚምድሪቱ አባሚሚፀ እንዲሁም አባቶቹ ዚሠሯ቞ውን አስጞያፊ ጣዖቶቜ በሙሉ አስወገደ።
ሌላው ቀርቶ አያቱ ማአካ ለማምለኪያ ግንዱ አምልኮ ጞያፍ ጣዖት ሠርታ ስለነበር ኚእመቀትነቷ ሻራት። አሳ፣ አያቱ ዚሠራቜውን ጞያፍ ጣዖት ቆርጩ በቄድሮን ሾለቆ አቃጠለው።
ኹፍ ያሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ግን አልተወገዱም ነበር። ያም ሆኖ አሳ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ልቡ በይሖዋ ዘንድ ሙሉ ነበር።
እሱና አባቱ ዚቀደሷ቞ውን ነገሮቜ ይኾውም ብሩን፣ ወርቁንና ልዩ ልዩ ዕቃዎቜን ወደ ይሖዋ ቀት አስገባ።
በአሳና ዚእስራኀል ንጉሥ በሆነው በባኊስ መካኚል ዚማያቋርጥ ጊርነት ነበር።
በመሆኑም ዚእስራኀል ንጉሥ ባኊስ በይሁዳ ላይ ዘመተፀ እሱም ማንም ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ አሳ እንዳይገባና እንዳይወጣ ለማድሚግ ራማን መገንባት ጀመሚ።
በዚህ ጊዜ አሳ በይሖዋ ቀት ግምጃ ቀትና በንጉሡ ቀት ግምጃ ቀት ዹቀሹውን ብርና ወርቅ ሁሉ አውጥቶ ለአገልጋዮቹ ሰጣ቞ው። ኚዚያም ንጉሥ አሳ እነዚህን አገልጋዮቹን በደማስቆ ወደሚገኘው ዚሶርያ ንጉሥ ማለትም ዚሄዝዮን ልጅ፣ ዚታብሪሞን ልጅ ወደሆነው ወደ ቀንሃዳድ እንዲህ ሲል ላካ቞ውፊ
“በእኔና በአንተ እንዲሁም በአባ቎ና በአባትህ መካኚል ውል አለ። እኔ ዚብርና ዹወርቅ ስጊታ ልኬልሃለሁ። ስለዚህ ና፣ ዚእስራኀል ንጉሥ ባኊስ ኚእኔ እንዲርቅ ኚእሱ ጋር ዚገባኞውን ውል አፍርስ።”
ቀንሃዳድ ዚንጉሥ አሳን ሐሳብ ተቀብሎ ዹጩር ሠራዊቱን አለቆቜ በእስራኀል ኚተሞቜ ላይ አዘመተፀ እነሱም ኢዮንን፣ ዳንን፣ አቀልቀትማዓካን እንዲሁም ኪኔሬትን ሁሉና መላውን ዚንፍታሌም ምድር መቱ።
ባኊስም ይህን ሲሰማ ወዲያውኑ ራማን መገንባቱን አቁሞ በቲርጻ መኖሩን ቀጠለ።
ኚዚያም ንጉሥ አሳ ማንንም ሳያስቀር ዚይሁዳን ሰዎቜ ሁሉ ሰበሰበፀ እነሱም ባኊስ እዚገነባባ቞ው ዚነበሩትን ዚራማን ድንጋዮቜና ሳንቃዎቜ አጋዙፀ ንጉሥ አሳም በድንጋዮቹና በሳንቃዎቹ በቢንያም ዚምትገኘውን ጌባንና ምጜጳን ገነባ።
ዹቀሹው ዚአሳ ታሪክ ሁሉ፣ ኃያልነቱ ሁሉ፣ ያደሚጋ቞ው ነገሮቜ በሙሉና ዚገነባ቞ው ኚተሞቜ በይሁዳ ነገሥታት ዘመን ስለተፈጞሙት ነገሮቜ በሚተርኹው ዚታሪክ መጜሐፍ ውስጥ ተጜፈው ይገኙ ዹለም? ሆኖም አሳ ባሚጀ ጊዜ በእግር ሕመም ይሠቃይ ነበር።
በመጚሚሻም አሳ ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ በአባቱ በዳዊት ኹተማም ኚእነሱ ጋር ተቀበሚፀ በእሱም ምትክ ልጁ ኢዮሳፍጥ ነገሠ።
ዚይሁዳ ንጉሥ አሳ በነገሠ በሁለተኛው ዓመት ዚኢዮርብዓም ልጅ ናዳብ ዚእስራኀል ንጉሥ ሆነፀ እሱም በእስራኀል ላይ ለሁለት ዓመት ገዛ።
በይሖዋም ፊት መጥፎ ዹሆነውን ነገር ማድሚጉን ገፋበትፀ ዚአባቱንም መንገድ ተኚተለፀ እንዲሁም አባቱ እስራኀላውያን እንዲፈጜሙ ባደሚገው ኃጢአት ተመላለሰ።
ኚይሳኮር ቀት ዹሆነው ዚአኪያህ ልጅ ባኊስ በእሱ ላይ አሎሚፀ ናዳብና እስራኀል ሁሉ ዚፍልስጀማውያን ኹተማ ዚሆነቜውን ጊበቶንን ኹበው ሳሉ ባኊስ ጊበቶን ላይ ናዳብን ገደለው።
በመሆኑም ባኊስ ዚይሁዳ ንጉሥ አሳ በነገሠ በሊስተኛው ዓመት ናዳብን ገድሎ በምትኩ ነገሠ።
እሱም እንደነገሠ ወዲያውኑ ዚኢዮርብዓምን ቀት ሁሉ ፈጀ። ኚኢዮርብዓም ቀት እስትንፋስ ያለውን አንድም ሰው አላስቀሚምፀ ይሖዋ በአገልጋዩ በሮሎናዊው በአኪያህ በኩል በተናገሹው መሠሚት ሁሉንም ደመሰሳ቞ው።
ይህም ዹሆነው ኢዮርብዓም በፈጾመው ኃጢአትና እስራኀላውያን እንዲፈጜሙ ባደሚገው ኃጢአት ዚእስራኀልን አምላክ ይሖዋን ክፉኛ ስላስቆጣው ነው።
ዹቀሹው ዚናዳብ ታሪክና ያደሚጋ቞ው ነገሮቜ በሙሉ በእስራኀል ነገሥታት ዘመን ስለተፈጞሙት ነገሮቜ በሚተርኹው ዚታሪክ መጜሐፍ ውስጥ ተጜፈው ይገኙ ዹለም?
በአሳና ዚእስራኀል ንጉሥ በሆነው በባኊስ መካኚል ዚማያቋርጥ ጊርነት ነበር።
ዚይሁዳ ንጉሥ አሳ በነገሠ በሊስተኛው ዓመት ዚአኪያህ ልጅ ባኊስ በቲርጻ ሆኖ በመላው እስራኀል ላይ ለ24 ዓመት ገዛ።
ሆኖም በይሖዋ ፊት መጥፎ ዹሆነውን ነገር ማድሚጉን ገፋበትፀ ዚኢዮርብዓምን መንገድ ተኚተለፀ እንዲሁም ኢዮርብዓም እስራኀላውያን እንዲፈጜሙ ባደሚገው ኃጢአት ተመላለሰ።
ንጉሥ ሰለሞን መላውን እስራኀል ይገዛ ነበር።
ኹፍተኛ ባለሥልጣናቱ እነዚህ ነበሩፊ ዚሳዶቅ ልጅ አዛርያስ ካህን ነበርፀ
ዚሺሻ ልጆቜ ኀሌሆሬፍና አኪያህ ጞሐፊዎቜ ነበሩፀ ዚአሂሉድ ልጅ ኢዮሳፍጥ ታሪክ ጾሐፊ ነበርፀ
ዚዮዳሄ ልጅ በናያህ ዚሠራዊቱ አዛዥ ነበርፀ ሳዶቅና አብያታር ካህናት ነበሩፀ
ዚናታን ልጅ አዛርያስ ዚአስተዳዳሪዎቹ ኃላፊ ነበርፀ ዚናታን ልጅ ዛቡድ ካህንና ዚንጉሡ ወዳጅ ነበርፀ
አሂሻር ዚቀቱ አዛዥ ነበርፀ ዚአብዳ ልጅ አዶኒራም ዚግዳጅ ሥራ እንዲሠሩ በተመለመሉት ላይ አዛዥ ነበር።
ሰለሞን በመላው እስራኀል ላይ ዚተሟሙ ለንጉሡና ለቀተሰቡ ቀለብ ዚሚያቀርቡ 12 አስተዳዳሪዎቜ ነበሩት። እያንዳንዳ቞ውም በዓመት ውስጥ ለአንድ ወር ቀለብ ዚማቅሚብ ኃላፊነት ተጥሎባ቞ው ነበር።
ስማ቞ውም ዹሚኹተለው ነው፩ በኀፍሬም ተራራማ አካባቢ ዹሁር ልጅ፣
በማቃጜ፣ በሻአልቢም፣ በቀትሌሜሜ እና በኀሎንቀትሃናን ዹዮቀር ልጅ፣
በአሩቊት ዚሄሎድ ልጅ (ሶኮህ እና ዹሄፌር ምድር በሙሉ በሥሩ ነበሩ)፣
በዶር ሾንተሹር በሙሉ ዚአቢናዳብ ልጅ (እሱም ዹሰለሞንን ልጅ ጣፋትን አግብቶ ነበር)፣
በታአናክ እና በመጊዶ እንዲሁም ኚኢይዝራኀል በታቜ ኚጞሚታን አጠገብ በሚገኘው በቀትሌን በሙሉና ኚቀትሌን አንስቶ በዮቅመአም እስኚሚገኘው እስኚ አቀልምሆላ ድሚስ ዚአሂሉድ ልጅ ባአና፣
በራሞትጊልያድ ዚጌቀር ልጅ (በጊልያድ ዚሚገኙት ዹምናሮ ልጅ ዚያኢር ዚድንኳን ሰፈሮቜ በእሱ ሥር ነበሩፀ እንዲሁም በባሳን ዹሚገኘው ዚአርጎብ ክልል ይኾውም በቅጥር ዚታጠሩና ዚመዳብ መቀርቀሪያ ያላ቞ው 60 ትላልቅ ኚተሞቜ በእሱ ሥር ነበሩ)፣
በማሃናይም ዚኢዶ ልጅ አሂናዳብ፣
በንፍታሌም አኪማዓስ (እሱም ሌላኛዋን ዹሰለሞንን ልጅ፣ ባሎማትን አግብቶ ነበር)፣
በአሮርና በበዓሎት ዚኩሲ ልጅ ባአና፣
በይሳኮር ዚፓሩህ ልጅ ኢዮሳፍጥ፣
በቢንያም ዚኀላ ልጅ ሺምአይ
እንዲሁም ዚአሞራውያን ንጉሥ ዚሲሖን እና ዚባሳን ንጉሥ ዹኩግ ምድር በሆነው በጊልያድ ምድር ዚዖሪ ልጅ ጌቀር። በተጚማሪም በምድሪቱ አስተዳዳሪዎቜ ሁሉ ላይ ዚተሟመ አንድ አስተዳዳሪ ነበር።
ይሁዳና እስራኀል ኚብዛታ቞ው ዚተነሳ እንደ ባሕር አሾዋ ነበሩፀ እነሱም ይበሉና ይጠጡ እንዲሁም ይደሰቱ ነበር።
ሰለሞን ኹወንዙ አንስቶ እስኚ ፍልስጀማውያን ምድርና እስኚ ግብፅ ወሰን ድሚስ ባሉት መንግሥታት ሁሉ ላይ ገዛ። እነሱም በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ግብር ያመጡለት እንዲሁም ያገለግሉት ነበር።
ሰለሞን በዹቀኑ ዚሚገባለት ቀለብ ይህ ነበር፩ 30 ዚቆሮስ መስፈሪያ ዹላመ ዱቄት፣ 60 ዚቆሮስ መስፈሪያ ዱቄት
እንዲሁም 10 ቅልብ ኚብቶቜ፣ ኚግጊሜ ዚመጡ 20 ኚብቶቜ፣ 100 በጎቜና ዹተወሰኑ ዚርኀም ዝርያዎቜ፣ ዚሜዳ ፍዚሎቜና ዚሰቡ ወፎቜ።
እሱም ኹወንዙ ወዲህ ያሉትን ነገሥታት ሁሉ ጚምሮ ኚቲፍሳ አንስቶ እስኚ ጋዛ ድሚስ ዚሚገኙትን ኹወንዙ ወዲህ ያሉትን አካባቢዎቜ በሙሉ ተቆጣጥሮ ነበርፀ በዙሪያው ባለው አካባቢ ሁሉ ሰላም ሰፍኖለት ነበር።
በሰለሞን ዘመን ኚዳን አንስቶ እስኚ ቀርሳቀህ ድሚስ በይሁዳና በእስራኀል ዹሚገኝ እያንዳንዱ ሰው ኹገዛ ወይኑና ኚበለስ ዛፉ ሥር ያለስጋት ይኖር ነበር።
ሰለሞን ሠሚገሎቹን ለሚጎትቱት ፈሚሶቜ ዹሚሆኑ 4,000 ጋጣዎቜና 12,000 ፈሚሶቜ ነበሩት።
እነዚህ አስተዳዳሪዎቜ ለንጉሥ ሰለሞንና ኚንጉሥ ሰለሞን ማዕድ ለሚመገቡት ሁሉ ቀለብ ያቀርቡ ነበር። እያንዳንዳ቞ውም በተመደበላቾው ወር ዚሚጠበቅባ቞ውን ያቀርቡ ዹነበሹ ሲሆን ምንም ነገር እንዳይጓደል ጥንቃቄ ያደርጉ ነበር።
እንዲሁም እያንዳንዳ቞ው በተመደበላቾው ድርሻ መሠሚት ለፈሚሶቹና ለሰንጋ ፈሚሶቹ ዹሚሆነውን ገብስና ገለባ ወደተፈለገው ቊታ ያመጡ ነበር።
አምላክም ለሰለሞን እጅግ ታላቅ ጥበብና ማስተዋል እንዲሁም በባሕር ዳርቻ ላይ እንዳለ አሞዋ፣ ሰፊ ልብ ሰጠው።
ዹሰለሞን ጥበብ ኚምሥራቅ ሰዎቜ ሁሉ ጥበብና ኚግብፅ ሁሉ ጥበብ ዹላቀ ነበር።
እሱም ኹማንኛውም ሰው ይልቅ ጥበበኛ ነበርፀ ኚዛራዊው ኚኀታን እንዲሁም ዹማሆል ልጆቜ ኚሆኑት ኚሄማን፣ ኚካልኮል እና ኚዳርዳ ይልቅ ጥበበኛ ነበርፀ ዝናውም በዙሪያው ባሉት ብሔራት ሁሉ ዘንድ ተሰማ።
እሱም 3,000 ምሳሌዎቜን አቀናበሚፀ ዚመዝሙሮቹም ብዛት 1,005 ነበር።
በሊባኖስ ኹሚገኘው አርዘ ሊባኖስ አንስቶ በቅጥር ላይ እስኚሚበቅለው ሂሶጵ ድሚስ ስለ ዛፎቜ ተናግሯልፀ እንዲሁም ስለ እንስሳት፣ ስለ አእዋፍ፣ መሬት ለመሬት ስለሚሄዱ ፍጥሚታትና ስለ ዓሣዎቜ ተናግሯል።
ስለ እሱ ጥበብ ሲወራ ዹሰሙ በተለያዚ ዚምድር ክፍል ዹሚገኙ ነገሥታትን ጚምሮ ኚልዩ ልዩ ብሔራት፣ ሰዎቜ ዹሰለሞንን ጥበብ ለመስማት ይመጡ ነበር።
በዚህ ጊዜ ዚሶርያ ንጉሥ ቀንሃዳድ ጩር ሠራዊቱን በሙሉ አሰባሰበፀ በተጚማሪም ሌሎቜ 32 ነገሥታትን ኚነፈሚሶቻ቞ውና ኚነሠሚገሎቻ቞ው አሰባሰበፀ ወጥቶም ሰማርያን በመክበብ ውጊያ ኚፈተባት።
ኚዚያም በኹተማዋ ውስጥ ወደሚገኘው ወደ እስራኀል ንጉሥ ወደ አክዓብ መልእክተኞቜ ልኮ እንዲህ አለው፩ “ቀንሃዳድ እንዲህ ይላል፩
‘ብርህና ወርቅህ እንዲሁም ኚሚስቶቜህና ኚልጆቜህ መካኚል ምርጥ ዚሆኑት ዚእኔ ና቞ው።’”
በዚህ ጊዜ ዚእስራኀል ንጉሥ “ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፣ አንተ እንዳልኚው እኔም ሆንኩ ዚእኔ ዹሆነው ሁሉ ዹአንተ ነን” ሲል መለሰለት።
በኋላም መልእክተኞቹ ተመልሰው በመምጣት እንዲህ አሉትፊ “ቀንሃዳድ እንዲህ ይላል፩ ‘እንዲህ ዹሚል መልእክት ልኬብህ ነበር፩ “ብርህን፣ ወርቅህን፣ ሚስቶቜህንና ልጆቜህን ትሰጠኛለህ።”