text
stringlengths
4
267
“በአንተ ላይ ኃጢአት ቢሠሩ (መቌም ኃጢአት ዚማይሠራ ሰው ዹለም)፣ አንተም በእነሱ እጅግ ተቆጥተህ ለጠላት አሳልፈህ ብትሰጣ቞ው፣ ጠላቶቻ቞ውም ራቅ ወዳለ ወይም ቅርብ ወደሆነ ዚጠላት ምድር ምርኮኛ አድርገው ቢወስዷ቞ው
እነሱም በምርኮ በተወሰዱበት ምድር ወደ ልቩናቾው ቢመለሱና ወደ አንተ ዞር በማለት ‘ኃጢአት ሠርተናልፀ አጥፍተናልፀ ክፉ ድርጊትም ፈጜመናል’ በማለት በተማሚኩበት ምድር ሆነው ሞገስ ለማግኘት ወደ አንተ ልመና ቢያቀርቡ፣
ማርኹው በወሰዷ቞ው ጠላቶቻ቞ውም ምድር ሆነው በሙሉ ልባ቞ውና በሙሉ ነፍሳ቞ው ወደ አንተ ቢመለሱ እንዲሁም ለአባቶቻ቞ው በሰጠሃቾው ምድር፣ አንተ በመሚጥካት ኹተማና ለስምህ በሠራሁት ቀት አቅጣጫ ወደ አንተ ቢጞልዩ
ጞሎታ቞ውንና ሞገስ ለማግኘት ያቀሚቡትን ልመና ኚመኖሪያ ቊታህ ኚሰማያት ሆነህ ስማፀ ፍሚድላ቞ውምፀ
በአንተ ላይ ዚፈጞሙትን በደል ሁሉ ይቅር በማለት በአንተ ላይ ኃጢአት ዚሠራውን ሕዝብህን ይቅር በል። ዚማሚኳ቞ውም ሰዎቜ እንዲያዝኑላ቞ው ታደርጋለህፀ እነሱም ያዝኑላ቞ዋል
(ምክንያቱም እነሱ እንደ ብሚት ማቅለጫ ኚሆነቜው ኚግብፅ ያወጣሃ቞ው ሕዝቊቜህና ርስትህ ናቾው)።
አገልጋይህም ሆነ ሕዝብህ እስራኀል ወደ አንተ በሚጮኹበት ጊዜ ሁሉ ስማ቞ውፀ ሞገስ ለማግኘት ዚሚያቀርቡትንም ልመና ዓይኖቜህ ይመልኚቱ።
ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ ሆይ፣ አባቶቻቜንን ኚግብፅ ባወጣሃ቞ው ጊዜ በአገልጋይህ በሙሮ በኩል በተናገርኹው መሠሚት ኚምድር ሕዝቊቜ ሁሉ መካኚል ርስትህ አድርገህ ለይተሃ቞ዋልና።”
ሰለሞንም ይህን ሁሉ ጞሎትና ልመና ወደ ይሖዋ አቅርቩ እንደጚሚሰ እጆቹን ወደ ሰማይ ዘርግቶ ኚተንበሚኚኚበት ኹይሖዋ መሠዊያ ፊት ተነሳ።
ኚዚያም ቆሞ ዚእስራኀልን ጉባኀ በሙሉ ጮክ ብሎ እንዲህ ሲል ባሚኚፊ
“በገባው ቃል መሠሚት ለሕዝቡ ለእስራኀል ዚእሚፍት ቊታ ዹሰጠው ይሖዋ ይወደስ። በአገልጋዩ በሙሮ አማካኝነት ኹሰጠው መልካም ተስፋ ሁሉ መካኚል ሳይፈጞም ዹቀሹ አንድም ቃል ዚለም።
አምላካቜን ይሖዋ ኚአባቶቻቜን ጋር እንደነበሚ ሁሉ ኚእኛም ጋር ይሁን። አይተወንፀ ደግሞም አይጣለን።
በመንገዱ ሁሉ እንድንሄድ እንዲሁም አባቶቻቜን እንዲጠብቁ ያዘዛ቞ውን ትእዛዛቱን፣ ሥርዓቱንና ድንጋጌዎቹን እንድንጠብቅ ልባቜንን ወደ እሱ ያዘንብል።
ሞገስ ለማግኘት ወደ ይሖዋ ያቀሚብኩት ይህ ልመና በአምላካቜን በይሖዋ ፊት ቀንና ሌሊት ይታወስፀ ለአገልጋዩና ለሕዝቡ ለእስራኀልም በዚዕለቱ ዚሚያስፈልገውን ፍርድ ይፍሚድላ቞ውፀ
ይህም ዚምድር ሕዝቊቜ ሁሉ እውነተኛው አምላክ ይሖዋ መሆኑን እንዲያውቁ ነው። ኚእሱ ሌላ ማንም ዹለም!
በመሆኑም እንደ ዛሬው ዕለት ሁሉ በአምላካቜን በይሖዋ ሥርዓቶቜ በመሄድና ትእዛዛቱን በመጠበቅ ልባቜሁ በእሱ ዘንድ ሙሉ ይሁን።”
ኚዚያም ንጉሡና ኚእሱ ጋር ዚነበሩት እስራኀላውያን በሙሉ በይሖዋ ፊት ታላቅ መሥዋዕት አቀሚቡ።
ሰለሞን 22,000 ኚብቶቜና 120,000 በጎቜ ለይሖዋ ዚኅብሚት መሥዋዕት አድርጎ አቀሚበ። በዚህ መንገድ ንጉሡና እስራኀላውያን በሙሉ ዹይሖዋን ቀት መሚቁ።
ንጉሡም በዚያ ቀን በይሖዋ ቀት ፊት ዹሚገኘውን ዚግቢውን መሃል መቀደስ አስፈልጎት ነበርፀ ምክንያቱም ዚሚቃጠሉትን መሥዋዕቶቜ፣ ዚእህል መባዎቹንና ዚኅብሚት መሥዋዕቶቹን በዚያ ማቅሚብ ነበሚበትፀ ይህም ዹሆነው በይሖዋ ፊት ያለው ዚመዳብ መሠዊያ ዚሚቃጠሉትን መሥዋዕቶቜ፣ ዚእህል መባዎቹንና ዚኅብሚት መሥዋዕቶቹን ስብ መያዝ ስላልቻለ ነው።
በዚያ ጊዜ ሰለሞን ኹመላው እስራኀል ጋር ይኾውም ኚሌቊሃማት አንስቶ እስኚ ግብፅ ደሹቅ ወንዝ ድሚስ ካለው ምድር ኚመጣው ታላቅ ጉባኀ ጋር በመሆን በአምላካቜን በይሖዋ ፊት ለ7 ቀን፣ ኚዚያም ለተጚማሪ 7 ቀን በአጠቃላይ ለ14 ቀን በዓሉን አኚበሚ።
በቀጣዩም ቀን ሕዝቡን አሰናበተፀ እነሱም ንጉሡን ባሚኩፀ ይሖዋ ለአገልጋዩ ለዳዊትና ለሕዝቡ ለእስራኀል ባሳዚው ጥሩነት ሁሉ እዚተደሰቱና ኚልባ቞ው እዚፈነደቁ ወደዚቀታ቞ው ሄዱ።
ዚይሁዳ ንጉሥ አካዝ በነገሠ በ12ኛው ዓመት ዚኀላህ ልጅ ሆሺአ በሰማርያ ሆኖ በእስራኀል ላይ ነገሠፀ እሱም ለዘጠኝ ዓመት ገዛ።
ኚእሱ በፊት ዚነበሩትን ዚእስራኀል ነገሥታት ያህል አይሁን እንጂ በይሖዋ ፊት መጥፎ ዹሆነውን ነገር አደሚገ።
ዹአሩር ንጉሥ ሰልምናሶር በእሱ ላይ መጣፀ ሆሺአም አገልጋዩ ሆነፀ ገበሚለትም።
ሆኖም ዹአሩር ንጉሥ ሰልምናሶር ሆሺአ እንዳሎሚበት አወቀፀ ምክንያቱም ሆሺአ ወደ ግብፅ ንጉሥ ወደ ሶህ መልእክተኞቜ ልኮ ነበርፀ ደግሞም ቀደም ባሉት ዓመታት ያደርግ እንደነበሚው ለአሩር ንጉሥ መገበሩን አቁሞ ነበር። ስለሆነም ዹአሩር ንጉሥ እስር ቀት ውስጥ አስሮ አስቀመጠው።
ዹአሩር ንጉሥ መላ አገሪቱን ወሚሚፀ ወደ ሰማርያም መጥቶ ኹተማዋን ለሊስት ዓመት ኚበባት።
ሆሺአ በነገሠ በዘጠነኛው ዓመት ዹአሩር ንጉሥ ሰማርያን ያዘ። ኚዚያም ዚእስራኀልን ሕዝብ ወደ አሩር በግዞት በመውሰድ በሃላህ፣ በጎዛን ወንዝ አጠገብ በምትገኘው በሃቩርና በሜዶናውያን ኚተሞቜ አሰፈራ቞ው።
ይህ ዹሆነው ዚእስራኀል ሰዎቜ ኚግብፅ ንጉሥ ኹፈርዖን ቀንበርና ኚግብፅ ምድር ነፃ ባወጣ቞ው በአምላካ቞ው በይሖዋ ላይ ኃጢአት ስለሠሩ ነው። እነሱም ሌሎቜ አማልክትን አመለኩፀ
ይሖዋ ኚእስራኀላውያን ፊት ያባሚራ቞ውን ብሔራት ልማዶቜ ተኚተሉፀ ደግሞም ዚእስራኀል ነገሥታት ያቋቋሟ቞ውን ልማዶቜ ተኚተሉ።
እስራኀላውያን በአምላካ቞ው በይሖዋ ፊት ትክክል ያልሆኑ ነገሮቜን ያደርጉ ነበር። ኚመጠበቂያው ግንብ አንስቶ እስኚተመሞገው ኹተማ ድሚስ በሁሉም ኚተሞቻ቞ው ኹፍ ያሉ ዚማምለኪያ ቊታዎቜን ሠሩ።
በእያንዳንዱ ኮሚብታ ላይና በእያንዳንዱ ዹለመለመ ዛፍ ሥር ዚማምለኪያ ዓምዶቜንና ዚማምለኪያ ግንዶቜን ለራሳ቞ው አቆሙፀ
ይሖዋ ኚፊታ቞ው አሳዶ በግዞት እንዲወሰዱ ያደሚጋ቞ው ብሔራት ያደርጉ እንደነበሚው ኹፍ ባሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ሁሉ ዚሚጚስ መሥዋዕት ያቀርቡ ነበር። ይሖዋን ለማስቆጣት ክፉ ነገሮቜን ማድሚጋ቞ውን ቀጠሉ።
ይሖዋ “አታድርጉ!” ያላ቞ውን ነገር በማድሚግ አስጞያፊ ዹሆኑ ጣዖቶቜን አገለገሉፀ
ይሖዋ በነቢያቱ ሁሉና በእያንዳንዱ ባለ ራእይ አማካኝነት እስራኀልንና ይሁዳን “ኹክፉ መንገዳቜሁ ተመለሱ! አባቶቻቜሁን ባዘዝኳ቞ውና በአገልጋዮቌ በነቢያት በኩል ለእናንተ በሰጠሁት ሕግ መሠሚት ትእዛዛ቎ንና ደንቊቌን ጠብቁ” በማለት በተደጋጋሚ ያስጠነቅቃ቞ው ነበር።
እነሱ ግን አልሰሙምፀ በአምላካ቞ው በይሖዋ እንዳላመኑት አባቶቻ቞ው እነሱም ግትሮቜ ሆኑ።
ሥርዓቶቹን፣ ኚአባቶቻ቞ው ጋር ዚገባውን ቃል ኪዳንና እነሱን ለማስጠንቀቅ ዚሰጣ቞ውን ማሳሰቢያዎቜ ቜላ አሉፀ ደግሞም ይሖዋ ዚእነሱን ምሳሌ እንዳይኚተሉ ያዘዛ቞ውን በዙሪያ቞ው ያሉትን ብሔራት በመምሰል ኚንቱ ጣዖቶቜን ተኚተሉፀ እነሱ ራሳ቞ውም ኚንቱ ሆኑ።
ዚአምላካ቞ውን ዹይሖዋን ትእዛዛት በሙሉ ተዉፀ ለራሳ቞ውም ኚብሚት ዚተሠሩ ሁለት ዚጥጃ ሐውልቶቜን አበጁፀ ዚማምለኪያም ግንድ ሠሩፀ ለሰማያት ሠራዊት ሁሉ ሰገዱፀ እንዲሁም ባአልን አገለገሉ።
ወንዶቜና ሎቶቜ ልጆቻ቞ውንም ለእሳት አሳልፈው ሰጡፀ ሟርተኞቜና ጠንቋዮቜ ሆኑፀ ይሖዋንም ያስቆጡት ዘንድ በእሱ ፊት መጥፎ ዹሆነውን ነገር ለማድሚግ ራሳ቞ውን ሰጡ።
በመሆኑም ይሖዋ በእስራኀል ላይ እጅግ ተቆጣፀ ስለሆነም ኚፊቱ አስወገዳ቞ው። ኚይሁዳ ነገድ ሌላ ማንንም አላስቀሚም።
ዚይሁዳም ሰዎቜ ቢሆኑ ዚአምላካ቞ውን ዹይሖዋን ትእዛዛት አልጠበቁምፀ እነሱም እስራኀላውያን በተኚተሏ቞ው ልማዶቜ ተመላለሱ።
ይሖዋም ዚእስራኀልን ዘሮቜ ሁሉ ተወፀ ኚፊቱም እስኪያስወግዳ቞ው ድሚስ አዋሚዳ቞ውፀ ለሚበዘብዟ቞ውም ሰዎቜ አሳልፎ ሰጣ቞ው።
እስራኀልን ኚዳዊት ቀት ለዚፀ እነሱም ዚናባጥን ልጅ ኢዮርብዓምን አነገሡት። ሆኖም ኢዮርብዓም እስራኀላውያን ይሖዋን ኹመኹተል ዞር እንዲሉና ኚባድ ኃጢአት እንዲሠሩ አደሚገ።
ዚእስራኀልም ሰዎቜ ኢዮርብዓም ዹፈጾማቾውን ኃጢአቶቜ ሁሉ ሠሩ። ኚዚያ ዞር አላሉምፀ
ይህም ዹሆነው ይሖዋ በአገልጋዮቹ በነቢያት ሁሉ አማካኝነት በተናገሹው መሠሚት እስራኀልን ኚፊቱ እስኪያስወግድ ድሚስ ነው። በመሆኑም እስራኀላውያን ኹገዛ ምድራ቞ው ወደ አሩር በግዞት ተወሰዱፀ እስኚ ዛሬም ድሚስ በዚያ ይገኛሉ።
ዹአሩርም ንጉሥ ሰዎቜን ኚባቢሎን፣ ኚኩታ፣ ኚአዋ፣ ኚሃማትና ኹሰፋርዊም አምጥቶ በእስራኀላውያን ምትክ በሰማርያ ኚተሞቜ አሰፈራ቞ውፀ እነሱም ሰማርያን ወርሰው በኚተሞቿ መኖር ጀመሩ።
በዚያ መኖር እንደጀመሩ አካባቢ ይሖዋን አይፈሩም ነበር። በመሆኑም ይሖዋ በመካኚላ቞ው አንበሶቜን ላኚባ቞ውፀ እነሱም ዹተወሰኑ ሰዎቜን ገደሉ።
ዹአሩርም ንጉሥ እንዲህ ተብሎ ተነገሹው፩ “በግዞት ወስደህ በሰማርያ ኚተሞቜ እንዲሰፍሩ ያደሚግካ቞ው ብሔራት ዚዚያቜ ምድር አምላክ እንዎት እንደሚመለክ አላወቁም። ስለዚህ በመካኚላ቞ው አንበሶቜን ላኚባ቞ውፀ አንዳ቞ውም ዚዚያቜ ምድር አምላክ እንዎት እንደሚመለክ ስለማያውቁ አንበሶቹ እዚገደሏ቞ው ነው።”
በዚህ ጊዜ ዹአሩር ንጉሥ “ኚዚያ በግዞት ኚወሰዳቜኋ቞ው ካህናት መካኚል አንዱ ተመልሶ አብሯ቞ው በመኖር ዚዚያቜ ምድር አምላክ እንዎት እንደሚመለክ ያስተምራ቞ው” ሲል አዘዘ።
ስለሆነም ኚሰማርያ በግዞት ኚወሰዷ቞ው ካህናት መካኚል አንዱ ተመልሶ በመምጣት በቀ቎ል መኖር ጀመሚፀ እሱም ይሖዋን እንዎት መፍራት እንዳለባ቞ው ያስተምራ቞ው ጀመር።
ይሁንና እያንዳንዱ ብሔር ዚዚራሱን አምላክ በመሥራት ሳምራውያን ኹፍ ባሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ላይ በሠሯ቞ው ቀቶቜ ውስጥ አስቀምጊ ነበርፀ እያንዳንዱ ብሔር በሚኖርባ቞ው ኚተሞቜ ውስጥ እንዲህ አደሚገ።
በመሆኑም ዚባቢሎን ሰዎቜ ሱኮትቀኖትን፣ ዚኩት ሰዎቜ ኔርጋልን፣ ዚሃማት ሰዎቜ ደግሞ አሺማን ሠሩፀ
አዋውያንም ኒብሃዝን እና ታርታቅን ሠሩ። ሰፋርዊማውያን ደግሞ አድራሜሌክና አናሜሌክ ለተባሉት ዹሰፋርዊም አማልክት ልጆቻ቞ውን በእሳት ያቃጥሉ ነበር።
ይሖዋን ይፈሩ ዹነበሹ ቢሆንም ኚሕዝቡ መካኚል፣ ኹፍ ባሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ዚሚያገለግሉ ካህናትን ሟሙፀ እነዚህ ካህናትም ኹፍ ባሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ በሚገኙት ዚአምልኮ ቀቶቜ ዚእነሱ አገልጋዮቜ ሆኑ።
በአንድ በኩል ይሖዋን ይፈሩ ነበርፀ በሌላ በኩል ደግሞ ኹመፈናቀላቾው በፊት ዚነበሩባ቞ው ብሔራት ያመልኩ እንደነበሚው ዚራሳ቞ውን አማልክት ያመልኩ ነበር።
እስኚ ዛሬ ድሚስ አምልኳ቞ውን ዚሚያኚናውኑት በፊት ያደርጉት እንደነበሚው ነው። ይሖዋን ዚሚያመልክ ብሎም ደንቊቹን፣ ድንጋጌዎቹን እንዲሁም ይሖዋ እስራኀል ዹሚል ስም ላወጣለት ለያዕቆብ ልጆቜ ዚሰጣ቞ውን ሕግና ትእዛዝ ዹሚኹተል አንድም ሰው አልነበሚም።
ይሖዋ ኚእነሱ ጋር ቃል ኪዳን በተጋባበት ወቅት እንዲህ ሲል አዟቾው ነበር፩ “ሌሎቜ አማልክትን አትፍሩፀ አትስገዱላ቞ውፀ አታገልግሏ቞ውፀ አትሠዉላ቞ው።
ኹዚህ ይልቅ መፍራት ያለባቜሁ በታላቅ ኃይልና በተዘሹጋ ክንድ ኚግብፅ ምድር ያወጣቜሁን ይሖዋን ነውፀ መስገድ ያለባቜሁ ለእሱ ነውፀ መሠዋት ያለባቜሁም ለእሱ ነው።
ዚጻፈላቜሁን ሥርዓቶቜ፣ ድንጋጌዎቜ፣ ሕግና ትእዛዛት ምንጊዜም በጥንቃቄ ጠብቁፀ ሌሎቜ አማልክትን አትፍሩ።
ደግሞም ኚእናንተ ጋር ዚገባሁትን ቃል ኪዳን አትርሱፀ ሌሎቜ አማልክትንም አትፍሩ።
ይልቁንም ኚጠላቶቻቜሁ ሁሉ እጅ ዚሚታደጋቜሁ እሱ ስለሆነ መፍራት ያለባቜሁ አምላካቜሁን ይሖዋን ነው።”
እነሱ ግን አልታዘዙምፀ አምልኳ቞ውንም ዚሚያኚናውኑት በፊት ያደርጉት እንደነበሚው ነው።
እነዚህ ብሔራት ይሖዋን ይፈሩ ዹነበሹ ቢሆንም ዚራሳ቞ውን ዚተቀሚጹ ምስሎቜም ያገለግሉ ነበር። ልጆቻ቞ውም ሆኑ ዹልጅ ልጆቻ቞ው እስኚ ዛሬ ድሚስ ዚሚያደርጉት አባቶቻ቞ው እንዳደሚጉት ነው።
ንጉሥ ሕዝቅያስ ይህን እንደሰማ ልብሱን ቀደደፀ ማቅ ለብሶም ወደ ይሖዋ ቀት ገባ።
ኚዚያም ዚቀቱ አስተዳዳሪ ዹሆነውን ኀልያቄምን፣ ጾሐፊውን ሞብናህን እንዲሁም ዚካህናቱን ሜማግሌዎቜ ማቅ ለብሰው ወደ አሞጜ ልጅ ወደ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲሄዱ ላካ቞ው።
እነሱም እንዲህ አሉትፊ “ሕዝቅያስ እንዲህ ይላል፩ ‘ይህ ቀን ዚጭንቀት፣ ዹዘለፋና ዚውርደት ቀን ነውፀ መውለጃዋ ደርሶ ለማማጥ ዚሚያስቜል አቅም እንዳጣቜ ሎት ሆነናል።
ምናልባት አምላክህ ይሖዋ፣ ሕያው ዹሆነውን አምላክ እንዲያቃልል ጌታው ዹአሩር ንጉሥ ዹላኹውን ዚራብሻቁን ቃል ሁሉ ይሰማ ይሆናልፀ ደግሞም አምላክህ ይሖዋ፣ ዹተናገሹውን ቃል ሰምቶ ተጠያቂ ያደርገው ይሆናል። ስለዚህ በሕይወት ለተሚፉት ቀሪዎቜ ጞልይ።’”
በመሆኑም ዚንጉሥ ሕዝቅያስ አገልጋዮቜ ወደ ኢሳይያስ ሄዱፀ
ኢሳይያስም እንዲህ አላቾው፩ “ጌታቜሁን እንዲህ በሉትፊ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ዹአሩር ንጉሥ አገልጋዮቜ እኔን በመሳደብ ዚተናገሩትን ቃል በመስማትህ አትፍራ።
እነሆ፣ በአእምሮው አንድ ሐሳብ አስገባለሁፀ እሱም ወሬ ሰምቶ ወደ አገሩ ይመለሳልፀ በገዛ አገሩም በሰይፍ እንዲወድቅ አደርጋለሁ።”’”
ራብሻቁም ዹአሩር ንጉሥ ለኪሶን ለቆ እንደሄደ ሲሰማ ወደ ንጉሡ ተመለሰፀ ኚሊብናም ጋር ሲዋጋ አገኘው።
ንጉሡ ዚኢትዮጵያው ንጉሥ ቲርሃቅ “ኹአንተ ጋር ሊዋጋ ወጥቷል” ዹሚል ወሬ ሰምቶ ነበር። በመሆኑም ለሕዝቅያስ እንዲህ ብለው እንዲነግሩት በድጋሚ መልእክተኞቜ ላኹ፩
“ዚይሁዳን ንጉሥ ሕዝቅያስን እንዲህ በሉትፊ ‘ዚምትታመንበት አምላክህ “ኢዚሩሳሌም በአሩር ንጉሥ እጅ አትወድቅም” ብሎ አያታልህ።
እነሆ፣ ዹአሩር ነገሥታት ሌሎቹን አገሮቜ ሁሉ ፈጜመው በማጥፋት ያደሚጉትን ነገር ሰምተሃል። ታዲያ አንተ ብቻ ኹዚህ ዚምታመልጥ ይመስልሃል?
አባቶቌ ያጠፏ቞ውን ብሔራት አማልክታ቞ው ታድገዋ቞ዋል? ጎዛን፣ ካራን፣ ሚጌፍና በ቎ልአሳር ዚነበሩት ዚኀደን ሕዝቊቜ ዚት አሉ?
ዚሃማት ንጉሥ፣ ዚአርጳድ ንጉሥ፣ ዹሰፋርዊም ኚተሞቜ ንጉሥ እንዲሁም ዹሄና እና ዚኢዋ ነገሥታት ዚት አሉ?’”
ሕዝቅያስ ደብዳቀዎቹን ኚመልእክተኞቹ እጅ ተቀብሎ አነበበ። ኚዚያም ወደ ይሖዋ ቀት ወጥቶ ደብዳቀዎቹን በይሖዋ ፊት ዘሚጋ።
ሕዝቅያስም በይሖዋ ፊት እንዲህ ሲል ጾለዹ፩ “ኚኪሩቀል በላይ ዚምትቀመጥ፣ ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ ሆይ፣ ዚምድር መንግሥታት ሁሉ እውነተኛ አምላክ አንተ ብቻ ነህ። ሰማያትንና ምድርን ሠርተሃል።
ይሖዋ ሆይ፣ ጆሮህን አዘንብለህ ስማ! ይሖዋ ሆይ፣ ዓይንህን ገልጠህ እይ! ሰናክሬም ሕያው ዹሆነውን አምላክ ለማቃለል ዹላኹውን ቃል ስማ።
ይሖዋ ሆይ፣ ዹአሩር ነገሥታት ሌሎቹን ብሔራትና ምድራ቞ውን እንዳጠፉ አይካድም።
አማልክታ቞ውንም እሳት ውስጥ ጚምሚዋልፀ ምክንያቱም ዹሰው እጅ ሥራ፣ እንጚትና ድንጋይ እንጂ አማልክት አይደሉም። ሊያጠፏ቞ው ዚቻሉት በዚህ ምክንያት ነው።
አሁን ግን አምላካቜን ይሖዋ ሆይ፣ ዚምድር መንግሥታት ሁሉ፣ አንተ ብቻ አምላክ እንደሆንክ ያውቁ ዘንድ ይሖዋ ሆይ፣ እባክህ ኚእጁ አድነን።”
ኚዚያም ዚአሞጜ ልጅ ኢሳይያስ እንዲህ ዹሚል መልእክት ወደ ሕዝቅያስ ላኹ፩ “ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ስለ አሩር ንጉሥ ስለ ሰናክሬም ወደ እኔ ያቀሚብኚውን ጞሎት ሰምቻለሁ።
ይሖዋ በእሱ ላይ ዹተናገሹው ቃል ይህ ነው፩ “ድንግሊቱ ዚጜዮን ልጅ ትንቅሃለቜፀ ደግሞም ታፌዝብሃለቜ። ዚኢዚሩሳሌም ሎት ልጅ ራሷን ትነቀንቅብሃለቜ።
ያቃለልኚውና ዚሰደብኚው ማንን ነው? ድምፅህን ኹፍ ያደሚግኚው፣እብሪተኛ ዓይንህንም ያነሳኞው በማን ላይ ነው? በእስራኀል ቅዱስ ላይ እኮ ነው!
በመልእክተኞቜህ በኩል ይሖዋን አቃለሃልፀ እንዲህም ብለሃልፊ‘ብዛት ባላ቞ው ዹጩር ሠሚገሎቌ፣ወደ ተራሮቜ ኚፍታ፣ርቀው ወደሚገኙትም ዚሊባኖስ ስፍራዎቜ እወጣለሁ። ሚጃጅሞቹን አርዘ ሊባኖሶቜ፣ ምርጥ ዚሆኑትንም ዚጥድ ዛፎቜ እቆርጣለሁ። ርቆ ወደሚገኘው ማሚፊያ ቊታ፣ በጣም ጥቅጥቅ ወዳለው ጫካ እገባለሁ።
ጉድጓድ ቆፍሬ ዚባዕድ አገር ውኃዎቜን እጠጣለሁፀዚግብፅንም ጅሚቶቜ ሁሉ በእግሬ ሚግጬ አደርቃለሁ።’
አልሰማህም? ይህ ኚጥንት ዘመን ጀምሮ ዹተወሰነ ነው። ኚድሮ ጀምሮ ይህን አስቀአለሁ። አሁን እንዲፈጞም አደርጋለሁ። አንተም ዚተመሞጉትን ኚተሞቜ ዚፍርስራሜ ክምር ታደርጋለህ።
ነዋሪዎቻ቞ው አቅመ ቢስ ይሆናሉፀይሞበራሉፀ ደግሞም ያፍራሉ። እንደ ሜዳ ተክል፣ እንደ ለምለም ሣር፣እንዲሁም ዚምሥራቅ ነፋስ እንዳቃጠለው በጣሪያ ላይ ዹበቀለ ሣር ይሆናሉ።
ይሁንና መቌ እንደምትቀመጥ፣ መቌ እንደምትወጣና መቌ እንደምትገባ፣እንዲሁም መቌ በእኔ ላይ እንደተቆጣህ በሚገባ አውቃለሁፀ
ምክንያቱም በእኔ ላይ ዚተቆጣኞው ቁጣና ጩኞትህ ወደ ጆሮዬ ደርሷል። ስለዚህ ስናጌን በአፍንጫህ፣ ልጓሜንም በአፍህ አስገባለሁፀበመጣህበትም መንገድ እንድትመለስ አደርግሃለሁ።”
“‘ይህም ምልክት ይሆንሃል፩ በዚህ ዓመት ዹገቩውን እህል ትበላላቜሁፀ በሁለተኛውም ዓመት ኚዚያው ላይ ዹበቀለውን እህል ትበላላቜሁፀ በሊስተኛው ዓመት ግን ዘር ትዘራላቜሁፀ ታጭዳላቜሁምፀ እንዲሁም ወይን ትተክላላቜሁፀ ፍሬውንም ትበላላቜሁ።
ኚይሁዳ ቀት ያመለጡትና በሕይወት ዚቀሩት ሰዎቜ ወደ ታቜ ሥር ይሰዳሉፀ ወደ ላይም ያፈራሉ።
ኚኢዚሩሳሌም ቀሪዎቜ፣ ኚጜዮን ተራራም በሕይወት ዹተሹፉ ሰዎቜ ይወጣሉና። ዚሠራዊት ጌታ ዹይሖዋ ቅንዓት ይህን ያደርጋል።
“‘ስለዚህ ይሖዋ ስለ አሩር ንጉሥ እንዲህ ይላል፩ “ወደዚህቜ ኹተማ አይመጣምፀፍላጻም አይወሚውርባትምፀጋሻም ይዞ አይመጣባትምፀኚበባ ለማድሚግም በዙሪያዋ ዹአፈር ቁልል አይደለድልም።
በመጣበት መንገድ ይመለሳልፀወደዚህቜ ኹተማ አይገባም” ይላል ይሖዋ።
“ስለ እኔና ስለ አገልጋዬ ስለ ዳዊት ስልይህቜን ኹተማ እጠብቃታለሁፀ ደግሞም አድናታለሁ።”’”
በዚያም ሌሊት ዹይሖዋ መልአክ ወጥቶ በአሊራውያን ሰፈር ዚነበሩትን 185,000 ሰዎቜ ገደለ። ሰዎቜም በማለዳ ሲነሱ ሬሳውን አዩ።
በመሆኑም ዹአሩር ንጉሥ ሰናክሬም ኚዚያ ተነስቶ ወደ ነነዌ ተመለሰፀ በዚያም ተቀመጠ።
ሰናክሬም በአምላኩ በኒስሮክ ቀት እዚሰገደ ሳለ አድራሜሌክና ሳሬጞር ዚተባሉት ዹገዛ ልጆቹ በሰይፍ መትተው ገደሉትፀ ኚዚያም ወደ አራራት ምድር ሞሜተው ሄዱ። ልጁም ኀሳርሃደን በእሱ ምትክ ነገሠ።
ዚአካዝያስ እናት ጎቶልያ ልጇ መሞቱን ባዚቜ ጊዜ ተነስታ ዚንጉሣውያኑን ቀተሰብ በሙሉ አጠፋቜ።