text
stringlengths
4
267
ኚዚያም ዚእስራኀልን መኳንንት፣ ካህናቱንና ሌዋውያኑን ሁሉ ሰበሰበ።
ዕድሜያ቞ው 30 እና ኚዚያ በላይ ዹሆኑ ሌዋውያን ተቆጠሩፀ እያንዳንዱ ወንድ በነፍስ ወኹፍ ሲቆጠር 38,000 ነበር።
ኚእነዚህም መካኚል 24,000ዎቹ ዹይሖዋን ቀት ሥራ በበላይነት ይቆጣጠሩ ነበርፀ በተጚማሪም 6,000 አለቆቜና ዳኞቜ ነበሩፀ
ደግሞም 4,000 በር ጠባቂዎቜ እንዲሁም ዳዊት “ውዳሎ ለማቅሚብ ዚሠራኋ቞ው ናቾው” ባላ቞ው መሣሪያዎቜ ለይሖዋ ውዳሎ ዚሚያቀርቡ 4,000 ሰዎቜ ነበሩ።
ኚዚያም ዳዊት በሌዊ ልጆቜ በጌድሶን፣ በቀአት እና በሜራሪ ምድብ አደራጃ቞ው።
ኚጌድሶናውያን ወገን ላዳን እና ሺምአይ ነበሩ።
ዚላዳን ወንዶቜ ልጆቜ መሪው ዚሂኀል፣ ዜታም እና ኢዩኀል ሲሆኑ በአጠቃላይ ሊስት ነበሩ።
ዚሺምአይ ወንዶቜ ልጆቜ ሞሎሞት፣ ሃዚኀል እና ካራን ሲሆኑ በአጠቃላይ ሊስት ነበሩ። እነዚህ ዚላዳን ወገን ዚዚአባቶቻ቞ው ቀቶቜ መሪዎቜ ነበሩ።
ዚሺምአይ ወንዶቜ ልጆቜ ያሃት፣ ዚና፣ ዚኡሜ እና በሪአ ነበሩ። እነዚህ አራቱ ዚሺምአይ ወንዶቜ ልጆቜ ነበሩ።
መሪው ያሃት ነበርፀ ሁለተኛው ደግሞ ዚዛህ ነበር። ዚኡሜ እና በሪአ ግን ብዙ ወንዶቜ ልጆቜ ስላልነበሯ቞ው በአንድ ዚሥራ መደብ እንደ አንድ ዚአባቶቜ ቀት ሆነው ተቆጠሩ።
ዚቀአት ወንዶቜ ልጆቜ አምራም፣ ይጜሃር፣ ኬብሮን እና ዑዚኀል ሲሆኑ በአጠቃላይ አራት ነበሩ።
ዚአምራም ወንዶቜ ልጆቜ አሮን እና ሙሮ ነበሩ። ሆኖም አሮንና ወንዶቜ ልጆቹ ቅድስተ ቅዱሳኑን እንዲቀድሱ፣ በይሖዋ ፊት መሥዋዕት እንዲያቀርቡ፣ እሱን እንዲያገለግሉና ምንጊዜም በስሙ እንዲባርኩ በቋሚነት ተለይተው ነበር።
ዚእውነተኛው አምላክ ሰው ዹሙሮ ወንዶቜ ልጆቜ ዚሌዋውያን ነገድ ክፍል ሆነው ተቆጠሩ።
ዹሙሮ ወንዶቜ ልጆቜ ጌርሳም እና ኀሊዔዘር ነበሩ።
ኚጌርሳም ወንዶቜ ልጆቜ መካኚል መሪው ሞቡኀል ነበር።
ኚኀሊዔዘር ዘሮቜ መካኚል መሪው ሚሃቢያህ ነበርፀ ኀሊዔዘር ሌሎቜ ወንዶቜ ልጆቜ አልነበሩትምፀ ይሁንና ዚሚሃብያህ ወንዶቜ ልጆቜ እጅግ ብዙ ነበሩ።
ኚይጜሃር ወንዶቜ ልጆቜ መካኚል መሪው ሞሎሚት ነበር።
ዚኬብሮን ወንዶቜ ልጆቜ መሪ ዹሆነው ዚሪያ፣ ሁለተኛው አማርያህ፣ ሊስተኛው ያሃዚኀል እና አራተኛው ዹቃምአም ነበሩ።
ዚዑዚኀል ወንዶቜ ልጆቜ መሪ ዹሆነው ሚክያስ እና ሁለተኛው ይሜሺያህ ነበሩ።
ዚሜራሪ ወንዶቜ ልጆቜ ማህሊ እና ሙሺ ነበሩ። ዹማህሊ ወንዶቜ ልጆቜ አልዓዛር እና ቂስ ነበሩ።
ሆኖም አልዓዛር ሎቶቜ ልጆቜ ብቻ እንጂ ወንዶቜ ልጆቜ ሳይወልድ ሞተ። በመሆኑም ዘመዶቻ቞ው ዚቂስ ልጆቜ አገቧ቞ው።
ዚሙሺ ወንዶቜ ልጆቜ ማህሊ፣ ኀዎር እና ዚሬሞት ሲሆኑ በአጠቃላይ ሊስት ነበሩ።
በአባቶቻ቞ው ቀት ይኾውም በአባቶቻ቞ው ቀት መሪዎቜ ተቆጥሚውና በስም ተዘርዝሹው ዚተመዘገቡት በይሖዋ ቀት ያለውን አገልግሎት ያኚናውኑ ዚነበሩ 20 ዓመትና ኚዚያ በላይ ዹሆናቾው ዹሌዊ ወንዶቜ ልጆቜ እነዚህ ና቞ው።
ዳዊት እንዲህ ብሎ ነበርና፩ “ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ ለሕዝቡ እሚፍት ሰጥቷልፀ እሱም በኢዚሩሳሌም ለዘላለም ይኖራል።
ሌዋውያኑም ዚማደሪያ ድንኳኑን ወይም በውስጡ ያሉትን ለአምልኮ ዚሚያገለግሉ ዕቃዎቜ ሁሉ መሾኹም አያስፈልጋ቞ውም።”
ዳዊት በሰጠው ዚመጚሚሻ መመሪያ መሠሚት ኹሌዊ ልጆቜ መካኚል ዚተቆጠሩት 20 ዓመትና ኚዚያ በላይ ዹሆናቾው ሰዎቜ እነዚህ ነበሩ።
ዚሌዋውያኑ ተግባር በይሖዋ ቀት አገልግሎት ዹሚኹናወነውን ሥራ ይኾውም ቅጥር ግቢዎቹንና ዚመመገቢያ ክፍሎቹን፣ ቅዱስ ዹሆነውን ነገር ሁሉ ዚማንጻቱን ሥራና በእውነተኛው አምላክ ቀት ዚሚኚናወኑትን አስፈላጊ ሥራዎቜ ሁሉ ኃላፊነት ወስደው በመሥራት ዚአሮንን ልጆቜ መርዳት ነበር።
ደግሞም ዚሚነባበሚውን ዳቊ፣ ለእህል መባ ዚሚያገለግለውን ዹላመ ዱቄት፣ እርሟ ያልገባበትን ስስ ቂጣ፣ በምጣድ ዹሚጋገሹውን ቂጣና በዘይት ዹሚለወሰውን ሊጥ በማዘጋጀት እንዲሁም ኹሁሉም ዓይነት መለኪያዎቜና መስፈሪያዎቜ ጋር ዚተያያዙ ሥራዎቜን በማኹናወን ያግዟ቞ው ነበር።
ለይሖዋ ምስጋናና ውዳሎ ለማቅሚብ ጠዋት ጠዋትም ሆነ ማታ ማታ ይቆሙ ነበር።
ሕጉ በሚያዘው ቁጥር መሠሚት ዘወትር በይሖዋ ፊት በዚሰንበቱ፣ በዹወር መባቻውና በበዓላት ወቅት ለይሖዋ ዹሚቃጠል መሥዋዕት በቀሹበ ጊዜ ሁሉ ያግዟ቞ው ነበር።
በተጚማሪም በይሖዋ ቀት ለሚኹናወነው አገልግሎት ኹመገናኛ ድንኳኑ፣ ኚቅዱሱ ስፍራና ወንድሞቻ቞ው ኚሆኑት ዚአሮን ወንዶቜ ልጆቜ ጋር በተያያዘ ያሉባ቞ውን ኃላፊነቶቜ ይወጡ ነበር።
ዹሌዊ ወንዶቜ ልጆቜ ጌድሶን፣ ቀአት እና ሜራሪ ነበሩ።
ዚቀአት ወንዶቜ ልጆቜ አምራም፣ ይጜሃር፣ ኬብሮን እና ዑዚኀል ነበሩ።
ዚአምራምልጆቜ አሮን፣ ሙሮ እና ሚርያም ነበሩ። ዚአሮን ወንዶቜ ልጆቜ ናዳብ፣ አቢሁ፣ አልዓዛር እና ኢታምር ነበሩ።
አልዓዛር ፊንሃስን ወለደፀ ፊንሃስ አቢሹዓን ወለደ።
አቢሹዓ ቡቂን ወለደፀ ቡቂ ዑዚን ወለደ።
ዑዚ ዘራህያህን ወለደፀ ዘራህያህ መራዮትን ወለደ።
መራዮት አማርያህን ወለደፀ አማርያህ አኪጡብን ወለደ።
አኪጡብ ሳዶቅን ወለደፀ ሳዶቅ አኪማዓስን ወለደ።
አኪማዓስ አዛርያስን ወለደፀ አዛርያስ ዮሃናንን ወለደ።
ዮሃናን አዛርያስን ወለደ። እሱም ሰለሞን በኢዚሩሳሌም በገነባው ቀት ውስጥ ካህን ሆኖ ያገለግል ነበር።
አዛርያስ አማርያህን ወለደፀ አማርያህ አኪጡብን ወለደ።
አኪጡብ ሳዶቅን ወለደፀ ሳዶቅ ሻሉምን ወለደ።
ሻሉም ኬልቅያስን ወለደፀ ኬልቅያስ አዛርያስን ወለደ።
አዛርያስ ሰራያህን ወለደፀ ሰራያህ ዚሆጌዎቅን ወለደ።
ይሖዋ፣ ይሁዳና ኢዚሩሳሌም በናቡኚደነጟር እጅ በግዞት እንዲወሰዱ ሲያደርግ ዚሆጌዎቅም በግዞት ተወሰደ።
ዹሌዊ ወንዶቜ ልጆቜ ጌርሳም፣ ቀአት እና ሜራሪ ነበሩ።
ዚጌርሳም ወንዶቜ ልጆቜ እነዚህ ናቾው፩ ሊብኒ እና ሺምአይ።
ዚቀአት ወንዶቜ ልጆቜ አምራም፣ ይጜሃር፣ ኬብሮን እና ዑዚኀል ነበሩ።
ዚሜራሪ ወንዶቜ ልጆቜ ማህሊ እና ሙሺ ነበሩ። ዚሌዋውያን ቀተሰቊቜ በዚአባቶቻ቞ው ስም ሲዘሚዘሩ እነዚህ ናቾው፩
ጌርሳም፣ ዚጌርሳም ልጅ ሊብኒ፣ ዚሊብኒ ልጅ ያሃት፣ ዚያሃት ልጅ ዚማ፣
ዹዚማ ልጅ ዮአህ፣ ዚዮአህ ልጅ ኢዶ፣ ዚኢዶ ልጅ ዛራ፣ ዚዛራ ልጅ ዚአትራይ።
ዚቀአት ወንዶቜ ልጆቜፊ አሚናዳብ፣ ዚአሚናዳብ ልጅ ቆሬ፣ ዚቆሬ ልጅ አሲር፣
ዚአሲር ልጅ ሕልቃና፣ ዹሕልቃና ልጅ ኀቢያሳፍ፣ ዚኀቢያሳፍ ልጅ አሲርፀ
ዚአሲር ልጅ ታሃት፣ ዚታሃት ልጅ ዑሪኀል፣ ዚዑሪኀል ልጅ ዖዝያ፣ ዚዖዝያ ልጅ ሻኡል።
ዹሕልቃና ወንዶቜ ልጆቜ አማሳይ እና አሂሞት ነበሩ።
ጟፋይ ዹሕልቃና ልጅ ነበርፀ ዚጟፋይ ልጅ ናሃት፣
ዚናሃት ልጅ ኀልያብ፣ ዚኀልያብ ልጅ ዚሮሃም እና ዚዚሮሃም ልጅ ሕልቃና ነበር።
ዚሳሙኀል ወንዶቜ ልጆቜ ዚበኩር ልጁ ኢዩኀልና ሁለተኛው አቢያህ ነበሩ።
ዚሜራሪ ወንዶቜ ልጆቜፊ ማህሊ፣ ዹማህሊ ልጅ ሊብኒ፣ ዚሊብኒ ልጅ ሺምአይ፣ ዚሺምአይ ልጅ ዖዛ፣
ዹዖዛ ልጅ ሺምአ፣ ዚሺምአ ልጅ ሃጊያህ፣ ዚሃጊያህ ልጅ አሳያህ።
ዳዊት፣ ታቊቱ በይሖዋ ቀት ኹተቀመጠ በኋላ በዚያ ዹሚዘመሹውን መዝሙር እንዲመሩ ዚሟማ቞ው እነዚህ ነበሩ።
እነሱ ሰለሞን ዹይሖዋን ቀት በኢዚሩሳሌም እስኪገነባ ድሚስ በማደሪያ ይኾውም በመገናኛ ድንኳኑ ኹመዝሙር ጋር ዚተያያዘ ኃላፊነት ተሰጣ቞ውፀ በተሰጣ቞ውም ኃላፊነት መሠሚት አገልግሎታ቞ውን ያኚናውኑ ነበር።
ኚወንዶቜ ልጆቻ቞ው ጋር አብሚው ዚሚያገለግሉት ሰዎቜ እነዚህ ነበሩፊ ኚቀአታውያን መካኚል ዘማሪው ሄማን፣ ዚኢዩኀል ልጅ፣ ዚሳሙኀል ልጅ፣
ዹሕልቃና ልጅ፣ ዚዚሮሃም ልጅ፣ ዚኀሊዔል ልጅ፣ ዚቶአ ልጅ፣
ዚጹፍ ልጅ፣ ዹሕልቃና ልጅ፣ ዚማሃት ልጅ፣ ዚአማሳይ ልጅ፣
ዹሕልቃና ልጅ፣ ዚኢዩኀል ልጅ፣ ዚአዛርያስ ልጅ፣ ዚሶፎንያስ ልጅ፣
ዚታሃት ልጅ፣ ዚአሲር ልጅ፣ ዚኀቢያሳፍ ልጅ፣ ዚቆሬ ልጅ፣
ዚይጜሃር ልጅ፣ ዚቀአት ልጅ፣ ዹሌዊ ልጅ፣ ዚእስራኀል ልጅ ነበር።
ወንድሙ አሳፍ በቀኙ በኩል ሆኖ ያገለግል ነበርፀ አሳፍ ዚቀራክያህ ልጅ፣ ዚሺምአ ልጅ፣
ዚሚካኀል ልጅ፣ ዚባአሎያህ ልጅ፣ ዚማልኪያህ ልጅ፣
ዚኀትኒ ልጅ፣ ዚዛራ ልጅ፣ ዚአዳያህ ልጅ፣
ዚኀታን ልጅ፣ ዹዚማ ልጅ፣ ዚሺምአይ ልጅ፣
ዚያሃት ልጅ፣ ዚጌርሳም ልጅ፣ ዹሌዊ ልጅ ነበር።
ወንድሞቻ቞ው ዚሆኑት ዚሜራሪ ዘሮቜ በስተ ግራ ዚነበሩ ሲሆን ኀታን በዚያ ነበርፀ እሱም ዚቂሺ ልጅ፣ ዚአብዲ ልጅ፣ ዹማሉክ ልጅ፣
ዚሃሻብያህ ልጅ፣ ዚአሜስያስ ልጅ፣ ዚኬልቅያስ ልጅ፣
ዚአማሲ ልጅ፣ ዚባኒ ልጅ፣ ዚሌሜር ልጅ፣
ዹማህሊ ልጅ፣ ዚሙሺ ልጅ፣ ዚሜራሪ ልጅ፣ ዹሌዊ ልጅ ነበር።
ሌዋውያን ወንድሞቻ቞ው በእውነተኛው አምላክ ቀት፣ በማደሪያ ድንኳኑ ውስጥ ሁሉንም አገልግሎት እንዲያኚናውኑ ተሹመው ነበር።
አሮንና ወንዶቜ ልጆቹ ዚእውነተኛው አምላክ አገልጋይ ሙሮ ባዘዘው መሠሚት እጅግ ቅዱስ ኚሆኑት ነገሮቜ ጋር ዚተያያዙትን ሥራዎቜ በማኹናወን ለእስራኀል ቀት ለማስተሰሚይ፣ ዹሚቃጠል መባ በሚቀርብበት መሠዊያና በዕጣን መሠዊያው ላይ ዚሚጚስ መሥዋዕት አቀሚቡ።
ዚአሮን ዘሮቜ እነዚህ ነበሩፊ ዚአሮን ልጅ አልዓዛር፣ ዹአልዓዛር ልጅ ፊንሃስ፣ ዚፊንሃስ ልጅ አቢሹዓ፣
ዚአቢሹዓ ልጅ ቡቂ፣ ዚቡቂ ልጅ ዑዚ፣ ዹዑዚ ልጅ ዘራህያህ፣
ዚዘራህያህ ልጅ መራዮት፣ ዚመራዮት ልጅ አማርያህ፣ ዚአማርያህ ልጅ አኪጡብ፣
ዚአኪጡብ ልጅ ሳዶቅ፣ ዚሳዶቅ ልጅ አኪማዓስ።
በክልላቾው ውስጥ በሰፈሮቻ቞ው ዚሚገኙት ዚመኖሪያ ቊታዎቻ቞ው እነዚህ ነበሩፊ ዚቀአታውያን ቀተሰብ ዚሆኑት ዚአሮን ዘሮቜ ዚመጀመሪያው ዕጣ ደሚሳ቞ውፀ
በይሁዳ ምድር ዚምትገኘውን ኬብሮንን በዙሪያዋ ካሉት ዚግጊሜ መሬቶቜ ጋር ሰጧ቞ው።
ይሁንና ዹኹተማዋን እርሻና ሰፈሮቿን ለዹፎኒ ልጅ ለካሌብ ሰጡ።
ለአሮንም ዘሮቜ ዹመማጾኛ ኚተሞቜን፣ ኬብሮንን እንዲሁም ሊብናንና ዚግጊሜ መሬቶቿን፣ ያቲርን፣ ኀሜተሞዓንና ዚግጊሜ መሬቶቿን ሰጡፀ
ሂሌንንና ዚግጊሜ መሬቶቿን፣ ደቢርንና ዚግጊሜ መሬቶቿን፣
አሻንንና ዚግጊሜ መሬቶቿን፣ ቀትሌሜሜንና ዚግጊሜ መሬቶቿን ሰጡፀ
ኚቢንያም ነገድም ጌባና ዚግጊሜ መሬቶቿ፣ አለሜትና ዚግጊሜ መሬቶቿ እንዲሁም አናቶትና ዚግጊሜ መሬቶቿ ተሰጣ቞ው። ለወገኖቻ቞ው ዚተሰጡት ኚተሞቻ቞ው በአጠቃላይ 13 ኚተሞቜ ነበሩ።
ለቀሩት ቀአታውያን ኹሌላው ነገድ ቀተሰብና ኹምናሮ ነገድ እኩሌታ ላይ አሥር ኚተሞቜ በዕጣ መደቡላ቞ው።
ለጌርሳማውያን በዚቀተሰቊቻ቞ው ኚይሳኮር ነገድ፣ ኹአሮር ነገድ፣ ኚንፍታሌም ነገድና በባሳን ኹሚገኘው ኹምናሮ ነገድ 13 ኚተሞቜ መደቡላ቞ው።
ለሜራራውያን በዚቀተሰቊቻ቞ው ኚሮቀል ነገድ፣ ኚጋድ ነገድና ኚዛብሎን ነገድ 12 ኚተሞቜ በዕጣ መደቡላ቞ው።
በዚህ መንገድ እስራኀላውያን ለሌዋውያኑ እነዚህን ኚተሞቜ ኚነግጊሜ መሬታ቞ው ሰጧ቞ው።
በተጚማሪም ኚይሁዳ ነገድ፣ ኚስምዖን ነገድና ኚቢንያም ነገድ በስማ቞ው ዚተጠቀሱትን እነዚህን ኚተሞቜ በዕጣ መደቡላ቞ው።
ኚቀአታውያን ቀተሰቊቜ መካኚል ዚተወሰኑት ኚኀፍሬም ነገድ ያገኟ቞ው ዚራሳ቞ው ዹሆኑ ኚተሞቜ ነበሯ቞ው።
እነሱም ዹመማጾኛ ኚተሞቹን፣ ተራራማ በሆነው ዚኀፍሬም ምድር ያለቜውን ሎኬምንና ዚግጊሜ መሬቶቿን እንዲሁም ጌዜርንና ዚግጊሜ መሬቶቿን ሰጧ቞ውፀ
ዮቅመአምንና ዚግጊሜ መሬቶቿን፣ ቀትሆሮንንና ዚግጊሜ መሬቶቿን፣
አይሎንንና ዚግጊሜ መሬቶቿን እንዲሁም ጋትሪሞንንና ዚግጊሜ መሬቶቿን ሰጧ቞ውፀ