text
stringlengths
4
267
ዚእስራኀል ሰዎቜ በሙሉ በሰባተኛው ወር በሚኹበሹው በዓል ላይ በንጉሡ ፊት ተሰበሰቡ።
ዚእስራኀል ሜማግሌዎቜም በሙሉ መጡፀ ሌዋውያኑም ታቊቱን አነሱ።
ታቊቱን፣ ዹመገናኛ ድንኳኑንና በድንኳኑ ውስጥ ዚነበሩትን ቅዱስ ዕቃዎቜ በሙሉ አመጡ። እነዚህንም ያመጡት ካህናቱና ሌዋውያኑ ና቞ው።
ንጉሥ ሰለሞንና ወደ እሱ እንዲመጣ ዚተጠራው መላው ዚእስራኀል ማኅበሚሰብ ታቊቱ ፊት ነበሩ። ኚብዛታ቞ው ዚተነሳ ሊቆጠሩ ዚማይቜሉ ብዙ በጎቜና ኚብቶቜ መሥዋዕት ሆነው ቀሚቡ።
ኚዚያም ካህናቱ ዹይሖዋን ዹቃል ኪዳን ታቊት አምጥተው ቊታው ላይ ማለትም በቀቱ ውስጠኛ ክፍል ይኾውም በቅድስተ ቅዱሳኑ ውስጥ ኚኪሩቊቹ ክንፎቜ በታቜ አስቀመጡት።
ዚኪሩቊቹ ክንፎቜ ታቊቱ ባለበት ቊታ ላይ ተዘርግተው ስለነበር ኪሩቊቹ ታቊቱንና መሎጊያዎቹን ኹላይ ሾፍነዋቾው ነበር።
መሎጊያዎቹ ሹጅም ስለነበሩ ዚመሎጊያዎቹን ጫፎቜ ኚውስጠኛው ክፍል ፊት ለፊት ባለው በቅድስቱ ውስጥ ሆኖ ማዚት ይቻል ነበርፀ ኹውጭ ግን አይታዩም ነበር። እስኚ ዛሬም ድሚስ እዚያው ይገኛሉ።
ዚእስራኀል ሰዎቜ ኚግብፅ ምድር ሲወጡ ይሖዋ ኚእነሱ ጋር ቃል ኪዳን በገባበት ጊዜ ሙሮ በኮሬብ ታቊቱ ውስጥ ካስቀመጣ቞ው ኚሁለቱ ዚድንጋይ ጜላቶቜ በስተቀር በታቊቱ ውስጥ ምንም አልነበሚም።
ካህናቱ ኚቅዱሱ ስፍራ በወጡ ጊዜ (በዚያ ዚተገኙት ካህናት ሁሉ ኚዚትኛውም ምድብ ይሁኑ ራሳ቞ውን ቀድሰው ነበር)፣
ኚአሳፍ፣ ኚሄማን፣ ኚዚዱቱን እንዲሁም ኚወንዶቜ ልጆቻ቞ውና ኚወንድሞቻ቞ው ወገን ዚሆኑት ሌዋውያን ዘማሪዎቜ ሁሉ ጥራት ያለው ልብስ ለብሰውና ሲምባል፣ ባለ አውታር መሣሪያዎቜና በገና ይዘው ነበርፀ ኚመሠዊያው በስተ ምሥራቅ ቆመው ዹነበሹ ሲሆን ኚእነሱም ጋር መለኚት ዹሚነፉ 120 ካህናት ነበሩ።
መለኚት ነፊዎቹና ዘማሪዎቹ በኅብሚት ይሖዋን ባወደሱና ባመሰገኑ ጊዜ እንዲሁም “እሱ ጥሩ ነውናፀ ታማኝ ፍቅሩ ለዘላለም ጞንቶ ይኖራል” እያሉ ይሖዋን በማወደስ ዚመለኚቱን፣ ዚሲምባሉንና ዚሌሎቹን ዹሙዚቃ መሣሪያዎቜ ድምፅ ባሰሙ ጊዜ ቀቱ ይኾውም ዹይሖዋ ቀት በደመና ተሞልቶ ነበር።
ዹይሖዋ ክብር ዚእውነተኛውን አምላክ ቀት ሞልቶት ስለነበር ካህናቱ ኹደመናው ዚተነሳ በዚያ ቆመው ማገልገል አልቻሉም።
በመጚሚሻም አቢያህ ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ በዳዊት ኹተማም ቀበሩትፀ በምትኩም ልጁ አሳ ነገሠ። በእሱም ዘመን ምድሪቱ ለአሥር ዓመት አሚፈቜ።
አሳ በአምላኩ በይሖዋ ፊት መልካምና ትክክል ዹሆነውን ነገር አደሚገ።
ዚባዕድ አማልክቱን መሠዊያዎቜና ኹፍ ያሉትን ዚማምለኪያ ቊታዎቜ አስወገደፀ ዚማምለኪያ ዓምዶቹንም ሰባበሚፀ እንዲሁም ዚማምለኪያ ግንዶቹን ቆራሚጠ።
በተጚማሪም ዚይሁዳ ሰዎቜ ዚአባቶቻ቞ውን አምላክ ይሖዋን እንዲፈልጉ እንዲሁም ሕጉንና ትእዛዙን እንዲያኚብሩ አዘዘ።
ኚይሁዳም ኚተሞቜ ሁሉ ኹፍ ያሉትን ዚማምለኪያ ቊታዎቜና ዚዕጣን ማጚሻዎቹን አስወገደፀ መንግሥቱም በእሱ አገዛዝ ሥር ሰላም አገኘ።
ምድሪቱ እሚፍት አግኝታ ስለነበር በይሁዳ ዹተመሾጉ ኚተሞቜን ገነባፀ ይሖዋ እሚፍት ሰጥቶት ስለነበር በእነዚያ ዓመታት በእሱ ላይ ጊርነት ዹኹፈተ አልነበሚም።
ዚይሁዳንም ሰዎቜ እንዲህ አላቾው፩ “እነዚህን ኚተሞቜ እንገንባፀ በዙሪያ቞ውም ቅጥርና ማማዎቜ እንዲሁም በሮቜና መቀርቀሪያዎቜ እንሥራ። አምላካቜንን ይሖዋን ስለፈለግነው ምድሪቱ አሁንም በእጃቜን ናት። እኛ ፈልገነዋልፀ እሱም በዙሪያቜን ካሉት ጠላቶቻቜን ሁሉ እሚፍት ሰጥቶናል።” በመሆኑም ዚግንባታ ሥራ቞ው ስኬታማ ሆነ።
አሳ ትልቅ ጋሻና ጩር ዚታጠቁ 300,000 ዚይሁዳ ሰዎቜን ያቀፈ ሠራዊት ነበሚው። ኚቢንያምም ነገድ ትንሜ ጋሻ ዚሚያነግቡና ደጋን ዹሚይዙ 280,000 ኃያላን ተዋጊዎቜ ነበሩ።
ኹጊዜ በኋላ ኢትዮጵያዊው ዛራ 1,000,000 ሰዎቜንና 300 ሠሚገሎቜን ያቀፈ ሠራዊት አስኚትሎ ዘመተባ቞ው። ማሬሻህ በደሹሰ ጊዜ
አሳ ሊገጥመው ወጣፀ በማሬሻህ በሚገኘው በጞፋታ ሾለቆም ለውጊያ ተሰለፉ።
በዚህ ጊዜ አሳ ወደ አምላኩ ወደ ይሖዋ እንዲህ ሲል ጮኞፊ “ይሖዋ ሆይ፣ ዚምትሚዳው ሕዝብ ብዛት ያለውም ይሁን ደካማ ለአንተ ዚሚያመጣው ለውጥ ዚለም። ይሖዋ አምላካቜን ሆይ፣ እርዳንፀ በአንተ ታምነናልናፀ በስምህ ይህን ታላቅ ሠራዊት ለመግጠም ወጥተናል። ይሖዋ ሆይ፣ አንተ አምላካቜን ነህ። ሟቜ ዹሆነ ሰው በአንተ ላይ አይበርታ።”
በመሆኑም ይሖዋ ኢትዮጵያውያንን በአሳና በይሁዳ ፊት ድል አደሚጋ቞ውፀ ኢትዮጵያውያኑም ሞሹ።
አሳና ኚእሱ ጋር ያለው ሕዝብም እስኚ ጌራራ ድሚስ አሳደዷ቞ውፀ ኢትዮጵያውያኑም ፈጜመው እስኪጠፉ ድሚስ ተመተው ወደቁፀ በይሖዋና በሠራዊቱ ተደምስሰው ነበርና። በኋላም ዚይሁዳ ሰዎቜ እጅግ ብዙ ምርኮ ወሰዱ።
በተጚማሪም ይሖዋ በኚተሞቹ ላይ ታላቅ ፍርሃት ለቆባ቞ው ስለነበር በጌራራ ዙሪያ ያሉትን ኚተሞቜ ሁሉ መቱፀ እነሱም በኚተሞቹ ውስጥ ብዙ ዹሚበዘበዝ ነገር ስለነበር ኚተሞቹን ሁሉ በዘበዙ።
በተጚማሪም ዚእሚኞቜን ድንኳኖቜ በመምታት እጅግ ብዙ በጎቜንና ግመሎቜን ማሚኩፀ ኚዚያም ወደ ኢዚሩሳሌም ተመለሱ።
አካዝ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 20 ዓመት ነበርፀ በኢዚሩሳሌምም ሆኖ ለ16 ዓመት ገዛ። አባቱ ዳዊት እንዳደሚገው በይሖዋ ፊት ትክክል ዹሆነውን ነገር አላደሚገም።
ኹዚህ ይልቅ ዚእስራኀልን ነገሥታት መንገድ ተኚተለፀ አልፎ ተርፎም ኚብሚት ዚተሠሩ ዚባአል ሐውልቶቜን ሠራ።
በተጚማሪም በሂኖም ልጅ ሾለቆ ዚሚጚስ መሥዋዕት ያቀሚበ ኹመሆኑም ሌላ ይሖዋ ኚእስራኀላውያን ፊት ያባሚራ቞ው ብሔራት ይፈጜሙ ዹነበሹውን አስጞያፊ ድርጊት በመኹተል ወንዶቜ ልጆቹን በእሳት አቃጠለ።
ደግሞም ኹፍ ባሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ፣ በኮሚብቶቹና በእያንዳንዱ ዹለመለመ ዛፍ ሥር ይሠዋ እንዲሁም ዚሚጚስ መሥዋዕት ያቀርብ ነበር።
ስለዚህ አምላኩ ይሖዋ በሶርያ ንጉሥ እጅ አሳልፎ ሰጠውፀ እነሱም ድል አደሚጉትፀ ኚሕዝቡም መካኚል ብዙዎቹን ማርኹው ወደ ደማስቆ ወሰዱ። ደግሞም አምላክ በእስራኀል ንጉሥ እጅ አሳልፎ ሰጠውፀ እሱም ኚባድ እልቂት አደሚሰበት።
ዚሚማልያህ ልጅ ፋቁሄ በይሁዳ 120,000 ሰዎቜን በአንድ ቀን ዹገደለ ሲሆን ሁሉም ደፋር ተዋጊዎቜ ነበሩፀ ይህም ዹሆነው ዚአባቶቻ቞ውን አምላክ ይሖዋን በመተዋቾው ነው።
ዚክሪ ዚተባለው ኀፍሬማዊ ተዋጊም ዚንጉሡን ልጅ ማአሎያህን፣ ዚቀተ መንግሥቱን አዛዥ አዝሪቃምንና ዚንጉሡ ምክትል ዹሆነውን ሕልቃናን ገደለ።
በተጚማሪም እስራኀላውያን ኚአይሁዳውያን ወገኖቻ቞ው መካኚል 200,000 ሎቶቜን፣ ወንዶቜ ልጆቜንና ሎቶቜ ልጆቜን ማሚኩፀ እጅግ ብዙ ምርኮም ወሰዱፀ ዚበዘበዙትንም ወደ ሰማርያ ይዘው ሄዱ።
ይሁንና በዚያ ኊዎድ ዚተባለ ዹይሖዋ ነቢይ ነበር። እሱም ወደ ሰማርያ እዚመጣ ዹነበሹውን ሠራዊት ለመገናኘት ወጥቶ እንዲህ አላቾው፩ “እነሆ፣ ዚአባቶቻቜሁ አምላክ ይሖዋ ዚይሁዳ ሰዎቜን በእጃቜሁ አሳልፎ ዚሰጣቜሁ በእነሱ ላይ ስለተቆጣ ነውፀ እናንተም እስኚ ሰማይ በሚደርስ ታላቅ ቁጣ ፈጃቜኋ቞ው።
አሁንም ዚይሁዳንና ዚኢዚሩሳሌምን ሕዝብ ለራሳቜሁ ወንድ አገልጋዮቜና ሎት አገልጋዮቜ ልታደርጓ቞ው ታስባላቜሁ። እናንተስ ብትሆኑ በአምላካቜሁ በይሖዋ ፊት ተጠያቂ አይደላቜሁም?
እንግዲህ ስሙኝፀ ዹይሖዋ ቁጣ በእናንተ ላይ ስለነደደ ኚወንድሞቻቜሁ መካኚል ዚማሚካቜኋ቞ውን ሰዎቜ መልሱ።”
በዚህ ጊዜ ኚኀፍሬማውያን አለቆቜ መካኚል አንዳንድ ሰዎቜ ይኾውም ዹዹሆሃናን ልጅ አዛርያስ፣ ዚመሺሌሞት ልጅ ቀራክያህ፣ ዚሻሉም ልጅ ዚሂዝቂያ እና ዚሃድላይ ልጅ አሜሳይ ኚጊርነቱ ዚተመለሱትን ሰዎቜ በመቃወም
እንዲህ አሏቾው፩ “ምርኮኞቹን ወደዚህ አታምጧ቞ውፀ በይሖዋ ፊት በደለኞቜ ታደርጉናላቜሁ። በደላቜን ብዙ ሆኖ ሳለ፣ በኃጢአታቜንና በበደላቜን ላይ ልትጚምሩብን ታስባላቜሁ? በእስራኀል ላይ ቁጣ ነዷልና።”
ስለዚህ ዚታጠቁት ወታደሮቜ ምርኮኞቹንና ዚበዘበዙትን ነገር ለመኳንንቱና ለመላው ጉባኀ አስሚኚቡ።
ኚዚያም በስም ተጠቅሰው ኃላፊነት ዚተሰጣ቞ው ሰዎቜ ተነስተው ምርኮኞቹን ተሚኚቡፀ ራቁታ቞ውን ለነበሩት ሁሉ ኚምርኮው ልብስ ሰጧ቞ው። ልብስ አለበሷ቞ውፀ እንዲሁም ጫማ ሰጧ቞ውፀ ዚሚበሉትና ዚሚጠጡት ነገር አቀሚቡላ቞ውፀ ለገላቾውም ዘይት ሰጧ቞ው። ኹዚህም ሌላ ዚደኚሙትን በአህያ ላይ አስቀምጠው ወንድሞቻ቞ው ወደሚገኙባት ዚዘንባባ ዛፎቜ ኹተማ ወደሆነቜው ወደ ኢያሪኮ ወሰዷ቞ው። ኚዚያም ወደ ሰማርያ ተመለሱ።
በዚህ ጊዜ ንጉሥ አካዝ፣ ዹአሩር ነገሥታት እንዲሚዱት ጠዚቀ።
ኀዶማውያንም በድጋሚ መጥተው ይሁዳን በመውሹር ጥቃት ሰነዘሩፀ ምርኮኞቜንም ወሰዱ።
ፍልስጀማውያን ደግሞ በይሁዳ ዚሚገኙትን ዹሾፌላንና ዚኔጌብን ኚተሞቜ ወሚሩፀ ቀትሌሜሜን፣ አይሎንን፣ ገዎሮትን፣ ሶኮንና በሥሯ ያሉትን ኚተሞቜ፣ ቲምናንና በሥሯ ያሉትን ኚተሞቜ እንዲሁም ጊምዞንና በሥሯ ያሉትን ኚተሞቜ ያዙፀ በዚያም ተቀመጡ።
ይሖዋ በእስራኀል ንጉሥ በአካዝ ዚተነሳ ይሁዳን አዋሚደፀ ምክንያቱም አካዝ ዚይሁዳን ሰዎቜ መሹን ለቆ ነበርፀ ይህም ንጉሡ ለይሖዋ ዹነበሹውን ታማኝነት በኹፍተኛ ሁኔታ እንዲያጓድል አደሚገው።
በመጚሚሻም ዹአሩር ንጉሥ ቎ልጌል቎ልፌልሶር እሱን ኚመርዳት ይልቅ በእሱ ላይ ዘምቶ አስጚነቀው።
አካዝ ዹይሖዋን ቀት እንዲሁም ዚንጉሡን ቀትና ዚመኳንንቱን ቀቶቜ አራቁቶ ለአሩር ንጉሥ ስጊታ አበሚኚተፀ ይህ ግን ምንም ዚፈዚደለት ነገር ዚለም።
ንጉሥ አካዝ በተጹነቀ ጊዜ በይሖዋ ላይ ታማኝነት ዹጎደለው ድርጊት መፈጾሙን ይበልጥ ገፋበት።
እሱም “ዚሶርያ ነገሥታት አማልክት እነሱን ስለሚሚዷ቞ው፣ እኔንም እንዲሚዱኝ መሥዋዕት አቀርብላ቞ዋለሁ” በማለት ላሞነፉት ዚደማስቆ አማልክት መሥዋዕት ያቀርብ ጀመር። ይሁንና እነሱ፣ ለእሱም ሆነ ለመላው እስራኀል እንቅፋት ሆኑ።
በተጚማሪም አካዝ ዚእውነተኛውን አምላክ ቀት ዕቃዎቜ ሰበሰበፀ ኚዚያም ዚእውነተኛውን አምላክ ቀት ዕቃዎቜ ሰባበሚፀ ዹይሖዋን ቀት በሮቜ ዘጋፀ በኢዚሩሳሌምም በዚመንገዱ ማዕዘን ላይ መሠዊያዎቜን ለራሱ ሠራ።
በይሁዳ ኚተሞቜ ሁሉ ለሌሎቜ አማልክት ዚሚጚስ መሥዋዕት ዚሚቀርቡባ቞ው ኹፍ ያሉ ዚማምለኪያ ቊታዎቜን ሠራፀ በዚህም ዚአባቶቹን አምላክ ይሖዋን አስቆጣ።
ዹቀሹው ታሪክ፣ ኚመጀመሪያ አንስቶ እስኚ መጚሚሻ ድሚስ ያኚናወነው ነገር ሁሉ በይሁዳና በእስራኀል ነገሥታት መጜሐፍ ውስጥ ተጜፏል።
በመጚሚሻም አካዝ ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ እነሱም በኢዚሩሳሌም ኹተማ ቀበሩትፀ ሆኖም ዚቀበሩት በእስራኀል ነገሥታት ዚመቃብር ስፍራ አልነበሚም። በእሱም ምትክ ልጁ ሕዝቅያስ ነገሠ።
ኚዚያም ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ ዚመጚሚሻ ልጁን አካዝያስን በእሱ ምትክ አነገሡትፀ ኚዓሚቊቹ ጋር ወደ ሰፈሩ ዚመጡት ወራሪዎቜ ታላላቆቹን በሙሉ ገድለዋ቞ው ነበር። በመሆኑም ዚኢዮራም ልጅ አካዝያስ ዚይሁዳ ንጉሥ ሆኖ መግዛት ጀመሚ።
አካዝያስ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 22 ዓመት ነበርፀ በኢዚሩሳሌምም ሆኖ አንድ ዓመት ገዛ። እናቱም ጎቶልያ ዚተባለቜ ዚኊምሪ ዹልጅ ልጅ ነበሚቜ።
እናቱ ክፉ ነገር እንዲያደርግ ትመክሚው ስለነበር እሱም ዚአክዓብን ቀት መንገድ ተኚተለ።
ኚአባቱ ሞት በኋላ ዚአክዓብ ቀት ሰዎቜ አማካሪዎቹ በመሆን ወደ ጥፋት ስለመሩት ልክ እንደ አክዓብ ቀት እሱም በይሖዋ ፊት መጥፎ ዹሆነውን ነገር ማድሚጉን ቀጠለ።
እሱም ዚእነሱን ምክር ተኚትሎ ኚሶርያ ንጉሥ ኚሃዛኀል ጋር በራሞትጊልያድ ለመዋጋት ኚእስራኀል ንጉሥ ኚአክዓብ ልጅ ኚኢዮራም ጋር ሄደፀ በዚያም ቀስተኞቜ ኢዮራምን አቆሰሉት።
እሱም ኚሶርያ ንጉሥ ኚሃዛኀል ጋር በተዋጋበት ጊዜ በራማ ካቆሰሉት ቁስል ለማገገም ወደ ኢይዝራኀል ተመለሰ። ዚይሁዳ ንጉሥ ዚኢዮራም ልጅ አካዝያስ ዚአክዓብ ልጅ ኢዮራም ቆስሎ ስለነበር እሱን ለማዚት ወደ ኢይዝራኀል ወሚደ።
ይሁንና አካዝያስ ወደ ኢዮራም በመምጣቱ አምላክ ለውድቀት ዳሚገውፀ እዚያ ኹደሹሰ በኋላም ኚኢዮራም ጋር ዚኒምሺን ዹልጅ ልጅ ኢዩን ለማግኘት ሄዱፀ ኢዩ ዚአክዓብን ቀት እንዲያጠፋ ይሖዋ ዚቀባው ሰው ነበር።
ኢዩም በአክዓብ ቀት ላይ ዹተላለፈውን ፍርድ ማስፈጞም ሲጀምር ዚአካዝያስ አገልጋዮቜ ዚነበሩትን ዚይሁዳን መኳንንትና ዚአካዝያስን ወንድሞቜ ልጆቜ አግኝቶ ገደላ቞ው።
ኚዚያም አካዝያስን ለመፈለግ ሄደፀ እነሱም በሰማርያ ተደብቆ ሳለ ያዙትፀ ወደ ኢዩም አመጡት። ኚዚያም ገደሉትፀ ይሁንና “ይሖዋን በሙሉ ልቡ ዹፈለገው ዚኢዮሳፍጥ ዹልጅ ልጅ ነው” በማለት ቀበሩት። ኚአካዝያስ ቀት ዚመንግሥቱን ሥልጣን ዚመያዝ ብቃት ያለው ሰው አልነበሚም።
ዚአካዝያስ እናት ጎቶልያ ልጇ መሞቱን ባዚቜ ጊዜ ተነስታ ዚይሁዳን ንጉሣውያን ቀተሰብ በሙሉ አጠፋቜ።
ይሁንና ዚንጉሡ ልጅ ዚሆነቜው ዮሳቀት ሊገደሉ ኚነበሩት ዚንጉሡ ልጆቜ መካኚል ዚአካዝያስን ልጅ ኢዮዓስን ሰርቃ በመውሰድ እሱንና ሞግዚቱን በውስጠኛው መኝታ ክፍል አስቀመጠቻ቞ው። ዚንጉሥ ኢዮራም ልጅ ዚሆነቜው ዮሳቀት (ዚካህኑ ዮዳሄ ሚስትና ዚአካዝያስ እህት ነበሚቜ) ኚጎቶልያ ደብቃ አቆዚቜውፀ በመሆኑም ጎቶልያ ሳትገድለው ቀሚቜ።
እሱም ኚእነሱ ጋር ለስድስት ዓመት በእውነተኛው አምላክ ቀት ተደብቆ ቆዚፀ በዚህ ጊዜ ጎቶልያ በምድሪቱ ላይ ትገዛ ነበር።
ዹአምላክ መንፈስ በኊዎድ ልጅ በአዛርያስ ላይ ወሚደ።
እሱም ኚአሳ ጋር ለመገናኘት ወጥቶ እንዲህ አለው፩ “አሳ ሆይ፣ ይሁዳና ቢንያም ሁሉ ስሙኝ! እናንተ ኚእሱ ጋር እስኚሆናቜሁ ድሚስ ይሖዋ ኚእናንተ ጋር ይሆናልፀ ብትፈልጉት ይገኝላቜኋልፀ ብትተዉት ግን ይተዋቜኋል።
እስራኀል ያለእውነተኛው አምላክ፣ ያለአስተማሪ ካህንና ያለሕግ ብዙ ዘመን አሳልፏል።
በተጹነቁ ጊዜ ግን ወደ እስራኀል አምላክ ወደ ይሖዋ ተመልሰው ፈለጉትፀ እሱም ተገኘላ቞ው።
በዚያ ዘመን በሰላም መጓዝ ዚሚቜል ሰው አልነበሚምፀ ምክንያቱም በዹክልሉ በሚኖሩት ሰዎቜ ሁሉ መካኚል ኹፍተኛ ሁኚት ነበር።
አምላክ በተለያዚ ቜግር ያውካ቞ው ስለነበር አንዱ ብሔር ሌላውን ብሔር፣ አንዱ ኹተማም ሌላውን ኹተማ ያደቅ ነበር።
እናንተ ግን ዚድካማቜሁን ዋጋ ስለምታገኙ በርቱፀ ተስፋም አትቁሚጡ።”
አሳ ይህን ቃልና ነቢዩ ኊዎድ ዹተናገሹውን ትንቢት ሲሰማ ተበሚታታፀ አስጞያፊ ዚሆኑትን ጣዖቶቜም ኚይሁዳና ኚቢንያም ምድር ሁሉ እንዲሁም በተራራማው ዚኀፍሬም ክልል ኚያዛ቞ው ኚተሞቜ አስወገደፀ ኹይሖዋ ቀት በሚንዳ ፊት ለፊት ዹነበሹውን ዹይሖዋን መሠዊያም አደሰ።
እሱም ይሁዳንና ቢንያምን ሁሉ እንዲሁም ኚኀፍሬም፣ ኹምናሮና ኚስምዖን መጥተው ኚእነሱ ጋር ዚተቀመጡትን ዚባዕድ አገር ሰዎቜ ሰበሰበፀ አምላኩ ይሖዋ ኚእሱ ጋር እንደሆነ ባዩ ጊዜ በርካታ ዚባዕድ አገር ሰዎቜ እስራኀልን ትተው ወደ እሱ መጥተው ነበር።
በመሆኑም አሳ በነገሠ በ15ኛው ዓመት፣ በሊስተኛው ወር በኢዚሩሳሌም ተሰበሰቡ።
በዚያም ቀን፣ ካመጡት ምርኮ ላይ 700 ኚብቶቜንና 7,000 በጎቜን ለይሖዋ መሥዋዕት አድርገው አቀሚቡ።
በተጚማሪም ዚአባቶቻ቞ውን አምላክ ይሖዋን በሙሉ ልባ቞ውና በሙሉ ነፍሳ቞ው ለመፈለግ ቃል ኪዳን ገቡ።
ዚእስራኀልን አምላክ ይሖዋን ዹማይፈልግ ማንኛውም ሰው ትንሜም ሆነ ትልቅ፣ ወንድም ሆነ ሎት እንዲገደል ተስማሙ።
በታላቅ ድምፅ፣ በእልልታ፣ በመለኚትና በቀንደ መለኚት ለይሖዋ ማሉ።
ዚይሁዳ ሰዎቜ ሁሉ በሙሉ ልባ቞ው ስለማሉ በመሐላው ሐሎት አደሚጉፀ አምላክንም ኚልባ቞ው ፈለጉትፀ እሱም ተገኘላ቞ውፀ ይሖዋም በዙሪያ቞ው ካሉት ጠላቶቻ቞ው እሚፍት ሰጣ቞ው።
ሌላው ቀርቶ ንጉሥ አሳ አያቱ ማአካ ለማምለኪያ ግንዱ አምልኮ ጞያፍ ጣዖት ሠርታ ስለነበር ኚእመቀትነቷ ሻራት። ኚዚያም አሳ፣ አያቱ ዚሠራቜውን ጞያፍ ጣዖት ቆርጩ በማድቀቅ በቄድሮን ሾለቆ አቃጠለው።
ኹፍ ያሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ ግን ኚእስራኀል አልተወገዱም ነበር። ይሁንና አሳ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ በሙሉ ልቡ ተመላልሷል።
እሱና አባቱ ዚቀደሷ቞ውን ነገሮቜ ይኾውም ብሩን፣ ወርቁንና ልዩ ልዩ ዕቃዎቜን ወደ እውነተኛው አምላክ ቀት አስገባ።
እስኚ 35ኛው ዚአሳ ዘመነ መንግሥት ድሚስ ጊርነት አልነበሚም።
እነዚህ ነገሮቜ ኹተኹናወኑና ሕዝቅያስ በታማኝነት ሲመላለስ ኹቆዹ በኋላ ዹአሩር ንጉሥ ሰናክሬም መጥቶ ይሁዳን ወሚሚ። ቅጥራ቞ውን አፍርሶ ለመያዝ ስላሰበ ዚተመሞጉትን ኚተሞቜ ኚበበ።
ሕዝቅያስ ሰናክሬም ኢዚሩሳሌምን ለመውጋት አስቊ እንደመጣ ባዚ ጊዜ፣
ኚመኳንንቱና ኚተዋጊዎቹ ጋር ተማክሮ ኚኚተማዋ ውጭ ያሉትን ዹውኃ ምንጮቜ ለመድፈን ወሰነፀ እነሱም ሚዱት።
ብዙ ሰዎቜ ተሰብስበው “ዹአሩር ነገሥታት መጥተው ለምን ብዙ ውኃ ያግኙ?” በማለት ምንጮቹንና በምድሪቱ መካኚል ዹሚፈሰውን ጅሚት በሙሉ ደፈኑ።
በተጚማሪም ሕዝቅያስ በትጋት በመሥራት ዹፈሹሰውን ቅጥር በሙሉ ገነባፀ በላዩም ላይ ማማዎቜን ሠራፀ ኹውጭ በኩልም ሌላ ቅጥር ገነባ። ደግሞም ዚዳዊትን ኹተማ ጉብታ ጠገነፀ እንዲሁም ብዙ ዹጩር መሣሪያዎቜና ጋሻዎቜ ሠራ።
ኚዚያም በሕዝቡ ላይ ዹጩር አለቆቜን ሟሞ በኹተማዋ በር በሚገኘው አደባባይ ሰበሰባ቞ውፀ እንዲህም በማለት አበሚታታ቞ውፊ
“ደፋርና ብርቱዎቜ ሁኑ። ኹአሩር ንጉሥና ኚእሱ ጋር ካለው ብዙ ሠራዊት ዚተነሳ አትፍሩ ወይም አትሞበሩፀ ኚእሱ ጋር ካሉት ይልቅ ኚእኛ ጋር ያሉት ይበልጣሉ።
ኚእሱ ጋር ያለው ዚሥጋ ክንድ ሲሆን ኚእኛ ጋር ያለው ግን አምላካቜን ይሖዋ ነውፀ እሱ ይሚዳናልፀ ደግሞም ይዋጋልናል።” ሕዝቡም ዚይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስ በተናገሹው ቃል ተበሚታታ።
ኹዚህ በኋላ ዹአሩር ንጉሥ ሰናክሬም ኚሠራዊቱ ሁሉ ጋር በለኪሶ ሳለ አገልጋዮቹን ወደ ኢዚሩሳሌም ይኾውም ወደ ይሁዳ ንጉሥ ወደ ሕዝቅያስና በኢዚሩሳሌም ወደሚኖሩት አይሁዳውያን ሁሉ እንዲህ ሲል ላኹ፩
“ዹአሩር ንጉሥ ሰናክሬም እንዲህ ይላል፩ ‘ኢዚሩሳሌም ተኚባ ሳለ ኹኹተማዋ ሳትወጡ ዚቀራቜሁት በምን ተማምናቜሁ ነው?
ሕዝቅያስ “አምላካቜን ይሖዋ ኹአሩር ንጉሥ እጅ ይታደገናል” እያለ እናንተን በማታለል በሚሃብና በጥም እንድትሞቱ አሳልፎ ሊሰጣቜሁ አይደለም?
ዚአምላካቜሁን ኹፍ ያሉ ዚማምለኪያ ቊታዎቜና መሠዊያዎቜ ካስወገደ በኋላ ይሁዳንና ኢዚሩሳሌምን “በአንድ መሠዊያ ፊት ስገዱፀ በዚያም ላይ ዚሚጚስ መሥዋዕት አቅርቡ” ያለው ሕዝቅያስ ራሱ አይደለም?
እኔም ሆንኩ አባቶቌ በተለያዩ አገሮቜ ሕዝቊቜ ሁሉ ላይ ያደሚግነውን አታውቁም? ዚእነዚህ አገሮቜ ሕዝቊቜ አማልክት ምድራ቞ውን ኚእጄ መታደግ ቜለዋል?
አባቶቌ ፈጜመው ካጠፏ቞ው ኚእነዚህ ብሔራት አማልክት ሁሉ መካኚል ሕዝቡን ኚእጄ መታደግ ዚቻለ ዚትኛው ነው? ታዲያ ዚእናንተስ አምላክ ቢሆን ኚእጄ ሊታደጋቜሁ ይቜላል?
አሁንም ሕዝቅያስ በዚህ መንገድ አያታላቜሁ ወይም አያሳስታቜሁ! አትመኑትፀ ዚዚትኛውም ብሔርም ሆነ መንግሥት አምላክ ኚእኔና ኚአባቶቌ እጅ ሕዝቡን መታደግ አልቻለም። ዚእናንተ አምላክማ ኚእጄ ይታደጋቜሁ ዘንድ ምንኛ ያንስ!’”