text
stringlengths
4
267
ዚሰናክሬም አገልጋዮቜ በእውነተኛው አምላክ በይሖዋና በአገልጋዩ በሕዝቅያስ ላይ ሌላ ብዙ ነገር ተናገሩ።
በተጚማሪም ንጉሡ ዚእስራኀልን አምላክ ይሖዋን ለመስደብና እሱን ለማቃለል እንዲህ ሲል ደብዳቀ ጻፈፊ “ዚሌሎቜ ብሔራት አማልክት ሕዝባ቞ውን ኚእጄ መታደግ እንዳልቻሉ ሁሉ ዚሕዝቅያስም አምላክ ሕዝቡን ኚእጄ ሊታደግ አይቜልም።”
በቅጥሩ ላይ ያሉትን ዚኢዚሩሳሌም ሰዎቜ በማስፈራራትና በማሾበር ኹተማዋን ለመያዝ ሲሉ ድምፃ቞ውን ኹፍ አድርገው በአይሁዳውያን ቋንቋ ለሰዎቹ መናገራ቞ውን ቀጠሉ።
ዹሰው እጅ ሥራ በሆኑት በሌሎቜ ዚምድር ሕዝቊቜ አማልክት ላይ እንደተናገሩ ሁሉ፣ በኢዚሩሳሌም አምላክ ላይም ተናገሩ።
ንጉሥ ሕዝቅያስና ዚአሞጜ ልጅ ነቢዩ ኢሳይያስ ግን ይህን ጉዳይ በተመለኹተ አጥብቀው ጞለዩፀ እርዳታ ለማግኘትም ወደ ሰማይ ጮኹ።
ኚዚያም ይሖዋ አንድ መልአክ ልኮ በአሩር ንጉሥ ሰፈር ዚነበሩትን ኃያላን ተዋጊዎቜ እንዲሁም መሪዎቜና አለቆቜ ሁሉ ጠራርጎ አጠፋፀ ንጉሡም ኀፍሚት ተኹናንቩ ወደ ገዛ አገሩ ተመለሰ። በኋላም ወደ አምላኩ ቀት ገባፀ በዚያም ሳለ ዹገዛ ወንዶቜ ልጆቹ በሰይፍ ገደሉት።
በዚህ መንገድ ይሖዋ ሕዝቅያስንና ዚኢዚሩሳሌምን ነዋሪዎቜ ኹአሩር ንጉሥ ኚሰናክሬም እጅና ኚሌሎቜ ሁሉ እጅ አዳና቞ውፀ በዙሪያ቞ውም ካሉ ጠላቶቻ቞ው ሁሉ እሚፍት ሰጣ቞ው።
ብዙዎቜም ለይሖዋ ስጊታ፣ ለይሁዳ ንጉሥ ለሕዝቅያስም ምርጥ ዹሆኑ ነገሮቜ ይዘው ወደ ኢዚሩሳሌም መጡፀ እሱም ኚዚያ በኋላ በብሔራት ሁሉ ዘንድ ታላቅ አክብሮት አተሚፈ።
በዚያን ጊዜ ሕዝቅያስ በጠና ታሞ ሞት አፋፍ ደርሶ ነበርፀ ወደ ይሖዋም ጞለዚፀ እሱም መለሰለትፀ ምልክትም ሰጠው።
ይሁንና ሕዝቅያስ ልቡ ታብዮ ስለነበር ለተደሚገለት መልካም ነገር አድናቆት ሳያሳይ ቀሚፀ ዹአምላክም ቁጣ በእሱ፣ በይሁዳና በኢዚሩሳሌም ላይ መጣ።
ይሁን እንጂ ሕዝቅያስ ስለ ልቡ ትዕቢት ራሱን ዝቅ አደሚገፀ እሱና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ ትሕትና አሳዩፀ ዹይሖዋም ቁጣ በሕዝቅያስ ዘመን አልመጣባ቞ውም።
ሕዝቅያስም እጅግ ብዙ ሀብት አገኘፀ ታላቅ ክብርም ተጎናጞፈፀ ብሩን፣ ወርቁን፣ ዚኚበሩ ድንጋዮቹን፣ ዚበለሳን ዘይቱን፣ ጋሻዎቹንና ውድ ዚሆኑትን ዕቃዎቜ ሁሉ ዚሚያስቀምጥባ቞ው ግምጃ ቀቶቜ ሠራ።
በተጚማሪም ለእህሉ፣ ለአዲሱ ዹወይን ጠጅና ለዘይቱ ዚማኚማቻ ቊታዎቜ አዘጋጀፀ እንዲሁም ለተለያዩ እንስሳት በሚት፣ ለበጎቜና ለፍዚሎቜ ደግሞ ጉሹኖ ሠራ።
ለራሱም ኚተሞቜን ገነባፀ እጅግ ብዙ ኚብቶቜ፣ መንጎቜና እንስሳት ነበሩትፀ አምላክ ብዙ ንብሚት ሰጥቶት ነበር።
ዚግዮንን ውኃ ዹላይኛውን መውጫ ደፍኖ ውኃው በምዕራብ በኩል በቀጥታ ወደ ዳዊት ኹተማ እንዲወርድ ያደሚገው ሕዝቅያስ ነበርፀ ሥራውም ሁሉ ተሳካለት።
ይሁንና ዚባቢሎን መኳንንት ቃል አቀባዮቜ በምድሪቱ ላይ ስለተኚሰተው ምልክት እንዲጠይቁት ወደ እሱ በተላኩ ጊዜ እውነተኛው አምላክ እሱን ለመፈተንና በልቡ ያለውን ሁሉ ለማወቅ ሲል ተወው።
ዹቀሹው ዚሕዝቅያስ ታሪክና ያሳዚው ታማኝ ፍቅር ዚአሞጜ ልጅ ነቢዩ ኢሳይያስ ባዚው ራእይ ላይ፣ በይሁዳና በእስራኀል ነገሥታት መጜሐፍ ተጜፏል።
በመጚሚሻም ሕዝቅያስ ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ ወደ ዳዊት ልጆቜ ዚመቃብር ስፍራ በሚወስድ ኹፍ ያለ ቊታ ላይ ቀበሩትፀ በሞተበት ጊዜም መላው ይሁዳና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ አኚበሩት። በእሱም ምትክ ልጁ ምናሮ ነገሠ።
ኚዚያም ርዝመቱ 20 ክንድ፣ ወርዱ 20 ክንድ፣ ኚፍታውም 10 ክንድ ዹሆነ ዚመዳብ መሠዊያ ሠራ።
ባሕሩን በቀለጠ ብሚት ሠራ። ባሕሩ ክብ ቅርጜ ዹነበሹው ሲሆን ኚአንዱ ጠርዝ እስኚ ሌላኛው ጠርዝ 10 ክንድ፣ ኚፍታው ደግሞ 5 ክንድ ነበርፀ መጠነ ዙሪያውም በመለኪያ ገመድ ሲለካ 30 ክንድ ሆነ።
በባሕሩም ዙሪያ ኚሥሩ በእያንዳንዱ ክንድ ላይ በቅል ቅርጜ ዚተሠሩ አሥር ጌጊቜ ነበሩ። ቅሎቹም ኚባሕሩ ጋር አንድ ወጥ ሆነው በሁለት ሚድፍ ቀልጠው ተሠርተው ነበር።
ባሕሩ 3ቱ ወደ ሰሜን፣ 3ቱ ወደ ምዕራብ፣ 3ቱ ወደ ደቡብ እንዲሁም 3ቱ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ ፊታ቞ውን ባዞሩ 12 በሬዎቜ ላይ ተቀምጩ ነበርፀ ባሕሩም ላያ቞ው ላይ ነበርፀ ዹሁሉም ሜንጥ ወደ መሃል ገባ ያለ ነበር።
ዹውኃ ማጠራቀሚያው ውፍሚት አንድ ጋት ነበርፀ ጠርዙ ዚጜዋ ኹንፈር ይመስል ዹነበሹ ሲሆን በአበባ ቅርጜ ዚተሠራ ነበር። ዹውኃ ማጠራቀሚያው 3,000 ዚባዶስ መስፈሪያ መያዝ ይቜላል።
በተጚማሪም ለመታጠቢያ ዹሚሆኑ አሥር ዹውኃ ገንዳዎቜ ሠርቶ አምስቱን በስተ ቀኝ፣ አምስቱን ደግሞ በስተ ግራ አስቀመጣ቞ው። ገንዳዎቹን ዹሚቃጠለውን መባ ለማቅሚብ ዚሚያገለግሉትን ነገሮቜ ለማጠብ ይጠቀሙባ቞ው ነበር። ባሕሩ ግን ዚካህናቱ መታጠቢያ ነበር።
ኚዚያም በተሰጠው መመሪያ መሠሚት አሥር ዹወርቅ መቅሚዞቜን ሠርቶ በቀተ መቅደሱ ውስጥ አምስቱን በስተ ቀኝ፣ አምስቱን ደግሞ በስተ ግራ አስቀመጣ቞ው።
በተጚማሪም አሥር ጠሚጎዛዎቜን ሠርቶ በቀተ መቅደሱ ውስጥ አምስቱን በስተ ቀኝ፣ አምስቱን በስተ ግራ አስቀመጣ቞ውፀ ኚዚያም 100 ጎድጓዳ ዹወርቅ ሳህኖቜን ሠራ።
ኚዚያም ዚካህናቱን ግቢ እንዲሁም ትልቁን ግቢና ዚግቢውን በሮቜ ሠራፀ ዚግቢዎቹንም በሮቜ በመዳብ ለበጣ቞ው።
ባሕሩንም በስተ ቀኝ በኩል፣ በስተ ደቡብ ምሥራቅ አቅጣጫ አስቀመጠው።
በተጚማሪም ኪራም አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ አካፋዎቹንና ጎድጓዳ ሳህኖቹን ሠራ። ኪራምም በእውነተኛው አምላክ ቀት ለንጉሥ ሰለሞን ያኚናውን ዹነበሹውን ሥራ ጚሚሰፀ
ሁለቱን ዓምዶቜ፣ በሁለቱ ዓምዶቜ አናት ላይ ዚነበሩትን ዚጎድጓዳ ሳህን ቅርጜ ያላ቞ው ዚዓምድ ራሶቜ፣ በዓምዶቹ አናት ላይ ዚነበሩትን ዚጎድጓዳ ሳህን ቅርጜ ያላ቞ውን ሁለቱን ክብ ዚዓምድ ራሶቜ ዚሚያስጌጡትን ሁለት መሚቊቜ፣
ለሁለቱ መሚቊቜ ዚተሠሩትን 400 ሮማኖቜ ማለትም በዓምዶቹ አናት ላይ ዚነበሩትን ዚጎድጓዳ ሳህን ቅርጜ ያላ቞ውን ሁለት ዚዓምድ ራሶቜ ለማስጌጥ ዚተሠሩትን በእያንዳንዱ መሚብ ላይ በሁለት ሚድፍ ዚተደሚደሩትን ሮማኖቜ፣
አሥሩን ጋሪዎቜና በጋሪዎቹ ላይ ዚነበሩትን አሥር ዹውኃ ገንዳዎቜ፣
ባሕሩንና ኚሥሩ ዚነበሩትን 12 በሬዎቜ፣
አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ አካፋዎቹን፣ ሹካዎቹንና ኹዚህ ጋር ተያያዥነት ያላ቞ውን ዕቃዎቜ ሁሉ ኪራምአቢቭ ለይሖዋ ቀት መገልገያ እንዲሆኑ ለንጉሥ ሰለሞን ኹተወለወለ መዳብ ሠራ።
ንጉሡ እነዚህ ነገሮቜ በዮርዳኖስ አውራጃ፣ በሱኮትና በጞሬዳህ መካኚል በሚገኝ ስፍራ በሾክላ ጭቃ ውስጥ ቀልጠው እንዲሠሩ አደሚገ።
ሰለሞን ዚሠራ቞ው ዕቃዎቜ እጅግ ብዙ ነበሩፀ ዚመዳቡም ክብደት ምን ያህል እንደሆነ አልታወቀም።
ሰለሞን ለእውነተኛው አምላክ ቀት መገልገያ ዚሚሆኑትን ዚሚኚተሉትን ነገሮቜ ሠራፊ ዹወርቅ መሠዊያውን፣ ገጾ ኅብስቱ ዚሚቀመጥባ቞ውን ጠሚጎዛዎቜ፣
በመመሪያው መሠሚት በውስጠኛው ክፍል ፊት ዚሚበሩትን ኚንጹሕ ወርቅ ዚተሠሩ መቅሚዞቜና መብራቶቻ቞ውን፣
ኹወርቅ ይኾውም እጅግ ኚጠራ ወርቅ ዚተሠሩትን ዚፈኩ አበቊቜ፣ መብራቶቜና መቆንጠጫዎቜ፣
ኚንጹሕ ወርቅ ዚተሠሩትን ዚእሳት ማጥፊያዎቜ፣ ጎድጓዳ ሳህኖቜ፣ ጜዋዎቜና መኮስተሪያዎቜ እንዲሁም ኹወርቅ ዚተሠሩትን ዚቀቱን መግቢያ፣ ዚቅድስተ ቅዱሳኑን ዚውስጥ በሮቜና ዚቀተ መቅደሱን ቀት በሮቜ።
ኹጊዜ በኋላ ሞዓባውያንና አሞናውያን ኹተወሰኑ ዹአሞኒም ሰዎቜ ጋር ሆነው ኚኢዮሳፍጥ ጋር ለመዋጋት መጡ።
በመሆኑም ኢዮሳፍጥ እንዲህ ዹሚል ወሬ ሰማ፩ “በባሕሩ አካባቢ ካለው ክልል፣ ኚኀዶም ታላቅ ሠራዊት አንተን ሊወጋ መጥቷልፀ ሠራዊቱም በሃጻጟንታማር ማለትም በኀንገዲ ይገኛል።”
ኢዮሳፍጥ ይህን ሲሰማ ፈራፀ ይሖዋንም ለመፈለግ ቆርጩ ተነሳ። በመሆኑም በመላው ይሁዳ ጟም አወጀ።
ኚዚያም ዚይሁዳ ሰዎቜ ይሖዋን ለመጠዹቅ ተሰበሰቡፀ ዹይሖዋን መመሪያ ለማግኘት ኚይሁዳ ኚተሞቜ ሁሉ መጡ።
ኚዚያም ኢዮሳፍጥ በይሖዋ ቀት ኚአዲሱ ግቢ ፊት ለፊት በይሁዳና በኢዚሩሳሌም ጉባኀ መካኚል ቆመፀ
እንዲህም አለ፩ “ዚአባቶቻቜን አምላክ ይሖዋ ሆይ፣ አንተ በሰማያት ያለህ አምላክ አይደለህም? ዚብሔራትን መንግሥታት ሁሉ ዚምትገዛ አንተ አይደለህም? ኃይልና ብርታት በእጅህ ነውፀ አንተን ሊቋቋም ዚሚቜል ማንም ዚለም።
አምላካቜን ሆይ፣ ዚዚህቜን ምድር ነዋሪዎቜ ኚሕዝብህ ኚእስራኀል ፊት አሳደህ ምድሪቱን ለወዳጅህ ለአብርሃም ዘሮቜ ለዘለቄታው ርስት አድርገህ ዹሰጠኾው አንተ አይደለህም?
እነሱም በምድሪቱ መኖር ጀመሩፀ በዚያም ለስምህ መቅደስ ሠሩፀ እንዲህም አሉፊ
‘ሰይፍ፣ ዚቅጣት ፍርድ፣ ቾነፈር ወይም ሚሃብ በእኛ ላይ ጥፋት ቢያደርስብን በዚህ ቀትና በአንተ ፊት እንቆማለን (ይህን ቀት ለስምህ መርጠኾዋልና)ፀ ኚጭንቀታቜንም እንድትገላግለን ወደ አንተ እንጮኻለንፀ አንተም ሰምተህ አድነን።’
አሁንም ዹአሞንና ዚሞዓብ ሰዎቜ እንዲሁም በሮይር ተራራማ ክልል ዚሚኖሩ ሰዎቜ ዚሚያደርጉትን ተመልኚት። እስራኀላውያን ኚግብፅ ምድር በወጡበት ጊዜ እነሱን እንዲወሩ አልፈቀድክም ነበር። እነሱም አልነኳ቞ውምፀ ደግሞም አላጠፏ቞ውም።
እነሱ ግን ርስት አድርገህ ካወሚስኚን ምድር እኛን በማባሚር ብድራት ሊመልሱልን መጥተዋል።
አምላካቜን ሆይ፣ በእነሱ ላይ አትፈርድባ቞ውም? እኛ ዚመጣብንን ይህን ታላቅ ሠራዊት ለመቋቋም ዚሚያስቜል ኃይል ዚለንምፀ ምን ማድሚግ እንዳለብንም አናውቅምፀ ነገር ግን ዓይኖቻቜን ወደ አንተ ይመለኚታሉ።”
በዚህ ጊዜ ዚይሁዳ ሰዎቜ በሙሉ ኚሕፃኖቻ቞ው፣ ኚሚስቶቻ቞ውና ኚልጆቻ቞ው ጋር በይሖዋ ፊት ቆመው ነበር።
ኚዚያም በጉባኀው መካኚል ዹይሖዋ መንፈስ ኚአሳፍ ልጆቜ ወገን በሆነው በሌዋዊው በማታንያህ ልጅ፣ በዚኢዔል ልጅ፣ በበናያህ ልጅ፣ በዘካርያስ ልጅ በያሃዚኀል ላይ መጣ።
እሱም እንዲህ አለ፩ “ዚይሁዳ ሰዎቜ ሁሉ፣ እናንተም ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜና ንጉሥ ኢዮሳፍጥ፣ አዳምጡ! ይሖዋ እንዲህ ይላቜኋልፊ ‘ኹዚህ ታላቅ ሠራዊት ዚተነሳ አትፍሩፀ አትሞበሩፀ ውጊያው ዹአምላክ እንጂ ዚእናንተ አይደለምና።
ነገ በእነሱ ላይ ውሚዱ። እነሱ በጺጜ መተላለፊያ ሜቅብ ይወጣሉፀ እናንተም ዚሩኀል ምድሚ በዳ ኚመድሚሳቜሁ በፊት በሾለቆው መጚሚሻ ላይ ታገኟ቞ዋላቜሁ።
እናንተ ይህን ጊርነት መዋጋት አያስፈልጋቜሁም። ቊታ ቊታቜሁን ይዛቜሁ ዝም ብላቜሁ ቁሙፀ ይሖዋ ለእናንተ ሲል ዚሚወስደውን ዚማዳን እርምጃ ተመልኚቱ። ይሁዳና ኢዚሩሳሌም ሆይ፣ አትፍሩ ወይም አትሞበሩ። ነገ በእነሱ ላይ ውጡፀ ይሖዋም ኚእናንተ ጋር ይሆናል።’”
ኢዮሳፍጥ ወዲያውኑ በግንባሩ ወደ መሬት ተደፋፀ ዚይሁዳ ሰዎቜ ሁሉና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜም በይሖዋ ፊት ተደፍተው ይሖዋን አመለኩ።
ኚዚያም ዚቀአታውያንና ዚቆሬያውያን ዘሮቜ ዚሆኑት ሌዋውያን ዚእስራኀልን አምላክ ይሖዋን እጅግ ኹፍ ባለ ድምፅ ለማወደስ ተነሱ።
በማግስቱም በማለዳ ተነስተው በተቆአ ወደሚገኘው ምድሚ በዳ ሄዱ። እዚሄዱ ሳሉ ኢዮሳፍጥ ቆሞ እንዲህ አለፊ “ይሁዳና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ ሆይ፣ ስሙኝ! ጞንታቜሁ መቆም እንድትቜሉ በአምላካቜሁ በይሖዋ እመኑ። በነቢያቱም እመኑፀ እንዲህ ካደሚጋቜሁ ይሳካላቜኋል።”
ኚሕዝቡ ጋር ኹተማኹሹ በኋላም ኚታጠቁት ሰዎቜ ፊት ፊት እዚሄዱ “ለይሖዋ ምስጋና አቅርቡፀ ታማኝ ፍቅሩ ለዘላለም ጞንቶ ይኖራልና” እያሉ ለይሖዋ ዚሚዘምሩ እንዲሁም ያጌጠ ዚቅድስና ልብስ ለብሰው ውዳሎ ዚሚያቀርቡ ሰዎቜን መደበ።
በደስታ ዚውዳሎ መዝሙር መዘመር በጀመሩ ጊዜ ይሖዋ ይሁዳን በወሚሩት በአሞን፣ በሞዓብና በሮይር ተራራማ ክልል በሚኖሩት ሰዎቜ ላይ ድንገተኛ ጥቃት ሰነዘሚባ቞ውፀ እነሱም እርስ በርስ ተፋጁ።
አሞናውያኑና ሞዓባውያኑ በሮይር ተራራማ ክልል በሚኖሩት ሰዎቜ ላይ ተነስተው አጠፏ቞ውፀ ደመሰሷ቞ውምፀ ዹሮይርን ነዋሪዎቜ ካጠፉም በኋላ እርስ በርስ ተላለቁ።
ዚይሁዳ ሰዎቜ በምድሚ በዳ ወዳለው መጠበቂያ ግንብ መጥተው ሠራዊቱን ሲመለኚቱ መሬቱ ሬሳ በሬሳ ሆኖ አዩፀ በሕይወት ዹተሹፈ አንድም ሰው አልነበሚም።
በመሆኑም ኢዮሳፍጥና ሕዝቡ ኚእነሱ ላይ ምርኮ ለመውሰድ መጡፀ በእነሱም መካኚል እጅግ ብዙ ዕቃ፣ ልብስና ውድ ነገሮቜ አገኙፀ መሾኹም እስኪያቅታ቞ው ድሚስ ብዙ ነገር ገፈፏ቞ው። ኚብዛቱ ዚተነሳ ለሊስት ቀን ያህል ምርኮ ሲሰበስቡ ቆዩ።
በአራተኛውም ቀን በቀራካ ሾለቆ ተሰበሰቡፀ በዚያም ይሖዋን አወደሱ። ይህን ስፍራ እስኚ ዛሬ ድሚስ ዚቀራካ ሾለቆ ብለው ዚሚጠሩት ኹዚህ ዚተነሳ ነው።
ኚዚያም ዚይሁዳና ዚኢዚሩሳሌም ሰዎቜ ሁሉ ይሖዋ በጠላቶቻ቞ው ላይ ድል ስላቀዳጃ቞ው በኢዮሳፍጥ እዚተመሩ በታላቅ ደስታ ወደ ኢዚሩሳሌም ተመለሱ።
በባለ አውታር መሣሪያዎቜ፣ በበገናና በመለኚት ድምፅ ታጅበው ወደ ኢዚሩሳሌም መጡፀ ኚዚያም ወደ ይሖዋ ቀት ሄዱ።
ይሖዋ ዚእስራኀልን ጠላቶቜ እንደተዋጋ በሰሙ ጊዜ በምድሪቱ ያሉ መንግሥታት ሁሉ አምላክን ፈሩ።
በመሆኑም ዚኢዮሳፍጥ መንግሥት ኚሁኚት ነፃ ሆነፀ አምላኩም በዙሪያው ካሉት ጠላቶቹ ሁሉ እሚፍት ሰጠው።
ኢዮሳፍጥም በይሁዳ መግዛቱን ቀጠለ። በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 35 ዓመት ዹነበሹ ሲሆን በኢዚሩሳሌም 25 ዓመት ገዛ። እናቱ ዚሺልሂ ልጅ አዙባ ነበሚቜ።
እሱም በአባቱ በአሳ መንገድ ሄደ። ኚዚያ ፈቀቅ አላለምፀ በይሖዋም ፊት ትክክል ዹሆነውን ነገር አደሚገ።
ይሁን እንጂ ኹፍ ያሉት ዚማምለኪያ ቊታዎቜ አልተወገዱም ነበርፀ ሕዝቡም ልቡን ለአባቶቹ አምላክ ገና አላዘጋጀም ነበር።
ኚመጀመሪያ አንስቶ እስኚ መጚሚሻ ድሚስ ያለው ዹቀሹው ዚኢዮሳፍጥ ታሪክ ዹሃናኒ ልጅ ኢዩ በጻፈው ዘገባ ላይ ሰፍሯልፀ ይህም በእስራኀል ነገሥታት መጜሐፍ ውስጥ ተካቷል።
ኹዚህ በኋላ ዚይሁዳ ንጉሥ ኢዮሳፍጥ፣ ክፉ ድርጊት ኹፈጾመው ኚእስራኀል ንጉሥ ኚአካዝያስ ጋር ግንባር ፈጠሚ።
ወደ ተርሎስ ዚሚሄዱ መርኚቊቜን ለመሥራትም ተሻሚኩፀ መርኚቊቹንም በዔጜዮንጋብር ሠሩ።
ይሁን እንጂ ዚማሬሻ ሰው ዹሆነው ዚዶዳዋ ልጅ ኀሊዔዘር “ኚአካዝያስ ጋር ግንባር በመፍጠርህ ይሖዋ ሥራህን ያፈርሰዋል” ሲል በኢዮሳፍጥ ላይ ትንቢት ተናገሚ። በመሆኑም መርኚቊቹ ተሰባበሩፀ ወደ ተርሎስም መሄድ ሳይቜሉ ቀሩ።
ሮብዓም በበሚታና ንግሥናው በጾና ጊዜ እሱም ሆነ አብሚውት ያሉት እስራኀላውያን ሁሉ ዹይሖዋን ሕግ ተዉ።
ለይሖዋ ታማኝ ሳይሆኑ በመቅሚታ቞ው ንጉሥ ሮብዓም በነገሠ በአምስተኛው ዓመት ዚግብፅ ንጉሥ ሺሻቅ በኢዚሩሳሌም ላይ ዘመተ።
እሱም 1,200 ሠሚገሎቜና 60,000 ፈሚሰኞቜ አስኚትሎ ነበርፀ ኚእሱም ጋር ኚግብፅ ዚመጡት ሊቢያውያን፣ ሱኪማውያንና ኢትዮጵያውያን ወታደሮቜ ስፍር ቁጥር አልነበራ቞ውም።
እሱም ዚይሁዳን ዹተመሾጉ ኚተሞቜ ያዘፀ በመጚሚሻም ኢዚሩሳሌም ደሚሰ።
ነቢዩ ሞማያህ ወደ ሮብዓምና ሺሻቅን ፈርተው በኢዚሩሳሌም ወደተሰበሰቡት ዚይሁዳ መኳንንት መጥቶ እንዲህ አላቾው፩ “ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እናንተ ትታቜሁኛልፀ ስለዚህ እኔም በሺሻቅ እጅ ትቻቜኋለሁ።’”
በዚህ ጊዜ ዚእስራኀል መኳንንትና ንጉሡ ራሳ቞ውን ዝቅ በማድሚግ “ይሖዋ ጻድቅ ነው” አሉ።
ይሖዋ ራሳ቞ውን ዝቅ እንዳደሚጉ ባዚ ጊዜ፣ ዹይሖዋ ቃል እንዲህ ሲል ወደ ሞማያህ መጣፊ “ራሳ቞ውን ዝቅ ስላደሚጉ አላጠፋ቞ውምፀ በቅርቡም እታደጋ቞ዋለሁ። ቁጣዬንም በሺሻቅ እጅ በኢዚሩሳሌም ላይ አላፈስም።
ይሁን እንጂ እኔን በማገልገልና ዚሌሎቜ አገሮቜ ነገሥታትን በማገልገል መካኚል ያለውን ልዩነት እንዲያውቁ ዚእሱ አገልጋዮቜ ይሆናሉ።”
በመሆኑም ዚግብፁ ንጉሥ ሺሻቅ ኢዚሩሳሌምን ለመውጋት መጣ። እሱም በይሖዋ ቀት ዚነበሩትን ውድ ንብሚቶቜና በንጉሡ ቀት ዚነበሩትን ውድ ንብሚቶቜ ወሰደ። ሰለሞን ዚሠራ቞ውን ዹወርቅ ጋሻዎቜ ጚምሮ ሁሉንም ነገር ወሰደ።
በመሆኑም ንጉሥ ሮብዓም በእነሱ ምትክ ዚመዳብ ጋሻዎቜን ሠርቶ ዚንጉሡን ቀት በር ለሚጠብቁት ዚዘብ አለቆቜ ሰጣ቞ው።
ዘቊቹም ንጉሡ ወደ ይሖዋ ቀት በመጣ ቁጥር ገብተው ጋሻዎቹን ያነግቡ ነበርፀ ኚዚያም ወደ ዘቊቹ ክፍል ይመልሷ቞ው ነበር።
ንጉሡ ራሱን ስላዋሚደ ዹይሖዋ ቁጣ ኚእሱ ተመለሰፀ ሙሉ በሙሉም አላጠፋ቞ውም። በተጚማሪም በይሁዳ አንዳንድ መልካም ነገሮቜ ተገኝተው ነበር።
ንጉሥ ሮብዓም በኢዚሩሳሌም ሥልጣኑን አጠናክሮ መግዛቱን ቀጠለፀ ሮብዓም በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 41 ዓመት ነበርፀ እሱም ይሖዋ ስሙ እንዲኖርባት ኚእስራኀል ነገዶቜ ሁሉ መካኚል በመሚጣት ኹተማ በኢዚሩሳሌም ሆኖ 17 ዓመት ገዛ። ዚንጉሡም እናት ናዕማ ዚተባለቜ አሞናዊት ነበሚቜ።
ሆኖም ይሖዋን ለመፈለግ ኚልቡ ቆርጩ ስላልተነሳ ክፉ ነገር አደሚገ።
ኚመጀመሪያ አንስቶ እስኚ መጚሚሻ ድሚስ ያለው ዚሮብዓም ታሪክ ነቢዩ ሞማያህና ባለ ራእዩ ኢዶ በትውልድ ሐሹግ መዝገቡ ላይ ባሰፈሩት ጜሑፍ ውስጥ ይገኝ ዹለም? በሮብዓምና በኢዮርብዓም መካኚል ምንጊዜም ጊርነት ይካሄድ ነበር።
በመጚሚሻም ሮብዓም ኚአባቶቹ ጋር አንቀላፋፀ በዳዊት ኹተማም ተቀበሚፀ በእሱም ምትክ ልጁ አቢያህ ነገሠ።
ኢዮሳፍጥ ብዙ ሀብትና ታላቅ ክብር አገኘፀ ይሁንና ኚአክዓብ ጋር በጋብቻ ተዛመደ።
ኹተወሰኑ ዓመታት በኋላም በሰማርያ ወደሚገኘው ወደ አክዓብ ወሚደፀ አክዓብም ለኢዮሳፍጥና አብሚውት ለነበሩት ሰዎቜ እጅግ ብዙ በግና ኚብት መሥዋዕት አደሚገ። ደግሞም በራሞትጊልያድ ላይ እንዲዘምት ገፋፋው።
ኚዚያም ዚእስራኀል ንጉሥ አክዓብ ዚይሁዳን ንጉሥ ኢዮሳፍጥን “ወደ ራሞትጊልያድ ኚእኔ ጋር አብሚህ ትሄዳለህ?” አለው። እሱም “እኔ ማለት እኮ አንተ ማለት ነህፀ ሕዝቀም ሕዝብህ ነውፀ በጊርነቱም አብሚንህ እንሰለፋለን” አለው።
ሆኖም ኢዮሳፍጥ ዚእስራኀልን ንጉሥ “እባክህ፣ በመጀመሪያ ይሖዋ ምን እንደሚል ጠይቅ” አለው።
በመሆኑም ዚእስራኀል ንጉሥ 400 ዹሚሆኑ ነቢያትን አንድ ላይ ሰብስቊ “ራሞትጊልያድን ለመውጋት ልዝመት ወይስ ይቅርብኝ?” አላ቞ው። እነሱም “ዝመትፀ እውነተኛው አምላክ በንጉሡ እጅ አሳልፎ ይሰጣታል” አሉት።
ኚዚያም ኢዮሳፍጥ “በዚህ ቊታ ዹይሖዋ ነቢይ ዹለም? ካለ በእሱም አማካኝነት እንጠይቅ” አለ።
በዚህ ጊዜ ዚእስራኀል ንጉሥ ኢዮሳፍጥን “በእሱ አማካኝነት ይሖዋን ልንጠይቅ ዚምንቜልበት አንድ ሰው ይቀራልፀ ሆኖም ሁልጊዜ ስለ እኔ መጥፎ ነገር እንጂ መልካም ነገር ፈጜሞ ስለማይተነብይ በጣም እጠላዋለሁ። እሱም ዹይምላ ልጅ ሚካያህ ነው” አለው። ኢዮሳፍጥ ግን “ንጉሡ እንዲህ ሊል አይገባም” አለ።