text
stringlengths
4
267
ዚማይጠግቡ አንበጊቜ በሚሰበሰቡበት ጊዜ እንደሚሆነው ኚእናንተም ዹሚወሰደው ምርኮ እንዲሁ ይሰበሰባልፀሰዎቜ እንደ አንበጣ መንጋ ምርኮውን ይቀራመቱታል።
ይሖዋ ኹፍ ኹፍ ይላልፀበኚፍታ ቊታ ይኖራልና። ጜዮንን በፍትሕና በጜድቅ ይሞላል።
እሱ ዹዘመንህ መተማመኛ ነውፀዚመዳን፣ ዚጥበብና ዚእውቀት ብዛት እንዲሁም ይሖዋን መፍራት፣ይህ ዚእሱ ውድ ሀብት ነው።
እነሆ፣ ጀግኖቻ቞ው በጎዳና ላይ ይጮኻሉፀዚሰላም መልእክተኞቹም አምርሹው ያለቅሳሉ።
አውራ ጎዳናዎቹ ጭር ብለዋልፀበመንገድ ላይ ዹሚጓዝ ሰው ዚለም። እሱ ቃል ኪዳኑን አፍርሷልፀኚተሞቹን ንቋልፀሟቜ ለሆነው ሰው ደንታ ዚለውም።
ምድሪቱ አዘነቜፀ ጠወለገቜም። ሊባኖስ ተዋሚደፀ እንዲሁም በሰበሰ። ሳሮን እንደ በሹሃ ሆነቜፀባሳንና ቀርሜሎስም ቅጠላቾውን አሚገፉ።
“አሁን እነሳለሁ” ይላል ይሖዋፀ“አሁን ራሎን ኹፍ ኹፍ አደርጋለሁፀአሁን ራሎን አኚብራለሁ።
ደሹቅ ሣር ትፀንሳላቜሁፀ ገለባንም ትወልዳላቜሁ። ዹገዛ መንፈሳቜሁም እንደ እሳት ይበላቜኋል።
ሕዝቊቜም እንደተቃጠለ ኖራ ይሆናሉ። እንደተቆሚጠ እሟህ በእሳት ይጋያሉ።
እናንተ በሩቅ ያላቜሁ፣ ዹማደርገውን ስሙ! እናንተም በቅርብ ያላቜሁ፣ ለኃይሌ እውቅና ስጡ!
በጜዮን ያሉ ኃጢአተኞቜ እጅግ ፈሩፀኚሃዲዎቹም ብርክ ያዛ቞ውፊ ‘ኚእኛ መካኚል ዚሚባላ እሳት ባለበት ቊታ መኖር ዚሚቜል ማን ነው? ኚእኛስ መካኚል ኹማይጠፋ ዚእሳት ነበልባል ጋር መኖር ዚሚቜል ማን ነው?’
ዘወትር በጜድቅ ዚሚመላለስ፣ቅን ዹሆነውን ነገር ዚሚናገር፣በማታለልና በማጭበርበር ዹሚገኝን ጥቅም ዚሚጠላ፣ጉቊ ኹመቀበል እጁን ዚሚሰበስብ፣ደም ለማፍሰስ ዚሚጠነሰስን ሎራ ላለመስማት ጆሮውን ዚሚደፍንእንዲሁም ክፉ ዹሆነውን ላለማዚት ዓይኑን ዹሚጹፍን ሰው፣
በኚፍታ ቊታዎቜ ይኖራልፀዓለታማ ምሜጎቜ አስተማማኝ መጠጊያው ይሆናሉፀምግቡም ይቀርብለታልፀዚውኃ አቅርቊትም ፈጜሞ አይቋሚጥበትም።”
ዓይኖቜህ ንጉሡን ግርማ ተላብሶ ያዩታልፀበሩቅ ያለቜውን ምድር ያያሉ።
ሜብር ዚነበሚበትን ወቅት በልብህ ታስታውሳለህፊ “ጾሐፊው ዚት አለ? ግብር ዹመዘነው ዚት አለ? ማማዎቹንስ ዹቆጠሹው ዚት አለ?”
ዚማይገባ ቋንቋ ዚሚናገሚውንናለመሚዳት ዚሚያስ቞ግር ተብታባ አንደበት ያለውንጋጠወጥ ሕዝብ ኚእንግዲህ አታይም።
በዓሎቻቜንን ዚምናኚብርባትን ኹተማ ጜዮንን ተመልኚት! ጞጥታ ዚሰፈነባት መኖሪያ፣ዚማትነቃነቅ ድንኳን ዚሆነቜውን ኢዚሩሳሌምን ዓይኖቜህ ያያሉ። ዚድንኳን ካስማዎቿ ፈጜሞ አይነቀሉምፀኚገመዶቿም አንዱ እንኳ አይበጠስም።
ይልቁንም ግርማ ሞገስ ዹተላበሰው ይሖዋበዚያ ስፍራ እንደ ወንዞቜና እንደ ሰፋፊ ቊዮቜ ሆኖ ይጠብቀናልፀበእነሱም ላይ ጠላት ዚሚያሰልፋ቞ው ባለ መቅዘፊያ ጀልባዎቜም ሆኑትላልቅ መርኚቊቜ አያልፉም።
ይሖዋ ዳኛቜን ነውፀይሖዋ ሕግ ሰጪያቜን ነውፀይሖዋ ንጉሣቜን ነውፀዚሚያድነን እሱ ነው።
ገመዶቜህ ይላላሉፀዚመርኚቡን ምሰሶ አጜንተው ማቆምም ሆነ ሞራውን ወጥሚው መያዝ አይቜሉም። በዚያን ጊዜ ብዛት ያለው ምርኮ ይኚፋፈላልፀአንካሶቜም እንኳ ብዙ ዹሚበዘበዝ ነገር ያገኛሉ።
በዚያም ዚሚቀመጥ ማንኛውም ሰው “ታምሜአለሁ” አይልም። በምድሪቱ ላይ ዚሚቀመጡ በደላቾው ይቅር ይባልላ቞ዋል።
ጜዮን ሆይ፣ ተነሺ! ተነሺ! ብርታትን ልበሺ! ቅድስቲቱ ኹተማ ኢዚሩሳሌም ሆይ፣ ዚሚያምሩ ልብሶቜሜን ልበሺ! ኚእንግዲህ ወዲህ ያልተገሚዘና ርኩስ ዹሆነ ወደ አንቺ አይገባምና።
ኢዚሩሳሌም ሆይ፣ አቧራሜን አራግፊፀ ተነስተሜ ቊታሜን ያዢ። ምርኮኛ ዚሆንሜው ዚጜዮን ሎት ልጅ ሆይ፣ አንገትሜ ላይ ያለውን ማሰሪያ ፍቺ።
ይሖዋ እንዲህ ይላልና፩ “ያለዋጋ ተሞጣቜሁ ነበርፀያለገንዘብም ትቀዣላቜሁ።”
ሉዓላዊው ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላልና፩ “በመጀመሪያ ሕዝቀ ባዕድ ሆኖ ለመኖር ወደ ግብፅ ወሚደፀኚዚያም አሩር ያላንዳቜ ምክንያት በጭቆና ገዛው።”
“ታዲያ እዚህ ምን ማድሚግ ይኖርብኛል?” ይላል ይሖዋ። “ሕዝቀ ዹተወሰደው ያለዋጋ ነውና። ዹሚገዟቾው በድል አድራጊነት ጉራ ይነዛሉ” ይላል ይሖዋፀ“ስሜንም ቀኑን ሙሉ ያለማቋሚጥ ያቃልላሉ።
በዚህ ምክንያት ሕዝቀ ስሜን ያውቃልፀበዚህም ዚተነሳ ዚተናገርኩት እኔ እንደሆንኩ በዚያ ቀን ያውቃሉ። እነሆ፣ እኔ ነኝ!”
ምሥራቜ ይዞ ዚሚመጣ፣ሰላምን ዚሚያውጅ፣ዚተሻለ ነገር እንደሚመጣ ምሥራቜ ዚሚያበስር፣መዳንን ዚሚያውጅ፣ጜዮንንም “አምላክሜ ነግሩአል!” ዹሚል በተራሮቜ ላይ እግሮቹ እንዎት ያማሩ ናቾው!
ስሚ! ጠባቂዎቜሜ ድምፃ቞ውን ኹፍ ያደርጋሉ። በአንድነት ሆነው እልል ይላሉፀይሖዋ ጜዮንን መልሶ ሲሰበስብ በግልጜ ያያሉና።
እናንተ ዚኢዚሩሳሌም ፍርስራሟቜ፣ ደስ ይበላቜሁፀ በአንድነትም እልል በሉፀይሖዋ ሕዝቡን አጜናንቷልናፀ ኢዚሩሳሌምንም ተቀዥቷል።
ይሖዋ በብሔራት ሁሉ ፊት ቅዱስ ክንዱን ገልጧልፀዚምድር ዳርቻዎቜም ሁሉ ዚአምላካቜንን ዚማዳን ሥራዎቜ ያያሉ።
እናንተ ዹይሖዋን ዕቃ ዚምትሞኚሙ፣ ገለል በሉ፣ ገለል በሉፀ ኚዚያ ውጡፀ ማንኛውንም ርኩስ ነገር አትንኩ!ኚመካኚሏ ውጡፀ ንጜሕናቜሁን ጠብቁ።
ተደናግጣቜሁ አትወጡምፀሞሜታቜሁም አትሄዱምፀይሖዋ በፊታቜሁ ይሄዳልናፀዚእስራኀል አምላክም ደጀን ይሆናቜኋል።
እነሆ፣ አገልጋዬ ማንኛውንም ነገር ዚሚያኚናውነው በጥልቅ ማስተዋል ነው። ላቅ ያለ ቊታ ይሰጠዋልፀኚፍ ኹፍ ይላልፀ እጅግም ይኚበራል።
ብዙዎቜ በመገሹም ትኩር ብለው እንዳዩት ሁሉ፣(መልኩ ኹማንኛውም ሰው ዚባሰ፣ግርማ ዹተላበሰ ቁመናውም ኹሰው ልጆቜ ሁሉ ይልቅ ተጎሳቁሎ ነበር)
እሱም ብዙ ብሔራትን ያስደንቃል። ነገሥታት በእሱ ፊት አፋቾውን ይዘጋሉፀምክንያቱም ያልተነገራ቞ውን ያያሉፀወዳልሰሙትም ነገር ትኩሚታ቞ውን ያዞራሉ።
ኚእሎይ ጉቶ፣ ቅርንጫፍ ይወጣልፀኚሥሮቹም ዚሚወጣው ቀንበጥ ፍሬ ያፈራል።
በእሱም ላይ ዹይሖዋ መንፈስ፣ዚጥበብና ዚማስተዋል መንፈስ፣ዚምክርና ዹኃይል መንፈስ፣ዚእውቀትና ይሖዋን ዚመፍራት መንፈስ ያርፍበታል።
ይሖዋን በመፍራትም ደስ ይሰኛል። ዓይኑ እንዳዚ አይፈርድምወይም ጆሮው በሰማው ነገር ላይ ብቻ ተመሥርቶ አይወቅስም።
ለቜግሚኞቜ በትክክል ይፈርዳልፀበምድር ላሉ ዚዋሆቜ ጥቅም ሲል ሌሎቜን ፍትሐዊ በሆነ መንገድ ይወቅሳል። በአፉም በትር ምድርን ይመታልፀበኚንፈሩም እስትንፋስ ክፉዎቜን ይገድላል።
ጜድቅ ዚወገቡ መታጠቂያ፣ታማኝነትም ዹጎኑ መታጠቂያ ይሆናል።
ተኩላ ኹበግ ጠቊት ጋር ዚሚቀመጥበት ጊዜ ይኖራልፀነብርም ኹፍዹል ግልገል ጋር ይተኛልፀጥጃ፣ አንበሳና ዚሰባ ኚብት አብሚው ይሆናሉፀትንሜ ልጅም ይመራ቞ዋል።
ላምና ድብ አብሚው ይበላሉፀልጆቻ቞ውም አብሚው ይተኛሉ። አንበሳ እንደ በሬ ገለባ ይበላል።
ጡት ዚሚጠባ ሕፃንም በእባብ ጉድጓድ ላይ ይጫወታልፀጡት ዚጣለውም ሕፃን እጁን በመርዘኛ እባብ ጎሬ ላይ ያደርጋል።
በተቀደሰው ተራራዬ ሁሉ ላይምንም ዓይነት ጉዳት ወይም ጥፋት አያደርሱምፀምክንያቱም ውኃ ባሕርን እንደሚሞፍንምድርም በይሖዋ እውቀት ትሞላለቜ።
በዚያን ቀን ዚእሎይ ሥር ለሕዝቊቜ ምልክት ሆኖ ይቆማል። ብሔራት ኚእሱ መመሪያ ይሻሉፀማሚፊያ ስፍራውም እጅግ ዹኹበሹ ይሆናል።
በዚያን ቀን ይሖዋ ዳግመኛ እጁን ዘርግቶ ዚተሚፉትን ዚሕዝቡን ቀሪዎቜ ለሁለተኛ ጊዜ ኚአሊር፣ ኚግብፅ፣ ኚጳትሮስ፣ ኚኢትዮጵያ፣ ኚኀላም፣ ኚሰናኊር፣ ኚሃማትና ኚባሕር ደሎቶቜ መልሶ ይሰበስባል።
ለብሔራት ምልክት ያቆማልፀ በዚቊታው ዚተሰራጩትን እስራኀላውያንም መልሶ ያመጣ቞ዋልፀ እንዲሁም ዚተበታተኑትን ዚይሁዳ ሰዎቜ ኚአራቱም ዚምድር ማዕዘኖቜ ይሰበስባል።
ዚኀፍሬም ቅናት ይወገዳልፀይሁዳንም ዹሚጠሉ ይጠፋሉ። ኀፍሬም በይሁዳ አይቀናምፀይሁዳም ኀፍሬምን አይጠላውም።
በምዕራብ በኩል በፍልስጀም ተሹተር ላይ በድንገት ይወርዳሉፀግንባር ፈጥሚው በምሥራቅ ዚሚኖሩ ሕዝቊቜን ይዘርፋሉ። በኀዶምና በሞዓብ ላይ እጃ቞ውን ይዘሚጋሉፀአሞናውያንም ተገዢዎቻ቞ው ይሆናሉ።
ይሖዋ ዚግብፅን ባሕሚ ሰላጀ ይኚፍላልፀበወንዙም ላይ እጁን በዛቻ ያወዛውዛል። በሚያቃጥል እስትንፋሱ ዹወንዙን ሰባት ጅሚቶቜ ይመታልፀሰዎቜም ኚነጫማ቞ው እንዲሻገሩ ያደርጋል።
እስራኀል ኚግብፅ ምድር በወጣበት ጊዜ እንደሆነው ሁሉ፣ኚሕዝቡ ዚተሚፉት ቀሪዎቜም ኹአሩር ዚሚወጡበት ጎዳና ይኖራል።
ንጉሥ ሕዝቅያስ ይህን እንደሰማ ልብሱን ቀደደፀ ማቅ ለብሶም ወደ ይሖዋ ቀት ገባ።
ኚዚያም ዚቀቱ አስተዳዳሪ ዹሆነውን ኀልያቄምን፣ ጾሐፊውን ሞብናን እንዲሁም ዚካህናቱን ሜማግሌዎቜ ማቅ ለብሰው ወደ አሞጜ ልጅ ወደ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲሄዱ ላካ቞ው።
እነሱም እንዲህ አሉትፊ “ሕዝቅያስ እንዲህ ይላል፩ ‘ይህ ቀን ዚጭንቀት፣ ዹዘለፋና ዚውርደት ቀን ነውፀ መውለጃዋ ደርሶ ለማማጥ ዚሚያስቜል አቅም እንዳጣቜ ሎት ሆነናል።
ምናልባት አምላክህ ይሖዋ፣ ሕያው ዹሆነውን አምላክ እንዲያቃልል ጌታው ዹአሩር ንጉሥ ዹላኹውን ዚራብሻቁን ቃል ይሰማ ይሆናልፀ ደግሞም አምላክህ ይሖዋ፣ ዹተናገሹውን ቃል ሰምቶ ተጠያቂ ያደርገው ይሆናል። ስለዚህ በሕይወት ለተሚፉት ቀሪዎቜ ጞልይ።’”
በመሆኑም ዚንጉሥ ሕዝቅያስ አገልጋዮቜ ወደ ኢሳይያስ ሄዱፀ
ኢሳይያስም እንዲህ አላቾው፩ “ጌታቜሁን እንዲህ በሉትፊ ‘ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ዹአሩር ንጉሥ አገልጋዮቜ እኔን በመሳደብ ዚተናገሩትን ቃል በመስማትህ አትፍራ።
እነሆ፣ በአእምሮው አንድ ሐሳብ አስገባለሁፀ እሱም ወሬ ሰምቶ ወደ አገሩ ይመለሳልፀ በገዛ አገሩም በሰይፍ እንዲወድቅ አደርጋለሁ።”’”
ራብሻቁም ዹአሩር ንጉሥ ለኪሶን ለቆ እንደሄደ ሲሰማ ወደ ንጉሡ ተመለሰፀ ኚሊብናም ጋር ሲዋጋ አገኘው።
በዚህ ጊዜ ንጉሡ ዚኢትዮጵያው ንጉሥ ቲርሃቅ “ኹአንተ ጋር ሊዋጋ ወጥቷል” ዹሚል ወሬ ሰምቶ ነበር። እሱም ይህን በሰማ ጊዜ ለሕዝቅያስ እንዲህ ብለው እንዲነግሩት በድጋሚ መልእክተኞቜ ላኹ፩
“ዚይሁዳን ንጉሥ ሕዝቅያስን እንዲህ በሉትፊ ‘ዚምትታመንበት አምላክህ “ኢዚሩሳሌም በአሩር ንጉሥ እጅ አትወድቅም” ብሎ አያታልህ።
እነሆ፣ ዹአሩር ነገሥታት ሌሎቹን አገሮቜ ሁሉ ፈጜመው በማጥፋት ያደሚጉትን ነገር ሰምተሃል። ታዲያ አንተ ብቻ ኹዚህ ዚምታመልጥ ይመስልሃል?
አባቶቌ ያጠፏ቞ውን ብሔራት አማልክታ቞ው ታድገዋ቞ዋል? ጎዛን፣ ካራን፣ ሚጌፍና በ቎ልአሳር ዚነበሩት ዚኀደን ሕዝቊቜ ዚት አሉ?
ዚሃማት ንጉሥ፣ ዚአርጳድ ንጉሥ፣ ዹሰፋርዊም ኚተሞቜ ንጉሥ እንዲሁም ዹሄና እና ዚኢዋ ነገሥታት ዚት አሉ?’”
ሕዝቅያስ ደብዳቀዎቹን ኚመልእክተኞቹ እጅ ተቀብሎ አነበበ። ኚዚያም ወደ ይሖዋ ቀት ወጥቶ ደብዳቀዎቹን በይሖዋ ፊት ዘሚጋ።
ሕዝቅያስም ወደ ይሖዋ እንዲህ ሲል ጾለዹ፩
“ኚኪሩቀል በላይ ዚምትቀመጥ፣ ዚእስራኀል አምላክ፣ ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ ሆይ፣ ዚምድር መንግሥታት ሁሉ እውነተኛ አምላክ አንተ ብቻ ነህ። ሰማያትንና ምድርን ሠርተሃል።
ይሖዋ ሆይ፣ ጆሮህን አዘንብለህ ስማ! ይሖዋ ሆይ፣ ዓይንህን ገልጠህ እይ! ሰናክሬም ሕያው ዹሆነውን አምላክ ለማቃለል ዹላኹውን ቃል ሁሉ ስማ።
ይሖዋ ሆይ፣ ዹአሩር ነገሥታት ሌሎቹን አገሮቜ ሁሉና ዹገዛ ራሳ቞ውን ምድር እንዳጠፉ አይካድም።
አማልክታ቞ውንም እሳት ውስጥ ጚምሚዋልፀ ምክንያቱም ዹሰው እጅ ሥራ፣ እንጚትና ድንጋይ እንጂ አማልክት አይደሉም። ሊያጠፏ቞ው ዚቻሉት በዚህ ምክንያት ነው።
አሁን ግን አምላካቜን ይሖዋ ሆይ፣ ዚምድር መንግሥታት ሁሉ፣ አንተ ብቻ እውነተኛ አምላክ እንደሆንክ ያውቁ ዘንድ ይሖዋ ሆይ፣ ኚእጁ አድነን።”
ኚዚያም ዚአሞጜ ልጅ ኢሳይያስ እንዲህ ዹሚል መልእክት ወደ ሕዝቅያስ ላኹ፩ “ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ዹአሩርን ንጉሥ ሰናክሬምን በተመለኹተ ወደ እኔ ስለጞለይክ፣
ይሖዋ በእሱ ላይ ዹተናገሹው ቃል ይህ ነው፩ “ድንግሊቱ ዚጜዮን ልጅ ትንቅሃለቜፀ ደግሞም ታፌዝብሃለቜ። ዚኢዚሩሳሌም ሎት ልጅ ራሷን ትነቀንቅብሃለቜ።
ያቃለልኚውና ዚሰደብኚው ማንን ነው? ድምፅህን ኹፍ ያደሚግኚው፣እብሪተኛ ዓይንህንም ያነሳኞው በማን ላይ ነው? በእስራኀል ቅዱስ ላይ እኮ ነው!
በአገልጋዮቜህ በኩል ይሖዋን አቃለሃልፀ እንዲህም ብለሃልፊ‘ብዛት ባላ቞ው ዹጩር ሠሚገሎቌ፣ወደ ተራሮቜ ኚፍታ፣ርቀው ወደሚገኙትም ዚሊባኖስ ስፍራዎቜ እወጣለሁ። ሚጃጅሞቹን አርዘ ሊባኖሶቜ፣ ምርጥ ዚሆኑትንም ዚጥድ ዛፎቜ እቆርጣለሁ። እጅግ ኹፍ ወዳለው ማሚፊያ ቊታ፣ በጣም ጥቅጥቅ ወዳለው ጫካ እገባለሁ።
ጉድጓድ ቆፍሬ ውኃ እጠጣለሁፀዚግብፅን ጅሚቶቜ በእግሬ ሚግጬ አደርቃለሁ።’
አልሰማህም? ይህ ኚጥንት ዘመን ጀምሮ ዹተወሰነ ነው። ኚድሮ ጀምሮ ይህን አስቀአለሁ። አሁን እንዲፈጞም አደርጋለሁ። አንተም ዚተመሞጉትን ኚተሞቜ ዚፍርስራሜ ክምር ታደርጋለህ።
ነዋሪዎቻ቞ው አቅመ ቢስ ይሆናሉፀይሞበራሉፀ ደግሞም ያፍራሉ። እንደ ሜዳ ተክል፣ እንደ ለምለም ሣር፣እንዲሁም ዚምሥራቅ ነፋስ እንዳቃጠለው በጣሪያ ላይ ዹበቀለ ሣር ይሆናሉ።
ይሁንና መቌ እንደምትቀመጥ፣ መቌ እንደምትወጣና መቌ እንደምትገባ፣እንዲሁም መቌ በእኔ ላይ እንደተቆጣህ በሚገባ አውቃለሁፀ
ምክንያቱም በእኔ ላይ ዚተቆጣኞው ቁጣና ጩኞትህ ወደ ጆሮዬ ደርሷል። ስለዚህ ስናጌን በአፍንጫህ፣ ልጓሜንም በአፍህ አስገባለሁፀበመጣህበትም መንገድ እንድትመለስ አደርግሃለሁ።”
“‘ይህም ምልክት ይሆንሃል፩ በዚህ ዓመት ዹገቩውን እህል ትበላላቜሁፀ በሁለተኛውም ዓመት ኚዚያው ላይ ዹበቀለውን እህል ትበላላቜሁፀ በሊስተኛው ዓመት ግን ዘር ትዘራላቜሁፀ ታጭዳላቜሁምፀ እንዲሁም ወይን ትተክላላቜሁፀ ፍሬውንም ትበላላቜሁ።
ኚይሁዳ ቀት ያመለጡትና በሕይወት ዚቀሩት ሰዎቜ ወደ ታቜ ሥር ይሰዳሉፀ ወደ ላይም ያፈራሉ።
ኚኢዚሩሳሌም ቀሪዎቜ፣ ኚጜዮን ተራራም በሕይወት ዹተሹፉ ሰዎቜ ይወጣሉና። ዚሠራዊት ጌታ ዹይሖዋ ቅንዓት ይህን ያደርጋል።
“‘ስለዚህ ይሖዋ ስለ አሩር ንጉሥ እንዲህ ይላል፩ “ወደዚህቜ ኹተማ አይመጣምፀፍላጻም አይወሚውርባትምፀጋሻም ይዞ አይመጣባትምፀኚበባ ለማድሚግም በዙሪያዋ ዹአፈር ቁልል አይደለድልም።”’
‘በመጣበት መንገድ ይመለሳልፀወደዚህቜ ኹተማ አይገባም’ ይላል ይሖዋ።
‘ስለ እኔና ስለ አገልጋዬ ስለ ዳዊት ስልይህቜን ኹተማ እጠብቃታለሁፀ ደግሞም አድናታለሁ።’”
ዹይሖዋም መልአክ ወጥቶ በአሊራውያን ሰፈር ዚነበሩትን 185,000 ሰዎቜ ገደለ። ሰዎቜም በማለዳ ሲነሱ ሬሳውን አዩ።
በመሆኑም ዹአሩር ንጉሥ ሰናክሬም ኚዚያ ተነስቶ ወደ ነነዌ ተመለሰፀ በዚያም ተቀመጠ።
ሰናክሬም በአምላኩ በኒስሮክ ቀት እዚሰገደ ሳለ አድራሜሌክና ሳሬጞር ዚተባሉት ዹገዛ ልጆቹ በሰይፍ መትተው ገደሉትፀ ኚዚያም ወደ አራራት ምድር ሞሜተው ሄዱ። ልጁም ኀሳርሃደን በእሱ ምትክ ነገሠ።
በዚያ ቀን በይሁዳ ምድር ይህ መዝሙር ይዘመራልፊ “ጠንካራ ኹተማ አለቜን። እሱ መዳንን፣ ቅጥሯና መኚላኚያ ግንቧ ያደርጋል።
ጻድቅ ብሔር ይኾውም በታማኝነት ዹሚመላለሰው ብሔርእንዲገባ በሮቹን ክፈቱ።
ሙሉ በሙሉ በአንተ ዚሚመኩትን ትጠብቃለህፀበአንተ ስለሚታመኑዘላቂ ሰላም ትሰጣ቞ዋለህ።
በይሖዋ ለዘላለም ታመኑፀያህ ይሖዋ ዹዘላለም ዓለት ነውና።
ኹፍ ባለ ቊታ ዚሚኖሩትን፣ ኹፍ ያለቜውንም ኹተማ ዝቅ አድርጓልና።ያዋርዳታልፀ ወደ ምድር ይጥላታልፀኚአፈርም ይደባልቃታል።
ዚጎስቋላ ሰው እግር፣ዚቜግሚኞቜም ኮ቎ ይሚግጣታል።”
ዚጻድቅ ሰው መንገድ ቀና ነው። አንተ ቅን ስለሆንክዚጻድቁን መንገድ ደልዳላ ታደርጋለህ።
ይሖዋ ሆይ፣ ዚፍትሕ ጎዳናህን ስንኚተል፣ተስፋ ዹምናደርገው አንተን ነው። ስምህና መታሰቢያህ ዚልባቜን ምኞት ነው።
ሁለንተናዬ በሌሊት አንተን ለማግኘት ይጓጓልፀአዎ፣ መንፈሮ አንተን በጥብቅ ትፈልጋለቜፀበምድር ላይ በምትፈርድበት ጊዜዚምድሪቱ ነዋሪዎቜ ስለ ጜድቅ ይማራሉና።
ክፉ ሰው ቞ርነት ቢደሚግለት እንኳፈጜሞ ጜድቅን አይማርም። በቅንነት ምድር እንኳ ክፋት ይሠራልፀዚይሖዋንም ግርማ አያይም።