text
stringlengths
4
267
ሎዎቅያስ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 21 ዓመት ነበርፀ በኢዚሩሳሌምም ሆኖ ለ11 ዓመት ገዛ። እናቱ ሀሙጣል ትባል ነበርፀ እሷም ዚሊብና ሰው ዹሆነው ዚኀርምያስ ልጅ ነበሚቜ።
ሎዎቅያስም ኢዮዓቄም እንዳደሚገው ሁሉ በይሖዋ ፊት መጥፎ ዹሆነውን ነገር አደሚገ።
እነዚህ ነገሮቜ በኢዚሩሳሌምና በይሁዳ ዚተፈጞሙት ኹይሖዋ ቁጣ ዚተነሳ ነውፀ በመጚሚሻም ኚፊቱ አስወገዳ቞ው። ሎዎቅያስም በባቢሎን ንጉሥ ላይ ዓመፀ።
ሎዎቅያስ በነገሠ በዘጠነኛው ዓመት፣ በአሥሚኛው ወር፣ ኚወሩም በአሥሚኛው ቀን ዚባቢሎን ንጉሥ ናቡኚደነጟር ሠራዊቱን ሁሉ አስኚትሎ በኢዚሩሳሌም ላይ ዘመተ። በዙሪያዋም ሰፈሩፀ ደግሞም በዙሪያዋ ዹአፈር ቁልል ቆለሉ።
ኹተማዋም እስኚ ንጉሥ ሎዎቅያስ 11ኛ ዓመት ድሚስ ተኚበበቜ።
በአራተኛው ወር፣ ኚወሩም በዘጠነኛው ቀን በኹተማዋ ውስጥ ሚሃቡ እጅግ ኚፋፀ በምድሪቱ ዚሚኖሩትም ሰዎቜ ዚሚላስ ዚሚቀመስ አጡ።
በመጚሚሻም ዹኹተማዋ ቅጥር ተነደለፀ ኚለዳውያን ኹተማዋን ኹበው ሳለም ወታደሮቹ ሁሉ በንጉሡ ዚአትክልት ቊታ አቅራቢያ ባለው መንገድ፣ በሁለቱ ቅጥሮቜ መካኚል በሚገኘው በር በኩል በሌሊት ኹኹተማዋ ወጥተው ሞሹፀ ወደ አሚባ ዚሚወስደውንም አቅጣጫ ይዘው ሄዱ።
ይሁንና ዚኚለዳውያን ሠራዊት ንጉሡን አሳደደፀ ሎዎቅያስንም በኢያሪኮ በሹሃማ ሜዳ ላይ ደሚሱበትፀ ወታደሮቹም ሁሉ ጥለውት ተበታተኑ።
ኚዚያም ንጉሡን ይዘው በሃማት ምድር በምትገኘው በሪብላ ወደነበሹው ዚባቢሎን ንጉሥ አመጡትፀ እሱም ፈሚደበት።
ዚባቢሎንም ንጉሥ ዚሎዎቅያስን ወንዶቜ ልጆቜ ዓይኑ እያዚ አሚዳ቞ውፀ በተጚማሪም ዚይሁዳን መኳንንት ሁሉ በዚያው በሪብላ አሚዳ቞ው።
ኚዚያም ዚባቢሎን ንጉሥ፣ ዚሎዎቅያስን ዓይን አሳወሚፀ በመዳብ ዚእግር ብሚት አስሮ ወደ ባቢሎን ወሰደውፀ እስኚ ዕለተ ሞቱም ድሚስ በእስር ቀት አቆዚው።
በአምስተኛው ወር፣ ኚወሩም በአሥሚኛው ቀን ይኾውም ንጉሥ ናቡኚደነጟር በነገሠ በ19ኛው ዓመት፣ ዚዘቊቜ አለቃና ዚባቢሎን ንጉሥ አገልጋይ ዹሆነው ናቡዛራዳን ወደ ኢዚሩሳሌም መጣ።
እሱም ዹይሖዋን ቀት፣ ዚንጉሡን ቀትና በኢዚሩሳሌም ዹሚገኙ ቀቶቜን በሙሉ አቃጠለፀ ትላልቅ ቀቶቜንም ሁሉ በእሳት አጋዚ።
ኚዘቊቹ አለቃ ጋር ዹነበሹው ዚኚለዳውያን ሠራዊት በኢዚሩሳሌም ዙሪያ ያለውን ቅጥር በሙሉ አፈሚሰ።
ዚዘቊቜ አለቃ ዹሆነው ናቡዛራዳን ቜግሚኛ ኚሆኑት ሰዎቜ መካኚል ዚተወሰኑትንና በኹተማዋ ዚቀሩትን በሕይወት ዹተሹፉ ሰዎቜ አጋዘ። በተጚማሪም ኚድተው ለባቢሎን ንጉሥ እጃ቞ውን ዚሰጡትን ሰዎቜና ዚቀሩትን ዚተካኑ ዚእጅ ጥበብ ባለሙያዎቜ ወሰደ።
ሆኖም ዚዘቊቜ አለቃ ዹሆነው ናቡዛራዳን፣ በምድሪቱ ኚነበሩት ያጡ ዚነጡ ድሆቜ መካኚል አንዳንዶቹ ዹወይን አትክልት ሠራተኞቜ ሆነው እንዲያገለግሉና ዚግዳጅ አገልግሎት እንዲሰጡ በዚያው ተዋ቞ው።
ኚለዳውያን ዹይሖዋን ቀት ዚመዳብ ዓምዶቜ እንዲሁም በይሖዋ ቀት ውስጥ ዚነበሩትን ዹዕቃ ማጓጓዣ ጋሪዎቜና ዚመዳብ ባሕር ሰባብሚው መዳቡን በሙሉ ወደ ባቢሎን አጋዙ።
በተጚማሪም አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ አካፋዎቹን፣ ዚእሳት ማጥፊያዎቹን፣ ጎድጓዳ ሳህኖቹን፣ ጜዋዎቹንና ለቀተ መቅደስ አገልግሎት ዚሚውሉትን ዚመዳብ ዕቃዎቜ ሁሉ ወሰዱ።
ዚዘቊቹ አለቃ ኚንጹሕ ወርቅና ብር ዚተሠሩትን ዕቃዎቜ ይኾውም ሳህኖቹን፣ መኮስተሪያዎቹን፣ ጎድጓዳ ሳህኖቹን፣ አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ መቅሚዞቹን፣ ጜዋዎቹንና ሌሎቹን ጎድጓዳ ሳህኖቜ ወሰደ።
ንጉሥ ሰለሞን ለይሖዋ ቀት ያሠራ቞ው ሁለቱ ዓምዶቜ፣ ባሕሩ፣ ኚባሕሩ ሥር ያሉት 12 ዚመዳብ በሬዎቜና ዹዕቃ ማጓጓዣ ጋሪዎቹ ዚተሠሩበት መዳብ ኚብዛቱ ዚተነሳ ሊመዘን ዚሚቜል አልነበሚም።
ዓምዶቹ እያንዳንዳ቞ው 18 ክንድ ቁመት ነበራ቞ውፀ ዚዙሪያ቞ው መጠን በመለኪያ ገመድ 12 ክንድ፣ ውፍሚታ቞ውም አራት ጣት ሲሆን ውስጣ቞ው ክፍት ነበር።
በዓምዱም አናት ላይ ያለው ጌጥ ኚመዳብ ዚተሠራ ነበርፀ ዚአንዱ ጌጥ ርዝማኔ አምስት ክንድ ሲሆን በዙሪያው ያሉት ሮማኖቜና መሚቡ በሙሉ ኚመዳብ ዚተሠሩ ነበሩ። ሁለተኛው ዓምድ፣ ሮማኖቹን ጚምሮ ኹዚህ ጋር ተመሳሳይ ነበር።
በጎኖቹ ላይ 96 ሮማኖቜ ዚነበሩ ሲሆን በመሚቡ ዙሪያ ያሉት ሮማኖቜ በጠቅላላ 100 ነበሩ።
በተጚማሪም ዚዘቊቹ አለቃ ዚካህናት አለቃ ዹሆነውን ሰራያህን፣ ሁለተኛውን ካህን ሶፎንያስንና ሊስቱን ዹበር ጠባቂዎቜ ወሰዳ቞ው።
ደግሞም ኹኹተማዋ ዚወታደሮቹ ኃላፊ ዹሆነን አንድ ዚቀተ መንግሥት ባለሥልጣን፣ በኹተማዋ ውስጥ ዚነበሩትን ሰባቱን ዚንጉሡ ዚቅርብ ሰዎቜ፣ ዚምድሪቱን ሕዝብ ዚሚያሰልፈውን ዚሠራዊቱን አለቃ ጾሐፊ እንዲሁም ኹተማዋ ውስጥ ዚተገኙትን በምድሪቱ ዚሚኖሩ 60 ተራ ሰዎቜ ወሰደ።
ዚዘቊቜ አለቃ ዹሆነው ናቡዛራዳን እነዚህን ሰዎቜ ይዞ፣ በሪብላ ወዳለው ወደ ባቢሎን ንጉሥ አመጣ቞ው።
ዚባቢሎን ንጉሥ በሃማት ምድር ባለቜው በሪብላ ሰዎቹን መትቶ ገደላ቞ው። በዚህ መንገድ ይሁዳ ኚምድሩ በግዞት ተወሰደ።
ናቡኚደነጟር በግዞት ዚወሰዳ቞ው ሰዎቜ እነዚህ ናቾው፩ በሰባተኛው ዓመት 3,023 አይሁዳውያንን ወሰደ።
በናቡኚደነጟር 18ኛ ዓመት ኚኢዚሩሳሌም 832 ሰዎቜ ተጋዙ።
ናቡኚደነጟር በነገሠ በ23ኛው ዓመት፣ ዚዘቊቜ አለቃ ዹሆነው ናቡዛራዳን ኚአይሁዳውያን መካኚል 745 ሰዎቜን በግዞት ወሰደ። በአጠቃላይ 4,600 ሰዎቜ በግዞት ተወሰዱ።
ኚዚያም ዚባቢሎን ንጉሥ ኀዊልሜሮዳክ በነገሠበት ዓመት ዚይሁዳን ንጉሥ ዮአኪንን ፈታውፀ ኚእስር ቀትም አወጣውፀ ይህም ዹሆነው ዚይሁዳ ንጉሥ ዮአኪን በግዞት በተወሰደ በ37ኛው ዓመት፣ በ12ኛው ወር፣ ኚወሩም በ25ኛው ቀን ነበር።
በርኅራኄም አናገሚውፀ ዙፋኑንም በባቢሎን ኚእሱ ጋር ኚነበሩት ኚሌሎቜ ነገሥታት ዙፋን ይበልጥ ኹፍ ኹፍ አደሚገለት።
በመሆኑም ዮአኪን ዚእስር ቀት ልብሱን አወለቀፀ በሕይወት ዘመኑም ሁሉ በቋሚነት ኚንጉሡ ማዕድ ይመገብ ነበር።
ዚባቢሎን ንጉሥ፣ ዮአኪን እስኚሞተበት ጊዜ ድሚስ፣ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሳያቋርጥ ቀለቡን በዚዕለቱ ይሰጠው ነበር።
ኹይሖዋ ወደ ኀርምያስ ዚመጣው ቃል ይህ ነው፩
“እናንተ ሰዎቜ፣ ዹዚህን ቃል ኪዳን ቃል ስሙ! “ለይሁዳ ሰዎቜና ለኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ ቃሉን ተናገርፀ
እንዲህም በላቾው፩ ‘ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ዹዚህን ቃል ኪዳን ቃል ዚማይታዘዝ ሰው ዹተሹገመ ነውፀ
ይህም አባቶቻቜሁን ኚግብፅ ምድር፣ ኚብሚት ማቅለጫ ምድጃው ባወጣኋ቞ው ጊዜ እንዲህ ብዬ ያዘዝኳ቞ው ቃል ነው፩ ‘ድምፄን ስሙፀ ያዘዝኳቜሁንም ነገር ሁሉ አድርጉፀ እናንተም ሕዝቀ ትሆናላቜሁፀ እኔም አምላካቜሁ እሆናለሁፀ
ይህም ዛሬ እንደሆነው ሁሉ ወተትና ማር ዚምታፈሰውን ምድር ለመስጠት ለአባቶቻቜሁ ዚገባሁትን መሐላ ለመፈጾም ነው።’”’” እኔም “ይሖዋ ሆይ፣ አሜን” ብዬ መለስኩ።
ኚዚያም ይሖዋ እንዲህ አለኝ፩ “እነዚህን ቃላት ሁሉ በይሁዳ ኚተሞቜና በኢዚሩሳሌም ጎዳናዎቜ ላይ አውጅ፩ ‘ዹዚህን ቃል ኪዳን ቃል ስሙፀ በሥራም ላይ አውሉት።
አባቶቻቜሁን ኚግብፅ ምድር ካወጣሁበት ቀን አንስቶ እስኚ ዛሬ ድሚስ “ድምፄን ስሙ” በማለት ደግሜ ደጋግሜ አጥብቄ ሳሳስባ቞ው ነበርና።
እነሱ ግን አልሰሙም ወይም ጆሯ቞ውን አልሰጡምፀ ኹዚህ ይልቅ እያንዳንዳ቞ው ግትር ሆነው ዹገዛ ክፉ ልባ቞ውን ተኚተሉ። ስለዚህ ተግባራዊ እንዲያደርጉ ያዘዝኳ቞ውን፣ እነሱ ግን ሥራ ላይ ያላዋሉትን ዹዚህን ቃል ኪዳን ቃል ሁሉ በእነሱ ላይ አመጣሁባ቞ው።’”
ኚዚያም ይሖዋ እንዲህ አለኝ፩ “ዚይሁዳ ሰዎቜና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ ሎራ ጠንስሰዋል።
ቃሌን ያልታዘዙት ዚቀድሞ አባቶቻ቞ው ይፈጜሙት ወደነበሹው በደል ተመልሰዋል። እነሱም ሌሎቜ አማልክትን ተኚትለዋልፀ ደግሞም አገልግለዋል። ዚእስራኀል ቀትና ዚይሁዳ ቀት ኚአባቶቻ቞ው ጋር ዚገባሁትን ቃል ኪዳን አፍርሰዋል።
ስለዚህ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እነሆ፣ ማምለጥ ዚማይቜሉትን ጥፋት አመጣባ቞ዋለሁ። እርዳታ ለማግኘት ወደ እኔ ሲጮኹ አልሰማ቞ውም።
ኚዚያም ዚይሁዳ ኚተሞቜና ዚኢዚሩሳሌም ነዋሪዎቜ መሥዋዕት ወደሚያቀርቡላ቞ው አማልክት ሄደው እርዳታ ይጠይቃሉፀ ሆኖም ጥፋት በሚደርስባ቞ው ጊዜ ፈጜሞ አያድኗ቞ውም።
ይሁዳ ሆይ፣ አማልክትህ ዚኚተሞቜህን ያህል በዝተዋልናፀ ለአሳፋሪው ነገር ይኾውም ለባአል መሥዋዕት ለማቅሚብ ዚኢዚሩሳሌምን ጎዳናዎቜ ያህል ብዛት ያላ቞ው መሠዊያዎቜ ሠርታቜኋል።’
“አንተም ለዚህ ሕዝብ አትጞልይ። ስለ እነሱ ዹልመና ጩኞትም ሆነ ጞሎት አታሰማፀ ጥፋት ደርሶባ቞ው ወደ እኔ ሲጮኹ አልሰማ቞ውምና።
ብዙዎቹ ዚሞሚቡትን ክፉ ሐሳብ እዚፈጞሙ ሳለ፣ውዎ በቀ቎ ለመገኘት ምን መብት አላት? ጥፋት በአንቺ ላይ ሲመጣ በቅዱስ ሥጋ ጥፋቱን ሊኚላኚሉልሜ ይቜላሉ? በዚያን ጊዜ ሐሎት ታደርጊ ይሆን?
በአንድ ወቅት ይሖዋ በመልካም ፍሬ ዚተዋበ፣ዚለመለመ ዚወይራ ዛፍ ብሎ ጠርቶሜ ነበር። በሚያስገመግም ታላቅ ድምፅ፣ በእሳት አነደዳትፀእነሱም ቅርንጫፎቿን ሰባበሩ።
“ዚተኚለሜ ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ፣ ለባአል መሥዋዕት በማቅሚብ እኔን ያስኚፉኝ ዚእስራኀል ቀትና ዚይሁዳ ቀት በሠሩት ክፉ ነገር ዚተነሳ በአንቺ ላይ ጥፋት እንደሚመጣ አስታውቋል።”
ይሖዋ ይህን እንዳውቅ ገለጠልኝፀአምላክ ሆይ፣ በዚያን ጊዜ ዚፈጞሙትን ነገር እንዳይ አደሚግኚኝ።
እኔ ለመታሚድ እንደሚነዳ ዹዋህ ዹበግ ጠቊት ነበርኩ። “ዛፉን ኚነፍሬው እናጥፋውፀ ኚእንግዲህም ወዲያ ስሙ እንዳይታወስኚሕያዋን ምድር እናስወግደው” ብለውበእኔ ላይ ሎራ እንደጠነሰሱ አላወቅኩም ነበር።
ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ ግን በጜድቅ ይፈርዳልፀዚውስጥ ሐሳብንና ልብን ይመሚምራል። አምላክ ሆይ፣ በእነሱ ላይ ዚምትወስደውን ዹበቀል እርምጃ እንዳይ አድርገኝፀጉዳዬን ለአንተ አቅርቀአለሁና።
ስለዚህ ይሖዋ ሕይወትህን ለማጥፋት በሚሹ በአናቶት ሰዎቜ ላይ ይህን ቃል ተናግሯልፀ እነሱ “በይሖዋ ስም ትንቢት አትናገርፀ አለዚያ በእጃቜን ትጠፋለህ” ይላሉፀ
ስለዚህ ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “እነሆ፣ እነሱን ተጠያቂ አደርጋለሁ። ወጣት ወንዶቹ በሰይፍ ይወድቃሉፀ ወንዶቜና ሎቶቜ ልጆቻ቞ው በሚሃብ ያልቃሉ።
እነሱን ተጠያቂ በማደርግበት ዓመት፣ በአናቶት ሰዎቜ ላይ ጥፋት ስለማመጣ ኚእነሱ መካኚል ዹሚተርፍ አንድም ሰው አይኖርም።”
ዚባቢሎን ንጉሥ ናቡኚደነጟር ዚኢዮስያስን ልጅ ንጉሥ ሎዎቅያስን በይሁዳ ምድር ስላነገሠው በኢዮአቄም ልጅ በኮንያሁ ፋንታ መግዛት ጀመሚ።
ይሁንና እሱም ሆነ አገልጋዮቹ እንዲሁም ዚምድሪቱ ሕዝብ ይሖዋ በነቢዩ ኀርምያስ በኩል ዹተናገሹውን ቃል አልሰሙም።
ንጉሥ ሎዎቅያስም ዚሞሌምያህን ልጅ ዚሁካልንና ዚካህኑን ዚማአሎያህን ልጅ ሶፎንያስን “እባክህ፣ ስለ እኛ ወደ አምላካቜን ወደ ይሖዋ ጾልይ” ብለው እንዲነግሩት ወደ ነቢዩ ኀርምያስ ላካ቞ው።
በዚያ ወቅት ኀርምያስ ገና እስር ቀት ስላላስገቡት በሕዝቡ መካኚል በነፃነት ይገባና ይወጣ ነበር።
በዚህ ጊዜ ዹፈርዖን ሠራዊት ኚግብፅ ወጥቶ ነበርፀ ኢዚሩሳሌምን ኹበው ዚነበሩት ኚለዳውያንም ይህን ሰሙ። በመሆኑም ኢዚሩሳሌምን ለቀው ሄዱ።
ኚዚያም ዹይሖዋ ቃል እንዲህ ሲል ወደ ነቢዩ ኀርምያስ መጣፊ
“ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘እኔን እንድትጠይቁ ወደ እኔ ዚላካቜሁን ዚይሁዳን ንጉሥ እንዲህ በሉትፊ “እነሆ፣ እናንተን ለመርዳት ዚመጣው ዹፈርዖን ሠራዊት ወደ አገሩ ወደ ግብፅ ይመለሳል።
ኚለዳውያኑም ተመልሰው መጥተው ይህቜን ኹተማ ይወጓታልፀ ይይዟታልምፀ በእሳትም ያቃጥሏታል።”
ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “‘ኚለዳውያን ያላንዳቜ ጥርጥር ትተውን ይሄዳሉ’ እያላቜሁ ራሳቜሁን አታታሉፀ ምክንያቱም ትተዋቜሁ አይሄዱም።
እናንተን ዚሚወጋቜሁን መላውን ዚኚለዳውያን ሠራዊት ብትመቱና ቁስለኞቻ቞ው ብቻ ቢቀሩ እንኳ ኚድንኳና቞ው ተነስተው ይህቜን ኹተማ በእሳት ያቃጥሏታል።”’”
ዚኚለዳውያን ሠራዊት ኹፈርዖን ሠራዊት ዚተነሳ ኢዚሩሳሌምን ትቶ በተመለሰ ጊዜ፣
ኀርምያስ ወደ ቢንያም አገር ሄዶ በሕዝቡ መካኚል ድርሻውን ለመውሰድ ኚኢዚሩሳሌም ተነሳ።
ይሁንና ወደ ቢንያም በር በደሹሰ ጊዜ ዚሃናንያህ ልጅ፣ ዚሞሌምያህ ልጅ ይሪያህ ዚተባለ ዚጠባቂዎቜ አለቃ ነቢዩ ኀርምያስን ይዞ “ኚድተህ ወደ ኚለዳውያን ልትሄድ ነው!” አለው።
ኀርምያስ ግን “በፍጹም! ኚድቌ ወደ ኚለዳውያን ልሄድ አይደለም” አለ። እሱ ግን አልሰማውም። በመሆኑም ይሪያህ ኀርምያስን ይዞ ወደ መኳንንቱ ወሰደው።
መኳንንቱ ኀርምያስን እጅግ ተቆጥተው መቱትፀ ኚዚያም በወቅቱ እስር ቀት አድርገውት በነበሹው በጾሐፊው በዚሆናታን ቀት አሰሩት።
ኀርምያስ በምድር ቀት ውስጥ ወደሚገኝ ዚእስሚኞቜ ክፍል እንዲገባ ተደሚገፀ በዚያም ለብዙ ቀናት ቆዚ።
ኚዚያም ንጉሥ ሎዎቅያስ ልኮ አስመጣውፀ ንጉሡም በቀቱ ውስጥ በሚስጥር ጠዚቀው። “ኹይሖዋ ዚመጣ ቃል አለ?” አለው። ኀርምያስም “አዎ፣ አለ!” ሲል መለሰለትፀ አክሎም “በባቢሎን ንጉሥ እጅ አልፈህ ትሰጣለህ!” አለው።
በተጚማሪም ኀርምያስ ንጉሥ ሎዎቅያስን እንዲህ አለው፩ “እስር ቀት ያስገባቜሁኝ በአንተ፣ በአገልጋዮቜህና በዚህ ሕዝብ ላይ ምን ዚሠራሁት በደል ቢኖር ነው?
‘ዚባቢሎን ንጉሥ እናንተንና ይህቜን ምድር ለመውጋት አይመጣም’ ብለው ዚተነበዩላቜሁ ነቢያታቜሁ አሁን ዚት አሉ?
አሁንም ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፣ እባክህ ስማኝ። በፊትህ ሞገስ ለማግኘት ዹማቀርበውን ልመና እባክህ ተቀበል። ወደ ጾሐፊው ወደ ዚሆናታን ቀት መልሰህ አትላኚኝፀ ካልሆነ ግን በዚያ እሞታለሁ።”
በመሆኑም ንጉሥ ሎዎቅያስ፣ ኀርምያስ በክብር ዘቊቹ ግቢ እንዲታሰር አዘዘፀ ዳቊ ኹኹተማዋ እስኪጠፋ ድሚስም ኚዳቊ ጋጋሪዎቜ ጎዳና በዚዕለቱ አንድ አንድ ዳቊ ይሰጠው ነበር። ኀርምያስም በክብር ዘቊቹ ግቢ ተቀመጠ።
በኢዮስያስ ልጅ፣ በይሁዳ ንጉሥ በኢዮዓቄም ዘመነ መንግሥት መጀመሪያ ላይ ይህ ቃል ኹይሖዋ ዘንድ መጣፊ
“ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘በይሖዋ ቀት ግቢ ውስጥ ቆመህ፣ ለአምልኮ ወደ ይሖዋ ቀት ስለሚመጡት፣ በይሁዳ ኚተሞቜ ስለሚኖሩት ሰዎቜ ሁሉ ተናገር። ዹማዝህን ቃል ሁሉ ንገራ቞ውፀ አንዲትም ቃል አታስቀር።
ምናልባት ይሰሙና እያንዳንዳ቞ው ኹክፉ መንገዳ቞ው ይመለሱ ይሆናልፀ እኔም በክፉ ሥራ቞ው ዚተነሳ በእነሱ ላይ ላመጣ ያሰብኩትን ጥፋት እተወዋለሁ።
እንዲህ በላቾው፩ “ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ዚማትሰሙኝና ዚሰጠኋቜሁን ሕግ ዚማትኚተሉ ኚሆነ፣
እንዲሁም ደግሜ ደጋግሜ ወደ እናንተ ዚላክኋ቞ውን፣ እናንተ ያልሰማቜኋ቞ውን ዚአገልጋዮቌን ዚነቢያትን ቃል ዚማትቀበሉ ኚሆነ፣
ይህን ቀት እንደ ሮሎ አደርገዋለሁፀ ይህቜንም ኹተማ ለምድር ብሔራት ሁሉ እርግማን አደርጋታለሁ።’”’”
ካህናቱ፣ ነቢያቱና ሕዝቡ ሁሉ ኀርምያስ በይሖዋ ቀት ይህን ቃል ሲናገር ሰሙ።
በመሆኑም ኀርምያስ፣ ይሖዋ ለሕዝቡ ሁሉ እንዲናገር ያዘዘውን ተናግሮ በጹሹሰ ጊዜ ካህናቱ፣ ነቢያቱና ሕዝቡ ሁሉ ይዘው እንዲህ አሉትፊ “አንተ በእርግጥ ትሞታለህ።
‘ይህ ቀት እንደ ሮሎ ይሆናልፀ ይህቜም ኹተማ ወድማ ሰው አልባ ትሆናለቜ’ ብለህ በይሖዋ ስም ዹተነበይኹው ለምንድን ነው?” ሕዝቡም ሁሉ በይሖዋ ቀት በኀርምያስ ዙሪያ ተሰበሰበ።
ዚይሁዳ መኳንንት ይህን ቃል በሰሙ ጊዜ ኚንጉሡ ቀት ወደ ይሖዋ ቀት መጥተው በይሖዋ ቀት ባለው በአዲሱ በር መግቢያ ተቀመጡ።
ካህናቱና ነቢያቱ፣ ለመኳንንቱና ለሕዝቡ ሁሉ እንዲህ አሉ፩ “ይህ ሰው በሞት ሊቀጣ ይገባዋልፀ ምክንያቱም በገዛ ጆሯቜሁ እንደሰማቜሁት በዚህቜ ኹተማ ላይ ትንቢት ተናግሯል።”
በዚህ ጊዜ ኀርምያስ ለመኳንንቱ ሁሉና ለሕዝቡ ሁሉ እንዲህ አለ፩ “ዚሰማቜሁትን ቃል ሁሉ በዚህ ቀትና በዚህቜ ኹተማ ላይ እንድተነብይ ዹላኹኝ ይሖዋ ነው።
እንግዲያው አሁን መንገዳቜሁንና ድርጊታቜሁን አስተካክሉፀ ዚአምላካቜሁንም ዹይሖዋን ቃል ስሙፀ ይሖዋም በእናንተ ላይ አመጣዋለሁ ብሎ ዹተናገሹውን ጥፋት ይተወዋል።
እኔ ግን በእጃቜሁ ነኝ። መልካምና ትክክል መስሎ ዚታያቜሁን ነገር ሁሉ አድርጉብኝ።
ኚገደላቜሁኝ በራሳቜሁ፣ በዚህቜ ኹተማና በነዋሪዎቿ ላይ ዚንጹሕ ሰው ደም ዕዳ እንደምታመጡ በእርግጥ እወቁፀ ይህን ሁሉ ቃል በጆሯቜሁ እንድናገር ዹላኹኝ በእርግጥ ይሖዋ ነውና።”
በዚህ ጊዜ መኳንንቱና ሕዝቡ ሁሉ ካህናቱንና ነቢያቱን “ይህ ሰው ዹተናገሹን በአምላካቜን በይሖዋ ስም ስለሆነ በሞት ሊቀጣ አይገባውም” አሏ቞ው።
በተጚማሪም በምድሪቱ ኚሚኖሩ ሜማግሌዎቜ መካኚል አንዳንዶቹ ተነስተው ለተሰበሰበው ሕዝብ ሁሉ እንዲህ አሉ፩
“ዚሞሚሞቱ ሚክያስ በይሁዳ ንጉሥ በሕዝቅያስ ዘመን ትንቢት ይናገር ነበርፀ ለይሁዳም ሕዝብ ሁሉ እንዲህ ብሎ ነበር፩ ‘ዚሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ “ጜዮን እንደ እርሻ ትታሚሳለቜፀኢዚሩሳሌም ዚፍርስራሜ ክምር ትሆናለቜፀዚቀቱም ተራራ፣ በጫካ እንዳሉ ኹፍ ያሉ ቊታዎቜ ይሆናል።”’
“ታዲያ በዚያ ጊዜ ዚይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስና ዚይሁዳ ሕዝብ ሁሉ ገደሉት? ይልቁንም ይሖዋን ፈርቶ፣ ይሖዋ እንዲራራለት አልተማጾነም? ኚዚህስ ዚተነሳ ይሖዋ በእነሱ ላይ ሊያመጣ አስቊት ዹነበሹውን ጥፋት አልተወውም? እኛ ግን በራሳቜን ላይ ጥፋት እዚጋበዝን ነው።
“ደግሞም በይሖዋ ስም ትንቢት ዹሚናገር ሌላ ሰው ነበርፀ እሱም ዚቂርያትዚአሪም ሰው ዹሆነው ዚሞማያህ ልጅ ዑሪያህ ሲሆን ኀርምያስ ዹተናገሹውን ዓይነት ቃል በመናገር በዚህቜ ኹተማና በዚህቜ ምድር ላይ ተንብዮአል።
ንጉሥ ኢዮዓቄም፣ ኃያል ተዋጊዎቹ ሁሉና መኳንንቱ ሁሉ እሱ ዹተናገሹውን ቃል ሰሙፀ ንጉሡም ሊገድለው ፈለገ። ዑሪያህ ይህን እንደሰማ በጣም ስለፈራ ሞሜቶ ወደ ግብፅ ሄደ።
በዚህ ጊዜ ንጉሥ ኢዮዓቄም ዹአክቩርን ልጅ ኀልናታንን እንዲሁም ኚእሱ ጋር ሌሎቜ ሰዎቜን ወደ ግብፅ ላኚ።