text
stringlengths
4
267
ሴዴቅያስ በነገሠ ጊዜ ዕድሜው 21 ዓመት ነበር፤ በኢየሩሳሌምም ሆኖ ለ11 ዓመት ገዛ። እናቱ ሀሙጣል ትባል ነበር፤ እሷም የሊብና ሰው የሆነው የኤርምያስ ልጅ ነበረች።
ሴዴቅያስም ኢዮዓቄም እንዳደረገው ሁሉ በይሖዋ ፊት መጥፎ የሆነውን ነገር አደረገ።
እነዚህ ነገሮች በኢየሩሳሌምና በይሁዳ የተፈጸሙት ከይሖዋ ቁጣ የተነሳ ነው፤ በመጨረሻም ከፊቱ አስወገዳቸው። ሴዴቅያስም በባቢሎን ንጉሥ ላይ ዓመፀ።
ሴዴቅያስ በነገሠ በዘጠነኛው ዓመት፣ በአሥረኛው ወር፣ ከወሩም በአሥረኛው ቀን የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነጾር ሠራዊቱን ሁሉ አስከትሎ በኢየሩሳሌም ላይ ዘመተ። በዙሪያዋም ሰፈሩ፤ ደግሞም በዙሪያዋ የአፈር ቁልል ቆለሉ።
ከተማዋም እስከ ንጉሥ ሴዴቅያስ 11ኛ ዓመት ድረስ ተከበበች።
በአራተኛው ወር፣ ከወሩም በዘጠነኛው ቀን በከተማዋ ውስጥ ረሃቡ እጅግ ከፋ፤ በምድሪቱ የሚኖሩትም ሰዎች የሚላስ የሚቀመስ አጡ።
በመጨረሻም የከተማዋ ቅጥር ተነደለ፤ ከለዳውያን ከተማዋን ከበው ሳለም ወታደሮቹ ሁሉ በንጉሡ የአትክልት ቦታ አቅራቢያ ባለው መንገድ፣ በሁለቱ ቅጥሮች መካከል በሚገኘው በር በኩል በሌሊት ከከተማዋ ወጥተው ሸሹ፤ ወደ አረባ የሚወስደውንም አቅጣጫ ይዘው ሄዱ።
ይሁንና የከለዳውያን ሠራዊት ንጉሡን አሳደደ፤ ሴዴቅያስንም በኢያሪኮ በረሃማ ሜዳ ላይ ደረሱበት፤ ወታደሮቹም ሁሉ ጥለውት ተበታተኑ።
ከዚያም ንጉሡን ይዘው በሃማት ምድር በምትገኘው በሪብላ ወደነበረው የባቢሎን ንጉሥ አመጡት፤ እሱም ፈረደበት።
የባቢሎንም ንጉሥ የሴዴቅያስን ወንዶች ልጆች ዓይኑ እያየ አረዳቸው፤ በተጨማሪም የይሁዳን መኳንንት ሁሉ በዚያው በሪብላ አረዳቸው።
ከዚያም የባቢሎን ንጉሥ፣ የሴዴቅያስን ዓይን አሳወረ፤ በመዳብ የእግር ብረት አስሮ ወደ ባቢሎን ወሰደው፤ እስከ ዕለተ ሞቱም ድረስ በእስር ቤት አቆየው።
በአምስተኛው ወር፣ ከወሩም በአሥረኛው ቀን ይኸውም ንጉሥ ናቡከደነጾር በነገሠ በ19ኛው ዓመት፣ የዘቦች አለቃና የባቢሎን ንጉሥ አገልጋይ የሆነው ናቡዛራዳን ወደ ኢየሩሳሌም መጣ።
እሱም የይሖዋን ቤት፣ የንጉሡን ቤትና በኢየሩሳሌም የሚገኙ ቤቶችን በሙሉ አቃጠለ፤ ትላልቅ ቤቶችንም ሁሉ በእሳት አጋየ።
ከዘቦቹ አለቃ ጋር የነበረው የከለዳውያን ሠራዊት በኢየሩሳሌም ዙሪያ ያለውን ቅጥር በሙሉ አፈረሰ።
የዘቦች አለቃ የሆነው ናቡዛራዳን ችግረኛ ከሆኑት ሰዎች መካከል የተወሰኑትንና በከተማዋ የቀሩትን በሕይወት የተረፉ ሰዎች አጋዘ። በተጨማሪም ከድተው ለባቢሎን ንጉሥ እጃቸውን የሰጡትን ሰዎችና የቀሩትን የተካኑ የእጅ ጥበብ ባለሙያዎች ወሰደ።
ሆኖም የዘቦች አለቃ የሆነው ናቡዛራዳን፣ በምድሪቱ ከነበሩት ያጡ የነጡ ድሆች መካከል አንዳንዶቹ የወይን አትክልት ሠራተኞች ሆነው እንዲያገለግሉና የግዳጅ አገልግሎት እንዲሰጡ በዚያው ተዋቸው።
ከለዳውያን የይሖዋን ቤት የመዳብ ዓምዶች እንዲሁም በይሖዋ ቤት ውስጥ የነበሩትን የዕቃ ማጓጓዣ ጋሪዎችና የመዳብ ባሕር ሰባብረው መዳቡን በሙሉ ወደ ባቢሎን አጋዙ።
በተጨማሪም አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ አካፋዎቹን፣ የእሳት ማጥፊያዎቹን፣ ጎድጓዳ ሳህኖቹን፣ ጽዋዎቹንና ለቤተ መቅደስ አገልግሎት የሚውሉትን የመዳብ ዕቃዎች ሁሉ ወሰዱ።
የዘቦቹ አለቃ ከንጹሕ ወርቅና ብር የተሠሩትን ዕቃዎች ይኸውም ሳህኖቹን፣ መኮስተሪያዎቹን፣ ጎድጓዳ ሳህኖቹን፣ አመድ ማጠራቀሚያዎቹን፣ መቅረዞቹን፣ ጽዋዎቹንና ሌሎቹን ጎድጓዳ ሳህኖች ወሰደ።
ንጉሥ ሰለሞን ለይሖዋ ቤት ያሠራቸው ሁለቱ ዓምዶች፣ ባሕሩ፣ ከባሕሩ ሥር ያሉት 12 የመዳብ በሬዎችና የዕቃ ማጓጓዣ ጋሪዎቹ የተሠሩበት መዳብ ከብዛቱ የተነሳ ሊመዘን የሚችል አልነበረም።
ዓምዶቹ እያንዳንዳቸው 18 ክንድ ቁመት ነበራቸው፤ የዙሪያቸው መጠን በመለኪያ ገመድ 12 ክንድ፣ ውፍረታቸውም አራት ጣት ሲሆን ውስጣቸው ክፍት ነበር።
በዓምዱም አናት ላይ ያለው ጌጥ ከመዳብ የተሠራ ነበር፤ የአንዱ ጌጥ ርዝማኔ አምስት ክንድ ሲሆን በዙሪያው ያሉት ሮማኖችና መረቡ በሙሉ ከመዳብ የተሠሩ ነበሩ። ሁለተኛው ዓምድ፣ ሮማኖቹን ጨምሮ ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነበር።
በጎኖቹ ላይ 96 ሮማኖች የነበሩ ሲሆን በመረቡ ዙሪያ ያሉት ሮማኖች በጠቅላላ 100 ነበሩ።
በተጨማሪም የዘቦቹ አለቃ የካህናት አለቃ የሆነውን ሰራያህን፣ ሁለተኛውን ካህን ሶፎንያስንና ሦስቱን የበር ጠባቂዎች ወሰዳቸው።
ደግሞም ከከተማዋ የወታደሮቹ ኃላፊ የሆነን አንድ የቤተ መንግሥት ባለሥልጣን፣ በከተማዋ ውስጥ የነበሩትን ሰባቱን የንጉሡ የቅርብ ሰዎች፣ የምድሪቱን ሕዝብ የሚያሰልፈውን የሠራዊቱን አለቃ ጸሐፊ እንዲሁም ከተማዋ ውስጥ የተገኙትን በምድሪቱ የሚኖሩ 60 ተራ ሰዎች ወሰደ።
የዘቦች አለቃ የሆነው ናቡዛራዳን እነዚህን ሰዎች ይዞ፣ በሪብላ ወዳለው ወደ ባቢሎን ንጉሥ አመጣቸው።
የባቢሎን ንጉሥ በሃማት ምድር ባለችው በሪብላ ሰዎቹን መትቶ ገደላቸው። በዚህ መንገድ ይሁዳ ከምድሩ በግዞት ተወሰደ።
ናቡከደነጾር በግዞት የወሰዳቸው ሰዎች እነዚህ ናቸው፦ በሰባተኛው ዓመት 3,023 አይሁዳውያንን ወሰደ።
በናቡከደነጾር 18ኛ ዓመት ከኢየሩሳሌም 832 ሰዎች ተጋዙ።
ናቡከደነጾር በነገሠ በ23ኛው ዓመት፣ የዘቦች አለቃ የሆነው ናቡዛራዳን ከአይሁዳውያን መካከል 745 ሰዎችን በግዞት ወሰደ። በአጠቃላይ 4,600 ሰዎች በግዞት ተወሰዱ።
ከዚያም የባቢሎን ንጉሥ ኤዊልሜሮዳክ በነገሠበት ዓመት የይሁዳን ንጉሥ ዮአኪንን ፈታው፤ ከእስር ቤትም አወጣው፤ ይህም የሆነው የይሁዳ ንጉሥ ዮአኪን በግዞት በተወሰደ በ37ኛው ዓመት፣ በ12ኛው ወር፣ ከወሩም በ25ኛው ቀን ነበር።
በርኅራኄም አናገረው፤ ዙፋኑንም በባቢሎን ከእሱ ጋር ከነበሩት ከሌሎች ነገሥታት ዙፋን ይበልጥ ከፍ ከፍ አደረገለት።
በመሆኑም ዮአኪን የእስር ቤት ልብሱን አወለቀ፤ በሕይወት ዘመኑም ሁሉ በቋሚነት ከንጉሡ ማዕድ ይመገብ ነበር።
የባቢሎን ንጉሥ፣ ዮአኪን እስከሞተበት ጊዜ ድረስ፣ በሕይወት ዘመኑ ሁሉ ሳያቋርጥ ቀለቡን በየዕለቱ ይሰጠው ነበር።
ከይሖዋ ወደ ኤርምያስ የመጣው ቃል ይህ ነው፦
“እናንተ ሰዎች፣ የዚህን ቃል ኪዳን ቃል ስሙ! “ለይሁዳ ሰዎችና ለኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ቃሉን ተናገር፤
እንዲህም በላቸው፦ ‘የእስራኤል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “የዚህን ቃል ኪዳን ቃል የማይታዘዝ ሰው የተረገመ ነው፤
ይህም አባቶቻችሁን ከግብፅ ምድር፣ ከብረት ማቅለጫ ምድጃው ባወጣኋቸው ጊዜ እንዲህ ብዬ ያዘዝኳቸው ቃል ነው፦ ‘ድምፄን ስሙ፤ ያዘዝኳችሁንም ነገር ሁሉ አድርጉ፤ እናንተም ሕዝቤ ትሆናላችሁ፤ እኔም አምላካችሁ እሆናለሁ፤
ይህም ዛሬ እንደሆነው ሁሉ ወተትና ማር የምታፈሰውን ምድር ለመስጠት ለአባቶቻችሁ የገባሁትን መሐላ ለመፈጸም ነው።’”’” እኔም “ይሖዋ ሆይ፣ አሜን” ብዬ መለስኩ።
ከዚያም ይሖዋ እንዲህ አለኝ፦ “እነዚህን ቃላት ሁሉ በይሁዳ ከተሞችና በኢየሩሳሌም ጎዳናዎች ላይ አውጅ፦ ‘የዚህን ቃል ኪዳን ቃል ስሙ፤ በሥራም ላይ አውሉት።
አባቶቻችሁን ከግብፅ ምድር ካወጣሁበት ቀን አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ “ድምፄን ስሙ” በማለት ደግሜ ደጋግሜ አጥብቄ ሳሳስባቸው ነበርና።
እነሱ ግን አልሰሙም ወይም ጆሯቸውን አልሰጡም፤ ከዚህ ይልቅ እያንዳንዳቸው ግትር ሆነው የገዛ ክፉ ልባቸውን ተከተሉ። ስለዚህ ተግባራዊ እንዲያደርጉ ያዘዝኳቸውን፣ እነሱ ግን ሥራ ላይ ያላዋሉትን የዚህን ቃል ኪዳን ቃል ሁሉ በእነሱ ላይ አመጣሁባቸው።’”
ከዚያም ይሖዋ እንዲህ አለኝ፦ “የይሁዳ ሰዎችና የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ሴራ ጠንስሰዋል።
ቃሌን ያልታዘዙት የቀድሞ አባቶቻቸው ይፈጽሙት ወደነበረው በደል ተመልሰዋል። እነሱም ሌሎች አማልክትን ተከትለዋል፤ ደግሞም አገልግለዋል። የእስራኤል ቤትና የይሁዳ ቤት ከአባቶቻቸው ጋር የገባሁትን ቃል ኪዳን አፍርሰዋል።
ስለዚህ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘እነሆ፣ ማምለጥ የማይችሉትን ጥፋት አመጣባቸዋለሁ። እርዳታ ለማግኘት ወደ እኔ ሲጮኹ አልሰማቸውም።
ከዚያም የይሁዳ ከተሞችና የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች መሥዋዕት ወደሚያቀርቡላቸው አማልክት ሄደው እርዳታ ይጠይቃሉ፤ ሆኖም ጥፋት በሚደርስባቸው ጊዜ ፈጽሞ አያድኗቸውም።
ይሁዳ ሆይ፣ አማልክትህ የከተሞችህን ያህል በዝተዋልና፤ ለአሳፋሪው ነገር ይኸውም ለባአል መሥዋዕት ለማቅረብ የኢየሩሳሌምን ጎዳናዎች ያህል ብዛት ያላቸው መሠዊያዎች ሠርታችኋል።’
“አንተም ለዚህ ሕዝብ አትጸልይ። ስለ እነሱ የልመና ጩኸትም ሆነ ጸሎት አታሰማ፤ ጥፋት ደርሶባቸው ወደ እኔ ሲጮኹ አልሰማቸውምና።
ብዙዎቹ የሸረቡትን ክፉ ሐሳብ እየፈጸሙ ሳለ፣ውዴ በቤቴ ለመገኘት ምን መብት አላት? ጥፋት በአንቺ ላይ ሲመጣ በቅዱስ ሥጋ ጥፋቱን ሊከላከሉልሽ ይችላሉ? በዚያን ጊዜ ሐሴት ታደርጊ ይሆን?
በአንድ ወቅት ይሖዋ በመልካም ፍሬ የተዋበ፣የለመለመ የወይራ ዛፍ ብሎ ጠርቶሽ ነበር። በሚያስገመግም ታላቅ ድምፅ፣ በእሳት አነደዳት፤እነሱም ቅርንጫፎቿን ሰባበሩ።
“የተከለሽ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ፣ ለባአል መሥዋዕት በማቅረብ እኔን ያስከፉኝ የእስራኤል ቤትና የይሁዳ ቤት በሠሩት ክፉ ነገር የተነሳ በአንቺ ላይ ጥፋት እንደሚመጣ አስታውቋል።”
ይሖዋ ይህን እንዳውቅ ገለጠልኝ፤አምላክ ሆይ፣ በዚያን ጊዜ የፈጸሙትን ነገር እንዳይ አደረግከኝ።
እኔ ለመታረድ እንደሚነዳ የዋህ የበግ ጠቦት ነበርኩ። “ዛፉን ከነፍሬው እናጥፋው፤ ከእንግዲህም ወዲያ ስሙ እንዳይታወስከሕያዋን ምድር እናስወግደው” ብለውበእኔ ላይ ሴራ እንደጠነሰሱ አላወቅኩም ነበር።
የሠራዊት ጌታ ይሖዋ ግን በጽድቅ ይፈርዳል፤የውስጥ ሐሳብንና ልብን ይመረምራል። አምላክ ሆይ፣ በእነሱ ላይ የምትወስደውን የበቀል እርምጃ እንዳይ አድርገኝ፤ጉዳዬን ለአንተ አቅርቤአለሁና።
ስለዚህ ይሖዋ ሕይወትህን ለማጥፋት በሚሹ በአናቶት ሰዎች ላይ ይህን ቃል ተናግሯል፤ እነሱ “በይሖዋ ስም ትንቢት አትናገር፤ አለዚያ በእጃችን ትጠፋለህ” ይላሉ፤
ስለዚህ የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “እነሆ፣ እነሱን ተጠያቂ አደርጋለሁ። ወጣት ወንዶቹ በሰይፍ ይወድቃሉ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻቸው በረሃብ ያልቃሉ።
እነሱን ተጠያቂ በማደርግበት ዓመት፣ በአናቶት ሰዎች ላይ ጥፋት ስለማመጣ ከእነሱ መካከል የሚተርፍ አንድም ሰው አይኖርም።”
የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነጾር የኢዮስያስን ልጅ ንጉሥ ሴዴቅያስን በይሁዳ ምድር ስላነገሠው በኢዮአቄም ልጅ በኮንያሁ ፋንታ መግዛት ጀመረ።
ይሁንና እሱም ሆነ አገልጋዮቹ እንዲሁም የምድሪቱ ሕዝብ ይሖዋ በነቢዩ ኤርምያስ በኩል የተናገረውን ቃል አልሰሙም።
ንጉሥ ሴዴቅያስም የሸሌምያህን ልጅ የሁካልንና የካህኑን የማአሴያህን ልጅ ሶፎንያስን “እባክህ፣ ስለ እኛ ወደ አምላካችን ወደ ይሖዋ ጸልይ” ብለው እንዲነግሩት ወደ ነቢዩ ኤርምያስ ላካቸው።
በዚያ ወቅት ኤርምያስ ገና እስር ቤት ስላላስገቡት በሕዝቡ መካከል በነፃነት ይገባና ይወጣ ነበር።
በዚህ ጊዜ የፈርዖን ሠራዊት ከግብፅ ወጥቶ ነበር፤ ኢየሩሳሌምን ከበው የነበሩት ከለዳውያንም ይህን ሰሙ። በመሆኑም ኢየሩሳሌምን ለቀው ሄዱ።
ከዚያም የይሖዋ ቃል እንዲህ ሲል ወደ ነቢዩ ኤርምያስ መጣ፦
“የእስራኤል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘እኔን እንድትጠይቁ ወደ እኔ የላካችሁን የይሁዳን ንጉሥ እንዲህ በሉት፦ “እነሆ፣ እናንተን ለመርዳት የመጣው የፈርዖን ሠራዊት ወደ አገሩ ወደ ግብፅ ይመለሳል።
ከለዳውያኑም ተመልሰው መጥተው ይህችን ከተማ ይወጓታል፤ ይይዟታልም፤ በእሳትም ያቃጥሏታል።”
ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “‘ከለዳውያን ያላንዳች ጥርጥር ትተውን ይሄዳሉ’ እያላችሁ ራሳችሁን አታታሉ፤ ምክንያቱም ትተዋችሁ አይሄዱም።
እናንተን የሚወጋችሁን መላውን የከለዳውያን ሠራዊት ብትመቱና ቁስለኞቻቸው ብቻ ቢቀሩ እንኳ ከድንኳናቸው ተነስተው ይህችን ከተማ በእሳት ያቃጥሏታል።”’”
የከለዳውያን ሠራዊት ከፈርዖን ሠራዊት የተነሳ ኢየሩሳሌምን ትቶ በተመለሰ ጊዜ፣
ኤርምያስ ወደ ቢንያም አገር ሄዶ በሕዝቡ መካከል ድርሻውን ለመውሰድ ከኢየሩሳሌም ተነሳ።
ይሁንና ወደ ቢንያም በር በደረሰ ጊዜ የሃናንያህ ልጅ፣ የሸሌምያህ ልጅ ይሪያህ የተባለ የጠባቂዎች አለቃ ነቢዩ ኤርምያስን ይዞ “ከድተህ ወደ ከለዳውያን ልትሄድ ነው!” አለው።
ኤርምያስ ግን “በፍጹም! ከድቼ ወደ ከለዳውያን ልሄድ አይደለም” አለ። እሱ ግን አልሰማውም። በመሆኑም ይሪያህ ኤርምያስን ይዞ ወደ መኳንንቱ ወሰደው።
መኳንንቱ ኤርምያስን እጅግ ተቆጥተው መቱት፤ ከዚያም በወቅቱ እስር ቤት አድርገውት በነበረው በጸሐፊው በየሆናታን ቤት አሰሩት።
ኤርምያስ በምድር ቤት ውስጥ ወደሚገኝ የእስረኞች ክፍል እንዲገባ ተደረገ፤ በዚያም ለብዙ ቀናት ቆየ።
ከዚያም ንጉሥ ሴዴቅያስ ልኮ አስመጣው፤ ንጉሡም በቤቱ ውስጥ በሚስጥር ጠየቀው። “ከይሖዋ የመጣ ቃል አለ?” አለው። ኤርምያስም “አዎ፣ አለ!” ሲል መለሰለት፤ አክሎም “በባቢሎን ንጉሥ እጅ አልፈህ ትሰጣለህ!” አለው።
በተጨማሪም ኤርምያስ ንጉሥ ሴዴቅያስን እንዲህ አለው፦ “እስር ቤት ያስገባችሁኝ በአንተ፣ በአገልጋዮችህና በዚህ ሕዝብ ላይ ምን የሠራሁት በደል ቢኖር ነው?
‘የባቢሎን ንጉሥ እናንተንና ይህችን ምድር ለመውጋት አይመጣም’ ብለው የተነበዩላችሁ ነቢያታችሁ አሁን የት አሉ?
አሁንም ጌታዬ ንጉሥ ሆይ፣ እባክህ ስማኝ። በፊትህ ሞገስ ለማግኘት የማቀርበውን ልመና እባክህ ተቀበል። ወደ ጸሐፊው ወደ የሆናታን ቤት መልሰህ አትላከኝ፤ ካልሆነ ግን በዚያ እሞታለሁ።”
በመሆኑም ንጉሥ ሴዴቅያስ፣ ኤርምያስ በክብር ዘቦቹ ግቢ እንዲታሰር አዘዘ፤ ዳቦ ከከተማዋ እስኪጠፋ ድረስም ከዳቦ ጋጋሪዎች ጎዳና በየዕለቱ አንድ አንድ ዳቦ ይሰጠው ነበር። ኤርምያስም በክብር ዘቦቹ ግቢ ተቀመጠ።
በኢዮስያስ ልጅ፣ በይሁዳ ንጉሥ በኢዮዓቄም ዘመነ መንግሥት መጀመሪያ ላይ ይህ ቃል ከይሖዋ ዘንድ መጣ፦
“ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘በይሖዋ ቤት ግቢ ውስጥ ቆመህ፣ ለአምልኮ ወደ ይሖዋ ቤት ስለሚመጡት፣ በይሁዳ ከተሞች ስለሚኖሩት ሰዎች ሁሉ ተናገር። የማዝህን ቃል ሁሉ ንገራቸው፤ አንዲትም ቃል አታስቀር።
ምናልባት ይሰሙና እያንዳንዳቸው ከክፉ መንገዳቸው ይመለሱ ይሆናል፤ እኔም በክፉ ሥራቸው የተነሳ በእነሱ ላይ ላመጣ ያሰብኩትን ጥፋት እተወዋለሁ።
እንዲህ በላቸው፦ “ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ ‘የማትሰሙኝና የሰጠኋችሁን ሕግ የማትከተሉ ከሆነ፣
እንዲሁም ደግሜ ደጋግሜ ወደ እናንተ የላክኋቸውን፣ እናንተ ያልሰማችኋቸውን የአገልጋዮቼን የነቢያትን ቃል የማትቀበሉ ከሆነ፣
ይህን ቤት እንደ ሴሎ አደርገዋለሁ፤ ይህችንም ከተማ ለምድር ብሔራት ሁሉ እርግማን አደርጋታለሁ።’”’”
ካህናቱ፣ ነቢያቱና ሕዝቡ ሁሉ ኤርምያስ በይሖዋ ቤት ይህን ቃል ሲናገር ሰሙ።
በመሆኑም ኤርምያስ፣ ይሖዋ ለሕዝቡ ሁሉ እንዲናገር ያዘዘውን ተናግሮ በጨረሰ ጊዜ ካህናቱ፣ ነቢያቱና ሕዝቡ ሁሉ ይዘው እንዲህ አሉት፦ “አንተ በእርግጥ ትሞታለህ።
‘ይህ ቤት እንደ ሴሎ ይሆናል፤ ይህችም ከተማ ወድማ ሰው አልባ ትሆናለች’ ብለህ በይሖዋ ስም የተነበይከው ለምንድን ነው?” ሕዝቡም ሁሉ በይሖዋ ቤት በኤርምያስ ዙሪያ ተሰበሰበ።
የይሁዳ መኳንንት ይህን ቃል በሰሙ ጊዜ ከንጉሡ ቤት ወደ ይሖዋ ቤት መጥተው በይሖዋ ቤት ባለው በአዲሱ በር መግቢያ ተቀመጡ።
ካህናቱና ነቢያቱ፣ ለመኳንንቱና ለሕዝቡ ሁሉ እንዲህ አሉ፦ “ይህ ሰው በሞት ሊቀጣ ይገባዋል፤ ምክንያቱም በገዛ ጆሯችሁ እንደሰማችሁት በዚህች ከተማ ላይ ትንቢት ተናግሯል።”
በዚህ ጊዜ ኤርምያስ ለመኳንንቱ ሁሉና ለሕዝቡ ሁሉ እንዲህ አለ፦ “የሰማችሁትን ቃል ሁሉ በዚህ ቤትና በዚህች ከተማ ላይ እንድተነብይ የላከኝ ይሖዋ ነው።
እንግዲያው አሁን መንገዳችሁንና ድርጊታችሁን አስተካክሉ፤ የአምላካችሁንም የይሖዋን ቃል ስሙ፤ ይሖዋም በእናንተ ላይ አመጣዋለሁ ብሎ የተናገረውን ጥፋት ይተወዋል።
እኔ ግን በእጃችሁ ነኝ። መልካምና ትክክል መስሎ የታያችሁን ነገር ሁሉ አድርጉብኝ።
ከገደላችሁኝ በራሳችሁ፣ በዚህች ከተማና በነዋሪዎቿ ላይ የንጹሕ ሰው ደም ዕዳ እንደምታመጡ በእርግጥ እወቁ፤ ይህን ሁሉ ቃል በጆሯችሁ እንድናገር የላከኝ በእርግጥ ይሖዋ ነውና።”
በዚህ ጊዜ መኳንንቱና ሕዝቡ ሁሉ ካህናቱንና ነቢያቱን “ይህ ሰው የተናገረን በአምላካችን በይሖዋ ስም ስለሆነ በሞት ሊቀጣ አይገባውም” አሏቸው።
በተጨማሪም በምድሪቱ ከሚኖሩ ሽማግሌዎች መካከል አንዳንዶቹ ተነስተው ለተሰበሰበው ሕዝብ ሁሉ እንዲህ አሉ፦
“የሞረሸቱ ሚክያስ በይሁዳ ንጉሥ በሕዝቅያስ ዘመን ትንቢት ይናገር ነበር፤ ለይሁዳም ሕዝብ ሁሉ እንዲህ ብሎ ነበር፦ ‘የሠራዊት ጌታ ይሖዋ እንዲህ ይላል፦ “ጽዮን እንደ እርሻ ትታረሳለች፤ኢየሩሳሌም የፍርስራሽ ክምር ትሆናለች፤የቤቱም ተራራ፣ በጫካ እንዳሉ ከፍ ያሉ ቦታዎች ይሆናል።”’
“ታዲያ በዚያ ጊዜ የይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስና የይሁዳ ሕዝብ ሁሉ ገደሉት? ይልቁንም ይሖዋን ፈርቶ፣ ይሖዋ እንዲራራለት አልተማጸነም? ከዚህስ የተነሳ ይሖዋ በእነሱ ላይ ሊያመጣ አስቦት የነበረውን ጥፋት አልተወውም? እኛ ግን በራሳችን ላይ ጥፋት እየጋበዝን ነው።
“ደግሞም በይሖዋ ስም ትንቢት የሚናገር ሌላ ሰው ነበር፤ እሱም የቂርያትየአሪም ሰው የሆነው የሸማያህ ልጅ ዑሪያህ ሲሆን ኤርምያስ የተናገረውን ዓይነት ቃል በመናገር በዚህች ከተማና በዚህች ምድር ላይ ተንብዮአል።
ንጉሥ ኢዮዓቄም፣ ኃያል ተዋጊዎቹ ሁሉና መኳንንቱ ሁሉ እሱ የተናገረውን ቃል ሰሙ፤ ንጉሡም ሊገድለው ፈለገ። ዑሪያህ ይህን እንደሰማ በጣም ስለፈራ ሸሽቶ ወደ ግብፅ ሄደ።
በዚህ ጊዜ ንጉሥ ኢዮዓቄም የአክቦርን ልጅ ኤልናታንን እንዲሁም ከእሱ ጋር ሌሎች ሰዎችን ወደ ግብፅ ላከ።