text
stringlengths
4
267
ለáŠĨናንተም ሆነ ከáŠĨናንተ ጋር ለሚኖር á‹¨á‰Ŗá‹•á‹ĩ አገር ሰው አንá‹ĩ ዓይነá‰ĩ ሕግና አንá‹ĩ ዓይነá‰ĩ á‹ĩንጋጌ ይኑርáĸ’”
ይሖዋ ሙሴን áŠĨንዲህ አለውáĻ
“áŠĨáˆĩáˆĢኤላውá‹Ģንን አናግáˆĢቸው፤ áŠĨንዲህም በላቸውáĻ â€˜á‹ˆá‹°áˆ›áˆ˜áŒŖá‰Ŋሁ ምá‹ĩር በምá‰ĩገቡበá‰ĩና
ከምá‹ĩáˆĒቱ ማንኛውንም ምግá‰Ĩ በምá‰ĩበሉበá‰ĩ ጊዜ ለይሖዋ መዋጮ ማá‹ĩረግ áŠ áˆˆá‰Ŗá‰Ŋሁáĸ
ከተፈጨው የáŠĨህላá‰Ŋሁ በኩር ላይ የቀለበá‰ĩ ቅርáŒŊ á‹Ģለው á‹ŗá‰Ļ በማዘጋጀá‰ĩ መዋጮ ማá‹ĩረግ á‹­áŠ–áˆ­á‰Ŗá‰Ŋኋልáĸ ይህን áˆ›á‹‹áŒŖá‰ĩ á‹¨áˆšáŠ–áˆ­á‰Ŗá‰Ŋሁ ከአውá‹ĩማ ላይ የሚገኘውን መዋጮ á‰ áˆá‰ŗá‹‹áŒĄá‰ á‰ĩ መንገá‹ĩ ነውáĸ
በá‰ĩውልá‹ļá‰ģá‰Ŋሁ áˆáˆ‰áŖ ከተፈጨው የáŠĨህላá‰Ŋሁ በኩር ላይ የተወሰነውን ለይሖዋ መዋጮ አá‹ĩርጋá‰Ŋሁ መáˆĩጠá‰ĩ á‹­áŠ–áˆ­á‰Ŗá‰Ŋኋልáĸ
â€œâ€˜áˆáŠ“áˆá‰Ŗá‰ĩ áˆĩህተá‰ĩ á‰Ĩá‰ĩሠሩና ይሖዋ ለሙሴ የተናገáˆĢቸውን áŠĨነዚህን á‰ĩáŠĨዛዛá‰ĩ ሁሉ áˆŗá‰ĩፈáŒŊሙ á‰Ĩá‰ĩቀሩ
ይኸውም ይሖዋ á‰ĩáŠĨዛዙን ከሰጠበá‰ĩ ዕለá‰ĩ አንáˆĩá‰ļ áˆĨáˆĢ ላይ የዋለውንና በá‰ĩውልá‹ļá‰ģá‰Ŋሁ ሁሉ ጸንá‰ļ የሚኖረውን ይሖዋ በሙሴ በኩል á‹Ģáˆĩተላለፈላá‰Ŋሁን á‰ĩáŠĨዛዝ ሁሉ á‰Ŗá‰ĩፈáŒŊሙና
ይህን á‹Ģደረጋá‰Ŋሁá‰ĩ ደግሞ በáˆĩህተá‰ĩና ማኅበረሰቡ áˆŗá‹Ģውቅ á‰ĸሆን መላው ማኅበረሰá‰Ĩ አንá‹ĩ ወይፈን ይሖዋን ደáˆĩ የሚá‹Ģሰኝ መዓዛ á‹Ģለው የሚቃጠል áˆ˜á‰Ŗ አá‹ĩርጎ á‹Ģቅርá‰Ĩ፤ ከáŠĨሱም ጋር በተለመደው አሠáˆĢር መሠረá‰ĩ የáŠĨህል áˆ˜á‰Ŗá‹áŠ•áŠ“ የመጠáŒĨ áˆ˜á‰Ŗá‹áŠ• áŠĨንዲሁም አንá‹ĩ የፍየል ጠá‰Ļá‰ĩ የኃáŒĸአá‰ĩ áˆ˜á‰Ŗ አá‹ĩርጎ á‹Ģቅርá‰Ĩáĸ
áŠĢህኑም ለመላው የáŠĨáˆĩáˆĢኤል ማኅበረሰá‰Ĩ á‹Ģáˆĩተሰርá‹Ģል፤ ኃáŒĸአቱም á‰Ŗáˆˆáˆ›á‹ˆá‰… የተፈጸመ áˆĩለሆነና ለሠሊá‰ĩም áˆĩህተá‰ĩ áˆ˜á‰Ŗá‰¸á‹áŠ• ለይሖዋ በáŠĨáˆŗá‰ĩ የሚቃጠል áˆ˜á‰Ŗ አá‹ĩርገው áˆĩላቀረቡ áŠĨንዲሁም በይሖዋ ፊá‰ĩ የኃáŒĸአá‰ĩ áˆ˜á‰Ŗá‰¸á‹áŠ• áˆĩላቀረቡ ይቅር á‹­á‰Ŗáˆáˆ‹á‰¸á‹‹áˆáĸ
ይህም ሕዝቡ ሁሉ á‰Ŗáˆˆáˆ›á‹ˆá‰… የፈጸመው áˆĩለሆነ መላው የáŠĨáˆĩáˆĢኤል ማኅበረሰá‰Ĩም ሆነ በመáŠĢከላቸው የሚኖር á‹¨á‰Ŗá‹•á‹ĩ አገር ሰው ይቅር á‹­á‰Ŗáˆ‹áˆáĸ
“‘ማንኛውም ሰው á‰Ŗáˆˆáˆ›á‹ˆá‰… ኃáŒĸአá‰ĩ á‰ĸሠáˆĢ አንá‹ĩ ዓመá‰ĩ ገደማ የሆናá‰ĩ አንዲá‰ĩ ፍየል የኃáŒĸአá‰ĩ áˆ˜á‰Ŗ አá‹ĩርጎ á‹Ģቅርá‰Ĩáĸ
ከዚá‹Ģም á‰Ŗáˆˆáˆ›á‹ˆá‰… በይሖዋ ፊá‰ĩ ኃáŒĸአá‰ĩ በመáˆĨáˆĢá‰ĩ á‹¨á‰°áˆŗáˆŗá‰°á‹ ሰው ኃáŒĸአቱ ይሰረይለá‰ĩ ዘንá‹ĩ áŠĢህኑ ማáˆĩተሰረá‹Ģ á‹Ģቀርá‰Ĩáˆˆá‰ŗáˆá¤ ኃáŒĸአቱም ይቅር á‹­á‰Ŗáˆáˆˆá‰ŗáˆáĸ
á‰Ŗáˆˆáˆ›á‹ˆá‰… ከሚፈጸም ነገር ጋር በተá‹Ģá‹Ģዘ በáŠĨáˆĩáˆĢኤላውá‹Ģን መáŠĢከል ለሚገኝ የአገáˆŦው ተወላጅም ሆነ በመáŠĢከላቸው ለሚኖር á‹¨á‰Ŗá‹•á‹ĩ አገር ሰው አንá‹ĩ ዓይነá‰ĩ ሕግ ይኑáˆĢá‰Ŋሁáĸ
“‘ይሁን áŠĨንጂ ሆን á‰Ĩሎ ኃáŒĸአá‰ĩ የሚሠáˆĢ ሰው የአገáˆŦው ተወላጅም ይሁን á‹¨á‰Ŗá‹•á‹ĩ አገር ሰው ይሖዋን áŠĨáŠ•á‹°á‰°áˆŗá‹°á‰  áˆĩለሚቆጠር ከሕዝቡ ተለይá‰ļ áŠĨንዲጠፋ መደረግ አለበá‰ĩáĸ
የይሖዋን ቃል áˆĩላቃለለና የáŠĨሱን á‰ĩáŠĨዛዝ áˆĩáˆˆáŒŖáˆ° á‹Ģ ሰው á‹Ģለምንም áŒĨርáŒĨር ተለይá‰ļ áŠĨንዲጠፋ መደረግ አለበá‰ĩáĸ áŒĨፋቱ የáˆĢሹ ነውáĸ’”
áŠĨáˆĩáˆĢኤላውá‹Ģን በምá‹ĩረ á‰ á‹ŗ áˆŗáˆ‰ አንá‹ĩ ሰው በሰንበá‰ĩ ቀን áŠĨንጨá‰ĩ ሲለቅም አገኙáĸ
ሰዎቹም áŠĨንጨá‰ĩ ሲለቅም á‹Ģገኙá‰ĩን ሰው ወደ áˆ™áˆ´áŖ ወደ አሮንና ወደ መላው ማኅበረሰá‰Ĩ አመጡá‰ĩáĸ
ሰውየው ምን መደረግ áŠĨáŠ•á‹ŗáˆˆá‰ á‰ĩ በግልáŒŊ የተቀመጠ ነገር áˆĩላልነበረ በáŒĨበቃ áˆĨር áŠĨንዲቆይ አደረጉáĸ
ይሖዋም ሙሴን “ሰውየው á‹Ģለምንም áŒĨርáŒĨር መገደል አለበá‰ĩ፤ መላው ማኅበረሰá‰Ĩም ከሰፈሩ ውጭ በá‹ĩንጋይ ይውገረው” አለውáĸ
áˆĩለዚህ ይሖዋ ሙሴን á‰Ŗá‹˜á‹˜á‹ መሠረá‰ĩ መላው ማኅበረሰá‰Ĩ ሰውየውን ከሰፈሩ ውጭ አውáŒĨá‰ļ áŠĨáˆĩáŠĒሞá‰ĩ á‹ĩረáˆĩ በá‹ĩንጋይ ወገረውáĸ
ይሖዋ ሙሴን áŠĨንዲህ አለውáĻ
“áŠĨáˆĩáˆĢኤላውá‹Ģን በá‰ĩውልá‹ļá‰ģቸው ሁሉ በልá‰Ĩáˆŗá‰¸á‹ áŒĢፍ ላይ ዘርፍ áŠĨንዲá‹Ģደርጉ ንገáˆĢቸው፤ ልá‰Ĩáˆŗá‰¸á‹áˆ ከዘርፉ በላይ ሰማá‹Ģዊ áŒĨለá‰ĩ ይኑረውáĸ
‘ይህን ዘርፍ በልá‰Ĩáˆŗá‰Ŋሁ ላይ አá‹ĩርጉ፤ ምክንá‹Ģቱም áŠĨሱን áˆĩá‰ŗá‹Š የይሖዋን á‰ĩáŠĨዛዛá‰ĩ ሁሉ á‰ŗáˆĩá‰ŗá‹áˆŗáˆ‹á‰Ŋሁ፤ áŠĨንዲሁም á‰ĩፈáŒŊማላá‰Ŋሁáĸ ወደ áˆ˜áŠ•áˆáˆŗá‹Š ምንዝር የሚመáˆĢá‰Ŋሁን á‹¨áŒˆá‹›Â áˆá‰Ŗá‰Ŋሁንና ዓይናá‰Ŋሁን አá‰ĩከተሉáĸ
ይህን መመáˆĒá‹Ģ የሰጠኋá‰Ŋሁ á‰ĩáŠĨዛዛቴን በሙሉ áŠĨንá‹ĩá‰ŗáˆĩá‰ŗá‹áˆąáŠ“ áŠĨንá‹ĩá‰ĩፈáŒŊሙ ነው፤ ለአምላáŠĢá‰Ŋሁም á‹¨á‰°á‰€á‹°áˆŗá‰Ŋሁ á‰ĩሆናላá‰Ŋሁáĸ
አምላáŠĢá‰Ŋሁ መሆኔን ለማáˆĩመáˆĨከር ከግá‰Ĩፅ ምá‹ĩር á‹Ģá‹ˆáŒŖáŠ‹á‰Ŋሁ áŠĨኔ አምላáŠĢá‰Ŋሁ ይሖዋ ነኝáĸ áŠ á‹ŽáŖ áŠĨኔ አምላáŠĢá‰Ŋሁ ይሖዋ ነኝáĸ’”
የሮቤል ልጆá‰Ŋና የጋá‹ĩ ልጆá‰Ŋ áŠĨጅግ á‰ áŒŖáˆ á‰Ĩዙ ከá‰Ĩá‰ĩ ነበáˆĢቸውáĸ áŠĨነሱም የá‹Ģዜር áŠĨና የጊልá‹Ģá‹ĩ ምá‹ĩር ለከá‰Ĩá‰ļá‰Ŋ የሚáˆĩማማ áˆĩፍáˆĢ áŠĨንደሆነ አዩáĸ
በመሆኑም የሮቤል ልጆá‰Ŋና የጋá‹ĩ ልጆá‰Ŋ መáŒĨተው áˆ™áˆ´áŠ•áŖ áŠĢህኑን አልዓዛርንና የማኅበረሰቡን አለቆá‰Ŋ áŠĨንዲህ አሏቸውáĻ
â€œá‹¨áŠ áŒŖáˆŽá‰ĩáŖ የዲá‰ĻáŠ•áŖ የá‹Ģá‹œáˆ­áŖ የኒምáˆĢáŖ የሃáˆŊá‰ĻáŠ•áŖ á‹¨áŠ¤áˆá‹“áˆŒáŖ á‹¨áˆ°á‰ŖáˆáŖ የነá‰Ļ áŠĨና የቤáŠĻን ምá‹ĩር
ይሖዋ በáŠĨáˆĩáˆĢኤል ማኅበረሰá‰Ĩ ፊá‰ĩ á‹ĩል á‹Ģደረገው ሲሆን ለከá‰Ĩá‰ļá‰Ŋ ምቹ ነው፤ አገልጋዮá‰Ŋህ ደግሞ á‰Ĩዙ ከá‰Ĩá‰ĩ አላቸውáĸ”
አክለውም áŠĨንዲህ አሉáĻ “áŠĨንግዲህ በፊá‰ĩህ ሞገáˆĩ áŠĢገኘን ይህ ምá‹ĩር ለአገልጋዮá‰Ŋህ ርáˆĩá‰ĩ ተደርጎ ይሰáŒĨáĸ á‹Žáˆ­á‹ŗáŠ–áˆĩን áŠĨንá‹ĩንáˆģገር áŠ á‰ŗá‹ĩርገንáĸ”
ከዚá‹Ģም ሙሴ የጋá‹ĩን ልጆá‰Ŋና የሮቤልን ልጆá‰Ŋ áŠĨንዲህ አላቸውáĻ “áŠĨናንተ áŠĨዚህ á‰°á‰€áˆáŒŖá‰Ŋሁ ወንá‹ĩሞá‰ģá‰Ŋሁ ወደ áŒĻርነá‰ĩ áŠĨንዲሄዱ á‰ĩፈልጋላá‰Ŋሁ?
የáŠĨáˆĩáˆĢኤል ልጆá‰Ŋ ይሖዋ á‹ˆá‹°áˆšáˆ°áŒŖá‰¸á‹ ምá‹ĩር áŠĨáŠ•á‹ŗá‹­áˆģገሩ ተáˆĩፋ á‹¨áˆá‰ŗáˆĩቆርጧቸው ለምንá‹ĩን ነው?
áŠ á‰Ŗá‰ļá‰ģá‰Ŋሁ ምá‹ĩáˆĒቱን áŠĨንዲá‹Ģዩ ከቃዴáˆĩበርኔ በላክኋቸው ጊዜ á‹Ģደረጉá‰ĩ ይህንኑ ነበርáĸ
ወደ ኤáˆŊኮል ሸለቆ አቅንተው ምá‹ĩáˆĒቱን áŠĢዩ በኋላ የáŠĨáˆĩáˆĢኤልን ሕዝá‰Ĩ ይሖዋ ወደሚሰጠው ምá‹ĩር áŠĨáŠ•á‹ŗá‹­áŒˆá‰Ŗ ተáˆĩፋ አáˆĩቆረጡá‰ĩáĸ
በዚá‹Ģ ቀን የይሖዋ á‰áŒŖ ነደደ፤ áŠĨንዲህም ሲል ማለáĻ
‘ከግá‰Ĩፅ ምá‹ĩር ከወጡá‰ĩ መáŠĢከል 20 ዓመá‰ĩና ከዚá‹Ģ በላይ የሆናቸው ለአá‰Ĩáˆ­áˆƒáˆáŖ ለይáˆĩሐቅና ለá‹Ģዕቆá‰Ĩ የማልኩላቸውን ምá‹ĩር አá‹Ģዩም፤ ምክንá‹Ģቱም በሙሉ áˆá‰Ŗá‰¸á‹ አልተከተሉኝም፤
ይሖዋን በሙሉ áˆá‰Ŗá‰¸á‹ ከተከተሉá‰ĩ ከቀኒዛዊው ከየፎኒ ልጅ ከáŠĢሌá‰Ĩና ከነዌ ልጅ ከáŠĸá‹Ģሹ በáˆĩተቀር áŠ áŠ•á‹ŗá‰¸á‹áˆ ምá‹ĩáˆĒቱን አá‹Ģዩምáĸ’
በመሆኑም የይሖዋ á‰áŒŖ በáŠĨáˆĩáˆĢኤል ላይ ነደደ፤ በይሖዋ ፊá‰ĩ ክፉ á‹ĩርጊá‰ĩ የፈጸመው á‹Ģ á‰ĩውልá‹ĩ በሙሉ áŠĨáˆĩáŠĒá‹Ģልቅ á‹ĩረáˆĩ ለ40 ዓመá‰ĩ በምá‹ĩረ á‰ á‹ŗ áŠĨንዲንከáˆĢተቱ አደረጋቸውáĸ
áŠĨናንተ የኃáŒĸአተኞá‰Ŋ ልጆá‰Ŋ ደግሞ ይኸው á‰ áŠ á‰Ŗá‰ļá‰ģá‰Ŋሁ áŠĨግር á‰°á‰°áŠ­á‰ŗá‰Ŋሁ ይሖዋ በáŠĨáˆĩáˆĢኤል ላይ ይበልáŒĨ áŠĨáŠ•á‹˛á‰†áŒŖ á‰ŗá‹°áˆ­áŒ‹áˆ‹á‰Ŋሁáĸ
áŠĨንግዲህ áŠĨናንተ áŠĨሱን ከመከተል ዞር áŠĢላá‰Ŋሁ áŠĨሱም áŠĨንደገና በምá‹ĩረ á‰ á‹ŗ ይተዋቸዋል፤ áŠĨናንተም በዚህ ሁሉ ሕዝá‰Ĩ ላይ áŒĨፋá‰ĩ á‰ŗáˆ˜áŒŖáˆ‹á‰Ŋሁáĸ”
በኋላም ወደ áŠĨሹ ቀርበው áŠĨንዲህ አሉá‰ĩáĻ “áŠĨንግዲá‹Ģው áŠĨዚሁ ለከá‰Ĩá‰ļá‰ģá‰Ŋን በá‹ĩንጋይ áŠĢá‰Ĩ በረá‰ĩ áŠĨንáˆĨáˆĢ፤ ለልጆá‰ģá‰Ŋንም ከተሞá‰Ŋ áŠĨáŠ•áŒˆáŠ•á‰Ŗáĸ
ይሁን áŠĨንጂ ወደ áˆĩፍáˆĢቸው áŠĨáˆĩክናáˆĩáŒˆá‰Ŗá‰¸á‹ á‹ĩረáˆĩ ለáŒĻርነá‰ĩ á‰ŗáŒĨቀን በáŠĨáˆĩáˆĢኤላውá‹Ģን ፊá‰ĩ áŠĨáŠ•áˆ„á‹ŗáˆˆáŠ•á¤ በዚህም ጊዜ ልጆá‰ģá‰Ŋን ከምá‹ĩáˆĒቱ ነዋáˆĒዎá‰Ŋ ተጠá‰Ĩቀው በተመሸጉá‰ĩ ከተሞá‰Ŋ ውáˆĩáŒĨ ይኖáˆĢሉáĸ
áŠĨኛም áŠĨá‹ĢáŠ•á‹ŗáŠ•á‹ą áŠĨáˆĩáˆĢኤላዊ የáˆĢሱን ርáˆĩá‰ĩ áŠĨáˆĩáŠĒá‹Ģገኝ á‹ĩረáˆĩ ወደ á‰¤á‰ŗá‰Ŋን አንመለáˆĩምáĸ
áŠĨኛ áŠ¨á‹Žáˆ­á‹ŗáŠ–áˆĩ በáˆĩተ ምáˆĨáˆĢቅ á‰Ŗáˆˆá‹ አáŠĢá‰Ŗá‰ĸ ርáˆĩá‰ĩ áŠĢገኘን áŠ¨á‹Žáˆ­á‹ŗáŠ–áˆĩ ማá‹ļና ከዚá‹Ģ á‰Ŗáˆģገር á‰Ŗáˆˆá‹ አáŠĢá‰Ŗá‰ĸ ከáŠĨነሱ ጋር ርáˆĩá‰ĩ አንáŠĢፈልምáĸ”
ሙሴም áŠĨንዲህ አላቸውáĻ “ይህን á‰Ĩá‰ŗá‹°áˆ­áŒ‰ ይኸውም በáŒĻርነቱ ለመáŠĢፈል በይሖዋ ፊá‰ĩ á‰ŗáŒĨቃá‰Ŋሁ á‰Ĩá‰ĩነሱ
áŠĨንዲሁም ጠላá‰ļቹን ከፊቱ áŠĨáˆĩáŠĒá‹Ģáˆĩወግá‹ĩ á‹ĩረáˆĩ áŠĨá‹ĢáŠ•á‹ŗáŠ•á‹ŗá‰Ŋሁ የáŒĻር áˆ˜áˆŖáˆĒá‹Ģá‰Ŋሁን ይዛá‰Ŋሁ በይሖዋ ፊá‰ĩ á‹Žáˆ­á‹ŗáŠ–áˆĩን á‰Ĩá‰ĩáˆģገሩና
ምá‹ĩáˆĒቱ በይሖዋ ፊá‰ĩ áŠĨáˆĩክá‰ĩገዛ á‹ĩረáˆĩ በዚá‹Ģ á‰Ĩá‰ĩá‰†á‹ŠáŖ ከዚá‹Ģ በኋላ መመለáˆĩ á‰ĩá‰Ŋላላá‰Ŋሁ፤ በይሖዋም ሆነ በáŠĨáˆĩáˆĢኤላውá‹Ģን ዘንá‹ĩ ከበደል ነፃ á‰ĩሆናላá‰Ŋሁáĸ ከዚá‹Ģም ይህá‰Ŋ ምá‹ĩር በይሖዋ ፊá‰ĩ የáŠĨናንተ ርáˆĩá‰ĩ á‰ĩሆናለá‰Ŋáĸ
ይህን á‰Ŗá‰ŗá‹°áˆ­áŒ‰ ግን በይሖዋ ላይ ኃáŒĸአá‰ĩ á‰ĩሠáˆĢላá‰Ŋሁáĸ ለሠáˆĢá‰Ŋሁá‰ĩም ኃáŒĸአá‰ĩ ተጠá‹Ģቂ áŠĨንደምá‰ĩሆኑ áŠĨወቁáĸ
áˆĩለዚህ ለልጆá‰ģá‰Ŋሁ ከተሞá‰Ŋን áˆ˜áŒˆáŠ•á‰Ŗá‰ĩና ለመንጎá‰ģá‰Ŋሁ በረá‰ĩ መáˆĨáˆĢá‰ĩ የምá‰ĩá‰Ŋሉ á‰ĸሆንም á‹¨áŒˆá‰Ŗá‰Ŋሁá‰ĩን ቃል መፈጸም á‹­áŠ–áˆ­á‰Ŗá‰Ŋኋልáĸ”
የጋá‹ĩ ልጆá‰Ŋና የሮቤል ልጆá‰Ŋም ሙሴን áŠĨንዲህ አሉá‰ĩáĻ “áŠĨኛ አገልጋዮá‰Ŋህ áŒŒá‰ŗá‰Ŋን áŠĨáŠ•á‹ŗá‹˜á‹˜áŠ• áŠĨናደርጋለንáĸ
ልጆá‰ģá‰ŊáŠ•áŖ ሚáˆĩá‰ļá‰ģá‰ŊáŠ•áŖ ከá‰Ĩá‰ļá‰ģá‰Ŋንና áŠĨንáˆĩáˆļá‰ģá‰Ŋን በሙሉ በጊልá‹Ģá‹ĩ ከተሞá‰Ŋ ውáˆĩáŒĨ ይቆá‹Ģሉ፤
ሆኖም áŠĨኛ አገልጋዮá‰Ŋህ ይኸውም በይሖዋ ፊá‰ĩ áŒĻርነá‰ĩ ለመግጠም á‹¨á‰ŗáŒ á‰…áŠ• áŠĨá‹ĢáŠ•á‹ŗáŠ•á‹ŗá‰Ŋን ልክ áŒŒá‰ŗá‰Ŋን በተናገረው መሠረá‰ĩ áŠĨንáˆģገáˆĢለንáĸ”
በመሆኑም ሙሴ ለáŠĢህኑ áˆˆáŠ áˆá‹“á‹›áˆ­áŖ ለነዌ ልጅ ለáŠĸá‹Ģሱና ለáŠĨáˆĩáˆĢኤል ነገá‹ļá‰Ŋ á‹¨áŠ á‰Ŗá‰ļá‰Ŋ ቤá‰ĩ መáˆĒዎá‰Ŋ áŠĨነሱን በተመለከተ á‰ĩáŠĨዛዝ ሰጠáĸ
ሙሴም áŠĨንዲህ አላቸውáĻ “የጋá‹ĩ ልጆá‰Ŋና የሮቤል ልጆá‰Ŋ ይኸውም በይሖዋ ፊá‰ĩ ለáŒĻርነá‰ĩ á‹¨á‰ŗáŒ á‰€ áŠĨá‹ĢáŠ•á‹ŗáŠ•á‹ą ሰው ከáŠĨናንተ ጋር á‹Žáˆ­á‹ŗáŠ–áˆĩን ከተáˆģáŒˆáˆ¨áŖ ምá‹ĩáˆĒቱም á‰ áŠá‰ŗá‰Ŋሁ ከተገዛá‰Ŋ የጊልá‹Ģá‹ĩን ምá‹ĩር ርáˆĩá‰ĩ አá‹ĩርጋá‰Ŋሁ á‰ĩሰጧቸዋላá‰Ŋሁáĸ
ሆኖም የáŒĻር áˆ˜áˆŖáˆĒá‹Ģ á‰ŗáŒĨቀው ከáŠĨናንተ ጋር áŠĢልተáˆģገሩ በከነአን ምá‹ĩር በመáŠĢከላá‰Ŋሁ ይኖáˆĢሉáĸ”
በዚህ ጊዜ የጋá‹ĩ ልጆá‰Ŋና የሮቤል ልጆá‰Ŋ áŠĨንዲህ ሲሉ መለሹáĻ “ይሖዋ ለአገልጋዮá‰Ŋህ የተናገረውን áŠĨንፈáŒŊማለንáĸ
áŠĨኛ áˆĢáˆŗá‰Ŋን የáŒĻር áˆ˜áˆŖáˆĒá‹Ģ á‰ŗáŒĨቀን በይሖዋ ፊá‰ĩ ወደ ከነአን ምá‹ĩር áŠĨንáˆģገáˆĢለን፤ የምንወርሰው ርáˆĩá‰ĩ ግን áŠ¨á‹Žáˆ­á‹ŗáŠ–áˆĩ ወዲህ á‹Ģለውን ይሆናልáĸ”
áˆĩለዚህ ሙሴ ለጋá‹ĩ ልጆá‰Ŋና ለሮቤል ልጆá‰Ŋ áŠĨንዲሁም ለዮሴፍ ልጅ ለምናሴ ነገá‹ĩ áŠĨáŠŠáˆŒá‰ŗ የአሞáˆĢውá‹Ģንን ንጉáˆĨ የሲሖንን ግዛá‰ĩና á‹¨á‰ŖáˆŗáŠ•áŠ• ንጉáˆĨ የáŠĻግን ግዛá‰ĩ ይኸውም በክልሎቹ ውáˆĩáŒĨ የሚገኙ ከተሞá‰Ŋ á‹­á‹žá‰ŗ የሆነውን ምá‹ĩር áŠĨንዲሁም በዙáˆĒá‹Ģው á‰Ŗáˆˆá‹ ምá‹ĩር á‹Ģሉá‰ĩን ከተሞá‰Ŋ áˆ°áŒŖá‰¸á‹áĸ
የጋá‹ĩ ልጆá‰Ŋም ዲá‰ĻáŠ•áŖ áŠ áŒŖáˆŽá‰ĩáŖ áŠ áˆŽá‹”áˆ­áŖ
አá‰ĩሎá‰ĩáˆžá‹áŠ•áŖ á‹Ģá‹œáˆ­áŖ á‹ŽáŒá‰ áˆƒáŖ
ቤá‰ĩኒምáˆĢ áŠĨና ቤá‰ĩሃáˆĢን á‹¨á‰°á‰Ŗáˆ‰á‰ĩን የተመሸጉ ከተሞá‰Ŋ ገነቡ፤ ለመንጎቹም በá‹ĩንጋይ áŠĢá‰Ĩ በረá‰ĩ ሠሊáĸ
የሮቤል ልጆá‰Ŋ ደግሞ ሃáˆŊá‰ĻáŠ•áŠ•áŖ áŠ¤áˆá‹“áˆŒáŠ•áŖ ቂርá‹Ģá‰ŗá‹­áˆáŠ•áŖ
áˆĩማቸው የተለወጠውን ነá‰Ļን áŠĨና በዓልመዖንን áŠĨንዲሁም ሲá‰Ĩማን ገነቡ፤ áŠĨነሱም መልሰው ለገነቧቸው ከተሞá‰Ŋ አዲáˆĩ áˆĩም አወጡላቸውáĸ
የምናሴ ልጅ የማáŠĒር ልጆá‰Ŋ በጊልá‹Ģá‹ĩ ላይ ዘምተው ምá‹ĩáˆĒቱን á‹Ģዙ፤ በዚá‹Ģም ይኖሩ የነበሩá‰ĩን አሞáˆĢውá‹Ģን አáˆĩወጧቸውáĸ
በመሆኑም ሙሴ ጊልá‹Ģá‹ĩን ለምናሴ ልጅ ለማáŠĒር ሰጠው፤ áŠĨሱም በዚá‹Ģ መኖር ጀመረáĸ
የምናሴ ልጅ á‹ĢáŠĸርም በáŠĨነሱ ላይ ዘምá‰ļ የá‹ĩáŠ•áŠŗáŠ• ሰፈሮá‰ģቸውን á‹Ģዘ፤ áŠĨነሱንም ሃዎá‰ĩá‹ĢáŠĸር á‰Ĩሎ ጠáˆĢቸውáĸ
áŠ–á‰Ŗáˆ…áˆ ዘምá‰ļ ቄናá‰ĩንና በáˆĨሯ á‹Ģሉá‰ĩን ከተሞá‰Ŋ á‹Ģዘ፤ áŠĨነሱንም በáˆĢሹ áˆĩም áŠ–á‰Ŗáˆ… á‰Ĩሎ ሰየማቸውáĸ
ይሖዋም ሙሴንና አሮንን áŠĨንዲህ አላቸውáĻ
“ከሌዊ ልጆá‰Ŋ መáŠĢከል የቀአá‰ĩን ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆá‰Ŋ á‰ á‹¨á‰¤á‰°áˆ°á‰Ŗá‰¸á‹áŠ“ á‰ á‹¨áŠ á‰Ŗá‰ļá‰ģቸው ቤá‰ļá‰Ŋ መሠረá‰ĩ ቁጠሩ፤
በመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘ ውáˆĩáŒĨ áŠĨንዲሠáˆĢ በተመደበው ቡá‹ĩን ውáˆĩáŒĨ á‹Ģሉá‰ĩን ዕá‹ĩሜá‹Ģቸው ከ30 áŠĨáˆĩከ 50 ዓመá‰ĩ የሆኑá‰ĩን ሁሉ ቁጠሩáĸ
“የቀአá‰ĩ ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆá‰Ŋ በመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘ ውáˆĩáŒĨ የሚá‹Ģከናውኑá‰ĩ አገልግሎá‰ĩ ይህ ነውáĸ ይህ áŠĨጅግ ቅዱáˆĩ የሆነ ነገር ነውáĻ
ሰፈሩ á‰ áˆšáŠáˆŗá‰ á‰ĩ ጊዜ አሮንና ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆቹ መáŒĨተው á‰ŗá‰Ļቱን የሚከልለውን መጋረጃ á‹Ģá‹ˆáˆ­á‹ąá‰ŗáˆá¤ የምáˆĨክሩንም á‰ŗá‰Ļá‰ĩ በáŠĨሹ á‹­áˆ¸ááŠ‘á‰ŗáˆáĸ
በላዩም ላይ ከአቆáˆĩáŒŖ á‰†á‹ŗ የተሠáˆĢ መሸፈኛ á‹­á‹°áˆ­á‰Ąá‰ á‰ŗáˆá¤ áŠĨንዲሁም ሙሉ በሙሉ ሰማá‹Ģዊ የሆነ ጨርቅ á‹Ģለá‰Ĩáˆąá‰ŗáˆá¤ ለመሸከሚá‹Ģ የሚá‹Ģገለግሉá‰ĩንም መሎጊá‹Ģዎá‰Ŋ በá‰Ļá‰ŗá‰¸á‹ ላይ á‹Ģደርጓቸዋልáĸ
“ገጸ ኅá‰Ĩáˆĩቱ የሚቀመáŒĨበá‰ĩንም ጠረጴዛ ሰማá‹Ģዊ ጨርቅ á‹Ģለá‰Ĩáˆąá‰ŗáˆá¤ በላዩም ላይ áˆŗáˆ…áŠ–á‰šáŠ•áŖ áŒŊá‹‹á‹Žá‰šáŠ•áŖ ጎá‹ĩáŒ“á‹ŗ áˆŗáˆ…áŠ–á‰šáŠ•áŠ“ ለመጠáŒĨ áˆ˜á‰Ŗ የሚሆኑá‰ĩን ማንቆርቆáˆĒá‹Ģዎá‰Ŋ á‹Ģáˆĩá‰€áˆáŒŖáˆ‰á¤ የዘወá‰ĩሩም á‹¨á‰‚áŒŖ áˆ˜á‰Ŗ ከላዩ ላይ áŠ á‹­áŠáˆŗáĸ
ደማቅ ቀይ ጨርቅ á‹Ģለá‰Ĩሷቸዋል፤ ከአቆáˆĩáŒŖ á‰†á‹ŗ የተሠáˆĢ መሸፈኛም á‹­á‹°áˆ­á‰Ąá‰ á‰ŗáˆá¤ áŠĨንዲሁም ለመሸከሚá‹Ģ የሚá‹Ģገለግሉá‰ĩን መሎጊá‹Ģዎá‰Ŋ በá‰Ļá‰ŗá‰¸á‹ ላይ á‹Ģደርጓቸዋልáĸ
ከዚá‹Ģም ሰማá‹Ģዊ ጨርቅ ወáˆĩደው የመá‰ĨáˆĢቱን መቅረዝ ከመá‰ĨáˆĢá‰ļá‰šáŖ ከመቆንጠáŒĢዎቹና ከመኮáˆĩተáˆĒá‹Ģዎቹ áŠĨንዲሁም ዘወá‰ĩር ዘይá‰ĩ áŠĨንዲኖር ለማá‹ĩረግ ከሚá‹Ģገለግሉá‰ĩ ዘይá‰ĩ የሚቀመáŒĨá‰Ŗá‰¸á‹ ዕቃዎá‰Ŋ ሁሉ ጋር á‹­áˆ¸ááŠ‘á‰ŗáˆáĸ
መቅረዙን ከዕቃዎቹ ሁሉ ጋር ከአቆáˆĩáŒŖ á‰†á‹ŗ በተሠáˆĢ መሸፈኛ á‹­áŒ á‰€áˆáˆ‰á‰ŗáˆá¤ በመሸከሚá‹Ģ áˆŗáŠ•á‰ƒ ላይም á‹Ģáˆĩá‰€áˆáŒĄá‰ŗáˆáĸ
የወርቁን መሠዊá‹Ģም ሰማá‹Ģዊ ጨርቅ á‹Ģለá‰Ĩáˆąá‰ŗáˆá¤ ከአቆáˆĩáŒŖ á‰†á‹ŗ የተሠáˆĢ መሸፈኛም á‹­á‹°áˆ­á‰Ąá‰ á‰ŗáˆá¤ ለመሸከሚá‹Ģ የሚá‹Ģገለግሉá‰ĩንም መሎጊá‹Ģዎá‰Ŋ በá‰Ļá‰ŗá‰¸á‹ ላይ á‹Ģደርጓቸዋልáĸ
ከዚá‹Ģም በቅዱሱ áˆĩፍáˆĢ ዘወá‰ĩር á‹¨áˆšáŒ á‰€áˆ™á‰Ŗá‰¸á‹áŠ• መገልገá‹Ģ ዕቃዎá‰Ŋ በሙሉ ወáˆĩደው በሰማá‹Ģዊ ጨርቅ ይጠቀልሏቸዋል፤ ከአቆáˆĩáŒŖ á‰†á‹ŗ የተሠáˆĢ መሸፈኛም á‹­á‹°áˆ­á‰Ąá‰Ŗá‰¸á‹‹áˆá¤ በመሸከሚá‹Ģ áˆŗáŠ•á‰ƒ ላይም á‹Ģáˆĩቀምጧቸዋልáĸ
“አመዱን ከመሠዊá‹Ģው ላይ á‹Ģáˆĩወግዱ፤ መሠዊá‹Ģውንም ሐምáˆĢዊ የሱፍ ጨርቅ á‹Ģልá‰Ĩሹá‰ĩáĸ
áŠĨንዲሁም በመሠዊá‹Ģው ላይ ለማገልገል á‹¨áˆšáŒ á‰€áˆ™á‰Ŗá‰¸á‹áŠ• ዕቃዎá‰Ŋ በሙሉ ይኸውም መኮáˆĩተáˆĒá‹Ģá‹Žá‰šáŠ•áŖ ሚáŠĢá‹Žá‰šáŠ•áŖ አáŠĢá‹á‹Žá‰šáŠ•áŖ ጎá‹ĩáŒ“á‹ŗ áˆŗáˆ…áŠ–á‰šáŠ•áŠ“ የመሠዊá‹Ģውን ዕቃዎá‰Ŋ በሙሉ በላዩ ላይ á‹Ģá‹°áˆ­áŒ‰á‰ á‰ŗáˆá¤ ከአቆáˆĩáŒŖ á‰†á‹ŗ የተሠáˆĢ መሸፈኛም á‹­á‹°áˆ­á‰Ąá‰ á‰ŗáˆá¤ ለመሸከሚá‹Ģ የሚá‹Ģገለግሉá‰ĩንም መሎጊá‹Ģዎá‰Ŋ በá‰Ļá‰ŗá‰¸á‹ ላይ á‹Ģደርጓቸዋልáĸ
“አሮንና ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆቹ ሰፈሩ áŠ¨áˆ˜áŠáˆŗá‰ą በፊá‰ĩ በቅዱሱ áˆĩፍáˆĢ á‹Ģሉá‰ĩን ነገሮá‰Ŋና የቅዱሱን áˆĩፍáˆĢ ዕቃዎá‰Ŋ በሙሉ ሸፍነው መጨረáˆĩ áŠ áˆˆá‰Ŗá‰¸á‹áĸ ከዚá‹Ģም የቀአá‰ĩ ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆá‰Ŋ ለመሸከም á‹­áˆ˜áŒŖáˆ‰á¤ ሆኖም በቅዱሱ áˆĩፍáˆĢ á‹Ģሉá‰ĩን ነገሮá‰Ŋ መንáŠĢá‰ĩ á‹¨áˆˆá‰Ŗá‰¸á‹áˆá¤ ከነኩ ግን á‹­áˆžá‰ŗáˆ‰áĸ ከመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘ ጋር በተá‹Ģá‹Ģዘ áŠĨነዚህን ነገሮá‰Ŋ የማከናወኑ ኃላፊነá‰ĩ á‹¨á‰°áŒŖáˆˆá‹ በቀአá‰ĩ ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆá‰Ŋ ላይ ነውáĸ
“የመá‰ĨáˆĢቱን ዘይá‰ĩáŖ áŒĨሊ መዓዛ á‹Ģለውን á‹•áŒŖáŠ•áŖ ዘወá‰ĩር የሚቀርበውን የáŠĨህል áˆ˜á‰ŖáŠ“ የቅá‰Ĩዓá‰ĩ ዘይቱን á‹¨áˆ˜á‰†áŒŖáŒ áˆŠ ኃላፊነá‰ĩ የáŠĢህኑ የአሮን ልጅ የአልዓዛር ነውáĸ ቅዱሱን áˆĩፍáˆĢና ዕቃዎቹን ጨምሮ የማደáˆĒá‹Ģ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘áŠ• ሁሉና በውáˆĩጡ á‹Ģለውን ነገር በሙሉ á‹¨áˆ˜á‰†áŒŖáŒ áˆŠ ኃላፊነá‰ĩ የáŠĨሹ ነውáĸ”
በተጨማáˆĒም ይሖዋ ሙሴንና አሮንን áŠĨንዲህ አላቸውáĻ
â€œá‹¨á‰€áŠ á‰ŗá‹á‹Ģን ቤተሰá‰Ļá‰Ŋ ነገá‹ĩ ከሌዋውá‹Ģን መáŠĢከል ተለይá‰ļ áŠĨንዲጠፋ áŠ á‰ŗá‹ĩርጉáĸ
áŠĨጅግ ቅዱáˆĩ ወደሆኑá‰ĩ ነገሮá‰Ŋ á‰ áˆ˜á‰…áˆ¨á‰Ŗá‰¸á‹ á‹¨á‰°áŠáˆŗ áŠĨáŠ•á‹ŗá‹­áˆžá‰ąáŖ ከዚህ ይልቅ በሕይወá‰ĩ áŠĨንዲኖሩ ይህን አá‹ĩርጉላቸውáĸ አሮንና ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆቹ ገá‰Ĩተው ለáŠĨá‹ĢáŠ•á‹ŗáŠ•á‹ŗá‰¸á‹ áˆĨáˆĢቸውንና የሚሸከሙá‰ĩን ነገር ይመá‹ĩቡላቸውáĸ
ቅዱáˆĩ የሆኑá‰ĩን ነገሮá‰Ŋ áˆˆáŠ áá‰ŗ áŠĨáŠ•áŠŗ ገá‰Ĩተው ማየá‰ĩ á‹¨áˆˆá‰Ŗá‰¸á‹áˆá¤ áŠĢዩ ግን á‹­áˆžá‰ŗáˆ‰áĸ”
ከዚá‹Ģም ይሖዋ ሙሴን áŠĨንዲህ አለውáĻ
“የጌá‹ĩáˆļንን ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆá‰Ŋ á‰ á‹¨áŠ á‰Ŗá‰ļá‰ģቸው ቤá‰ļá‰Ŋና á‰ á‹¨á‰¤á‰°áˆ°á‰Ŗá‰¸á‹ ቁጠርáĸ
በመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘ ውáˆĩáŒĨ áŠĨንዲá‹Ģገለግል በተመደበው ቡá‹ĩን ውáˆĩáŒĨ á‹Ģሉá‰ĩን ዕá‹ĩሜá‹Ģቸው ከ30 áŠĨáˆĩከ 50 ዓመá‰ĩ የሆኑá‰ĩን ሁሉ መዝግá‰Ĩáĸ
የጌá‹ĩáˆļናውá‹Ģን ቤተሰá‰Ļá‰Ŋ áŠĨáŠ•á‹˛áŠ•áŠ¨á‰ŖáŠ¨á‰ĄáŠ“ áŠĨንዲሸከሙ የተመደቡá‰ĩ áŠĨነዚህን ነገሮá‰Ŋ ነውáĻ
áŠĨነሱም የማደáˆĒá‹Ģ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘áŠ• የá‹ĩáŠ•áŠŗáŠ• ጨርቆá‰ŊáŖ የመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘áŠ• ጨርቆá‰ŊáŖ መደረá‰ĸá‹Ģውንና ከáŠĨሹ በላይ á‹Ģለውን ከአቆáˆĩáŒŖ á‰†á‹ŗ የተሠáˆĢ መደረá‰ĸá‹Ģ áŠĨንዲሁም የመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘áŠ• መግá‰ĸá‹Ģ መከለá‹Ģ ይሸከማሉ፤
በተጨማáˆĒም የግá‰ĸውን መጋረጃዎá‰ŊáŖ በማደáˆĒá‹Ģ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘áŠ“ በመሠዊá‹Ģው ዙáˆĒá‹Ģ á‰Ŗáˆˆá‹ ግá‰ĸ መግá‰ĸá‹Ģ ላይ የሚገኘውን መከለá‹ĢáŖ የá‹ĩáŠ•áŠŗáŠ• ገመá‹ļá‰ģቸውንና ዕቃዎá‰ģቸውን በሙሉ áŠĨንዲሁም ለአገልግሎቱ የሚውሉá‰ĩን ነገሮá‰Ŋ ሁሉ ይሸከማሉáĸ የáˆĨáˆĢ ምá‹ĩá‰Ŗá‰¸á‹ ይህ ነውáĸ
ጌá‹ĩáˆļናውá‹Ģን የሚá‹Ģከናውኑá‰ĩን አገልግሎá‰ĩና የሚሸከሟቸውን ነገሮá‰Ŋ ሁሉ á‹¨áˆšá‰†áŒŖáŒ áˆŠá‰ĩ አሮንና ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆቹ ናቸው፤ áŠĨነዚህን ነገሮá‰Ŋ ሁሉ የመሸከሙን ኃላፊነá‰ĩ ለáŠĨነሱ á‰ĩáˆ°áŒŖá‰¸á‹‹áˆˆáˆ…áĸ
የጌá‹ĩáˆļናውá‹Ģን ቤተሰá‰Ļá‰Ŋ በመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘ ውáˆĩáŒĨ የሚá‹Ģከናውኑá‰ĩ አገልግሎá‰ĩ ይህ ነው፤ áŠƒáˆ‹áŠáŠá‰ŗá‰¸á‹áŠ•áˆ የሚወጡá‰ĩ በáŠĢህኑ በአሮን ልጅ በáŠĸá‰ŗáˆáˆ­ አመáˆĢር áˆĨር ሆነው ነውáĸ
“የሜáˆĢáˆĒን ወንá‹ļá‰Ŋ ልጆá‰Ŋም á‰ á‹¨á‰¤á‰°áˆ°á‰Ŗá‰¸á‹áŠ“ á‰ á‹¨áŠ á‰Ŗá‰ļá‰ģቸው ቤá‰ĩ á‰ĩáˆ˜á‹˜áŒá‰Ŗá‰¸á‹‹áˆˆáˆ…áĸ
በመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘ áŠĨንዲá‹Ģገለግል በተመደበው ቡá‹ĩን ውáˆĩáŒĨ á‹Ģሉá‰ĩን ዕá‹ĩሜá‹Ģቸው ከ30 áŠĨáˆĩከ 50 ዓመá‰ĩ የሆኑá‰ĩን ሁሉ á‰ĩáˆ˜á‹˜áŒá‰Ŗáˆˆáˆ…áĸ
በመገናኛ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘ ከሚá‹Ģከናውኑá‰ĩ አገልግሎá‰ĩ ጋር በተá‹Ģá‹Ģዘ የሚከተሉá‰ĩን ነገሮá‰Ŋ የመሸከም ኃላፊነá‰ĩ ተáŒĨáˆŽá‰Ŗá‰¸á‹‹áˆáĻ የማደáˆĒá‹Ģ á‹ĩáŠ•áŠŗáŠ‘áŠ• ቋሚዎá‰ŊáŖ áŠ áŒá‹ŗáˆš áŠĨንጨá‰ļá‰šáŠ•áŖ ዓምá‹ļá‰šáŠ•áŖ መሰáŠĒá‹Ģá‹Žá‰šáŠ•áŖ
በግá‰ĸው ዙáˆĒá‹Ģ á‹Ģሉá‰ĩን ቋሚዎá‰ŊáŖ መሰáŠĒá‹Ģዎá‰ģá‰¸á‹áŠ•áŖ የá‹ĩáŠ•áŠŗáŠ• áŠĢáˆĩማዎá‰ģá‰¸á‹áŠ•áŖ የá‹ĩáŠ•áŠŗáŠ• ገመá‹ļá‰ģቸውን áŠĨንዲሁም á‰áˆŗá‰áˆļá‰ģቸውንና ከዚህ አገልግሎá‰ĩ ጋር የተá‹Ģá‹Ģዙá‰ĩን ነገሮá‰Ŋ ሁሉ ይሸከማሉáĸ በኃላፊነá‰ĩ የሚሸከሙá‰ĩንም ዕቃ በáˆĩም ጠቅሰህ á‰ĩመá‹ĩá‰Ĩላቸዋለህáĸ