text
stringlengths
4
267
ኚሃሜቊን እስኚ ራማትምጜጳ እና እስኚ በጩኒም እንዲሁም ኹማሃናይም እስኚ ደቢር ወሰን ድሚስ ያለውን አካባቢ፣
በሾለቆው ውስጥ ደግሞ ቀትሃራምን፣ ቀትኒምራን፣ ሱኮትን፣ ጻፎንን እና ወሰኑ ዮርዳኖስ ሆኖ ኚዮርዳኖስ በስተ ምሥራቅ ኹሚገኘው ኚኪኔሬት ባሕር ዚታቜኛው ጫፍ ጀምሮ ያለውን ቀሪውን ዚሃሜቊንን ንጉሥ ዚሲሖንን ንጉሣዊ ግዛት ያጠቃልላል።
ኚተሞቹንና መንደሮቹን ጚምሮ ጋዳውያን በዚቀተሰባ቞ው ዚያዙት ርስት ይህ ነው።
በተጚማሪም ሙሮ ለምናሮ ነገድ እኩሌታ ይኾውም ለግማሹ ዹምናሮ ነገድ በዚቀተሰባ቞ው ርስት ሰጠ።
ግዛታ቞ውም ኹማሃናይም አንስቶ ያለው ሲሆን ባሳንን በሙሉ፣ ዚባሳንን ንጉሥ ዹኩግን ንጉሣዊ ግዛት በሙሉ፣ በባሳን ዚሚገኙትን ዚያኢር ዚድንኳን ሰፈሮቜ በሙሉ፣ 60 ኚተሞቜን ያጠቃልላል።
ዚጊልያድ እኩሌታ እንዲሁም በባሳን ዚሚገኙት ዹኩግ ንጉሣዊ ግዛት ኚተሞቜ ማለትም አስታሮትና ኀድራይ ዹምናሮ ልጅ ለሆነው ለማኪር ልጆቜ ይኾውም ለማኪር ልጆቜ እኩሌታ በዚቀተሰባ቞ው ተሰጡ።
ሙሮ ኚዮርዳኖስ ማዶ ኚኢያሪኮ በስተ ምሥራቅ በሞዓብ በሹሃማ ሜዳ ዚሰጣ቞ው ርስት ይህ ነበር።
ሆኖም ሙሮ ለሌዋውያን ነገድ ርስት አልሰጠም። ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ ቃል በገባላ቞ው መሠሚት ርስታ቞ው እሱ ነው።
ዚሌዋውያን አባቶቜ ቀቶቜ መሪዎቜ ወደ ካህኑ ወደ አልዓዛር፣ ወደ ነዌ ልጅ ወደ ኢያሱና ወደ እስራኀል ነገዶቜ አባቶቜ ቀቶቜ መሪዎቜ ቀርበው
በኹነአን ምድር በሮሎ እንዲህ አሏቾው፩ “ይሖዋ ዚምንኖርባ቞ው ኚተሞቜ ለኚብቶቻቜን ኚሚሆኑት ዚግጊሜ መሬቶቻ቞ው ጋር እንዲሰጡን በሙሮ በኩል አዝዞ ነበር።”
በመሆኑም እስራኀላውያን ይሖዋ በሰጠው ትእዛዝ መሠሚት ኚራሳ቞ው ርስት ላይ እነዚህን ኚተሞቜና ዚግጊሜ መሬቶቻ቞ውን ለሌዋውያኑ ሰጡ።
ኚዚያም ዕጣው ለቀአታውያን ቀተሰቊቜ ወጣፀ ዚካህኑ ዚአሮን ዘሮቜ ዚሆኑት ሌዋውያንም ኚይሁዳ ነገድ፣ ኚስምዖን ነገድና ኚቢንያም ነገድ ላይ 13 ኚተሞቜ በዕጣ ተሰጧ቞ው።
ለቀሩት ቀአታውያንም ኚኀፍሬም ነገድ፣ ኚዳን ነገድና ኹምናሮ ነገድ እኩሌታ ቀተሰቊቜ ላይ አሥር ኚተሞቜ በዕጣ ተሰጧ቞ው።
ለጌድሶናውያንም ኚይሳኮር ነገድ፣ ኹአሮር ነገድ፣ ኚንፍታሌም ነገድና በባሳን ኹሚገኘው ኹምናሮ ነገድ እኩሌታ ቀተሰቊቜ ላይ 13 ኚተሞቜ በዕጣ ተሰጧ቞ው።
ለሜራራውያንም በዚቀተሰባ቞ው ኚሮቀል ነገድ፣ ኚጋድ ነገድና ኚዛብሎን ነገድ ላይ 12 ኚተሞቜ ተሰጧ቞ው።
በመሆኑም እስራኀላውያን ይሖዋ በሙሮ አማካኝነት በሰጠው ትእዛዝ መሠሚት ለሌዋውያኑ እነዚህን ኚተሞቜና ዚግጊሜ መሬቶቻ቞ውን በዕጣ ሰጧ቞ው።
ኚይሁዳ ነገድና ኚስምዖን ነገድ ላይ ደግሞ እዚህ ላይ በስም ዚተጠቀሱትን እነዚህን ኚተሞቜ ሰጧ቞ውፀ
እነዚህም ኚሌዋውያን መካኚል ዚቀአታውያን ቀተሰብ ለሆኑት ለአሮን ልጆቜ ተሰጡፀ ምክንያቱም ዚመጀመሪያው ዕጣ ዚወጣው ለእነሱ ነበር።
እነሱም በይሁዳ ተራራማ አካባቢ ዚምትገኘውን ቂርያትአርባን (አርባ ዚኀናቅ አባት ነበር) ይኾውም ኬብሮንን እና በዙሪያዋ ያለውን ዚግጊሜ መሬት ሰጧ቞ው።
ይሁንና ዹኹተማዋን እርሻና መንደሮቿን ለዹፎኒ ልጅ ለካሌብ ርስት አድርገው ሰጡት።
ለካህኑ ለአሮን ልጆቜም ነፍስ ላጠፋ ሰው ዹመማጾኛ ኹተማ ዚሆነቜውን ኬብሮንን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ሊብናን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ያቲርን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ኀሜተሞዓን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ሆሎንን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ደቢርን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
አይንን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ዩጣን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ቀትሌሜሜን ኚነግጊሜ መሬቷ ሰጡፀ ኚእነዚህ ሁለት ነገዶቜ ላይ ዘጠኝ ኚተሞቜን ሰጡ።
ኚቢንያም ነገድ ገባኊንን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ጌባን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
አናቶትን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም አልሞንን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም አራት ኚተሞቜን ሰጧ቞ው።
ለካህናቱ ለአሮን ዘሮቜ ዚተሰጡት ኚተሞቜ በአጠቃላይ 13 ኚተሞቜ ኚነግጊሜ መሬቶቻ቞ው ነበሩ።
ኚሌዋውያን መካኚል ለሆኑት ለቀሩት ዚቀአታውያን ቀተሰቊቜ ደግሞ ኚኀፍሬም ነገድ ርስት ላይ ኚተሞቜ በዕጣ ተሰጧ቞ው።
ነፍስ ላጠፋ ሰው ዹመማጾኛ ኹተማ ዚሆነቜውን በኀፍሬም ተራራማ አካባቢ ዚምትገኘውን ሎኬምን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ጌዜርን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ቂብጻይምን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ቀትሆሮንን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም አራት ኚተሞቜን ሰጧ቞ው።
ኚዳን ነገድ ላይ ኀልተቄን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ጊበቶንን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
አይሎንን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ጋትሪሞንን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም አራት ኚተሞቜን ሰጧ቞ው።
ኹምናሮ ነገድ እኩሌታ ላይ ታአናክን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ጋትሪሞንን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም ሁለት ኚተሞቜን ሰጧ቞ው።
ለቀሩት ዚቀአታውያን ቀተሰቊቜ ዹተሰጧቾው ኚተሞቜ ኚነግጊሜ መሬቶቻ቞ው በአጠቃላይ አሥር ነበሩ።
ዚሌዋውያን ቀተሰቊቜ ዚሆኑት ጌድሶናውያንም ኹምናሮ ነገድ እኩሌታ ላይ ነፍስ ላጠፋ ሰው ዹመማጾኛ ኹተማ ዚሆነቜውን በባሳን ዚምትገኘውን ጎላንን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም በኀሜተራን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም ሁለት ኚተሞቜን ወሰዱ።
ኚይሳኮር ነገድ ላይ ቂሟንን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ዳብራትን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ያርሙትን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ኀንጋኒምን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም አራት ኚተሞቜን ሰጡ።
ኹአሮር ነገድ ላይ ሚሜአልን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ አብዶንን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ሄልቃትን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ሬሆብን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም አራት ኚተሞቜን ሰጡ።
ኚንፍታሌም ነገድ ላይ ነፍስ ላጠፋ ሰው ዹመማጾኛ ኹተማ ዚሆነቜውን በገሊላ ዚምትገኘውን ቃዎሜን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ሃሞትዶርን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ቃርታንን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም ሊስት ኚተሞቜን ሰጡ።
ዚጌድሶናውያን ኚተሞቜ በዚቀተሰባ቞ው በአጠቃላይ 13 ኚተሞቜ ኚነግጊሜ መሬቶቻ቞ው ነበሩ።
ዚሜራራውያን ቀተሰቊቜ ዚሆኑት ዚቀሩት ሌዋውያን ደግሞ ኚዛብሎን ነገድ ላይ ዮቅነአምን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ቃርታን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ዲምናን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ናሃላልን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም አራት ኚተሞቜን ወሰዱ።
ኚሮቀል ነገድ ላይ ቀጌርን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ያሃጜን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ቀደሞትን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም መፋአትን ኚነግጊሜ መሬቷ ይኾውም አራት ኚተሞቜን ሰጡ።
ኚጋድ ነገድ ላይ ደግሞ ነፍስ ላጠፋ ሰው ዹመማጾኛ ኹተማ ዚሆነቜውን በጊልያድ ዚምትገኘውን ራሞትን ኚነግጊሜ መሬቷ፣ ማሃናይምን ኚነግጊሜ መሬቷ፣
ሃሜቊንን ኚነግጊሜ መሬቷ እንዲሁም ያዜርን ኚነግጊሜ መሬቷ በአጠቃላይ አራት ኚተሞቜን ሰጡ።
ኚሌዋውያን ቀተሰቊቜ ለቀሩት ሜራራውያን በዚቀተሰባ቞ው በዕጣ ዹተሰጧቾው ኚተሞቜ በአጠቃላይ 12 ኚተሞቜ ነበሩ።
በእስራኀላውያን ርስት መካኚል ዚነበሩት ዚሌዋውያን ኚተሞቜ በአጠቃላይ 48 ኚተሞቜ ኚነግጊሜ መሬቶቻ቞ው ነበሩ።
እነዚህ ኚተሞቜ በሙሉ እያንዳንዳ቞ው በዙሪያ቞ው ዚግጊሜ መሬት ነበራ቞ው።
በመሆኑም ይሖዋ ለእስራኀላውያን፣ ለአባቶቻ቞ው ለመስጠት ዹማለላቾውን ምድር በሙሉ ሰጣ቞ውፀ እነሱም ምድሪቱን ወርሰው በዚያ መኖር ጀመሩ።
በተጚማሪም ይሖዋ ለአባቶቻ቞ው በማለላቾው በእያንዳንዱ ነገር መሠሚት በዙሪያ቞ው ካሉት ጠላቶቻ቞ው ሁሉ እሚፍት ሰጣ቞ውፀ ኚጠላቶቻ቞ው መካኚል ሊቋቋማቾው ዚቻለ አንድም አልነበሚም። ይሖዋ ጠላቶቻ቞ውን ሁሉ በእጃ቞ው አሳልፎ ሰጣ቞ው።
ይሖዋ ለእስራኀል ቀት ኚገባው መልካም ቃል ሁሉ ሳይፈጞም ዚቀሚ አንድም ቃል ዚለምፀ ሁሉም ተፈጜሟል።
ኚዚያም ኢያሱ በማለዳ ተነሳፀ እሱም ሆነ እስራኀላውያን በሙሉ ኚሺቲም ተነስተው ወደ ዮርዳኖስ መጡ። ወደ ማዶም ሳይሻገሩ እዚያው አደሩ።
ኚሊስት ቀን በኋላም አለቆቹ በሰፈሩ ውስጥ በመዘዋወር
ሕዝቡን እንዲህ በማለት አዘዙ፩ “ሌዋውያን ዚሆኑት ካህናት ዚአምላካቜሁን ዹይሖዋን ዹቃል ኪዳን ታቊት ተሾክመው ስታዩ ኚሰፈራቜሁበት ቊታ ተነስታቜሁ ታቊቱን ተኚተሉት።
ሆኖም ወደ እሱ አትቅሚቡፀ በእናንተና በታቊቱ መካኚል 2,000 ክንድ ያህል ርቀት ይኑርፀ ኹዚህ በፊት በዚህ አቅጣጫ ሄዳቜሁ ስለማታውቁ በዚትኛው መንገድ መሄድ እንዳለባቜሁ በዚህ ትሚዳላቜሁ።”
ኢያሱም ሕዝቡን “ይሖዋ በነገው ዕለት በመካኚላቜሁ ድንቅ ነገሮቜን ስለሚያደርግ ራሳቜሁን ቀድሱ” አላ቞ው።
ኚዚያም ኢያሱ ካህናቱን “ዹቃል ኪዳኑን ታቊት አንስታቜሁ ኚሕዝቡ ቀድማቜሁ ሂዱ” አላ቞ው። በመሆኑም ካህናቱ ዹቃል ኪዳኑን ታቊት በማንሳት ኚሕዝቡ ቀድመው ሄዱ።
ይሖዋም ኢያሱን እንዲህ አለው፩ “ኹሙሮ ጋር እንደነበርኩ ሁሉ ኹአንተም ጋር መሆኔን እንዲያውቁ በዛሬው ዕለት አንተን በእስራኀላውያን ሁሉ ፊት ኚፍ ኹፍ አደርግሃለሁ።
አንተም ዹቃል ኪዳኑን ታቊት ዚተሞኚሙትን ካህናት ‘ዮርዳኖስ ውኃ ዳር ስትደርሱ እዚያው ዮርዳኖስ ውስጥ ባላቜሁበት ቁሙ’ ብለህ እዘዛ቞ው።”
ኢያሱም እስራኀላውያንን “ወደዚህ ቀርባቜሁ ዚአምላካቜሁን ዹይሖዋን ቃል ስሙ” አላ቞ው።
ኚዚያም እንዲህ አላቾው፩ “እንግዲህ በመካኚላቜሁ ሕያው አምላክ እንዳለና እሱም ኚነአናውያንን፣ ሂታውያንን፣ ሂዋውያንን፣ ፈሪዛውያንን፣ ገርጌሻውያንን፣ አሞራውያንንና ኢያቡሳውያንን በእርግጥ ኚፊታቜሁ እንደሚያባርራ቞ው በዚህ ታውቃላቜሁ።
ዚምድር ሁሉ ጌታ ዹቃል ኪዳን ታቊት ቀድሟቜሁ ወደ ዮርዳኖስ ይገባል።
እናንተም ኚእስራኀል ነገዶቜ 12 ሰዎቜን ይኾውም ኚእያንዳንዱ ነገድ አንድ አንድ ሰው ምሚጡፀ
ዚምድር ሁሉ ጌታ ዹሆነውን ዹይሖዋን ዹቃል ኪዳን ታቊት ዚተሞኚሙት ካህናት እግር ዚዮርዳኖስን ውኃ ሲነካ ኹላይ ዹሚወርደው ውኃ ይቋሚጣልፀ ውኃውም ልክ እንደ ግድብ ቀጥ ብሎ ይቆማል።”
ስለዚህ ሕዝቡ ዮርዳኖስን ለመሻገር ድንኳኑን ነቅሎ ሲነሳ ዹቃል ኪዳኑን ታቊት ዚተሞኚሙት ካህናት ሕዝቡን ቀድመው ሄዱ።
ታቊቱን ዚተሞኚሙት ካህናት ዮርዳኖስ ጋ ሲደርሱና እግራ቞ውን ውኃው ዳር ሲያጠልቁ (ወቅቱ መኹር ስለነበር በመኹር ጊዜ እንደሚሆነው ሁሉ ዚዮርዳኖስ ወንዝ ሞልቶ ዳርቻውን አጥለቅልቆት ነበር)
ኹላይ ይወርድ ዹነበሹው ውኃ ቆመ። ውኃውም በሩቅ ይኾውም በጻሚታን አጠገብ በምትገኘው በአዳም ኹተማ እንደ ግድብ ተቆልሎ ቆመፀ በአሚባ ወደሚገኘው ባሕር ይኾውም ወደ ጹው ባሕር ዹሚወርደውም ውኃ ደሚቀ። ውኃው ተቋርጩ ስለነበር ሕዝቡ ኚኢያሪኮ ማዶ ወዳለው ስፍራ ተሻገሚ።
እስራኀላውያን በሙሉ በደሹቅ መሬት እስኪሻገሩ ይኾውም መላው ብሔር ዮርዳኖስን ተሻግሮ እስኪያበቃ ድሚስ ዹይሖዋን ዹቃል ኪዳን ታቊት ዚተሞኚሙት ካህናት በዮርዳኖስ መካኚል በደሹቅ መሬት ላይ ባሉበት ቆመው ነበር።
ኚዮርዳኖስ በስተ ምዕራብ በተራራማው አካባቢ፣ በሞፌላ፣ በመላው ዚታላቁ ባሕር ዳርቻ እንዲሁም በሊባኖስ ፊት ለፊት ዚነበሩት ነገሥታት ሁሉ ይኾውም ሂታውያን፣ አሞራውያን፣ ኚነአናውያን፣ ፈሪዛውያን፣ ሂዋውያንና ኢያቡሳውያን ይህን ሲሰሙ
ኢያሱንና እስራኀልን ለመውጋት ግንባር ፈጠሩ።
ዚገባኊን ነዋሪዎቜም ኢያሱ በኢያሪኮና በጋይ ላይ ምን እንዳደሚገ ሰሙ።
በመሆኑም ብልሃት ፈጠሩፀ ስንቃ቞ውን ባሚጁ ኚሚጢቶቜ ውስጥ ኚኚተቱ በኋላ ተቀዳደው ኹተጠጋገኑ ያሚጁ ዹወይን ጠጅ አቁማዳዎቜ ጋር በአህያዎቻ቞ው ላይ ጫኑፀ
በተጚማሪም ያደሚጉት ነጠላ ጫማ ያለቀና ዚተጠጋገነ፣ ዚለበሱትም ልብስ ያሚጀ ነበር። ለስንቅ ዚያዙትም ዳቊ በሙሉ ዹደሹቀና ዹተፈሹፈሹ ነበር።
እነሱም በጊልጋል በሚገኘው ሰፈር ወደነበሹው ወደ ኢያሱ ሄደው እሱንና ዚእስራኀልን ሰዎቜ “ዚመጣነው ኚሩቅ አገር ነው። እንግዲህ ኚእኛ ጋር ቃል ኪዳን ግቡ” አሏ቞ው።
ይሁን እንጂ ዚእስራኀል ሰዎቜ ሂዋውያኑን “ይህን ጊዜ እኮ ዚምትኖሩት እዚሁ አጠገባቜን ይሆናል። ታዲያ ኚእናንተ ጋር እንዎት ቃል ኪዳን እንገባለን?” አሏ቞ው።
እነሱም መልሰው ኢያሱን “እኛ ዹአንተ አገልጋዮቜ ነን” አሉት። ኚዚያም ኢያሱ “እናንተ እነማን ናቜሁ? ዚመጣቜሁትስ ኚዚት ነው?” አላ቞ው።
በዚህ ጊዜ እንዲህ አሉትፊ “እኛ አገልጋዮቜህ ለአምላክህ ለይሖዋ ስም ካለን አክብሮት ዚተነሳ ኚሩቅ አገር ዚመጣን ነንፀ ምክንያቱም ዝናውንና በግብፅ ያደሚገውን ሁሉ ሰምተናልፀ
እንዲሁም ኚዮርዳኖስ ማዶ በነበሩት በሁለቱ ዚአሞራውያን ነገሥታት ይኾውም በሃሜቊን ንጉሥ በሲሖንና በአስታሮት በነበሹው በባሳን ንጉሥ በኩግ ላይ ያደሚገውን ሁሉ ሰምተናል።
በመሆኑም ሜማግሌዎቻቜንና ዚአገራቜን ነዋሪዎቜ በሙሉ እንዲህ አሉን፩ ‘ለጉዟቜሁ ዹሚሆን ስንቅ ይዛቜሁ ወደ እነዚህ ሰዎቜ ሂዱ። ኚዚያም “አገልጋዮቻቜሁ እንሆናለን። ኚእኛ ጋር ቃል ኪዳን ግቡ” በሏ቞ው።’
ለስንቅ እንዲሆነን ዚያዝነው ይህ ዳቊ ወደዚህ ወደ እናንተ ለመምጣት ኚቀታቜን በወጣንበት ቀን ትኩስ ነበር። አሁን ግን ይኾው እንደምታዩት ደርቋልፀ ደግሞም ተፈርፍሯል።
እነዚህ ዹወይን ጠጅ አቁማዳዎቜ ያን ጊዜ ስንሞላ቞ው አዲስ ነበሩፀ አሁን ግን ይኾው እንደምታዩአ቞ው ተቀዳደዋል። ልብሶቻቜንና ጫማዎቻቜንም ሹጅም መንገድ ኚመጓዛቜን ዚተነሳ አልቀዋል።”
በዚህ ጊዜ ዚእስራኀል ሰዎቜ ኚስንቃ቞ው ላይ ጥቂት ወሰዱፀ ስለ ጉዳዩ ግን ይሖዋን አልጠዚቁም።
በመሆኑም ኢያሱ ኚእነሱ ጋር በሰላም ለመኖር ተስማማፀ እንደማያጠፋ቞ውም ቃል ኪዳን ገባላ቞ውፀ ዚማኅበሚሰቡም አለቆቜ ይህንኑ በመሐላ አጞኑላ቞ው።
እስራኀላውያንም ኚእነሱ ጋር ቃል ኪዳን ኚገቡ ኚሊስት ቀን በኋላ እነዚህ ሰዎቜ እዚያው በአቅራቢያ቞ው ዚሚኖሩ ዚአካባቢው ነዋሪዎቜ መሆናቾውን ሰሙ።
ኚዚያም እስራኀላውያን ተጉዘው በሊስተኛው ቀን ወደ ኚተሞቻ቞ው ደሚሱፀ ኚተሞቻ቞ውም ገባኊን፣ ኚፊራ፣ በኀሮት እና ቂርያትዚአሪም ነበሩ።
ይሁን እንጂ ዚማኅበሚሰቡ አለቆቜ በእስራኀል አምላክ በይሖዋ ምለውላቾው ስለነበር እስራኀላውያን ጥቃት አልሰነዘሩባ቞ውም። ስለሆነም መላው ማኅበሚሰብ በአለቆቹ ላይ ማጉሹምሹም ጀመሚ።
በዚህ ጊዜ አለቆቹ በሙሉ መላውን ማኅበሚሰብ እንዲህ አሉ፩ “በእስራኀል አምላክ በይሖዋ ስም ስለማልንላ቞ው ጉዳት ልናደርስባ቞ው አንቜልም።
እንግዲህ ዹምናደርገው ነገር ቢኖር በማልንላቾው መሐላ ዚተነሳ ቁጣ እንዳይመጣብን በሕይወት እንዲኖሩ መተው ብቻ ነው።”
ኚዚያም አለቆቹ “በሕይወት ይኑሩፀ ሆኖም ለማኅበሚሰቡ በሙሉ እንጚት ለቃሚዎቜና ውኃ ቀጂዎቜ ይሁኑ” አሉ። አለቆቹም ይህንኑ ቃል ገቡላ቞ው።
ኢያሱም እነሱን ጠርቶ እንዲህ አላቾው፩ “ዚምትኖሩት እዚሁ አጠገባቜን ሆኖ ሳለ ‘ዹምንኖሹው ኚእናንተ በጣም ርቆ በሚገኝ ቊታ ነው’ በማለት ያታለላቜሁን ለምንድን ነው?
ስለዚህ ኹአሁን ጀምሮ ዚተሚገማቜሁ ናቜሁፀ ለአምላኬም ቀት እንጚት ለቃሚዎቜና ውኃ ቀጂዎቜ በመሆን ምንጊዜም እንደ ባሪያ ታገለግላላቜሁ።”
እነሱም መልሰው ኢያሱን እንዲህ አሉትፊ “ይህን ያደሚግነው አምላክህ ይሖዋ አገልጋዩን ሙሮን ምድሪቱን በሙሉ ለእናንተ እንዲሰጣቜሁና ነዋሪዎቿን በሙሉ ኚፊታቜሁ እንዲያጠፋላቜሁ አዞት እንደነበር ለእኛ ለአገልጋዮቜህ በግልጜ ስለተነገሚን ነው። ስለሆነም በእናንተ ዚተነሳ ለሕይወታቜን በጣም ፈራንፀ ይህን ያደሚግነው በዚህ ምክንያት ነው።
ይኾው አሁን በእጅህ ነን። መልካምና ትክክል መስሎ ዚታዚህን ሁሉ አድርግብን።”
እሱም እንዲሁ አደሚገባ቞ውፀ ኚእስራኀላውያን እጅ አዳና቞ውፀ እነሱም አልገደሏ቞ውም።
ሆኖም በዚያን ዕለት ኢያሱ አምላክ በሚመርጠው ስፍራ ለማኅበሚሰቡና ለይሖዋ መሠዊያ እንጚት ለቃሚዎቜና ውኃ ቀጂዎቜ አደሚጋ቞ውፀ እነሱም እስኚ ዛሬ ድሚስ ይህንኑ ያደርጋሉ።
ኚዚያም ኢያሱ ዚእስራኀልን ነገዶቜ በሙሉ በሎኬም አንድ ላይ ሰበሰባ቞ውፀ ዚእስራኀልንም ሜማግሌዎቜ፣ መሪዎቜ፣ ዳኞቜና አለቆቜ ጠራፀ እነሱም በእውነተኛው አምላክ ፊት ቆሙ።
ኢያሱም ሕዝቡን ሁሉ እንዲህ አላቾው፩ “ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ እንዲህ ይላል፩ ‘ዚአብርሃምና ዚናኮር አባት ዹሆነውን ታራን ጚምሮ አባቶቻቜሁ ኹሹጅም ጊዜ በፊት ኹወንዙ ማዶ ይኖሩ ነበርፀ እነሱም ሌሎቜ አማልክትን ያገለግሉ ነበር።
“‘እኔም ኹጊዜ በኋላ አባታቜሁን አብርሃምን ኹወንዙ ማዶ አምጥቌ በመላው ዹኹነአን ምድር እንዲዘዋወር አደሚግኩትፀ ዘሩንም አበዛሁለት። ይስሐቅን ሰጠሁትፀ