text
stringlengths
4
267
ኚዚያም ለይስሐቅ ያዕቆብንና ኀሳውን ሰጠሁት። በኋላም ለኀሳው ሮይር ተራራን ርስት አድርጌ ሰጠሁትፀ ያዕቆብና ልጆቹ ደግሞ ወደ ግብፅ ወሚዱ።
በኋላም ሙሮንና አሮንን ላክኋ቞ውፀ ግብፅንም በመካኚላ቞ው በፈጞምኩት ነገር በመቅሰፍት መታኋትፀ ኚዚያም እናንተን አወጣኋቜሁ።
አባቶቻቜሁን ኚግብፅ ባወጣኋ቞ውና ወደ ባሕሩ በደሚሳቜሁ ጊዜ ግብፃውያኑ ዹጩር ሠሚገሎቜንና ፈሚሰኞቜን አሰልፈው አባቶቻቜሁን እዚተኚታተሉ እስኚ ቀይ ባሕር ድሚስ መጡ።
እነሱም ወደ ይሖዋ መጮኜ ጀመሩፀ በመሆኑም በእናንተና በግብፃውያን መካኚል ጹለማ እንዲኖር አደሚገፀ ባሕሩንም በላያ቞ው ላይ በመመለስ አሰመጣ቞ውፀ በግብፅ ያደሚግኩትንም ዹገዛ ዓይኖቻቜሁ አይተዋል። ኚዚያም በምድሚ በዳ ለብዙ ዓመታት ኖራቜሁ።
“‘ኚዮርዳኖስ ማዶ ይኖሩ ወደነበሩት ወደ አሞራውያንም ምድር አመጣኋቜሁፀ እነሱም ተዋጓቜሁ። ሆኖም ምድራ቞ውን እንድትወርሱ እነሱን በእጃቜሁ አሳልፌ ሰጠኋቜሁፀ ኚፊታቜሁም አጠፋኋ቞ው።
ኚዚያም ዚሞዓብ ንጉሥ ዹሆነው ዹሮፎር ልጅ ባላቅ ተነስቶ ኚእስራኀል ጋር ተዋጋ። ዚቢዖርን ልጅ በለዓምንም እናንተን እንዲሚግም አስጠራው።
እኔ ግን በለዓምን ልሰማው አልፈለግኩም። በመሆኑም ደጋግሞ ባሚካቜሁፀ እኔም ኚእጁ አዳንኳቜሁ።
“‘ኚዚያም ዮርዳኖስን ተሻግራቜሁ ወደ ኢያሪኮ መጣቜሁ። ዚኢያሪኮ መሪዎቜ ዚሆኑት አሞራውያን፣ ፈሪዛውያን፣ ኚነአናውያን፣ ሂታውያን፣ ገርጌሻውያን፣ ሂዋውያንና ኢያቡሳውያን ተዋጓቜሁፀ እኔ ግን እነሱን በእጃቜሁ አሳልፌ ሰጠኋቜሁ።
ኚእናንተ አስቀድሜ ጭንቀት ላክሁፀ ሁለቱንም ዚአሞራውያን ነገሥታት ኚፊታቜሁ አባሚራ቞ው። ይህም ዹሆነው በሰይፋቜሁ ወይም በቀስታቜሁ አይደለም።
ስለዚህ ያልደኚማቜሁበትን ምድር፣ ያልገነባቜኋ቞ውንም ኚተሞቜ ሰጠኋቜሁፀ እናንተም በዚያ መኖር ጀመራቜሁ። ካልተኚላቜሁት ዹወይን ተክልና ዚወይራ ዛፍ እዚበላቜሁ ነው።’
“ስለዚህ ይሖዋን ፍሩፀ በንጹሕ አቋምና በታማኝነትም አገልግሉትፀ አባቶቻቜሁ ኹወንዙ ማዶና በግብፅ ምድር ያገለገሏ቞ውን አማልክት አስወግዱፀ ይሖዋን አገልግሉ።
ይሖዋን ማገልገል መጥፎ መስሎ ኚታያቜሁ ደግሞ ዚምታገለግሉትን ዛሬውኑ ምሚጡፀ ኹወንዙ ማዶ ዚነበሩት አባቶቻቜሁ ያገለገሏ቞ውን አማልክትም ይሁን አሁን በምትኖሩበት ምድር ያሉት አሞራውያን ዚሚያገለግሏ቞ውን አማልክት መምሚጥ ትቜላላቜሁ። እኔና ቀተሰቀ ግን ይሖዋን እናገለግላለን።”
በዚህ ጊዜ ሕዝቡ እንዲህ ሲል መለሰ፩ “በእኛ በኩል ይሖዋን መተውና ሌሎቜ አማልክትን ማገልገል ፈጜሞ ዚማይታሰብ ነው።
እኛንም ሆነ አባቶቻቜንን ኚግብፅ ምድር ኚባርነት ቀት ያወጣን፣ እነዚህን ታላላቅ ምልክቶቜ በፊታቜን ዹፈጾመው እንዲሁም በሄድንበት መንገድ ሁሉና አቋርጠን ባለፍና቞ው ሕዝቊቜ ሁሉ መካኚል ዹጠበቀን አምላካቜን ይሖዋ ነው።
ይሖዋ አሞራውያንን ጚምሮ ኚእኛ በፊት በምድሪቱ ላይ ይኖሩ ዚነበሩትን ሕዝቊቜ በሙሉ አባሚሚ። ስለዚህ እኛም ይሖዋን እናገለግላለንፀ ምክንያቱም እሱ አምላካቜን ነው።”
ኚዚያም ኢያሱ ሕዝቡን እንዲህ አላቾው፩ “እናንተ አምላክን ማገልገል አትቜሉምፀ ምክንያቱም እሱ ቅዱስ አምላክ ነውፀ እንዲሁም እሱ ብቻ እንዲመለክ ዹሚፈልግ አምላክ ነው። መተላለፋቜሁንና ኃጢአታቜሁን ይቅር አይልም።
ይሖዋን ትታቜሁ ባዕዳን አማልክትን ብታገለግሉ እሱም መልካም ነገር ካደሚገላቜሁ በኋላ በእናንተ ላይ ይዞርባቜኋልፀ ደግሞም ያጠፋቜኋል።”
ሕዝቡ ግን ኢያሱን “በፍጹም፣ እኛ ይሖዋን እናገለግላለን!” አሉት።
ስለዚህ ኢያሱ ሕዝቡን “በራሳቜሁ ፍላጎት ይሖዋን ለማገልገል ስለመሚጣቜሁ እናንተ በራሳቜሁ ላይ ምሥክሮቜ ናቜሁ” አላ቞ው። እነሱም “አዎ፣ ምሥክሮቜ ነን” አሉ።
“እንግዲህ አሁን በመካኚላቜሁ ያሉትን ባዕዳን አማልክት አስወግዱፀ ልባቜሁንም ወደ እስራኀል አምላክ ወደ ይሖዋ አዘንብሉ።”
ሕዝቡም ኢያሱን “አምላካቜንን ይሖዋን እናገለግላለንፀ ቃሉንም እንሰማለን!” አለው።
በመሆኑም ኢያሱ በዚያ ቀን ኚሕዝቡ ጋር ቃል ኪዳን ገባፀ ለእነሱም በሎኬም ሥርዓትና ደንብ ደነገገላ቞ው።
ኚዚያም ኢያሱ እነዚህን ቃላት በአምላክ ዹሕግ መጜሐፍ ላይ ጻፋ቞ውፀ ትልቅ ድንጋይም ወስዶ በይሖዋ መቅደስ አጠገብ በሚገኘው ትልቅ ዛፍ ሥር አቆመው።
ኢያሱ ሕዝቡን ሁሉ እንዲህ አላቾው፩ “እንግዲህ ይህ ድንጋይ ይሖዋ ዹነገሹንን ሁሉ ስለሰማ በእኛ ላይ እንደ ምሥክር ሆኖ ያገለግላልፀ እንዲሁም አምላካቜሁን እንዳትክዱ በእናንተ ላይ እንደ ምሥክር ሆኖ ያገለግላል።”
ኚዚያም ኢያሱ ሕዝቡን ሁሉ፣ እያንዳንዱን ወደዚርስቱ አሰናበተ።
ይህ ሁሉ ኹሆነ በኋላ፣ ዹይሖዋ አገልጋይ ዹሆነው ዹነዌ ልጅ ኢያሱ በ110 ዓመቱ ሞተ።
እነሱም ኚጋአሜ ተራራ በስተ ሰሜን በኀፍሬም ተራራማ አካባቢ በሚገኘው ርስቱ ውስጥ በቲምናትሰራ ቀበሩት።
እስራኀላውያን ኢያሱ በሕይወት በነበሚበት ዘመን ሁሉ እንዲሁም ኚኢያሱ በኋላ በሕይወት በኖሩትና ይሖዋ ለእስራኀላውያን ሲል ያደሚገውን ነገር በሙሉ በሚያውቁት ሜማግሌዎቜ ሁሉ ዘመን ይሖዋን ማገልገላቾውን ቀጠሉ።
እስራኀላውያን ኚግብፅ ይዘውት ዚወጡት ዚዮሎፍ አፅም ያዕቆብ ኚሎኬም አባት ኚኀሞር ልጆቜ ላይ በ100 ጥሬ ገንዘብ በገዛው በሎኬም በሚገኘው እርሻ ውስጥ ተቀብሮ ነበርፀ ይህም ዚዮሎፍ ልጆቜ ርስት ሆነ።
ዚአሮን ልጅ አልዓዛርም ሞተ። እነሱም በኀፍሬም ተራራማ አካባቢ ለልጁ ለፊንሃስ ተሰጥቶት በነበሹው ኮሚብታ ቀበሩት።
ኚዚያም ዹነዌ ልጅ ኢያሱ ኚሺቲም ሁለት ሰላዮቜን በድብቅ ላኚ። እነሱንም “እስቲ ሄዳቜሁ ምድሪቱን በተለይም ኢያሪኮን አይታቜሁ ኑ” አላ቞ው። ሰዎቹም ሄደው ሚዓብ ወደተባለቜ አንዲት ዝሙት አዳሪ ቀት ገቡፀ በዚያም አሚፉ።
ዚኢያሪኮም ንጉሥ “እስራኀላውያን ዚሆኑ ሰዎቜ ምድሪቱን ለመሰለል ዛሬ ማታ ወደዚህ መጥተዋል” ተብሎ ተነገሚው።
በዚህ ጊዜ ዚኢያሪኮ ንጉሥ ወደ ሚዓብ እንዲህ ዹሚል መልእክት ላኚባትፊ “ቀትሜ መጥተው ያሚፉትን ሰዎቜ አውጪፀ ምክንያቱም ወደዚህ ዚመጡት ምድሪቱን በሙሉ ለመሰለል ነው።”
ሎትዚዋ ግን ሁለቱን ሰዎቜ ደበቀቻ቞ው። ኚዚያም እንዲህ አለቜፊ “በእርግጥ ሰዎቹ ወደ እኔ መጥተው ነበርፀ ሆኖም ኚዚት እንደመጡ አላወቅኩም።
ምሜት ላይ ዹኹተማዋ በር ሊዘጋ ሲል ወጥተው ሄደዋል። ወዎት እንደሄዱ አላውቅምፀ ሆኖም ፈጥናቜሁ ኚተኚታተላቜኋ቞ው ልትደርሱባ቞ው ትቜላላቜሁ።”
(ይሁንና ሰዎቹን ጣሪያ ላይ ይዛቾው ወጥታ በተሹበሹበ ዚተልባ እግር ውስጥ ደብቃ቞ው ነበር።)
ሰዎቹም ሰላዮቹን በመኚታተል ወደ ዮርዳኖስ አቅጣጫ በመልካው በኩል ሄዱፀ አሳዳጆቹ ወጥተው እንደሄዱም ዹኹተማዋ በር ተዘጋ።
እሷም ሰላዮቹ ኚመተኛታ቞ው በፊት እነሱ ወዳሉበት ወደ ጣሪያው ወጣቜ።
እንዲህም አለቻ቞ውፊ “ይሖዋ ምድሪቱን እንደሚሰጣቜሁ አውቃለሁፀ እኛም እናንተን በመፍራት ተሞብሚናል። ዚምድሪቱ ነዋሪዎቜ በሙሉ በእናንተ ዚተነሳ ልባ቞ው ኚድቷ቞ዋልፀ
ምክንያቱም ኚግብፅ በወጣቜሁ ጊዜ ይሖዋ ቀይ ባሕርን በፊታቜሁ እንዎት እንዳደሚቀው እንዲሁም ኚዮርዳኖስ ማዶ በደመሰሳቜኋ቞ው በሁለቱ ዚአሞራውያን ነገሥታት፣ በሲሖንና በኩግ ላይ ምን እንዳደሚጋቜሁ ሰምተናል።
ይህን ስንሰማ ልባቜን ቀለጠፀ በእናንተም ዚተነሳ ወኔ ያልኚዳው ማንም አልነበሚምፀ ምክንያቱም አምላካቜሁ ይሖዋ በላይ በሰማይ በታቜም በምድር አምላክ ነው።
እንግዲህ እኔ ታማኝ ፍቅር እንዳሳዚኋቜሁ ሁሉ እናንተም ለአባ቎ ቀት ታማኝ ፍቅር እንደምታሳዩ እባካቜሁ በይሖዋ ማሉልኝፀ እንዲሁም አስተማማኝ ምልክት ስጡኝ።
አባ቎ን፣ እና቎ን፣ ወንድሞቌን፣ እህቶቌንና ዚእነሱ ዹሆነውን ሁሉ አትርፉልኝፀ ኚሞትም ታደጉን።”
በዚህ ጊዜ ሰዎቹ እንዲህ አሏትፊ “በእናንተ ምትክ ሕይወታቜንን እንሰጣለን! ስለ ተልእኳቜን ካልተናገራቜሁ ይሖዋ ምድሪቱን በሚሰጠን ጊዜ ታማኝ ፍቅርና ታማኝነት እናሳያቜኋለን።”
እሷም ሰዎቹን በመስኮት በኩል በገመድ አወሚደቻ቞ውፀ ምክንያቱም ቀቷ ኹኹተማው ቅጥር ጋር ተያይዞ ዚተሠራ ነበር። እንዲያውም ዚምትኖሚው ቅጥሩ ላይ ነበር።
ኚዚያም እንዲህ አለቻ቞ውፊ “ዚሚያሳድዷቜሁ ሰዎቜ እንዳያገኟቜሁ ወደ ተራራማው አካባቢ ሄዳቜሁ ለሊስት ቀን ተደበቁ። ኚዚያም ዚሚያሳድዷቜሁ ሰዎቜ ኚተመለሱ በኋላ ወደምትፈልጉት ቊታ መሄድ ትቜላላቜሁ።”
ሰዎቹም እንዲህ አሏትፊ “እንደሚኚተለው ካላደሚግሜ ባስማልሜን በዚህ መሐላ ተጠያቂ አንሆንም፩
ወደ ምድሪቱ በምንገባበት ጊዜ ይህን ቀይ ገመድ እኛን ባወሚድሜበት መስኮት በኩል አንጠልጥይው። እንዲሁም አባትሜ፣ እናትሜ፣ ወንድሞቜሜና ዚአባትሜ ቀት በሙሉ ቀትሜ ውስጥ እንዲሰበሰቡ ማድሚግ አለብሜ።
ኚቀትሜ ወጥቶ ደጅ ዹሚገኝ ማንኛውም ሰው ደሙ በራሱ ላይ ይሆናልፀ እኛም ኹበደል ነፃ እንሆናለን። ሆኖም ኚአንቺ ጋር ቀት ውስጥ ያለ ማንኛውም ሰው ጉዳት ቢደርስበት ደሙ በእኛ ላይ ይሆናል።
ስለ ተልእኳቜን ኚተናገርሜ ግን ባስማልሜን በዚህ መሐላ ተጠያቂ አንሆንም።”
እሷም “እንዳላቜሁት ይሁን” አለቻ቞ው። ኚዚያም አሰናበተቻ቞ውፀ እነሱም ሄዱ። እሷም ቀዩን ገመድ መስኮቱ ላይ አሰሚቜው።
እነሱም ወደ ተራራማው አካባቢ ሄደው አሳዳጆቹ እስኪመለሱ ድሚስ በዚያ ለሊስት ቀን ተቀመጡ። አሳዳጆቹም በዚመንገዱ ሁሉ ፈለጓ቞ውፀ ሆኖም አላገኟ቞ውም።
ኚዚያም ሁለቱ ሰዎቜ ኚተራራማው አካባቢ ወርደው ወንዙን በመሻገር ወደ ነዌ ልጅ ወደ ኢያሱ መጡ። ያጋጠማ቞ውንም ሁሉ ነገሩት።
ኢያሱንም እንዲህ አሉትፊ “ይሖዋ ምድሪቱን በሙሉ በእጃቜን ሰጥቶናል። እንዲያውም ዚምድሪቱ ነዋሪዎቜ ሁሉ በእኛ ዚተነሳ ልባ቞ው ኚድቷ቞ዋል።”
ዚኢዚሩሳሌም ንጉሥ አዶኒጌዎቅ፣ ኢያሱ ጋይን እንደተቆጣጠራትና እንደደመሰሳት፣ በኢያሪኮና በንጉሥዋ ላይ እንዳደሚገው ሁሉ በጋይና በንጉሥዋም ላይ እንዳደሚገ እንዲሁም ዚገባኊን ነዋሪዎቜ ኚእስራኀላውያን ጋር ሰላማዊ ግንኙነት ፈጥሚው በመካኚላ቞ው እዚኖሩ እንዳሉ ሲሰማ
በጣም ደነገጠፀ ምክንያቱም ገባኊን በንጉሥ እንደሚተዳደሩት ኚተሞቜ ሁሉ ታላቅ ኹተማ ነበሚቜ። ይህቜ ኹተማ ኹጋይ ትበልጥ ዹነበሹ ሲሆን ነዋሪዎቿም በሙሉ ጊሚኞቜ ነበሩ።
በመሆኑም ዚኢዚሩሳሌም ንጉሥ አዶኒጌዎቅ ለኬብሮን ንጉሥ ለሆሐም፣ ለያርሙት ንጉሥ ለፒራም፣ ለለኪሶ ንጉሥ ለያፊአ እና ለኀግሎን ንጉሥ ለደቢር እንዲህ ዹሚል መልእክት ላኹ፩
“መጥታቜሁ እርዱኝና በገባኊን ላይ ጥቃት እንሰንዝርፀ ምክንያቱም ገባኊን ኚኢያሱና ኚእስራኀላውያን ጋር ሰላማዊ ግንኙነት ፈጥራለቜ።”
በዚህ ጊዜ አምስቱ ዚአሞራውያን ነገሥታት ይኾውም ዚኢዚሩሳሌም ንጉሥ፣ ዚኬብሮን ንጉሥ፣ ዚያርሙት ንጉሥ፣ ዚለኪሶ ንጉሥና ዚኀግሎን ንጉሥ ኚነሠራዊታ቞ው አንድ ላይ ተሰብስበው በመዝመት ገባኊንን ለመውጋት ኚበቧት።
ዚገባኊን ሰዎቜም በጊልጋል በሚገኘው ሰፈር ወደነበሹው ወደ ኢያሱ እንዲህ ዹሚል መልእክት ላኩበትፊ “እኛን ባሪያዎቜህን አትተወን። ፈጥነህ ድሚስልን! አድነንፀ እርዳን! በተራራማው አካባቢ ዚሚኖሩት ዚአሞራውያን ነገሥታት በሙሉ እኛን ለመውጋት ተሰብስበዋል።”
በመሆኑም ኢያሱ ተዋጊዎቹንና ኃያላን ዚሆኑትን ጊሚኞቜ በሙሉ ይዞ ኹጊልጋል ወጣ።
ኚዚያም ይሖዋ ኢያሱን “በእጅህ አሳልፌ ስለሰጠኋ቞ው አትፍራ቞ው። አንዳ቞ውም እንኳ ሊቋቋሙህ አይቜሉም” አለው።
ኢያሱም ኹጊልጋል በመነሳት ሌሊቱን ሙሉ ሲገሰግስ አድሮ ድንገት መጣባ቞ው።
ይሖዋም በእስራኀላውያን ፊት ግራ እንዲጋቡ አደሚጋ቞ውፀ እነሱም ገባኊን ላይ ክፉኛ ጚፈጚፏ቞ውፀ ወደ ቀትሆሮን አቀበት በሚወስደው መንገድ ላይ በማሳደድ እስኚ አዜቃ እና እስኚ መቄዳ ድሚስ መቷ቞ው።
እነሱም ኚእስራኀላውያን በመሞሜ ዚቀትሆሮንን ቁልቁለት እዚወሚዱ ሳሉ እስኚ አዜቃ ድሚስ ይሖዋ ኹሰማይ ትላልቅ ዚበሚዶ ድንጋይ አወሚደባ቞ውፀ እነሱም ሞቱ። እንዲያውም በእስራኀላውያን ሰይፍ ኚሞቱት ይልቅ በበሚዶ ድንጋይ ዚሞቱት ይበልጣሉ።
ይሖዋ አሞራውያንን ኚእስራኀላውያን ፊት ባባሚሚበት ዕለት ኢያሱ በእስራኀላውያን ፊት ይሖዋን እንዲህ አለው፩ “ፀሐይ ሆይ፣ በገባኊን ላይ ቁሚፀ አንቺም ጹሹቃ ሆይ፣ በአይሎን ሾለቆ ላይ ቀጥ በይ!”
በመሆኑም ብሔሩ ጠላቶቹን እስኪበቀል ድሚስ ፀሐይ ባለቜበት ቆመቜፀ ጹሹቃም አልተንቀሳቀሰቜም። ይህስ በያሻር መጜሐፍ ላይ ተጜፎ ዹሚገኝ አይደለም? ፀሐይ በሰማይ መካኚል ባለቜበት ቆመቜፀ ለአንድ ቀን ያህል ለመጥለቅ አል቞ኮለቜም።
ይሖዋ ዹሰውን ቃል ዚሰማበት እንደዚያ ያለ ቀን ኚዚያ በፊትም ሆነ ኚዚያ በኋላ ፈጜሞ አልነበሚምፀ ምክንያቱም ይሖዋ ለእስራኀል እዚተዋጋ ነበር።
ኚዚያ በኋላ ኢያሱና መላው እስራኀል በጊልጋል ወደሚገኘው ሰፈር ተመለሱ።
በዚህ ጊዜ አምስቱ ነገሥታት ሞሜተው በመቄዳ በሚገኝ ዋሻ ውስጥ ተደብቀው ነበር።
ኚዚያም ኢያሱ “አምስቱ ነገሥታት በመቄዳ በሚገኘው ዋሻ ውስጥ ተደብቀው ተገኝተዋል” ዹሚል መልእክት ደሚሰው።
እሱም እንዲህ አለ፩ “ትላልቅ ድንጋዮቜ አንኚባላቜሁ ዚዋሻውን አፍ ግጠሙትና እነሱን ዚሚጠብቁ ሰዎቜ መድቡ።
ዚተቀራቜሁት ግን ዝም ብላቜሁ አትቁሙ። ጠላቶቻቜሁን እያሳደዳቜሁ ኹኋላ ምቷ቞ው። አምላካቜሁ ይሖዋ በእጃቜሁ አሳልፎ ስለሰጣ቞ው ወደ ኚተሞቻ቞ው እንዲገቡ አትፍቀዱላ቞ው።”
ኢያሱና እስራኀላውያን፣ አምልጠው ወደተመሞጉት ኚተሞቜ ኚገቡት ጥቂት ሰዎቜ በቀር ጠላቶቻ቞ውን እስኪጠፉ ድሚስ ክፉኛ ኹጹፈጹፏቾው በኋላ
ሕዝቡ ሁሉ በመቄዳ በሚገኘው ሰፈር ወደነበሹው ወደ ኢያሱ በሰላም ተመለሰ። በእስራኀላውያን ላይ አንዲት ቃል ሊናገር ዹደፈሹ ሰው አልነበሚም።
ኚዚያም ኢያሱ “ዚዋሻውን አፍ ኚፍታቜሁ አምስቱን ነገሥታት ኚዋሻው አውጥታቜሁ ወደ እኔ አምጧቾው” አለ።
ስለሆነም እነዚህን አምስት ነገሥታት ማለትም ዚኢዚሩሳሌምን ንጉሥ፣ ዚኬብሮንን ንጉሥ፣ ዚያርሙትን ንጉሥ፣ ዚለኪሶን ንጉሥና ዚኀግሎንን ንጉሥ ኚዋሻው አውጥተው ወደ እሱ አመጧ቞ው።
ኢያሱም እነዚህን ነገሥታት ወደ እሱ ባመጧ቞ው ጊዜ ዚእስራኀልን ሰዎቜ በሙሉ ጠርቶ አብሚውት ዚሄዱትን ዚሠራዊቱን አዛዊቜ “ወደዚህ ቅሚቡ። እግራቜሁን በእነዚህ ነገሥታት ማጅራት ላይ አድርጉ” አላ቞ው። እነሱም ቀርበው እግራ቞ውን በማጅራታ቞ው ላይ አደሚጉ።
ኚዚያም ኢያሱ እንዲህ አላቾው፩ “አትፍሩ ወይም አትሞበሩ። ይሖዋ በምትዋጓ቞ው ጠላቶቻቜሁ ሁሉ ላይ እንዲህ ስለሚያደርግ ደፋርና ብርቱ ሁኑ።”
ኚዚያም ኢያሱ መትቶ ገደላ቞ውፀ በአምስት እንጚቶቜም ላይ ሰቀላ቞ውፀ በእንጚቶቹም ላይ እንደተሰቀሉ እስኚ ምሜት ድሚስ ቆዩ።
ፀሐይም ልትጠልቅ ስትቃሚብ ኢያሱ፣ አስኚሬኖቻ቞ው ኚእንጚቶቹ ላይ እንዲወርዱና ተደብቀውበት በነበሹው ዋሻ ውስጥ እንዲጣሉ ትእዛዝ ሰጠ። ኚዚያም በዋሻው አፍ ላይ ትላልቅ ድንጋዮቜን አደሚጉፀ እነዚህም እስኚ ዛሬ ድሚስ እዚያው ይገኛሉ።
ኢያሱም በዚያን ዕለት መቄዳን በመቆጣጠር ሕዝቡን በሰይፍ ፈጀ። ንጉሥዋንና በውስጧ ያለውን ሰው ሁሉ አንድም ሳያስቀር ፈጜሞ አጠፋ። በኢያሪኮ ንጉሥ ላይ እንዳደሚገውም ሁሉ በመቄዳ ንጉሥ ላይ አደሚገ።
ኚዚያም ኢያሱና ኚእሱ ጋር ዚነበሩት እስራኀላውያን በሙሉ ኚመቄዳ ወደ ሊብና በመሄድ ሊብናን ወጓት።
ይሖዋም ኹተማዋንና ንጉሥዋን በእስራኀላውያን እጅ አሳልፎ ሰጣ቞ውፀ እነሱም ኹተማዋንና በውስጧ ያለውን ሰው ሁሉ አንድም ሳያስቀሩ በሰይፍ መቱ። በኢያሪኮ ንጉሥ ላይ እንዳደሚጉትም ሁሉ በንጉሥዋ ላይ አደሚጉ።
በመቀጠልም ኢያሱና ኚእሱ ጋር ዚነበሩት እስራኀላውያን በሙሉ ኚሊብና ወደ ለኪሶ ሄዱፀ እሷንም ኹበው ወጓት።
ይሖዋም ለኪሶን ለእስራኀላውያን አሳልፎ ሰጣትፀ እነሱም በሁለተኛው ቀን ያዟት። በሊብና ላይ እንዳደሚጉትም ሁሉ ኹተማዋንና በውስጧ ያለውን ሰው ሁሉ በሰይፍ መቱ።
በዚህ ጊዜ ዹጌዜር ንጉሥ ሆራም ለኪሶን ለመርዳት ወጣፀ ሆኖም ኢያሱ እሱንና ሕዝቡን አንድም ሳያስቀር መታ቞ው።
በመቀጠልም ኢያሱና ኚእሱ ጋር ዚነበሩት እስራኀላውያን በሙሉ ኚለኪሶ ወደ ኀግሎን በመሄድ ኹበው ወጓት።
እነሱም በዚያን ቀን ኹተማዋን በመቆጣጠር በሰይፍ መቷት። በለኪሶ ላይ እንዳደሚጉት ሁሉ በውስጧ ያለውን ሰው ሁሉ በዚያኑ ዕለት ሙሉ በሙሉ አጠፉ።
ኚዚያም ኢያሱና ኚእሱ ጋር ዚነበሩት እስራኀላውያን በሙሉ ኚኀግሎን ወደ ኬብሮን በመውጣት ኬብሮንን ወጓት።
እሷንም ተቆጣጥሚው ኚተማዋን፣ ንጉሥዋንና በዙሪያዋ ያሉትን አነስተኛ ኚተሞቜ እንዲሁም በውስጧ ያለውን ሰው ሁሉ አንድም ሳያስቀሩ በሰይፍ መቱ። በኀግሎንም ላይ እንዳደሚገው ሁሉ ኹተማዋንና በውስጧ ያለውን ሰው ሁሉ ሙሉ በሙሉ አጠፋ።
በመጚሚሻም ኢያሱና ኚእሱ ጋር ዚነበሩት እስራኀላውያን በሙሉ ወደ ደቢር በመዞር ወጓት።
ኚተማዋን፣ ንጉሥዋንና በዙሪያዋ ያሉትን አነስተኛ ኚተሞቜ ተቆጣጠሚፀ እነሱንም በሰይፍ መቷ቞ውፀ በውስጧ ያለውንም ሰው ሁሉ አንድም ሳያስቀሩ ፈጜመው አጠፉ። በኬብሮን እንዲሁም በሊብና እና በንጉሥዋ ላይ እንዳደሚገው ሁሉ በደቢርና በንጉሥዋ ላይ አደሚገ።
ኢያሱም ምድሩን ሁሉ ይኾውም ተራራማውን አካባቢ፣ ኔጌብን፣ ሞፌላን፣ ሞንተሚሮቹንና ነገሥታታ቞ውን በሙሉ ድል አደሚገፀ አንድም ሰው አላስቀሚምፀ ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ ባዘዘውም መሠሚት እስትንፋስ ያለውን ሁሉ ፈጜሞ አጠፋ።
ኢያሱ ኚቃዎስበርኔ አንስቶ እስኚ ጋዛ ድሚስ እንዲሁም ዹጎሾንን ምድር በሙሉ እስኚ ገባኊን ድሚስ ድል አደሚገ።
ኢያሱ እነዚህን ሁሉ ነገሥታትና ምድራ቞ውን በሙሉ በአንድ ጊዜ ተቆጣጠሚፀ ምክንያቱም ዚእስራኀል አምላክ ይሖዋ ለእስራኀላውያን እዚተዋጋላ቞ው ነበር።
ኚዚያም ኢያሱና እስራኀላውያን በሙሉ በጊልጋል ወደሚገኘው ሰፈር ተመለሱ።
ለዮሎፍ ዘሮቜ በዕጣ ዚተሰጣ቞ው ምድር በኢያሪኮ አጠገብ ካለው ኚዮርዳኖስ አንስቶ ኚኢያሪኮ በስተ ምሥራቅ እስካሉት ውኃዎቜ ድሚስ ሲሆን ኚኢያሪኮ ሜቅብ ዚሚወጣውን ምድሚ በዳ አቋርጩ እስኚ ተራራማው ዚቀ቎ል አካባቢ ድሚስ ይዘልቃል።
እንዲሁም በሎዛ ኚምትገኘው ኚቀ቎ል አንስቶ በአጣሮት እስካለው ዚአርካውያን ወሰን ድሚስ ይሄዳልፀ
ኚዚያም በስተ ምዕራብ ወደ ያፍለጣውያን ወሰን ቁልቁል በመውሚድ እስኚ ታቜኛው ቀትሆሮን ወሰንና እስኚ ጌዜር ይደርሳልፀ ባሕሩም ጋ ሲደርስ ያበቃል።