text
stringlengths
4
267
ስለሆነም ዚዮሎፍ ዘሮቜ ምናሮና ኀፍሬም ርስታ቞ው ዹሆነውን መሬት ወሰዱ።
ዚኀፍሬም ዘሮቜ ወሰን በዚቀተሰባ቞ው ዹሚኹተለው ነው፩ በስተ ምሥራቅ በኩል ዚርስታ቞ው ወሰን አጣሮትዓዳር ሲሆን እስኚ ላይኛው ቀትሆሮንም ይደርሳልፀ
ኚዚያም እስኚ ባሕሩ ድሚስ ይዘልቃል። ወሰኑ በስተ ሰሜን ሚክመታት ሲሆን በስተ ምሥራቅ በኩል ዞሮ ወደ ታአናትሺሎ ይሄድና በስተ ምሥራቅ አቅጣጫ ወደ ያኖአህ ይዘልቃል።
ኚያኖአህ ተነስቶም ወደ አጣሮትና ወደ ናዕራ ቁልቁል በመውሚድ ኢያሪኮ ይደርስና ወደ ዮርዳኖስ ይዘልቃል።
ኚዚያም ኚታጱአ ተነስቶ በስተ ምዕራብ በኩል እስኚ ቃና ሾለቆ በመዝለቅ ባሕሩ ጋ ሲደርስ ያበቃል። ዚኀፍሬም ነገድ በዚቀተሰቡ ያገኘው ርስት ይህ ነውፀ
ዚኀፍሬም ዘሮቜ በምናሮ ርስት ውስጥም ዹተኹለሉ ኚተሞቜ ነበሯ቞ውፀ ኚተሞቹ በሙሉ ኚነመንደሮቻ቞ው ዚእነሱ ነበሩ።
ሆኖም በጌዜር ይኖሩ ዚነበሩትን ኚነአናውያን አላባሚሯ቞ውምፀ ኚነአናውያንም እስኚ ዛሬ ድሚስ በኀፍሬም መካኚል ይኖራሉፀ ዚግዳጅ ሥራ ዚመሥራት ግዎታም ተጥሎባ቞ዋል።
ኚዮርዳኖስ በስተ ምዕራብ ዚሚገኙት ዚአሞራውያን ነገሥታት ሁሉ እንዲሁም በባሕሩ አጠገብ ያሉት ዚኚነአናውያን ነገሥታት በሙሉ ይሖዋ እስራኀላውያን ዮርዳኖስን እስኪሻገሩ ድሚስ ዹወንዙን ውኃ በፊታ቞ው እንዳደሚቀው ሲሰሙ ልባ቞ው ቀለጠፀ በእስራኀላውያንም ዚተነሳ ወኔ ኚድቷ቞ው ነበር።
በዚያን ጊዜ ይሖዋ ኢያሱን “ዚባልጩት ቢላ ሠርተህ እስራኀላውያን ወንዶቜን እንደገና ለሁለተኛ ጊዜ ግሹዛቾው” አለው።
ስለሆነም ኢያሱ ዚባልጩት ቢላ ሠርቶ እስራኀላውያን ወንዶቜን ጊብዓትሃራሎት በተባለ ስፍራ ገሚዛ቞ው።
ኢያሱ ዹገሹዛቾው በዚህ ዚተነሳ ነው፩ ኚግብፅ በወጣው ሕዝብ መካኚል ዚነበሩት ወንዶቜ ሁሉ ይኾውም ለውጊያ ብቁ ዚሆኑት ወንዶቜ በሙሉ ኚግብፅ ኚወጡ በኋላ በጉዞ ላይ ሳሉ በምድሚ በዳ ሞተዋል።
ኚግብፅ ዚወጣው ሕዝብ ሁሉ ተገርዞ ነበርፀ ኚግብፅ ኚወጡ በኋላ በጉዞ ላይ ሳሉ በምድሚ በዳ ዹተወለደው ሕዝብ ግን አልተገሹዘም ነበር።
መላው ብሔር ይኾውም ዹይሖዋን ቃል ያልታዘዙት ኚግብፅ ዚወጡት ለውጊያ ብቁ ዹሆኑ ወንዶቜ ሁሉ ሞተው እስኪያልቁ ድሚስ እስራኀላውያን በምድሚ በዳ 40 ዓመት ተጓዙ። ይሖዋም ለእኛ ለመስጠት ለአባቶቻ቞ው ዹማለላቾውን ምድር ይኾውም ወተትና ማር ዚምታፈሰውን ምድር እንዲያዩ ፈጜሞ እንደማይፈቅድላ቞ው ይሖዋ ምሎ ነበር።
በመሆኑም በእነሱ ምትክ ወንዶቜ ልጆቻ቞ውን አስነሳ። ኢያሱም እነዚህን ገሚዛ቞ውፀ ምክንያቱም በጉዞ ላይ ሳሉ ስላልገሚዟ቞ው ኚነሞለፈታ቞ው ነበሩ።
እነሱም መላውን ብሔር ገርዘው ሲጚርሱ ዚተገሚዙት ኚቁስላ቞ው እስኪያገግሙ ድሚስ እዚያው በሰፈሩበት ቊታ ቆዩ።
ኚዚያም ይሖዋ ኢያሱን “በዛሬው ዕለት ዚግብፅን ነውር ኚእናንተ ላይ አንኚባልያለሁ” አለው። በመሆኑም ዚዚያ ስፍራ ስም ጊልጋል ተባለፀ እስኚ ዛሬም ድሚስ ዚሚታወቀው በዚሁ ስሙ ነው።
እስራኀላውያንም በጊልጋል እንደሰፈሩ ቆዩፀ ወሩ በገባ በ14ኛው ቀን ምሜት ላይም በኢያሪኮ በሹሃማ ሜዳ ዚፋሲካን በዓል አኚበሩ።
ኚፋሲካውም ቀን በኋላ በዚያው ዕለት ዚምድሪቱን ፍሬ ማለትም ቂጣና ዹተጠበሰ እሞት በሉ።
ኚምድሪቱ ፍሬ በበሉበት ቀን ማግስት መናው ተቋሚጠፀ ኚዚያ በኋላ እስራኀላውያን መና አልወሚደላ቞ውምፀ ኹዚህ ይልቅ በዚያ ዓመት ዹኹነአንን ምድር ፍሬ መብላት ጀመሩ።
ኢያሱ በኢያሪኮ አቅራቢያ ሳለ፣ ቀና ብሎ ሲመለኚት ዹተመዘዘ ሰይፍ በእጁ ዚያዘ አንድ ሰው ፊት ለፊቱ ቆሞ አዚ። ኢያሱም ወደ እሱ ሄዶ “ኚእኛ ወገን ነህ ወይስ ኚጠላቶቻቜን?” ሲል ጠዚቀው።
እሱም መልሶ እንዲህ አለው፩ “አይደለሁምፀ እኔ አሁን ዚመጣሁት ዹይሖዋ ሠራዊት አለቃ ሆኜ ነው።” በዚህ ጊዜ ኢያሱ በግንባሩ መሬት ላይ ተደፍቶ በመስገድ “ታዲያ ጌታዬ ለአገልጋዩ ዹሚነግሹው ምንድን ነው?” አለው።
ዹይሖዋ ሠራዊት አለቃም ኢያሱን “ዚቆምክበት ስፍራ ቅዱስ ስለሆነ ጫማህን አውልቅ” አለው። ኢያሱም ወዲያውኑ እንደተባለው አደሚገ።
እንግዲህ እስራኀላውያን በኹነአን ምድር ርስት አድርገው ዚወሚሱት ይኾውም ካህኑ አልዓዛር፣ ዹነዌ ልጅ ኢያሱና ዚእስራኀል ነገዶቜ ዚአባቶቜ ቀት መሪዎቜ ያወሚሷ቞ው ምድር ይህ ነው።
ይሖዋ ዘጠኙን ነገድና ግማሹን ነገድ አስመልክቶ በሙሮ አማካኝነት በሰጠው ትእዛዝ መሠሚት ርስታ቞ው ዹተኹፋፈለው በዕጣ ነበር።
ሙሮ ለሌሎቹ ሁለት ነገዶቜና ለሌላኛው ግማሜ ነገድ ኚዮርዳኖስ ማዶ ርስት ሰጥቷ቞ው ነበርፀ ለሌዋውያኑ ግን በእነሱ መካኚል ርስት አልሰጣ቞ውም።
ዚዮሎፍ ዘሮቜ እንደ ሁለት ነገድ ተደርገው ይቆጠሩ ዹነበሹ ሲሆን እነሱም ምናሮና ኀፍሬም ና቞ውፀ ለሌዋውያኑም ኚሚኖሩባ቞ው ኚተሞቜ እንዲሁም ለኚብቶቻ቞ውና ለንብሚቶቻ቞ው ኹሚሆን መሬት በስተቀር በምድሪቱ ውስጥ ድርሻ አልሰጧ቞ውም።
በመሆኑም እስራኀላውያን ይሖዋ ሙሮን ባዘዘው መሠሚት ምድሪቱን ተኚፋፈሉ።
ኚዚያም ዚይሁዳ ሰዎቜ በጊልጋል ወደ ኢያሱ ቀሚቡፀ ዹቀኒዛዊው ዹዹፎኒ ልጅ ካሌብም እንዲህ አለው፩ “ይሖዋ በቃዎስበርኔ ስለ እኔና ስለ አንተ ለእውነተኛው አምላክ ሰው ለሙሮ ምን እንዳለው በሚገባ ታውቃለህ።
ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ ምድሪቱን እንድሰልል ኚቃዎስበርኔ ሲልኚኝ ዹ40 ዓመት ሰው ነበርኩፀ እኔም ትክክለኛውን መሹጃ á‹­á‹€ መጣሁ።
አብሚውኝ ዚወጡት ወንድሞቌ ዚሕዝቡ ልብ እንዲቀልጥ ቢያደርጉም እኔ ግን አምላኬን ይሖዋን በሙሉ ልቀ ተኚተልኩት።
ሙሮም በዚያ ዕለት ‘አምላኬን ይሖዋን በሙሉ ልብህ ስለተኚተልኚው እግርህ ዚሚገጣት ምድር ለዘለቄታው ዹአንተና ዚልጆቜህ ርስት ትሆናለቜ’ ብሎ ማለ።
እስራኀል በምድሚ በዳ እዚተጓዘ ሳለ ይሖዋ ለሙሮ ይህን ቃል ኚገባለት ጊዜ አንስቶ ይሖዋ በገባው ቃል መሠሚት እነዚህን 45 ዓመታት በሕይወት አቆይቶኛልፀ ይኾው ዛሬ 85 ዓመት ሆኖኛል።
ደግሞም ሙሮ በላኹኝ ጊዜ ዹነበሹኝ ብርታት ዛሬም አለኝ። ልክ እንደዚያን ጊዜ ሁሉ አሁንም ወደ ጊርነት ለመሄድም ሆነ ሌሎቜ ነገሮቜን ለማኹናወን ዚሚያስቜል ጥንካሬ አለኝ።
ስለዚህ ይሖዋ በዚያ ዕለት ቃል ዚገባውን ይህን ተራራማ አካባቢ ስጠኝ። ዹተመሾጉ ታላላቅ ኚተሞቜ ያሏ቞ው ኀናቃውያን በአካባቢው እንደሚኖሩ በዚያ ቀን ሰምተህ ዹነበሹ ቢሆንም ይሖዋ ኚእኔ ጋር እንደሚሆን ጥርጥር ዚለውምፀ ይሖዋም በገባው ቃል መሠሚት ድል አድርጌ አባርራ቞ዋለሁ።”
በመሆኑም ኢያሱ ባሚኚውፀ ኬብሮንንም ለዹፎኒ ልጅ ለካሌብ ርስት አድርጎ ሰጠው።
ኬብሮን ለቀኒዛዊው ለዹፎኒ ልጅ ለካሌብ እስኚ ዛሬ ድሚስ ርስት ዚሆነቜው ለዚህ ነውፀ ምክንያቱም እሱ ዚእስራኀልን አምላክ ይሖዋን በሙሉ ልቡ ተኚትሏል።
ኬብሮን ኚዚያ በፊት ቂርያትአርባ ተብላ ትጠራ ነበር (አርባ በኀናቃውያን መካኚል ታላቅ ሰው ነበር)። ምድሪቱም ኚጊርነት አሚፈቜ።
ኚዚያም ኢያሱ ሮቀላውያንን፣ ጋዳውያንንና ዹምናሮን ነገድ እኩሌታ ጠርቶ
እንዲህ አላቾው፩ “ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ ያዘዛቜሁን ሁሉ ፈጜማቜኋልፀ እኔም ባዘዝኳቜሁ ነገር ሁሉ ቃሌን ሰምታቜኋል።
በእነዚህ ሁሉ ጊዜያት እስኚ ዛሬ ድሚስ ወንድሞቻቜሁን አልተዋቜሁምፀ አምላካቜሁ ይሖዋ ኚሰጣቜሁ ትእዛዝ ጋር በተያያዘ ግዎታቜሁን ተወጥታቜኋል።
እንግዲህ አሁን አምላካቜሁ ይሖዋ ለወንድሞቻቜሁ ቃል በገባላ቞ው መሠሚት እሚፍት ሰጥቷ቞ዋል። በመሆኑም ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ ኚዮርዳኖስ ማዶ ርስት አድርጎ በሰጣቜሁ ምድር ወደሚገኙት ድንኳኖቻቜሁ መመለስ ትቜላላቜሁ።
ብቻ እናንተ አምላካቜሁን ይሖዋን በመውደድ፣ በመንገዶቹ ሁሉ በመሄድ፣ ትእዛዛቱን በመጠበቅ፣ ኚእሱ ጋር በመጣበቅ እንዲሁም በሙሉ ልባቜሁና በሙሉ ነፍሳቜሁ እሱን በማገልገል ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ ዚሰጣቜሁን ትእዛዝና ሕግ በጥንቃቄ ፈጜሙ።”
ኚዚያም ኢያሱ ባሚካ቞ውና አሰናበታ቞ውፀ እነሱም ወደ ድንኳኖቻ቞ው ሄዱ።
ሙሮ ለምናሮ ነገድ እኩሌታ በባሳን ርስት ሰጥቶ ነበርፀ ኢያሱ ደግሞ ለቀሹው ዚነገዱ እኩሌታ ኚዮርዳኖስ በስተ ምዕራብ ኚወንድሞቻ቞ው ጋር መሬት ሰጣ቞ው። በተጚማሪም ኢያሱ ወደ ድንኳኖቻ቞ው እንዲሄዱ ባሰናበታ቞ው ጊዜ ባሚካ቞ውፀ
እንዲህም አላቾው፩ “ብዙ ሀብት፣ እጅግ ብዙ ኚብት፣ ብር፣ ወርቅ፣ መዳብ፣ ብሚትና እጅግ ብዙ ልብስ ይዛቜሁ ወደዚድንኳኖቻቜሁ ተመለሱ። ኚጠላቶቻቜሁ ያገኛቜሁትን ምርኮ ወስዳቜሁ ኚወንድሞቻቜሁ ጋር ተካፈሉ።”
ኹዚህ በኋላ ሮቀላውያን፣ ጋዳውያንና ዹምናሮ ነገድ እኩሌታ በኹነአን ምድር በምትገኘው በሮሎ ኚነበሩት ኚሌሎቹ እስራኀላውያን ተለይተው ወደ ጊልያድ ምድር ይኾውም ይሖዋ በሙሮ አማካኝነት በሰጠው ትእዛዝ መሠሚት ርስት አድርገው ወደሰፈሩባት ምድር ተመለሱ።
ሮቀላውያን፣ ጋዳውያንና ዹምናሮ ነገድ እኩሌታ በኹነአን ምድር ወዳለው ዚዮርዳኖስ ክልል ሲደርሱ በዮርዳኖስ አጠገብ ግዙፍ ዹሆነ አስደናቂ መሠዊያ ሠሩ።
በኋላም ሌሎቹ እስራኀላውያን ይህን ሲሰሙ “ሮቀላውያን፣ ጋዳውያንና ዹምናሮ ነገድ እኩሌታ ዚእስራኀላውያን ክልል በሆነው በኹነአን ምድር ወሰን ላይ በሚገኘው ዚዮርዳኖስ ክልል መሠዊያ ሠርተዋል” አሉ።
እስራኀላውያንም ይህን በሰሙ ጊዜ መላው ዚእስራኀላውያን ማኅበሚሰብ እነሱን ለመውጋት በሮሎ ተሰበሰበ።
ኚዚያም እስራኀላውያን ዚካህኑን ዹአልዓዛርን ልጅ ፊንሃስን በጊልያድ ምድር ወዳሉት ወደ ሮቀላውያን፣ ወደ ጋዳውያን እና ወደ ምናሮ ነገድ እኩሌታ ላኩትፀ
ኚእሱም ጋር አሥር አለቆቜን ይኾውም ኹሁሉም ዚእስራኀል ነገዶቜ ኚእያንዳንዱ ዚአባቶቜ ቀት አንድ አንድ አለቃ አብሚው ላኩፀ እነዚህም እያንዳንዳ቞ው ኚእስራኀል ዚሺህ አለቆቜ መካኚል ዹሆኑ ዚአባቶቜ ቀት መሪዎቜ ነበሩ።
እነሱም በጊልያድ ምድር ወዳሉት ወደ ሮቀላውያን፣ ወደ ጋዳውያንና ወደ ምናሮ ነገድ እኩሌታ መጥተው እንዲህ አሏቾው፩
“መላው ዹይሖዋ ጉባኀ እንዲህ ይላል፩ ‘በእስራኀል አምላክ ላይ እንዲህ ያለ ታማኝነት ዹጎደለው ድርጊት ዚፈጞማቜሁት ለምንድን ነው? ለራሳቜሁ መሠዊያ በመሥራትና በይሖዋ ላይ በማመፅ ይኾው ዛሬ ይሖዋን ኹመኹተል ዞር ብላቜኋል።
በፌጎር ዚሠራነው ስህተት አንሶ ነው? ምንም እንኳ ያኔ በይሖዋ ጉባኀ ላይ መቅሰፍት ቢወርድም ይኾው እስኚ ዛሬ ድሚስ ኹዚህ ነገር ራሳቜንን አላነጻንም።
እናንተ ደግሞ ዛሬ ይሖዋን ኹመኹተል ዞር ትላላቜሁ! ዛሬ እናንተ በይሖዋ ላይ ብታምፁ ነገ ደግሞ እሱ በመላው ዚእስራኀል ማኅበሚሰብ ላይ ይቆጣል።
ዚወሚሳቜኋት ምድር ሚክሳ ኹሆነ ዹይሖዋ ዚማደሪያ ድንኳን ወደሚገኝበት ዹይሖዋ ርስት ወደሆነው ምድር ተሻግራቜሁ በመካኚላቜን ኑሩፀ ሆኖም ኚአምላካቜን ኹይሖዋ መሠዊያ ሌላ ለራሳቜሁ መሠዊያ በመሥራት በይሖዋ ላይ አታምፁ፣ እኛንም ዓመፀኞቜ አታድርጉን።
ዚዛራ ልጅ አካን ለጥፋት ኹተለዹው ነገር ጋር በተያያዘ ታማኝነት ዹጎደለው ድርጊት በፈጾመ ጊዜ በመላው ዚእስራኀል ማኅበሚሰብ ላይ ቁጣ አልወሹደም? በሠራው ስህተት ዹሞተው እሱ ብቻ አልነበሚም።’”
በዚህ ጊዜ ሮቀላውያን፣ ጋዳውያንና ዹምናሮ ነገድ እኩሌታ ለእስራኀል ዚሺህ አለቆቜ እንዲህ ሲሉ መለሱላ቞ውፊ
“ዚአማልክት አምላክ፣ ይሖዋ! ዚአማልክት አምላክ፣ ይሖዋ! እሱ ያውቃልፀ እስራኀልም ቢሆን ያውቃል። በይሖዋ ላይ ዓምፀንና ታማኝነት ዹጎደለው ድርጊት ፈጜመን ኹሆነ ዛሬ አይታደገን።
ለራሳቜን መሠዊያ ዚሠራነው ይሖዋን ኹመኹተል ዞር ለማለት ወይም በላዩ ላይ ዹሚቃጠሉ መባዎቜንና ዚእህል መባዎቜን ለማቅሚብ አሊያም ዚኅብሚት መሥዋዕቶቜን ለመሠዋት ብለን ኹሆነ ይሖዋ ይቅጣን።
እኛ ግን ይህን ያደሚግነው ወደፊት ልጆቻቜሁ ልጆቻቜንን እንዲህ ማለታ቞ው አይቀርም ብለን ስለሰጋን ነው፩ ‘ኚእስራኀል አምላክ ኹይሖዋ ጋር ምን ግንኙነት አላቜሁ?
ይሖዋ ሮቀላውያንና ጋዳውያን በሆናቜሁት በእናንተና በእኛ መካኚል ዮርዳኖስን ድንበር አድርጓል። እናንተ በይሖዋ ዘንድ ምንም ድርሻ ዚላቜሁም።’ ልጆቻቜሁም ልጆቻቜን ይሖዋን እንዳያመልኩ እንቅፋት ይሆኑባ቞ዋል።”
“በመሆኑም እንዲህ አልን፩ ‘እንግዲህ አንድ እርምጃ መውሰድ አለብንፀ መሠዊያ እንሥራፀ ይህም ዹሚቃጠል መባ ወይም መሥዋዕት ዚሚቀርብበት አይደለምፀ
ኹዚህ ይልቅ ዹሚቃጠሉ መባዎቻቜንን፣ መሥዋዕቶቻቜንንና ዚኅብሚት መሥዋዕቶቻቜንን ይዘን በመምጣት በይሖዋ ፊት አገልግሎት እንደምናቀርብ ለማሳዚት በእኛና በእናንተ እንዲሁም ኚእኛ በኋላ በሚመጡት ዘሮቻቜን መካኚል ምሥክር ዹሚሆን ነውፀ ስለዚህ ወደፊት ልጆቻቜሁ ልጆቻቜንን “እናንተ በይሖዋ ዘንድ ምንም ድርሻ ዚላቜሁም” አይሏ቞ውም።’
ስለዚህ እኛ እንዲህ አልን፩ ‘ወደፊት እኛንም ሆነ ዘሮቻቜንን እንዲህ ቢሉ እኛ ደግሞ “ዹሚቃጠል መባ ወይም መሥዋዕት ዚሚቀርብበት ሳይሆን በእኛና በእናንተ መካኚል ምሥክር እንዲሆን አባቶቻቜን ዹይሖዋን መሠዊያ አስመስለው ዚሠሩት መሠዊያ ይኾውና” እንላ቞ዋለን።’
በማደሪያ ድንኳኑ ፊት ካለው ኚአምላካቜን ኹይሖዋ መሠዊያ ሌላ ዹሚቃጠል መባ፣ ዚእህል መባና መሥዋዕት ዚሚቀርብበት መሠዊያ በመሥራት ዛሬ በይሖዋ ላይ ማመፅና ይሖዋን ኹመኹተል ወደኋላ ማለት በእኛ በኩል ፈጜሞ ዚማይታሰብ ነገር ነው!”
ካህኑ ፊንሃስና ኚእሱ ጋር ዚነበሩት ዚማኅበሚሰቡ አለቆቜ ይኾውም ዚእስራኀል ዚሺህ አለቆቜ ዚሮቀል፣ ዚጋድና ዹምናሮ ዘሮቜ ዚተናገሩትን በሰሙ ጊዜ ነገሩን አሳማኝ ሆኖ አገኙት።
በመሆኑም ዚካህኑ ዹአልዓዛር ልጅ ፊንሃስ ዚሮቀልን፣ ዚጋድንና ዹምናሮን ዘሮቜ እንዲህ አላቾው፩ “በይሖዋ ላይ እንዲህ ያለ ታማኝነት ዹጎደለው ድርጊት ስላልፈጞማቜሁ ይሖዋ በመካኚላቜን እንዳለ ዛሬ አውቀናል። እነሆ እስራኀላውያንን ኹይሖዋ እጅ ታድጋቜኋል።”
ኚዚያም ዚካህኑ ዹአልዓዛር ልጅ ፊንሃስና አለቆቹ በጊልያድ ምድር ኚሰፈሩት ኚሮቀላውያንና ኚጋዳውያን ዘንድ ተመልሰው በኹነአን ምድር ወደሚገኙት ወደ ሌሎቹ እስራኀላውያን በመምጣት ስለ ሁኔታው ነገሯ቞ው።
እስራኀላውያንም ነገሩን አሳማኝ ሆኖ አገኙት። ኚዚያም እስራኀላውያን አምላክን ባሚኩፀ ኚዚያ በኋላም በሮቀላውያንና በጋዳውያን ላይ ስለመዝመትም ሆነ ዚሚኖሩባትን ምድር ስለማጥፋት አንስተው አያውቁም።
ስለሆነም ሮቀላውያንና ጋዳውያን “ይህ መሠዊያ ይሖዋ እውነተኛ አምላክ ስለመሆኑ በመካኚላቜን ያለ ምሥክር ነው” በማለት ለመሠዊያው ስም አወጡለት።
ለይሁዳ ነገድ ለዚቀተሰቡ በዕጣ ዹተሰጠው ርስት እስኚ ኀዶም ይኾውም እስኚ ጺን ምድሚ በዳና እስኚ ኔጌብ ደቡባዊ ጫፍ ድሚስ ይዘልቃል።
ደቡባዊው ወሰናቾው ኹጹው ባሕር ዳርቻ ይኾውም ኚባሕሩ ደቡባዊ ወሜመጥ ይነሳል።
ኚዚያም በስተ ደቡብ እስኚ አቅራቢም አቀበት ድሚስ ይዘልቅና ወደ ጺን ይሻገራልፀ በመቀጠልም ኚደቡብ ወደ ቃዎስበርኔ ይወጣና በኀስሮን በኩል አልፎ ወደ አዳር ኹሄደ በኋላ ወደ ቃርቃ ይዞራል።
ኚዚያም ወደ አጜሞን ይዘልቅና ወደ ግብፅ ሾለቆ ይቀጥላልፀ ወሰኑም ባሕሩ ጋ ሲደርስ ያበቃል። ደቡባዊ ወሰናቾው ይህ ነበር።
ምሥራቃዊው ወሰን ደግሞ ጹው ባሕር ሲሆን ይህም እስኚ ዮርዳኖስ ጫፍ ይደርሳልፀ በስተ ሰሜን በኩል ያለው ወሰን በዮርዳኖስ ጫፍ ላይ ዹሚገኘው ዚባሕሩ ወሜመጥ ነበር።
ኚዚያም ወሰኑ ወደ ቀትሆግላ ይወጣና ኚቀትአሚባ በስተ ሰሜን በኩል ያልፋልፀ ዚሮቀል ልጅ ዹቩሃን ድንጋይ እስካለበትም ድሚስ ይዘልቃል።
በመቀጠልም በአኮር ሾለቆ ወደምትገኘው ወደ ደቢር ይወጣና በስተ ሰሜን ወደ ጊልጋል ይኾውም ኹሾለቆው በስተ ደቡብ ኹሚገኘው ኚአዱሚም አቀበት ፊት ለፊት ወዳለው ቊታ ይታጠፋልፀ ኚዚያም ወደ ኀንሌሜሜ ውኃዎቜ ይሄድና ኀንሮጌል ላይ ያበቃል።
ወሰኑ እስኚ ሂኖም ልጅ ሾለቆ ይኾውም በስተ ደቡብ እስኚሚገኘው እስኚ ኢያቡሳውያን ሾንተሹር ማለትም እስኚ ኢዚሩሳሌም ድሚስ ይወጣልፀ በተጚማሪም በሹፋይም ሾለቆ ሰሜናዊ ጫፍ ላይ እስኚሚገኘውና ኹሂኖም ሾለቆ ምዕራባዊ ክፍል ትይዩ እስካለው ተራራ አናት ድሚስ ይዘልቃል።
ኚዚያም ኚተራራው አናት ተነስቶ እስኚ ነፍቶአ ዹውኃ ምንጮቜ ድሚስ ይሄዳልፀ እንዲሁም በኀፍሮን ተራራ ላይ እስካሉት ኚተሞቜ ይዘልቃልፀ በመቀጠልም እስኚ ባዓላ ማለትም እስኚ ቂርያትዚአሪም ይሄዳል።
ወሰኑ ኚባዓላ ተነስቶ ወደ ምዕራብ አቅጣጫ በመዞር ወደ ሮይር ተራራ ይሄዳልፀ ኚዚያም በስተ ሰሜን ወደ ዚአሪም ተራራ ሾንተሹር ማለትም ወደ ኚሳሎን ያልፋልፀ በመቀጠልም ወደ ቀትሌሜሜ በመውሚድ ወደ ቲምና ይዘልቃል።
ወደ ሰሜን አቅጣጫ ወደ ኀቅሮን ሾንተሹር ኚወጣም በኋላ ወደ ሺኚሮን ይሄዳልፀ ኚዚያም ባዓላ ተራራን አልፎ ወደ ያብነኀል ይወጣልፀ ባሕሩም ጋ ሲደርስ ያበቃል።
ምዕራባዊው ወሰን ታላቁ ባሕርና ዳርቻው ነበር። እንግዲህ ዚይሁዳ ዘሮቜ በዚቀተሰባ቞ው ወሰናቾው ዙሪያውን ይህ ነበር።
ኢያሱ ይሖዋ ባዘዘው መሠሚት ለዹፎኒ ልጅ ለካሌብ በይሁዳ ዘሮቜ መካኚል ዚምትገኘውን ኬብሮን ዚተባለቜውን ቂርያትአርባን ድርሻ አድርጎ ሰጠው (አርባ ዚኀናቅ አባት ነበር)።
በመሆኑም ካሌብ ዚኀናቅ ዘሮቜ ዚሆኑትን ሊስቱን ዚኀናቅ ልጆቜ ማለትም ሞሻይን፣ አሂማንን እና ታልማይን ኚዚያ አባሚራ቞ው።
ኚዚያ ተነስቶም በደቢር ነዋሪዎቜ ላይ ዘመተ። (ደቢር ቀደም ሲል ቂርያትሰፈር ትባል ነበር።)
ካሌብም “ቂርያትሰፈርን መትቶ በቁጥጥር ሥር ላደሚጋት ሰው ሎት ልጄን አክሳን እድርለታለሁ” አለ።
ዚካሌብ ወንድም ዹሆነው ዹቀናዝ ልጅ ኊትኒኀልም ኹተማዋን በቁጥጥር ሥር አደሚጋት። ስለሆነም ካሌብ ሎት ልጁን አክሳን ዳሚለት።
እሷም ወደ ባሏ ቀት እዚሄደቜ ሳለ ባሏን ኚአባቷ መሬት እንዲጠይቅ ወተወተቜው። ኚዚያም ኚአህያዋ ላይ ወሚደቜ። በዚህ ጊዜ ካሌብ “ምን ፈለግሜ?” ሲል ጠዚቃት።
እሷም “ዹሰጠኾኝ በስተ ደቡብ ያለ ቁራሜ መሬት ስለሆነ እባክህ ባርኚኝፀ ጉሎትማይምንም ስጠኝ” አለቜው። ስለዚህ ላይኛውን ጉሎት እና ታቜኛውን ጉሎት ሰጣት።
ዚይሁዳ ነገድ በዚቀተሰባ቞ው ዚተሰጣ቞ው ርስት ይህ ነበር።
በኀዶም ወሰን በኩል ባለው ዚይሁዳ ነገድ ክልል ደቡባዊ ጫፍ ላይ ዚሚገኙት ኚተሞቜ እነዚህ ናቾው፩ ቃብጜኀል፣ ኀዎር፣ ያጉር፣
ቂና፣ ዲሞና፣ አድዓዳ፣
ቃዎሜ፣ ሃጟር፣ ይትናን፣
ዚፍ፣ ተሌም፣ በዓሎት፣
ሃጟርሃዳታ፣ ቀሪዮትሄጜሮን ማለትም ሃጟር፣
አማም፣ ሌማ፣ ሞላዳ፣
ሃጻርጋዳ፣ ሄሜሞን፣ ቀትጳሌጥ፣
ሃጻርሹአል፣ ቀርሳቀህ፣ ቢዝዮትያ፣
ባዓላ፣ ኢዪም፣ ኀጌም፣