text
stringlengths
4
267
ኀልቶላድ፣ ኚሲል፣ ሆርማ፣
ጺቅላግ፣ ማድማና፣ ሳንሳና፣
ለባኊት፣ ሺልሂም፣ አይን እና ሪሞንፀ በአጠቃላይ 29 ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
በሾፌላ ዚነበሩት ኚተሞቜ እነዚህ ናቾው፩ ኀሜታዖል፣ ጟራ፣ አሜና፣
ዛኖሃ፣ ኀንጋኒም፣ ታጱአ፣ ኀናም፣
ያርሙት፣ አዱላም፣ ሶኮህ፣ አዜቃ፣
ሻአራይም፣ አዲታይም፣ ገዎራ እና ገዎሮታይምፀ በአጠቃላይ 14 ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ጞናን፣ ሃዳሻ፣ ሚግዳልጋድ፣
ዲልአን፣ ምጜጳ፣ ዮቅተኀል፣
ለኪሶ፣ ቊጜቃት፣ ኀግሎን፣
ካቊን፣ ላህማም፣ ኪትሊሜ፣
ገዎሮት፣ ቀትዳጎን፣ ናዕማ እና መቄዳፀ በአጠቃላይ 16 ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ሊብና፣ ኀ቎ር፣ አሻን፣
ይፍታህ፣ አሜና፣ ነጺብ፣
ቀኢላ፣ አክዚብ እና ማሬሻህፀ በአጠቃላይ ዘጠኝ ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ኀቅሮን እንዲሁም በሥሯ ያሉት ኚተሞቜና መንደሮቿ።
ኚኀቅሮን በስተ ምዕራብ በአሜዶድ በኩል ያሉት አካባቢዎቜ በሙሉና መንደሮቻ቞ው።
አሜዶድ እንዲሁም በሥሯ ያሉት ኚተሞቜና መንደሮቿፀ ጋዛ እንዲሁም በሥሯ ያሉት ኚተሞቜና መንደሮቿ እስኚ ግብፅ ሞለቆ፣ እስኚ ታላቁ ባሕርና በባሕሩ ጠሹፍ እስካለው አካባቢ ድሚስ።
በተራራማው አካባቢ ዚነበሩት ኚተሞቜ እነዚህ ናቾው፩ ሻሚር፣ ያቲር፣ ሶኮህ፣
ዳና፣ ቂርያትሳና ማለትም ደቢር፣
አናብ፣ ኀሜተሞህ፣ አኒም፣
ጎሞን፣ ሆሎን እና ጊሎፀ በአጠቃላይ 11 ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ዓሚብ፣ ዱማ፣ ኀሜዓን፣
ያኒም፣ ቀትታጱአ፣ አፌቃ፣
ሁምጣ፣ ቂርያትአርባ ማለትም ኬብሮን እና ጺኊርፀ በአጠቃላይ ዘጠኝ ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ማኊን፣ ቀርሜሎስ፣ ዚፍ፣ ዩጣ፣
ኢይዝራኀል፣ ዮቅደአም፣ ዛኖሃ፣
ቄይን፣ ጊብዓ እና ቲምናፀ በአጠቃላይ አሥር ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ሃልሁል፣ ቀትጹር፣ ጌዶር፣
ማአራት፣ ቀትአኖት እና ኀልተቆንፀ በአጠቃላይ ስድስት ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ቂርያትበኣል ማለትም ቂርያትዚአሪም እና ራባፀ በአጠቃላይ ሁለት ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
በምድሚ በዳው ዚነበሩት ኚተሞቜ እነዚህ ናቾው፩ ቀትአሚባ፣ ሚዲን፣ ሰካካ፣
ኒብሻን፣ ዹጹው ኹተማ እና ኀንገዲፀ በአጠቃላይ ስድስት ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ዚይሁዳ ሰዎቜ በኢዚሩሳሌም ይኖሩ ዚነበሩትን ኢያቡሳውያንን ሊያባርሯ቞ው አልቻሉም ነበርፀ ስለሆነም ኢያቡሳውያን እስኚ ዛሬ ድሚስ ኚይሁዳ ሰዎቜ ጋር በኢዚሩሳሌም ይኖራሉ።
መላው ብሔር ዮርዳኖስን እንደተሻገሚ ይሖዋ ኢያሱን እንዲህ አለው፩
“ኚሕዝቡ መካኚል 12 ሰዎቜን ይኾውም ኚእያንዳንዱ ነገድ አንድ አንድ ሰው ምሚጥፀ
እነሱንም እንዲህ ብለህ እዘዛ቞ውፊ ‘ኚዮርዳኖስ ወንዝ መሃል ይኾውም ዚካህናቱ እግር ኚቆመበት ስፍራ 12 ድንጋዮቜን ውሰዱፀ ድንጋዮቹንም ይዛቜሁ በመሄድ በምታድሩበት ስፍራ አስቀምጧ቞ው።’”
በመሆኑም ኢያሱ ኚእስራኀላውያን መካኚል ዚሟማ቞ውን 12 ሰዎቜ ይኾውም ኚእያንዳንዱ ነገድ አንድ አንድ ሰው ጠራፀ
ኢያሱም እንዲህ አላቾው፩ “ዚአምላካቜሁን ዹይሖዋን ታቊት ቀድማቜሁ ወደ ዮርዳኖስ መሃል ሂዱፀ እያንዳንዳቜሁም በእስራኀላውያን ነገዶቜ ቁጥር ልክ አንድ አንድ ድንጋይ አንስታቜሁ በትኚሻቜሁ ተሞኚሙፀ
ይህም በመካኚላቜሁ እንደ ምልክት ሆኖ ያገለግላል። ምናልባት ወደፊት ልጆቻቜሁ ‘እነዚህን ድንጋዮቜ እዚህ ያስቀመጣቜኋ቞ው ለምንድን ነው?’ ብለው ቢጠይቋቜሁ
እንዲህ በሏቾው፩ ‘ዚዮርዳኖስ ውኃ በይሖዋ ዹቃል ኪዳን ታቊት ፊት ተቋርጩ ስለነበር ነው። ታቊቱ ዮርዳኖስን ሲሻገር ዚዮርዳኖስ ውኃ ተቋሚጠ። እነዚህ ድንጋዮቜ ለእስራኀላውያን በዘላቂነት እንደ መታሰቢያ ሆነው ያገለግላሉ።’”
እስራኀላውያንም ኢያሱ እንዳዘዛ቞ው አደሚጉ። እነሱም ይሖዋ ኢያሱን ባዘዘው መሠሚት ኚዮርዳኖስ መሃል በእስራኀላውያን ነገዶቜ ቁጥር ልክ 12 ድንጋዮቜን አነሱ። ኚዚያም ወደሚያድሩበት ስፍራ ይዘዋቾው በመሄድ እዚያ አስቀመጧ቞ው።
በተጚማሪም ኢያሱ ዹቃል ኪዳኑን ታቊት ዚተሞኚሙት ካህናት እግር ቆሞበት በነበሹው በዮርዳኖስ መሃል ባለው ቊታ ላይ 12 ድንጋዮቜን አስቀምጊ ነበርፀ እነዚህም ድንጋዮቜ እስኚ ዛሬ ድሚስ በዚያ ይገኛሉ።
ሙሮ ለኢያሱ በሰጠው መመሪያ መሠሚት ይሖዋ፣ ኢያሱ ለሕዝቡ እንዲናገር ያዘዘው ነገር በሙሉ እስኪፈጞም ድሚስ ታቊቱን ዚተሞኚሙት ካህናት በዮርዳኖስ መሃል ቆመው ነበር። በዚህ ጊዜ ሕዝቡ ፈጥኖ ተሻገሚ።
ሕዝቡ ሁሉ ተሻግሮ እንዳበቃ ዹይሖዋ ታቊትና ካህናቱ ሕዝቡ እያያ቞ው ተሻገሩ።
ሮቀላውያን፣ ጋዳውያንና ዹምናሮ ነገድ እኩሌታ ሙሮ በሰጣ቞ው መመሪያ መሠሚት ዚጊርነት አሰላለፍ ተኚትለው ሌሎቹን እስራኀላውያን ቀድመው ተሻገሩ።
ወደ 40,000 ዹሚሆኑ ለጊርነት ዚታጠቁ ሰዎቜ ወደ ኢያሪኮ በሹሃማ ሜዳ በይሖዋ ፊት ተሻገሩ።
በዚያ ዕለት ይሖዋ ኢያሱን በእስራኀላውያን ሁሉ ፊት ኹፍ ኹፍ አደሚገውፀ እነሱም ሙሮን በጥልቅ ያኚብሩት እንደነበር ሁሉ እሱንም በሕይወት ዘመኑ ሁሉ በጥልቅ አኚበሩት።
ኚዚያም ይሖዋ ኢያሱን እንዲህ አለው፩
“ዚምሥክሩን ታቊት ዚተሞኚሙትን ካህናት ኚዮርዳኖስ እንዲወጡ እዘዛ቞ው።”
በመሆኑም ኢያሱ ካህናቱን “ኚዮርዳኖስ ውጡ” በማለት አዘዛ቞ው።
ዹይሖዋን ዹቃል ኪዳን ታቊት ዚተሞኚሙት ካህናት ኚዮርዳኖስ መሃል ሲወጡና ዚካህናቱ እግር ኹውኃው ወጥቶ ደሹቁን መሬት ሲሚግጥ ዚዮርዳኖስ ውኃ እንደቀድሞው መፍሰሱንና ዳርቻውን ሁሉ ማጥለቅለቁን ቀጠለ።
ሕዝቡም በመጀመሪያው ወር በአሥሚኛው ቀን ላይ ኚዮርዳኖስ ወጥቶ በኢያሪኮ ምሥራቃዊ ወሰን ላይ በምትገኘው በጊልጋል ሰፈሚ።
ኢያሱም ኚዮርዳኖስ ያወጧ቞ውን 12 ድንጋዮቜ በጊልጋል አቆማ቞ው።
ኚዚያም እስራኀላውያንን እንዲህ አላቾው፩ “ወደፊት ልጆቻቜሁ ‘እነዚህ ድንጋዮቜ ምንድን ናቾው?’ ብለው በሚጠይቋቜሁ ጊዜ
ልጆቻቜሁን እንዲህ በሏቾው፩ ‘እስራኀል ዮርዳኖስን በደሹቅ ምድር ተሻገሚፀ
ይህም ዹሆነው አምላካቜሁ ይሖዋ ቀይ ባሕርን እስኪሻገሩ ድሚስ ባሕሩን በፊታ቞ው እንዳደሚቀው ሁሉ እኛም ዮርዳኖስን እስክንሻገር ድሚስ አምላካቜሁ ይሖዋ ዚዮርዳኖስን ውኃ በፊታቜን ስላደሚቀው ነው።
ይህን ያደሚገው ዚምድር ሕዝቊቜ ሁሉ ዹይሖዋ ክንድ ምን ያህል ኃያል መሆኑን እንዲያውቁና እናንተም አምላካቜሁን ይሖዋን ሁልጊዜ እንድትፈሩ ነው።’”
ኚዚያም ይሖዋ ኢያሱን እንዲህ አለው፩
“እስራኀላውያንን እንዲህ በላቾው፩ ‘በሙሮ አማካኝነት በነገርኳቜሁ መሠሚት ለራሳቜሁ ዹመማጾኛ ኚተሞቜን ምሚጡፀ
ሳያስበው ወይም በድንገት ሰው ዹገደለ ግለሰብ ወደነዚህ ኚተሞቜ መሞሜ ይቜላል። እነሱም ኹደም ተበቃዩ መሞሞጊያ ሆነው ያገለግሏቜኋል።
ገዳዩ ኚእነዚህ ኚተሞቜ ወደ አንዱ በመሞሜ በኹተማዋ በር ላይ ቆሞ ለኹተማዋ ሜማግሌዎቜ ጉዳዩን ይናገር። እነሱም ወደ ኹተማቾው አስገብተው መኖሪያ ይስጡትፀ እሱም አብሯ቞ው ይኖራል።
ደም ተበቃዩ ቢያሳድደው ሰዎቹ ነፍሰ ገዳዩን አሳልፈው አይስጡትፀ ምክንያቱም ግለሰቡ ባልንጀራውን ዹገደለው ዹቆዹ ጥላቻ ኖሮት ሳይሆን በድንገት ነው።
ስለሆነም በማኅበሚሰቡ ፊት ለፍርድ እስኪቀርብ ድሚስ በኹተማዋ ውስጥ ይኑርፀ በዚያ ጊዜ ዚሚያገለግለው ሊቀ ካህናት እስኪሞት ድሚስም ኚዚያ መውጣት ዚለበትም። ኚዚያ በኋላ ገዳዩ ሞሜቶ ወደወጣባት ኹተማ መመለስ እንዲሁም ወደ ኹተማውና ወደ ቀቱ መግባት ይቜላል።’”
በመሆኑም በንፍታሌም ተራራማ አካባቢ በገሊላ ዚምትገኘውን ቃዎሜን፣ በኀፍሬም ተራራማ አካባቢ ዚምትገኘውን ሎኬምንና በይሁዳ ተራራማ አካባቢ ዚምትገኘውን ቂርያትአርባን ማለትም ኬብሮንን ለዚህ ዓላማ ቀደሱ።
ኚኢያሪኮ በስተ ምሥራቅ ባለው ዚዮርዳኖስ ክልል ደግሞ ኚሮቀል ነገድ ርስት በአምባው ላይ በሚገኘው ምድሚ በዳ ላይ ያለቜውን ቀጌርን፣ ኚጋድ ነገድ ርስት በጊልያድ ዚምትገኘውን ራሞትን እንዲሁም ኹምናሮ ነገድ ርስት በባሳን ዚምትገኘውን ጎላንን መሚጡ።
ሳያስበው ሰው ዹገደለ ማንኛውም ግለሰብ በማኅበሚሰቡ ፊት ለፍርድ ኚመቅሚቡ በፊት ደም ተበቃዩ አግኝቶ እንዳይገድለው ሞሜቶ እንዲሞሞግባ቞ው ለእስራኀላውያን በሙሉ ወይም በመካኚላ቞ው ለሚኖር ዚባዕድ አገር ሰው ዚተለዩት ኚተሞቜ እነዚህ ና቞ው።
እንግዲህ እስራኀላውያን ድል ያደሚጓ቞ውና ኚዮርዳኖስ በስተ ምሥራቅ ዹሚገኘውን ምድራ቞ውን ይኾውም ኹአርኖን ሾለቆ አንስቶ እስኚ ሄርሞን ተራራ ድሚስ ያለውን እንዲሁም በስተ ምሥራቅ ዹሚገኘውን አሚባን በሙሉ ዚወሚሱባ቞ው ነገሥታት እነዚህ ናቾው፩
በሃሜቊን ዹሚኖሹውና በአርኖን ሾለቆ ዳርቻ ላይ በምትገኘው በአሮዔር ሆኖ ዹሚገዛው ዚአሞራውያን ንጉሥ ሲሖንፀ እሱም በአርኖን ሾለቆ መሃል ካለው ስፍራ አንስቶ ዚአሞናውያን ወሰን እስኚሆነው እስኚ ያቊቅ ሾለቆ ድሚስ ያለውን ዚጊልያድን እኩሌታ ይገዛ ነበር።
በተጚማሪም ምሥራቃዊ አሚባን እስኚ ኪኔሬት ባሕር ድሚስ፣ በስተ ምሥራቅ በቀትዚሺሞት አቅጣጫ እስካለው ዚአሚባ ባሕር ይኾውም እስኚ ጹው ባሕር ድሚስና በስተ ደቡብ እስኚ ጲስጋ ሾንተሹር ድሚስ ያለውን አካባቢ ይገዛ ነበር።
እንዲሁም በአስታሮትና በኀድራይ ይኖር ዹነበሹውንና ኚመጚሚሻዎቹ ዹሹፋይም ወገኖቜ አንዱ ዹሆነውን ዚባሳንን ንጉሥ ዹኩግን ግዛትፀ
እሱም ዹሄርሞንን ተራራ፣ ሳልካን፣ ባሳንን በሙሉ እስኚ ገሹራውያንና እስኚ ማአካታውያን ወሰን ድሚስ እንዲሁም እስኚ ሃሜቊን ንጉሥ እስኚ ሲሖን ግዛት ድሚስ ያለውን ዚጊልያድን እኩሌታ ይገዛ ነበር።
ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮና እስራኀላውያን እነዚህን ነገሥታት ድል አደሚጓ቞ውፀ ኚዚያም ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ ምድራ቞ውን ለሮቀላውያን፣ ለጋዳውያንና ለምናሮ ነገድ እኩሌታ ርስት አድርጎ ሰጠ።
ኢያሱና እስራኀላውያን ድል ያደሚጓ቞ው ኚዮርዳኖስ በስተ ምዕራብ ያሉት ዚምድሪቱ ነገሥታት እነዚህ ና቞ውፀ ግዛታ቞ውም በሊባኖስ ሾለቆ ኹሚገኘው ኚበዓልጋድ አንስቶ ወደ ሮይር ሜቅብ እስኚሚወጣው እስኚ ሃላቅ ተራራ ድሚስ ነውፀ ኚዚያም ኢያሱ ምድራ቞ውን ለእስራኀል ነገዶቜ እንደዚድርሻ቞ው ርስት አድርጎ ሰጠፀ
ይህም በተራራማው አካባቢ፣ በሞፌላ፣ በአሚባ፣ በሞንተሚሮቹ ላይ፣ በምድሚ በዳውና በኔጌብ ዚሚኖሩት ዚሂታውያን፣ ዚአሞራውያን፣ ዚኚነአናውያን፣ ዚፈሪዛውያን፣ ዚሂዋውያንና ዚኢያቡሳውያን ምድር ነውፀ ነገሥታቱም ዚሚኚተሉት ናቾው፩
ዚኢያሪኮ ንጉሥ፣ አንድፀ በቀ቎ል አጠገብ ዚነበሚቜው ዹጋይ ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚኢዚሩሳሌም ንጉሥ፣ አንድፀ ዚኬብሮን ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚያርሙት ንጉሥ፣ አንድፀ ዚለኪሶ ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚኀግሎን ንጉሥ፣ አንድፀ ዚጌዜር ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚደቢር ንጉሥ፣ አንድፀ ዚጌዎር ንጉሥ፣ አንድፀ
ዹሆርማ ንጉሥ፣ አንድፀ ዚአራድ ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚሊብና ንጉሥ፣ አንድፀ ዚአዱላም ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚመቄዳ ንጉሥ፣ አንድፀ ዚቀ቎ል ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚታጱአ ንጉሥ፣ አንድፀ ዚሄፌር ንጉሥ፣ አንድፀ
ዹአፌቅ ንጉሥ፣ አንድፀ ዚላሻሮን ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚማዶን ንጉሥ፣ አንድፀ ዚሃጟር ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚሺምሮንመሮን ንጉሥ፣ አንድፀ ዚአክሻፍ ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚታአናክ ንጉሥ፣ አንድፀ ዚመጊዶ ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚቃዎሜ ንጉሥ፣ አንድፀ በቀርሜሎስ ዚምትገኘው ዚዮቅነአም ንጉሥ፣ አንድፀ
በዶር ሞንተሚሮቜ ዚምትገኘው ዚዶር ንጉሥ፣ አንድፀ በጊልጋል ዚምትገኘው ዹጎይም ንጉሥ፣ አንድፀ
ዚቲርጻ ንጉሥ፣ አንድፀ በአጠቃላይ 31 ነገሥታት ና቞ው።
ኚዚያም መላው ዚእስራኀላውያን ማኅበሚሰብ በሮሎ ተሰበሰበፀ በዚህ ጊዜ ምድሪቱ በፊታ቞ው ተገዝታላ቞ው ስለነበር ዹመገናኛ ድንኳኑን በዚያ ተኚሉ።
ይሁንና ኚእስራኀላውያን መካኚል ገና ርስት ያልተሰጣ቞ው ሰባት ነገዶቜ ነበሩ።
በመሆኑም ኢያሱ እስራኀላውያንን እንዲህ አላቾው፩ “ዚአባቶቻቜሁ አምላክ ይሖዋ ዚሰጣቜሁን ምድር ገብታቜሁ ለመውሚስ ቜላ ዚምትሉት እስኚ መቌ ነው?
ኚእያንዳንዱ ነገድ ሊስት ሊስት ወንዶቜን ስጡኝፀ እኔም እልካ቞ዋለሁፀ እነሱም ሄደው ምድሪቱን ተዘዋውሹው ኚተመለኚቱ በኋላ በሚወርሱት ድርሻ መሠሚት ይሞነሜኗታል። ኚዚያም ተመልሰው ወደ እኔ ይመጣሉ።
ምድሪቱንም ሰባት ቊታ ይኚፋፈሏታል። ይሁዳ በስተ ደቡብ ያለውን ክልሉን ይዞ ይኖራልፀ ዚዮሎፍ ቀት ደግሞ በስተ ሰሜን ያለውን ክልሉን ይዞ ይኖራል።
እናንተ ግን ምድሪቱን ሰባት ቊታ ትሞነሜኗታላቜሁፀ ኚዚያም ዚሞነሞናቜሁትን ይዛቜሁ ወደ እኔ ኑፀ እኔም እዚህ በአምላካቜን በይሖዋ ፊት ዕጣ አወጣላቜኋለሁ።
ሌዋውያኑ ግን ለይሖዋ ዚሚያቀርቡት ዚክህነት አገልግሎት ውርሻ቞ው ስለሆነ በመካኚላቜሁ ድርሻ አይኖራ቞ውምፀ ጋድ፣ ሮቀልና ዹምናሮ ነገድ እኩሌታም ቢሆኑ ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ በሰጣ቞ው መሠሚት ኚዮርዳኖስ በስተ ምሥራቅ ርስታ቞ውን አስቀድመው ወስደዋል።”
ሰዎቹም ለመሄድ ተነሱፀ ኢያሱም ምድሪቱን ለመሾንሾን ዚሚሄዱትን ሰዎቜ “ሂዱና ምድሪቱን ተዘዋውራቜሁ በማዚት ሞንሜኗትፀ ኚዚያም ተመልሳቜሁ ወደ እኔ ኑፀ እኔም እዚሁ በሮሎ በይሖዋ ፊት ዕጣ አወጣላቜኋለሁ” ሲል አዘዛ቞ው።
ሰዎቹም ሄደው በምድሪቱ ተዘዋወሩፀ ኚዚያም በኹተማ በኹተማ ሰባት ቊታ ሞንሜነው በመጜሐፍ አሰፈሩት። በኋላም በሮሎ ባለው ሰፈር ወደሚገኘው ወደ ኢያሱ ተመልሰው መጡ።