text
stringlengths
4
267
ኢያሱም በሮሎ በይሖዋ ፊት ዕጣ አወጣላ቞ው። በዚያም ኢያሱ ምድሪቱን ለእስራኀላውያን በዚድርሻ቞ው አኚፋፈላ቞ው።
ዚመጀመሪያውም ዕጣ ለቢንያም ነገድ በዚቀተሰቡ ወጣፀ በዕጣ ዚደሚሳ቞ውም ክልል በይሁዳ ሰዎቜና በዮሎፍ ሰዎቜ መካኚል ዹሚገኘው ነበር።
በሰሜን በኩል ያለው ወሰናቾው ኚዮርዳኖስ ተነስቶ በስተ ሰሜን ወዳለው ዚኢያሪኮ ሾንተሹር ይወጣና በስተ ምዕራብ ወደ ተራራው ያቀናልፀ ኚዚያም ወደ ቀትአዌን ምድሚ በዳ ይዘልቃል።
ኚዚያ ደግሞ ወሰኑ ቀ቎ል ወደምትባለው ወደ ሎዛ ማለትም ወደ ሎዛ ደቡባዊ ሾንተሹር ያቀናልፀ በመቀጠልም ኚታቜኛው ቀትሆሮን በስተ ደቡብ በሚገኘው ተራራ ላይ አድርጎ ወደ አጣሮትዓዳር ይወርዳል።
በስተ ምዕራብ ያለው ወሰንም በስተ ደቡብ በኩል ኚቀትሆሮን ትይዩ ኹሆነው ተራራ በመነሳት ወደ ደቡብ ይታጠፋልፀ ኚዚያም ዚይሁዳ ኹተማ ዚሆነቜው ቂርያትበአል ይኾውም ቂርያትዚአሪም ጋ ሲደርስ ያበቃል። ይህ ምዕራባዊው ወሰን ነው።
በስተ ደቡብ ያለው ወሰን ደግሞ ኚቂርያትዚአሪም ጫፍ ተነስቶ ወደ ምዕራብ ይዘልቃልፀ ኚዚያም ወደ ነፍቶአ ዹውኃ ምንጭ ይወጣል።
ኚዚያም ኹሂኖም ልጅ ሾለቆ ፊት ለፊት ወደሚገኘውና በሹፋይም ሾለቆ ሰሜናዊ ጫፍ ወዳለው ተራራ ግርጌ ይወርዳልፀ በመቀጠልም ወደ ሂኖም ሾለቆ ይኾውም በስተ ደቡብ ወደሚገኘው ወደ ኢያቡሳውያን ሾንተሹር ይወርድና እስኚ ኀንሮጌል ይዘልቃል።
ኚዚያም ወደ ሰሜን በማቅናት ወደ ኀንሌሜሜ ያልፍና ኚአዱሚም አቀበት ፊት ለፊት እስኚምትገኘው እስኚ ገሊሎት ይደርሳልፀ በመቀጠልም ዚሮቀል ልጅ ዹቩሃን ድንጋይ እስካለበት ድሚስ ይወርዳል።
ወሰኑ አሚባ ፊት ለፊት ወዳለው ሰሜናዊ ሾንተሹር ይሄድና ቁልቁል ወደ አሚባ ይወርዳል።
ኚዚያም ወደ ቀትሆግላ ሰሜናዊ ሾንተሹር ይዘልቅና በዮርዳኖስ ደቡባዊ ጫፍ፣ ዹጹው ባሕር ሰሜናዊ ዳርቻ ላይ ሲደርስ ያበቃል። ደቡባዊው ወሰን ይህ ነበር።
በስተ ምሥራቅ በኩል ወሰኑ ዮርዳኖስ ነበር። ዚቢንያም ዘሮቜ በዚቀተሰባ቞ው ያገኙት ርስት ወሰን ዙሪያውን ይህ ነበር።
ዚቢንያም ነገድ በዚቀተሰቡ ያገኛ቞ው ኚተሞቜ እነዚህ ናቾው፩ ኢያሪኮ፣ ቀትሆግላ፣ ኀሜቀጺጜ፣
ቀትአሚባ፣ ጞማራይም፣ ቀ቎ል፣
አዊም፣ ጳራ፣ ኊፍራ፣
ኚፋርአሞናይ፣ ኩፍኒ እና ጌባፀ በአጠቃላይ 12 ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ።
ገባኊን፣ ራማ፣ በኀሮት፣
ምጜጳ፣ ኚፊራ፣ ሞጻ፣
ራቄም፣ ይርጰኀል፣ ታራላ፣
ጞላህ፣ ኀሌፍ፣ ኢያቡስ ማለትም ኢዚሩሳሌም፣ ጊብዓ እና ቂርያትፀ በአጠቃላይ 14 ኚተሞቜ ኚነመንደሮቻ቞ው ነበሩ። ዚቢንያም ዘሮቜ በዚቀተሰባ቞ው ያገኙት ርስት ይህ ነበር።
ይሖዋ እስራኀላውያንን በዙሪያ቞ው ካሉት ጠላቶቻ቞ው ሁሉ ካሳሚፋ቞ው ኚብዙ ጊዜ በኋላ፣ ኢያሱም አርጅቶና ዕድሜው ገፍቶ ሳለ
ኢያሱ እስራኀላውያንን በሙሉ፣ ሜማግሌዎቻ቞ውን፣ መሪዎቻ቞ውን፣ ዳኞቻ቞ውንና አለቆቻ቞ውን ጠርቶ እንዲህ አላቾው፩ “እንግዲህ እኔ አርጅቻለሁፀ ዕድሜዬም ገፍቷል።
አምላካቜሁ ይሖዋ ለእናንተ ሲል በእነዚህ ብሔራት ላይ ያደሚገውን ሁሉ ራሳቜሁ አይታቜኋልፀ ምክንያቱም ለእናንተ እዚተዋጋላቜሁ ዹነበሹው አምላካቜሁ ይሖዋ ነው።
እኔም ኚዮርዳኖስ አንስቶ በስተ ምዕራብ እስኚሚገኘው እስኚ ታላቁ ባሕር ድሚስ ያጠፋኋ቞ውን ብሔራት ሁሉ ምድር ጚምሮ ዚቀሩትን ብሔራት ምድር ለዚነገዶቻቜሁ ርስት እንዲሆን በዕጣ አኚፋፍዬ ሰጥቻቜኋለሁ።
እነሱን ኚፊታቜሁ ያባሚራ቞ው አምላካቜሁ ይሖዋ ነውፀ እሱም ለእናንተ ሲል አባሚራ቞ውፀ እናንተም አምላካቜሁ ይሖዋ በገባላቜሁ ቃል መሠሚት ምድራ቞ውን ወሚሳቜሁ።
“እንግዲህ በሙሮ ዹሕግ መጜሐፍ ውስጥ ኚተጻፈው ወደ ቀኝም ሆነ ወደ ግራ ፈጜሞ ዞር ሳትሉ ሕጉን ሁሉ ለመጠበቅና ለመፈጾም ደፋሮቜ ሁኑፀ
እንዲሁም በመካኚላቜሁ ኚቀሩት ኚእነዚህ ብሔራት ጋር አትቀላቀሉ። ሌላው ቀርቶ ዚአማልክታ቞ውን ስም አታንሱፀ በእነሱም አትማሉፀ ፈጜሞ አታገልግሏ቞ው እንዲሁም አትስገዱላ቞ው።
ኹዚህ ይልቅ እስኚዚህ ቀን ድሚስ እንዳደሚጋቜሁት ሁሉ ኚአምላካቜሁ ኹይሖዋ ጋር ተጣብቃቜሁ ኑሩ።
ይሖዋ ታላላቅና ኃያላን ብሔራትን ኚፊታቜሁ ያባርራ቞ዋልፀ እስኚዚህ ቀን ድሚስ አንድም ሰው ሊቋቋማቜሁ አልቻለም።
አምላካቜሁ ይሖዋ በገባላቜሁ ቃል መሠሚት ለእናንተ ስለሚዋጋላቜሁ ኚእናንተ አንዱ፣ ሺህ ሰው ያሳድዳል።
ስለዚህ አምላካቜሁን ይሖዋን በመውደድ ዘወትር ነቅታቜሁ ጠብቁ።
“ይሁንና ወደ ኋላ ዞር ብትሉና ኚእነዚህ ብሔራት መካኚል ተርፈው ኚእናንተ ጋር ኚቀሩት ሰዎቜ ጋር ዹጠበቀ ግንኙነት ብትመሠርቱ፣ በጋብቻ ብትዛመዱ እንዲሁም እናንተ ኚእነሱ ጋር ብትወዳጁ፣ እነሱም ኚእናንተ ጋር ወዳጅነት ቢመሠርቱ
አምላካቜሁ ይሖዋ ኹዚህ በኋላ ለእናንተ ሲል እነዚህን ብሔራት እንደማያባርራ቞ው በእርግጥ እወቁ። እነሱም አምላካቜሁ ይሖዋ ኚሰጣቜሁ ኚዚህቜ መልካም ምድር ላይ እስክትጠፉ ድሚስ ወጥመድ፣ አሜክላ፣ ለጀርባቜሁ ጅራፍ እንዲሁም በዓይናቜሁ ውስጥ እንዳለ እሟህ ይሆኑባቜኋል።
“እንግዲህ እኔ መሞቻዬ ተቃርቧልፀ አምላካቜሁ ይሖዋ ኚገባላቜሁ መልካም ቃል ሁሉ አንዲቷም እንኳ ሳትፈጞም እንዳልቀሚቜ በሙሉ ልባቜሁና በሙሉ ነፍሳቜሁ ታውቃላቜሁ። ሁሉም ተፈጜሞላቜኋል። ኚመካኚላ቞ው ሳይፈጞም ዹቀሹ አንድም ቃል ዚለም።
ሆኖም አምላካቜሁ ይሖዋ ዚገባላቜሁ መልካም ቃል በሙሉ እንደተፈጞመላቜሁ ሁሉ ይሖዋ አመጣባቜኋለሁ ብሎ ዹተናገሹውን ጥፋት ሁሉ ያመጣባቜኋልፀ አምላካቜሁ ይሖዋ ኚሰጣቜሁ ኚዚህቜ መልካም ምድርም ያጠፋቜኋል።
አምላካቜሁ ይሖዋ እንድትጠብቁት ያዘዛቜሁን ቃል ኪዳን ካፈሚሳቜሁ እንዲሁም ሄዳቜሁ ሌሎቜ አማልክትን ካገለገላቜሁና ለእነሱ ኚሰገዳቜሁ ዹይሖዋ ቁጣ በእናንተ ላይ ይነድዳልፀ ኚሰጣቜሁም መልካም ምድር ላይ በፍጥነት ትጠፋላቜሁ።”
ኢያሪኮ በእስራኀላውያን ዚተነሳ ጥርቅም ተደርጋ ተዘግታ ነበርፀ ወደ ውጭ ዚሚወጣም ሆነ ወደ ውስጥ ዚሚገባ አልነበሚም።
ይሖዋም ኢያሱን እንዲህ አለው፩ “እንግዲህ ኢያሪኮን፣ ንጉሥዋንና ኃያል ተዋጊዎቿን በእጅህ አሳልፌ ሰጥቌሃለሁ።
ተዋጊ ዚሆናቜሁት ወንዶቜም ሁሉ ኹተማዋን ዙሪያዋን በመሄድ አንድ ጊዜ ዙሯት። ለስድስት ቀን እንዲህ አድርጉ።
ሰባት ካህናት ሰባት ቀንደ መለኚት ይዘው በታቊቱ ፊት ይሂዱ። በሰባተኛው ቀን ግን ኹተማዋን ሰባት ጊዜ ዙሯትፀ ካህናቱም ቀንደ መለኚቱን ይንፉ።
ቀንደ መለኚቱ ሲነፋና ዹቀንደ መለኚቱን ድምፅ ስትሰሙ ሕዝቡ ሁሉ ታላቅ ዚጊርነት ጩኞት ያሰማ። ኚዚያም ዹኹተማዋ ቅጥር ይፈራርሳልፀ ሕዝቡም ሁሉ፣ እያንዳንዱም ሰው ቀጥ ብሎ ወደ ፊት ይሂድ።”
ስለዚህ ዹነዌ ልጅ ኢያሱ ካህናቱን አንድ ላይ ጠርቶ “ዹቃል ኪዳኑን ታቊት አንሱፀ ሰባት ካህናትም ሰባት ቀንደ መለኚት ይዘው በይሖዋ ታቊት ፊት ይሂዱ” አላ቞ው።
ሕዝቡንም “እናንተ ተነሱና ኹተማዋን ዙሩፀ ዚታጠቁት ተዋጊዎቜም ኹይሖዋ ታቊት ቀድመው ይሄዳሉ” አላ቞ው።
ኢያሱ ለሕዝቡ በተናገሹው መሠሚት ሰባት ቀንደ መለኚት ዚያዙት ሰባት ካህናት በይሖዋ ፊት ቀድመው በመሄድ ቀንደ መለኚታ቞ውን ነፉፀ ዹይሖዋ ዹቃል ኪዳን ታቊትም ይኹተላቾው ነበር።
ዚታጠቁትም ተዋጊዎቜ ቀንደ መለኚቱን ኚሚነፉት ካህናት ቀድመው ሄዱፀ ዹኋላው ደጀን ደግሞ ታቊቱን ይኹተል ነበርፀ በዚህ ጊዜ ሁሉ ቀንደ መለኚቱ ያለማቋሚጥ ይነፋ ነበር።
ኢያሱም ሕዝቡን እንዲህ ሲል አዘዘ፩ “መጮኜም ሆነ ድምፃቜሁን ማሰማት ዚለባቜሁም። እኔ ‘ጩኹ!’ ብዬ እስኚማዛቜሁ ቀን ድሚስ ኚአፋቜሁ አንድም ቃል መውጣት ዚለበትም። ኚዚያ በኋላ ትጮኻላቜሁ።”
እሱም ዹይሖዋ ታቊት በኹተማዋ ዙሪያ በመሄድ ኹተማዋን አንድ ጊዜ እንዲዞር አደሚገፀ ኚዚያም ወደ ሰፈሩ ተመልሰው በዚያ አደሩ።
በሚቀጥለው ቀን ኢያሱ በማለዳ ተነሳፀ ካህናቱም ዹይሖዋን ታቊት አነሱፀ
ሰባት ቀንደ መለኚት ዚያዙ ሰባት ካህናት ያለማቋሚጥ መለኚታ቞ውን እዚነፉ ኹይሖዋ ታቊት ፊት ፊት ይሄዱ ነበር። ዚታጠቁት ተዋጊዎቜም ኚእነሱ ፊት ይሄዱ ነበርፀ ዹኋላው ደጀን ደግሞ ዹይሖዋን ታቊት ይኹተል ነበርፀ በዚህ ጊዜ ሁሉ ቀንደ መለኚቱ ያለማቋሚጥ ይነፋ ነበር።
በሁለተኛውም ቀን ኹተማዋን አንድ ጊዜ ዞሯትፀ ኚዚያም ወደ ሰፈሩ ተመለሱ። ለስድስት ቀን ልክ እንደዚሁ አደሚጉ።
በሰባተኛው ቀን ገና ጎህ ሲቀድ ተነስተው ኹተማዋን በዚሁ መንገድ ሰባት ጊዜ ዞሯት። ኹተማዋን ሰባት ጊዜ ዚዞሯት በዚያ ቀን ብቻ ነበር።
በሰባተኛው ዙር ላይ ካህናቱ ቀንደ መለኚቱን ነፉፀ ኢያሱም ሕዝቡን እንዲህ አለ፩ “ይሖዋ ኹተማዋን አሳልፎ ስለሰጣቜሁ ጩኹ!
ኹተማዋም ሆነቜ በውስጧ ያለው ነገር ሁሉ ሙሉ በሙሉ መጥፋት አለበትፀ ኹተማዋ ሙሉ በሙሉ ዹይሖዋ ነቜ። በሕይወት ዚሚተርፉት ዝሙት አዳሪዋ ሚዓብና ኚእሷ ጋር በቀቱ ውስጥ ያሉት ብቻ ና቞ውፀ ምክንያቱም እሷ ዹላክናቾውን መልእክተኞቜ ደብቃለቜ።
እናንተ ግን ለጥፋት ዹተለዹው ነገር እንዳያጓጓቜሁና እንዳትወስዱት፣ በእስራኀልም ሰፈር ላይ መዓት በማምጣት ሰፈሩን ለጥፋት ዹተለዹ እንዳታደርጉት ለጥፋት ኹተለዹው ነገር ራቁ።
ሆኖም ብሩ፣ ወርቁ እንዲሁም ኚመዳብና ኚብሚት ዚተሠሩት ዕቃዎቜ ሁሉ ለይሖዋ ዚተቀደሱ ና቞ው። ወደ ይሖዋ ግምጃ ቀት መግባት አለባ቞ው።”
ኚዚያም ቀንደ መለኚቱ ሲነፋ ሕዝቡ ጮኞ። ሕዝቡ ዹቀንደ መለኚቱን ድምፅ ሰምቶ ታላቅ ዚጊርነት ጩኞት ሲያሰማ ቅጥሩ ፈሚሰ። ኚዚያም ሕዝቡ ሁሉ፣ እያንዳንዱም ሰው በቀጥታ ወደ ኹተማዋ በመግባት ኹተማዋን ያዛት።
እነሱም በኹተማዋ ውስጥ ዹነበሹውን በሙሉ ይኾውም ወንዱንና ሎቱን፣ ወጣቱንና ሜማግሌውን እንዲሁም በሬውን፣ በጉንና አህያውን በሰይፍ ሙሉ በሙሉ አጠፉ።
ኢያሱም ምድሪቱን ዚሰለሉትን ሁለቱን ሰዎቜ “ወደ ዝሙት አዳሪዋ ቀት ገብታቜሁ በማላቜሁላት መሠሚት ሎትዚዋንና ዚእሷ ዹሆነውን ሁሉ ኚዚያ አውጡ” አላ቞ው።
በመሆኑም ወጣቶቹ ሰላዮቜ ገብተው ሚዓብን፣ አባቷን፣ እናቷን፣ ወንድሞቿንና ዚእሷ ዹሆነውን ሁሉ አዎ፣ ቀተሰቧን በሙሉ አውጥተው ኚእስራኀል ሰፈር ውጭ ወዳለ ስፍራ በሰላም አመጧ቞ው።
ኚዚያም ኹተማዋንና በውስጧ ዹነበሹውን ሁሉ በእሳት አቃጠሉ። ብሩን፣ ወርቁን እንዲሁም ኚመዳብና ኚብሚት ዚተሠሩትን ዕቃዎቜ ግን ወደ ይሖዋ ግምጃ ቀት አስገቡ።
ኢያሱ በሕይወት እንዲተርፉ ያደሚገው ዝሙት አዳሪዋን ሚዓብን፣ ዚአባቷን ቀተሰብና ዚእሷ ዹሆነውን ብቻ ነበርፀ እሷም እስኚ ዛሬ ድሚስ በእስራኀል መካኚል ትኖራለቜፀ ምክንያቱም ኢያሱ ኢያሪኮን እንዲሰልሉ ዚላካ቞ውን መልእክተኞቜ ደብቃ ነበር።
በዚያን ጊዜ ኢያሱ ይህን ቃለ መሐላ አወጀ፩ “ይህቜን ዚኢያሪኮን ኹተማ ለመገንባት ዚሚነሳ ሰው በይሖዋ ፊት ዹተሹገመ ይሁን። ዹኹተማዋን መሠሚት ሲጥል ዚበኩር ልጁ ይጥፋፀ በሮቿንም ሲያቆም ዚመጚሚሻ ልጁ ይጥፋ።”
ይሖዋም ኚኢያሱ ጋር ነበርፀ በመላውም ምድር ላይ ዝነኛ ሆነ።
ኚዚያም ይሖዋ ኢያሱን እንዲህ አለው፩ “አትፍራ ወይም አትሞበር። ተዋጊዎቹን ሁሉ ይዘህ በጋይ ላይ ዝመት። እነሆ፣ ዹጋይን ንጉሥ፣ ሕዝቡን፣ ኹተማውንና ምድሩን በእጅህ አሳልፌ ሰጥቌሃለሁ።
በኢያሪኮና በንጉሥዋ ላይ ያደሚግኚውን ሁሉ በጋይና በንጉሥዋም ላይ አድርግፀ ዚማሚካቜኋ቞ውን ነገሮቜና ኚብቶቿን ግን ለራሳቜሁ ውሰዱ። ኹኹተማዋም በስተ ጀርባ ዚደፈጣ ተዋጊዎቜን አስቀምጥ።”
ስለዚህ ኢያሱና ተዋጊዎቹ በሙሉ ጋይን ለመውጋት ወጡ። ኢያሱም 30,000 ኃያል ተዋጊዎቜን መርጩ በሌሊት ላካ቞ው።
እንዲህም ሲል አዘዛቾው፩ “እንግዲህ እናንተ ኹኹተማዋ በስተ ጀርባ አድፍጣቜሁ ትጠብቃላቜሁ። ኹኹተማዋ ብዙ አትራቁፀ ሁላቜሁም በተጠንቀቅ ጠብቁ።
እኔና አብሮኝ ያለው ሕዝብ ሁሉ ወደ ኹተማዋ እንቀርባለንፀ እነሱም ኹዚህ በፊት እንዳደሚጉት ሁሉ ሊወጉን ሲወጡ እኛ ኚፊታ቞ው እንሞሻለን።
እነሱም ‘ኹዚህ በፊት እንዳደሚጉት አሁንም ኚፊታቜን እዚሞሹ ነው’ በማለት ይኚታተሉናልፀ በዚህ መንገድ ኹኹተማዋ እንዲርቁ እናደርጋ቞ዋለን። እኛም ኚእነሱ እንሞሻለን።
እናንተም ካደፈጣቜሁበት ቊታ ተነስታቜሁ ኹተማዋን ትቆጣጠራላቜሁፀ አምላካቜሁ ይሖዋም ኹተማዋን በእጃቜሁ አሳልፎ ይሰጣቜኋል።
ኹተማዋን እንደያዛቜሁም በእሳት አቃጥሏት። ይሖዋ ባዘዘው መሠሚት አድርጉ። እንግዲህ እኔ አዝዣቜኋለሁ።”
ኚዚያም ኢያሱ ሰዎቹን ላካ቞ውፀ እነሱም አድፍጠው ወደሚጠባበቁበት ቊታ ሄዱፀ ኹጋይ በስተ ምዕራብ በቀ቎ልና በጋይ መካኚል በሚገኘው ስፍራም አደፈጡፀ ኢያሱ ግን ያን ሌሊት እዚያው ኚሕዝቡ ጋር አደሚ።
ኚዚያም ኢያሱ በማለዳ ተነስቶ ሠራዊቱን ኹሰበሰበ በኋላ እሱና ዚእስራኀል ሜማግሌዎቜ እዚመሯ቞ው ወደ ጋይ ይዘዋቾው ሄዱ።
ኚእሱም ጋር ዚነበሩት ተዋጊዎቜ በሙሉ ገስግሰው ወደ ኹተማዋ ፊት ቀሚቡ። እነሱም ኹጋይ በስተ ሰሜን ሰፈሩፀ በእነሱና በጋይ መካኚልም ሾለቆ ነበር።
በዚህ ጊዜ ኢያሱ 5,000 ገደማ ዹሚሆኑ ሰዎቜን ወስዶ ኹኹተማዋ በስተ ምዕራብ በኩል በቀ቎ልና በጋይ መካኚል አድፍጠው እንዲጠብቁ አድርጎ ነበር።
ሕዝቡም ዋና ሰፈሩን ኹኹተማዋ በስተ ሰሜን አደሚገፀ ዹኋላ ደጀን ዹሆነውን ሠራዊት ደግሞ ኹኹተማዋ በስተ ምዕራብ አደሚገፀ ኢያሱም በዚያ ሌሊት ወደ ሾለቆው መሃል ሄደ።
ዹጋይም ንጉሥ ይህን ባዚ ጊዜ እሱና ዹኹተማዋ ሰዎቜ ማልደው በመነሳት ኚእስራኀል ጋር ለመዋጋት በሹሃማውን ሜዳ ቁልቁል ማዚት ወደሚያስቜላ቞ው ስፍራ በፍጥነት ገሰገሱ። ሆኖም ንጉሡ ኹኹተማዋ በስተ ጀርባ በእሱ ላይ ያደፈጠ ሠራዊት መኖሩን አላወቀም ነበር።
ዹጋይ ሰዎቜም ጥቃት በሰነዘሩ ጊዜ ኢያሱና መላው እስራኀል ድል ዚተመቱ በማስመሰል ወደ ምድሚ በዳው ዚሚወስደውን መንገድ ይዘው ሞሹ።
ኚዚያም በኹተማዋ ውስጥ ዹነበሹው ሕዝብ በሙሉ ወጥቶ እንዲያሳድዳ቞ው ተጠራፀ እነሱም ኢያሱን እያሳደዱ ኹኹተማዋ ርቀው ሄዱ።
ኹጋይም ሆነ ኚቀ቎ል እስራኀልን ለማሳደድ ያልወጣ አንድም ወንድ አልነበሚም። ኹተማዋንም ወለል አድርገው ኹፍተው በመሄድ እስራኀልን ማሳደዳ቞ውን ተያያዙት።
በዚህ ጊዜ ይሖዋ ኢያሱን “ኹተማዋን በእጅህ አሳልፌ ስለምሰጥህ ዚያዝኚውን ጩር ወደ ጋይ አቅጣጫ ሰንዝር” አለው። ኢያሱም ይዞት ዹነበሹውን ጩር ወደ ኹተማዋ አቅጣጫ ሰነዘሚ።
ያደፈጠውም ሠራዊት ኢያሱ እጁን በሰነዘሚበት ቅጜበት ወዲያውኑ ኚቊታው ተነስቶ ወደ ኹተማዋ ሮጊ በመግባት ያዛት። ኚዚያም በፍጥነት ኹተማዋን በእሳት አያያዟት።
ዹጋይ ሰዎቜ ዞሹው ሲመለኚቱ ዹኹተማዋ ጭስ ወደ ሰማይ ሲወጣ አዩፀ ወደዚትኛውም አቅጣጫ መሞሜ ዚሚቜሉበት አቅም አልነበራ቞ውም። ወደ ምድሚ በዳው እዚሞሹ ዚነበሩትም ሰዎቜ ወደ አሳዳጆቻ቞ው ዞሩ።
ኢያሱና እስራኀላውያን በሙሉ፣ አድፍጊ ዹነበሹው ሠራዊት ኹተማዋን በቁጥጥር ሥር ማዋሉንና ዹኹተማዋ ጭስ ወደ ላይ መውጣቱን ሲመለኚቱ ወደ ኋላ ተመልሰው ዹጋይን ሰዎቜ ማጥቃት ጀመሩ።
ኹተማዋን ተቆጣጥሚው ዚነበሩትም ሰዎቜ እነሱን ለመግጠም ኹኹተማዋ ወጡፀ በመሆኑም ዹጋይ ሰዎቜ በሁለቱም በኩል ባሉት እስራኀላውያን መካኚል አጣብቂኝ ውስጥ ገቡፀ እነሱም ፈጇ቞ውፀ ኚመካኚላ቞ው ዹተሹፈም ሆነ ያመለጠ አንድም እንኳ አልነበሚም።
ዹጋይን ንጉሥ ግን ኚነሕይወቱ ይዘው ወደ ኢያሱ አመጡት።
እስራኀላውያን ዹጋይን ነዋሪዎቜ በሙሉ ሜዳ ላይ ይኾውም ሲያሳድዷ቞ው በነበሹው ምድሚ በዳ ላይ ፈጇ቞ውፀ አንድም ሳይቀር ሁሉም በሰይፍ አለቁ። ኚዚያም እስራኀላውያን በሙሉ ወደ ጋይ ተመልሰው ኹተማዋን በሰይፍ መቱ።
ወንድ ሎት ሳይል በዚያን ቀን ዚሞቱት ዹጋይ ሰዎቜ በጠቅላላ 12,000 ነበሩ።
ኢያሱም ዹጋይን ነዋሪዎቜ በሙሉ ፈጜሞ እስኪያጠፋ ድሚስ ጩር ዚሰነዘሚበትን እጁን አልመለሰውም።
እስራኀላውያንም ይሖዋ ለኢያሱ በሰጠው ትእዛዝ መሠሚት ዹኹተማዋን ምርኮና ኚብቶቜ ለራሳ቞ው ወሰዱ።
ኢያሱም ጋይን በእሳት አጋያትፀ ኹተማዋንም ዚፍርስራሜ ክምር ሆና እንድትቀር አደሚጋትፀ እስኚ ዛሬም ድሚስ ባድማ ናት።
ዹጋይንም ንጉሥ እስኚ ማታ ድሚስ እንጚት ላይ ሰቀለውፀ ኚዚያም ኢያሱ ፀሐይ ልትጠልቅ ስትል በድኑን ኚእንጚቱ ላይ እንዲያወርዱት ትእዛዝ ሰጠ። እነሱም በድኑን በኹተማዋ በር ላይ ጣሉትፀ በእሱም ላይ ትልቅ ዚድንጋይ ቁልል ኚመሩበትፀ ይህም እስኚ ዛሬ ድሚስ እዚያው ይገኛል።
ኢያሱም በኀባል ተራራ ላይ ለእስራኀል አምላክ ለይሖዋ መሠዊያ ዚሠራው በዚያን ጊዜ ነበርፀ
መሠዊያውንም ዚሠራው ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ ለእስራኀላውያን በሰጠው ትእዛዝና በሙሮ ዹሕግ መጜሐፍ ላይ በተጻፈው “መሠዊያው ዚብሚት መሣሪያ ካልነካው ያልተጠሚበ ድንጋይ ዚተሠራ ይሁን” በሚለው መመሪያ መሠሚት ነው። በዚያም ላይ ዹሚቃጠሉ መባዎቜንና ዚኅብሚት መሥዋዕቶቜን ለይሖዋ አቀሚቡ።
ኚዚያም በድንጋዮቹ ላይ ሙሮ በእስራኀላውያን ፊት ዚጻፈውን ሕግ ቅጂ ጻፈባ቞ው።
እስራኀላውያን በሙሉ፣ ሜማግሌዎቻ቞ው፣ አለቆቻ቞ውና ዳኞቻ቞ው ዹይሖዋን ዹቃል ኪዳን ታቊት በሚሞኚሙት በሌዋውያን ካህናት ፊት ኚታቊቱ ወዲህና ወዲያ ቆመው ነበር። ዚባዕድ አገር ሰዎቜም ሆኑ ዚአገሬው ተወላጆቜ በዚያ ነበሩ። ዚእስራኀልን ሕዝብ ለመባሚክ (ዹይሖዋ አገልጋይ ሙሮ ቀደም ሲል ባዘዘው መሠሚት) ግማሟቹ በገሪዛን ተራራ ፊት ለፊት፣ ግማሟቹ ደግሞ በኀባል ተራራ ፊት ለፊት ቆሙ።
ኹዚህ በኋላ ኢያሱ በሕጉ መጜሐፍ ላይ በተጻፈው መሠሚት ዹሕጉን ቃላት በሙሉ ይኾውም በሚኚቱንና እርግማኑን ድምፁን ኹፍ አድርጎ አነበበ።
ኢያሱ፣ ሙሮ ኹሰጠው ትእዛዝ ውስጥ፣ ሎቶቜንና ልጆቜን እንዲሁም በመካኚላ቞ው ዚሚኖሩ ዚባዕድ አገር ሰዎቜን ጚምሮ በመላው ዚእስራኀል ጉባኀ ፊት ድምፁን ኹፍ አድርጎ ያላነበበው አንድም ቃል አልነበሚም።
በኀፍሬም ተራራማ አካባቢ ዹሚኖር ሚክያስ ዚተባለ አንድ ሰው ነበር።
እሱም እናቱን እንዲህ አላትፊ “1,100 ዚብር ሰቅል ተወስዶብሜ ዹሰሹቀውን ሰው ስትራገሚ ሰምቌ ነበርፀ ብሩ ያለው እኔ ጋ ነው። ዚወሰድኩት እኔ ነበርኩ።” በዚህ ጊዜ እናቱ “ልጄ፣ ይሖዋ ይባርክህ” አለቜው።
በመሆኑም 1,100ውን ዚብር ሰቅል ለእናቱ መለሰላትፀ እናቱ ግን “ዹተቀሹጾ ምስልና ኚብሚት ዚተሠራ ሐውልት እንዲሠራበት ለልጄ ስል ብሩን ኚእጄ ለይሖዋ እቀድሰዋለሁ። ለአንተም መልሌ እሰጥሃለሁ” አለቜው።